Quantcast
Channel: ደላላው
Viewing all 213 articles
Browse latest View live

አገር ትርምስ ውስጥ እንዳትገባ ምን ይደረግ?!

$
0
0

በልዑል ዘሩ

በኢትዮጵያ 2008 ዓ.ም ከሰላምና መረጋጋት ይልቅ ነውጥ ጎልቶ ታይቷል ቢባል ያስማማናል፡፡ እንዲያውም በኢሕአዴግ ከ25 ዓመታት የመንግሥትነት ዘመን ፈታኝ የሚባለው ዓመት ይመስላል፡፡ በተለይ ደግሞ ሥርዓቱ አምስተኛውን ዙር ብሔራዊ ምርጫ ‹‹በሙሉ ጠቅላይነት›› አሸንፎ ሥልጣን በጨበጠበት ገና በአንደኛው ዓመት ሰው ሠራሽም ሆኑ የተፈጥሮ እንቅፋቶች አገሪቱን እያንገዳገዱ መሆናቸው ትኩረትን ስቧል፡፡

ዘንድሮ ከመስከረምና ከጥቅምት የፀደይ ወራት አንስቶ በአገሪቱ የተከሰተው ድርቅ ከአሥር ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ለዕርዳታ እጁን እንዲዘረጋ አድርጓል፡፡ ይህ በ50 ዓመታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በስፋትና በቆይታ አስፈሪ የተባለ የተፈጥሮ አደጋ በመንግሥት አቅም ብቻ ቢመከትም፣ አገሪቱን ከ16 ቢሊዮን ብር በላይ ያስወጣ ነው፡፡ በሰው ሕይወት ላይ የሚገለጽ የጎላ ጉዳት ባይከሰትም በእንስሳትና በሰብል ምርታማነት ላይ ያሳደረው ተፅዕኖ ቀላል አይደለም፡፡

ገዥው ፓርቲ በዚህ ዓመት ‹‹የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ተፋልመን እናስወግዳለን፤›› ብሎ በሥሩ ያሉ ፓርቲዎች አባላትን ደጋፊዎቹን አንቀሳቅሶና በጉባዔ ወስኖ፣ ጥናት አድርጐ በከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች (ባለሥልጣናት) ደረጃ የመከረበትን ያህል ሥራው የቀለለው አይመስልም፡፡ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም ከተሞችና ክልሎች በዝቅተኛ የሥራ ኃላፊነት ደረጃ ላይ የሚገኙ ሹማምንትን ያባረረው ወይም በሕግ የጠየቀው መንግሥት፣ በላይኛው እርከን የወሰደው እዚህ ግባ የሚባል ዕርምጃ አልታየም፡፡

በዚህ ሒደትም ‹‹የኪራይ ሰብሳቢነትና የሙስና ተራራን ለመናድ›› የሚለው መፈክር እንደተንጠለጠለ ይገኛል፡፡ ይህ ነባራዊ ሀቅ ባለበት ሁኔታ ነው ከሞላ ጎደል ለወራት ሞቅ ቀዝቀዝ እያለ የቀጠለ ሕዝባዊ እምቢተኝነት (ተቃውሞ) በኦሮሚያ ክልል የተቀሰቀሰው፡፡ በተለይ በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በምዕራብ አርሲ፣ ባሌ፣ ምዕራብ ሸዋ፣ ደቡብ ምዕራብ ሸዋና ምሥራቅ ወለጋ ዞኖች እንዲሁም በሰሜን ሸዋ ዞን በተለያዩ ጊዜያት የታየው የሕዝቡ ተቃውሞ አሁንም መፍትሔ ያገኘ አልመሰለም፡፡

በኦሮሚያ ክልል ወጣት፣ አዛውንት፣ የገጠርና የከተማ ሕዝብ ሳይባል በተለይ በኅዳርና በታኅሳስ የነበረውን የተቃውሞ ሠልፍ የተቀላቀሉ ቅሬታ አቅራቢዎች መነሻ ምክንያት ነበረው፡፡ ቢያንስ የአዲስ አበባና የፊንፊኔ ዙሪያ የጋራ ማስተር ፕላንን ትግበራ በመቃወም ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ይህ ሁኔታ ‹‹ለጊዜውም›› ቢሆን ተስተካከለ ከተባለ በኋላም ግን፣ በኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ መልኩን እየቀያየረ እስካሁን ቀጥሏል፡፡ እነ ጀዋር መሐመድን በመሳሰሉ የውጭ ኃይሎች ጥሪ የሚታዘዝም ሆኗል፡፡

በአማራ ክልል በተለይ በሰሜን ጐንደር ዞን የተነሳው ‹‹ሰላማዊ›› የሚመስል የሕዝብ ተቃውሞና እንቢተኝነትም ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ መነሻው ‹‹የወልቃይት የማንነት ጥያቄ›› ቢሆንም፣ ኢሕአዴግ መራሹን መንግሥት ፊት ለፊት በመቃወምና በማውገዝ ታጅቦ ቀጥሏል፡፡ ክፉው ነገርም በየአካባቢው በተነሱ ሁከቶችና አለመግባባቶች የሰው ሕይወትና ንብረት ጠፍቶ፣ የአካል መጉደልና የህሊና ቁስለትም ደርሷል፡፡

እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ያሉ ዓለም አቀፍ ተቋማት ቁጥሩ ከ400 ይበልጣል በማለት መከራከሪያ ሲያቀርቡ፣ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን መረጃ መሠረት የቅርብ ጊዜውን ጉዳት ሳይጨምር በኦሮሚያ ክልል ብቻ 173 ዜጐች ሞትና 956 የመቁሰል አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ በአማራ ክልልም የ97 ዜጐች ሕይወት ሕልፈትና የ86 ዜጐች የአካል ጉዳት ሲታሰብ በኢትዮጵያ ታሪክ ጥቁር መዝገብ ላይ የሚያርፍ አጉል ጊዜን አስከትሏል፡፡ ባሳለፍነው ሳምንት በጐንደር፣ ባህር ዳር፣ ምሥራቅ ሐረርጌ ሐሮማያ፣ ኮምቦልቻ፣ ጀልዱ፣ ባሌና አርሲ አካባቢዎችና በመሳሰሉት)፣ (ሰሜን ሸዋ ኦሮሚያ ዞን) በተደረገ ሕጋዊም ይበል ሕገወጥ ሠልፍና ሕዝባዊ ቅሬታ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችን ጨምሮ የንፁኃን ዜጐች ሕይወትና የአካል ጉዳት አጋጥሟል፡፡

የዘንድሮ ‹‹የተቀናጀ›› የሚመስል ሰላማዊ ብቻ ሳይሆን ኃይል የተቀላቀለበት የሕዝብ ቅሬታ መንግሥትን ክፉኛ ፈትኖታል፡፡ በአንድ በኩል ሠልፈኛው የመንግሥት ተቋማትና የሕዝብ መገልገያዎችን፣ የመንግሥት ‹‹ደጋፊ›› የሚመስሉ ድርጅቶችና ግለሰቦችን ሀብትና ንብረት ለውድመት ዳርጓል፡፡ ዘረፋ የተፈጸመባቸውም አካባቢዎችም ነበሩ፡፡ በሰሜን ጐንደር ዞን ደምቢያ ወረዳ የደረሰው ውድመት ደግሞ ከምንም ነገር በላይ የከፋ ነው፡፡ ከሁሉ በላይ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን የሚያሻክሩ፣ 25 ዓመት የተሄደበትን ቋንቋ ተኮር ፌዴራል ሥርዓት ‹‹ፉርሽ›› የሚያስመስሉ ክስተቶችም በገሃድ ታይተዋል፡፡

የተጀመረው ሁከትም ይባል ሕዝባዊ እምቢተኝነት ወደፊት ይቀጥል አይቀጥል ዋስትና ያለ አይመስልም፡፡ በአንድ በኩል በውጭ ካለው ተቃዋሚ አገር ውስጥ እስካለው ድረስ ሕዝቡ በመንግሥት ላይ የጀመረውን ተቃውሞ ‹‹አጠናክሮ›› እንዲቀጥል ያላሰለሰ ቅስቀሳ ቀጥሏል፡፡ በተለይ በማኅበራዊ ድረ ገጽ (ትዊተር፣ ፌስቡክ)፣ በውጭ የሚገኙ ሚዲያዎች በተዛባ ታሪክ፣ በአሉባልታና በተፈበረኩ ወሬዎች ጭምር አገሩን ሰንገው ይዘውታል፡፡ በሌላ በኩል መንግሥት ሒደቱን ፈጥኖ በውይይት፣ በሰላማዊ ድርድርና በምክክር ከመፍታት ይልቅ ኃይልን አማራጭ ያደረገ መስሏል፡፡ ሕግ ማስከበርና የአገር ደኅንነትን የመጠበቅ ኃላፊነት ቢኖርበትም ይህ ግን በኃይልና መሣሪያ ብቻ ሊመጣ አይችልም፡፡ ይልቁንም ሕዝብ ጥያቄ አለኝ ሲል የውጭ ኃይሎች ከመጥለፋቸው በፊት ቀድሞ ከሕዝብ ጋር መነጋገር የበለጠ የሚያግባባ መሆኑ ካልታመነበት ችግር አለ ማለት ነው፡፡

እንግዲህ በዚህ ምክንያት ነው ‹‹አገሪቱ ወደ ምስቅልቅል ቀጣና›› እንዳትወድቅ ምን ይደረግ? ከማንስ ምን ይጠበቃል? ወደሚሉ ውይይት ቀስቃሽ ሐሳቦች መግባት የተፈለገው፡፡ ሐሳቡን ደግፈንም ሆነ ተቃውመን ልንነጋገርበት እንደምንችልም እናምናለን፡፡

አሁን ሕዝቡን በጠባብ ምኅዳር መያዝ አይቻልም!

ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት የተለያዩ ፈታኝ ወቅቶችን ማለፉን በተደጋጋሚ ጊዜያት ተናግሯል፡፡ በደርግ ውድቀት 1983 ዓ.ም.፣ በኤርትራ ጦርነትና በሕወሓት መከፋፈል ወቅት 1993 ዓ.ም፣ እንዲሁም በምርጫ 97 ወቅትና የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ሕዝቡን እያወያየ፣ በፀጥታና በደኅንነት ኃይሉ እየታገዘ ችግሮችን ተሸጋግሮ ወደ ሰላማዊ ሁኔታም ተመልሷል፡፡ አሁን ግን ይህን ማድረግ ይቸግረዋል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡

አንድ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር ‹‹የአሁኑ አገራዊ ሁኔታ በመንግሥትና በገዥው ፓርቲ ብቸኛ ‹መፍትሔ አምጭነት› ብቻ አይፈታም›› ብለውኛል፡፡ በማስረጃ ሐሳባቸውን ሲያጠናክሩም፣ በቀዳሚነት የሕዝቡን በየአካባቢው አለመርካት፣ ቅሬታ ማንሳትና ‹‹ይለይለት›› እልህ ውስጥ እየገባ መምጣትን ለአብነት ይጠቅሳሉ፡፡

ችግሩ በትልልቆቹ (በሕዝብ ብዛትና የቆዳ ስፋት) ክልሎች ብቻ ያለ ይምሰል እንጂ በሐረሪ ክልል፣ በደቡብ (በተለይ በኮንሶና በሸካ) በጋምቤላ ክልል ሄደት መለስ ሲል ታይቷል፡፡ አዲስ አበባን ጨምሮ በዋና ዋና ከተሞች ከሥራ ማጣት፣ ከድህነትና የኑሮ ውድነት ጋር የሚነሱ ቅሬታዎች አሉ፡፡ በሕገወጥ የመሬት ወረራና መልሶ ማልማት የተፈናቀሉ፣ የመልካም አስተዳደር ዕጦት ያባዘናቸው፣ ወዘተ ሁሉ ቅሬታ ውስጥ እንደሚሆኑ መገንዘብ አያዳግትም ባይ ናቸው ምሁሩ፡፡ በሌላ በኩል የዴሞክራሲና የነፃነት ዕጦት፣ ከልማቱ ተጠቃሚ አለመሆንና የመገፋት ስሜቶችም መኖራቸውን ያክላሉ፡፡

ሌላኛው ነጥብ በዘንድሮው ወቅታዊ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን ከዓመታት በፊት ጀምሮ በፖለቲካ ልዩነትና በሐሳብ ነፃነት ሰበብ በሕግ የተጠየቁ፣ በፀረ ሽብር ሕጉ የተከሰሱና በተለያዩ ጊዜያት በተፈጸሙ ሁከቶች ‹‹በነውጠኝነት›› የተጠረጠሩ ዜጐች ቁጥር ትንሽ አይደለም፡፡ በተለይ በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በአዲስ አበባና በጋምቤላ አካባቢዎች ቁጥራቸው በርከት እንደሚሉ የሚገመቱ እነዚህ የፖለቲካ ተጠርጣሪዎች ከጀርባቸው የተለያዩ ደጋፊዎችና ቤተሰቦች አሏቸው በማለትም ምሁሩ ይናገራሉ፡፡

ከእነዚህ የአገር ውስጥ የቅሬታ ምንጮች ባሻገር ገዥው ፓርቲ ‹‹ምኅዳሩ ሰፍቷል›› ቢልም በምርጫ 2007 ያረጋገጠው የሥልጣን ጠቅላይነት በመድበለ ፓርቲ ሥርዓቱ ላይ እንቅፋት ተደርጎ እየተወሰደ ነው፡፡ በተለይ ከሰላማዊ ተገዳዳሪዎች አለመጠናከርና ‹‹መፈናፈኛ ማጣት›› ጋር ተደምሮ ነፃ ሐሳብ፣ ነፃ ማኅበር፣ መደራጀት፣ ነፃ ፕሬስ… በበቀሉበት ሁለት አሥርት ዓመታት ውስጥ ዕድገት አላሳዩም፡፡ ይህ እውነታ ደግሞ ከተቃውሞ ሠልፍ በላይ ነፍጥ አንስቶ ለመፋለም የሚሻውን ወገን እያበረከተው እንዳይሄድ ሥጋት አላቸው፡፡

መንግሥት ይህን መሬት ላይ ያለ እውነት ቸል ብሎ ችግሩን በእኔ መዘውር ብቻ እፈታዋለሁ ከሚል ስሌትም መውጣት እንዳለበት ይመክራሉ፡፡ ከ25 ዓመታት በኋላ አዲስና ሰፊ የውይይት ምኅዳር መፍጠር የተሻለ መሆኑን አጽንኦት በመስጠት፡፡

የተቃዋሚ ኃይልና አማራጭ ሐሳብ ስንዘራው በርትቷል

በአገር ውስጥ የሚገኙ ብሔራዊም ሆኑ ኅብረ ብሔራዊ የፖለቲካ ማኅበሮችና ድርጅቶችን ጨምሮ፣ በውጭ የሚኖሩ ‹‹ጽንፈኛ›› እና ነፍጥ ያነሱ ተቃዋሚዎች አንድ የጋራ ‹‹ጠላት›› አላቸው፡፡ እነዚህ በስትራቴጂ ቢለያዩም በኢሕአዴግ ከሥልጣን መውረድ ላይ የሚስማሙ ኃይሎች እንደ ኤርትራ መንግሥት፣ ግብፅና አንዳንድ የዓረብ መንግሥታትን ድጋፍም አያጡም፡፡ ምዕራቡ ዓለምም ቢሆን ‹‹አርፋችሁ ተቀመጡ›› የሚላቸው እንዳልሆነ ይገመታል፡፡

ሌላው ቀርቶ ካለፉት አራት አሥርት ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ያለፉ፣ በተለያዩ ጊዜያት ከኢሕአዴግ ካምፕ የወጡና የዳር ተመልካች የነበሩ ሁሉ ‹‹የለውጥ›› ሐሳብ ማቀንቀን ይዘዋል፡፡ ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት ማድረግ ካለበት ሥር ነቀል ለውጥ አንስቶ እስከ ሁሉ አቀፍ የፖለቲካ ድርድር እንዲጀመር የመወትወት ብቻ ሳይሆን፣ ሥርዓቱ ይህን ዕድል ካልተጠቀመበትም አገሪቱ አደጋ ላይ እንደምትወድቅ ማሳሰብ ይዘዋል፡፡

በቅርቡ በአሜሪካ አንዳንድ የፖለቲካ ኃይሎች የጀመሩት ውይይት፣ የአውሮፓ ኅብረትን ጨምሮ መንግሥት ‹‹ኒዮሊብራል›› የሚላቸው እንደ አምንስቲ ኢንተርናሽናል ያሉ ድርጅቶችም የተቃዋሚውን ሐሳብ እየገዙት ይመስላሉ፡፡ (በሰሞኑ የቢቢሲ፣ የአልጄዚራ፣ ሲኤንኤንና ፕሬስ ቲቪ ዘገባዎችና ድርጅቶቹ ያወጧቸው መግለጫ እንደሚያሳዩት)

የእነዚህ ውጫዊ የሚመስሉ ኃይሎች ተፅዕኖ ቀላል ነው እንዳይባል የሚያደርገው ማሳያ ደግሞ፣ ሕዝቡ በተለያዩ ድረ ገጾችና ሚዲያዎች የሚደርሰውን መረጃ ተከትሎ ተቃውሞን እያስቀጠለ መሆኑ ነው፡፡ በተለይ በተቃውሞ ሠልፍ ስም ሁከት ለመቀስቀስና ከሕግ የሚፃረሩ ተግባራትን ለመፈጸም የሚፈጸመው ድርጊት የአገርንና የሕዝብን ህልውና ክፉኛ የሚደፍቅ ነው፡፡ ቀስ በቀስም የእርስ በርስ ግጭትን የሚጋብዝና አገር የሚያፈርስ እንደመሆኑ ቆም ብሎ ማሰብንም ይጠይቃል፡፡

ገዥው ፓርቲና መንግሥትን ተፅዕኖ ውስጥ ለመክተት ያለመው ‹‹የተቀናጀ›› የሚመስለው ፖለቲካዊ ሁኔታ አደገኛ ጦስንም ሊቀሰቅስ እንደሚችል መታየት አለበት፡፡ አንደኛው የትግራይ ሕዝብ ከጥንት እስከ ዛሬ በአገሪቱ ታሪክና ነባራዊ ሁኔታ ውስጥ የነበረውን ድርሻ ቸል በማለት፣ ከሥርዓቱ ጋር እንዲወገዝ የሚደረገው ጥረት ነው፡፡ ይህ የዘረኝነትና የጥላቻ ልክፍት የተጠናወተው አስተሳሰብ ሕዝቡን ‹‹ብቸኛ የሥርዓቱ ተጠቃሚ›› አድርጐ እየሳለው በመሆኑ ሐሳቡን የሚገዛው የለም ሊባል አይችልም፡፡

ሁለተኛው በኦሮሚያ ያለው የተቃውሞ ሠልፈኛ የኦነግን ሰንደቅ ዓላማ አንስቶ በጠባብነት የታወረውን አስተሳሰብ በይፋ ያቀነቅን ይዟል፡፡ በአማራ ክልል ደግሞ በአሀዳዊነትና በትምክህተኝነት የሚተቸውን ‹‹የቀድሞ ሥርዓቶችን ሰንደቅ›› አንስቶ በየደጃፉ እስከ መስቀል ደፍሯል (በነገራችን ላይ እነዚህ ድርጊቶች በ25 ዓመታት ውስጥ በግላጭ በአገር ውስጥ የተፈጸሙ ኢ ሕገ መንግሥታዊ ሊባሉ የሚችሉ ተግባራት ናቸው)፡፡ እነዚህ ሁለት ጫፍ ላይ ያሉ አስተሳሰቦች ወደ ነፃ ውይይት መጥተው የሐሳብ ፍጭት ካልተደረገባቸውም የተቀበሩ ቦምቦች መሆናቸው አይቀርም፡፡ 25 ዓመታት የተጓዘውን ቋንቋ ተኮር ፌዴራሊዝም ጥያቄ አስነስተውበታል፡፡

ከእነዚህ እውነታዎች አንፃር ሲመዘን መንግሥትና ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች በአንድ ጊዜም ባይሆን ቀስ በቀስ ወደ ጋራ አጀንዳና ሁሉ አቀፍ ውይይት መምጣት እንዳለባቸው ይታመናል፡፡ ሕዝብን ማክበር፣ አገርን መውደድና ነገን ትውልዱ በተስፋ እንዲጠብቀው ማድረግ የሚቻለው በዚሁ መንገድ ብቻ ነው፡፡

ቀጣናው ያለበት ሁኔታ አሳሳቢ ነው

ተደጋግሞ እንደሚባለው አገራችን የምትገኝበት የምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና ለቀውስና ትርምስ አመቺ የሚባል ነው፡፡ በአንድ በኩል ከትርምስ ወጥታ በእግሯ መቆም ያልቻለችው ሶማሊያ፣ የውድቀት መንገድን የመረጠችው ደቡብ ሱዳንና ‹‹ሰላም የለም ጦርነት የለም›› ፍጥጫ ውስጥ የከተተችን ኤርትራ ከ68 በመቶ በላይ ድንበራችንን ከበውታል፡፡ ሱዳንና ኬንያም ቢሆኑ ከድንበር፣ ከውኃ አጠቃቀምና ከመሰል ጉዳዮች ጋር የተያያዘ የውስጥ ጥያቄዎች አሏቸው፡፡

በሌላ በኩል የቀይ ባህር ዙሪያው ፍጥጫ ከመቼውም ጊዜ ከፍ ባለ ደረጃ ለአገራችን ሥጋት እየሆነ መምጣቱን በርካታ ምሁራን እየገለጹ ነው፡፡ የየመን የእርስ በርስ ግጭት፣ የሳዑዲ ‑ ኢራን ፍጥጫ ሳይቀር በኤርትራ መንግሥት ተገለባባጭ ባህሪ ላይ ሲደመር ትኩረትን ሊስብ የሚችል ነው፡፡ በዚሁ መሀል እስራኤልና ቻይና ጭምር ለትልልቆቹ የምፅዋና የአሰብ ወደቦች በመቅረብ በእጅ አዙር ቀጣናዊ ጥቅማቸውን ለማስከበር እየማሰኑ ይገኛሉ፡፡

በዚህ መዘዝ ይመስላል አንዳንድ ተንታኞች በአሁኑ ወቅት ከኤርትራው አምባገነን ሥርዓት ጋር ጦር መማዘዝ ከዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ከሚደርሰው ጫና በላይ፣ በእጅ አዙር ሻዕቢያን የሚደግፉ ኃይሎች መበራከት ተፅዕኖአቸው ከፍተኛ ነው የሚሉት፡፡ በተለይ ጽንፈኛና አክራሪ እስልምናን ለመሸከም ጀርባው የተመቸው ሻዕቢያ በ‹‹እኔ ከሞትኩ…›› ሥሌት ቀጣናውን ለማተራመስ ወደኋላ እንደማይል እየታመነ መጥቷል፡፡

ከእነዚህ መሬት ላይ ካሉ እውነታዎች አንፃር ይመስላል የኤርትራ መንግሥት በድፍረትና በይፋ የኢተዮጵያ መንግሥትን የሚፋለሙ ኃይሎችን እየደገፈ፣ እያሠለጠነና እያስታጠቀ ማሰማራቱን የገፋበት፡፡ ከዚህም በላይ በማኅበራዊ ድረ ገጾችና ፕሮፓጋንዳ ጭምር ኢትዮጵያን የሚያዳክሙና አገር የሚበትኑ የዘረኝነትና የጥላቻ ቅስቀሳ ውስጥ የገባው፡፡ የዚህን ሥርዓት እኩይ ምግባር ደግሞ በዓባይ ውኃ አጠቃቀም ላይ ቅሬታ ያላቸው አገሮችም እንደሚደግፉት ከመጠርጠርም በላይ የሚታይ ሆኗል፡፡

በመሆኑም ወቅታዊው ቀጣናዊ ሁኔታ ብቻ ኢሕአዴግ መራሹ ሥርዓት ከተገዳዳሪዎቹም ጋር ሆነ ከሁሉም የአገሪቷ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በሆደ ሰፊነት እንዲወያይ ያስገድደዋል፡፡ ዓይኑን ገልጦ ለተመለከተ የፖለቲካ ተንታኝም ሆነ ከግትርነት ወጥቶ ለአገሩ የሚያስብ መሪ መደራደርና ውይይትን እንደ ነውር ሊቆጥር አይገባም፡፡ ውይይት ጥቅምን ብቻ አያስጥልም፡፡ የሚያስገኘው የጋራ ፋይዳም አለ፡፡ ስለዚህ አገርን ከትርምስ ውስጥ ለማውጣት አማራጭ ሆኖ መታየት አለበት፡፡

ለማጠቃለል

አገራችን ምንም እንኳን በተስፋ ሰጪ መንገድ ላይ ብትሆንም፣ ጉዞዋ በመንታ መንገድ ላይ የሚገኝም ነው፡፡ የገዥው ፓርቲ የውስጥ ፖለቲካም የቀድሞ ዓይነት ጥንካሬ የሌለውና ግራና ቀኝ የሚረግጥ መስሏል፡፡ በዚህ ላይ የሕዝቡ አለመርካትና ለውጥ መሻት፣ የፖለቲካ ኃይሉ በርዕዮተ ዓለም ቢስማማም ባይስማማም በጋራ መሠለፍ፣ እንዲሁም ጂኦ ፖለቲካዊ ሁኔታዎች መንግሥት ቆም ብሎ እንዲያስብ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ ስለሆነም መፍትሔው ሁሉን አቀፍ ውይይት ነው የሚል እምነት የብዙዎች እየሆነ ነው፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Lzeru@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

ውይይቶች ዘላቂ የመፍትሔ በሮችን ይክፈቱ!

$
0
0

በሒሩት ደበበ

የኢትዮጵያ መንግሥት በአሁኑ ወቅት ፈታኝ ሁኔታ እንደገጠመው በተለያዩ ክስተቶች እየተገለጠ ነው፡፡ ከድርቅና ከመልካም አስተዳደር ዕጦት በላይ የተለያዩ የሕዝብ ቅሬታዎችና ተቃውሞዎች እየበረቱበት መጥተዋል፡፡ ባሳለፍናቸው ቀናት በአንዳንድ አካባቢዎች ‹‹የተረጋጉ›› የሚመስሉ ገጽታዎች ቢታዩም፣ በአገሪቱ የማኅበረ ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ላይ ያረበበው ሥጋት ቀላል አይመስልም፡፡ ጠንከር ያለ መፍትሔንም ይሻል፡፡

ይህንን እውነታ የሚያሳየው ባለፈው ሳምንት ልዑል ዘሩ የተባሉ ጸሐፊ በዚሁ ጋዜጣ ላይ ‘አገርን ከምስቅልቅል እናድን’ በማለት ያቀረቡት ጽሑፍ ነው፡፡ ‹‹የአሁኒቷ ኢትዮጵያ ተስፋ ያላት ብትሆንም በመስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች፤›› ሲሉም የመንግሥትን ክፍተት፣ የሕዝቡን ጠንከር ያለና የተደራጀ ቅሬታ፣ የተቃዋሚውን ጎራ አሠላለፍና የተቀናጀ ዘመቻ፣ እንዲሁም የአካባቢያችንን ለአደጋ መጋለጥ በተጨባጭ ማሳያዎች ተንትነዋል፡፡

የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅም የአቶ ልዑልን ሐሳብ የምጋራባቸው የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡ በተለይ የሰሞኑን የሕዝብ ቅሬታና አገራዊ የፖለቲካ ተቃውሞ ተከትሎ ካለፈው ሳምንት ሰኞ ጀምሮ በብዙዎቹ የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች በተካሄዱ ውይይቶች፣ ከራሱ ከሲቪል ሰርቫንቱ እየተደመጠ ያለው የለውጥ መሻትና ቅሬታ ምናልባትም በኢሕአዴግ ሁለት አሥርትና ተኩል ዕድሜ ውስጥ የከረረና ከፍ ያለ መሆኑ በተለያዩ መድረኮች የታዘቡና የተሳተፉ ወገኖችም እያረጋገጡ መምጣታቸው ነው፡፡

ውይይት መጀመሩ መልካም ቢሆንም ሕዝብ ይደመጥበት!

ዘንድሮ የተነሳው የሕዝብ ቅሬታ በማንነት ጥያቄም፣ ይሁን በመልካም አስተዳደር ወይም በሙስናም ይበል በጋራ ማስተር ፕላን ጉዳይ ‹‹አስደንጋጭ›› ነው የተባለው ኢሕአዴግ መቶ በመቶ ምርጫ ‹‹ባሸነፈበት›› ወቅት መሆኑ ነው፡፡ አምስተኛው አገራዊና ብሔራዊ ምርጫ በግንቦት 2007 ዓ.ም. ሲካሄድ አንድም የግልም ሆነ የተቃዋሚ ዕጩ ተወዳዳሪ የፌዴራልም ሆነ የክልል ምክር ቤት ውስጥ ሊገባ አልቻለም፡፡

ይህ ክስተት ኢሕአዴግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ሕዝቡ ‹‹ተስፋ ጥሎብኛል›› የሚል መታበይ ውስጥ ሲከተው፣ የተቃዋሚ ኃይሎች ደግሞ የመድበለ ፓርቲ ሥርዓቱ ሥርዓተ ቀብር መፈጸሙን አወጁ፡፡ በተለይ በውጭ አገር የሚኖሩና አማራጩ ‹‹የትጥቅ ትግል ነው›› የሚሉቱ በኢትዮጵያ የሰላማዊና የዲሞክራሲያዊ ትግል በር ላይከፈት እንደተከረቸመ አድርገው አስተጋቡ፡፡ በእርግጥ በዚህ ውጤት ላይ የሰብዓዊና የዴሞክራሲ ተሟጋቾችና ምዕራባውያንም ‹‹ለምን? እንዴት?›› የሚል ጥያቄ እንዳነሱበት ይታወቃል፡፡

በምርጫ 2007 የተቃዋሚው ኃይል መዳከም፣ የምርጫ መጭበርበርም ይባል የኢሕአዴግ ጥንካሬ በሰፊ ብዝኃነት ውስጥ ‹‹የልማታዊ መንግሥት›› እሳቤ ብቻ አየሩን መሙላቱ ላያስገርም ይችላል፡፡ ግን ‹‹ኢሕአዴግ ብቸኛ ምርጫዬ ነው›› ያለው ሕዝብ በወራት ዕድሜ ውስጥ ለምንና እንዴት ተገልብጦ ቁጣ ቀሰቀሰ ነው አስገራሚው ጥያቄ፡፡ የሕዝቡ ቅሬታስ ምን ቢፈጠር ነው ከቀደሙት ጊዜያት ከፍ ያለና ያለፈ ሆኖ የታየው የሚለው ጥያቄ መንግሥትን ሊያነቃው ይገባል፡፡ እርግጥ እዚህ ላይ የተጠራቀመ ችግር ነው የሚሉ ትንተናዎች እየወጡ መሆናቸው ሳይዘነጋ፡፡

በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች፣ በሃይማኖት ተቋማትና በአንዳንድ የኅብረተሰብ ክፍሎች (በተለይ ወጣቶችና ሴቶች) ላይ ያተኮሩ ውይይቶች በመንግሥት በኩል ተጀምረዋል፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ የተጀመረው ውይይት መበረታታት ያለበትና ለአገር የሚጠቅመው ብቸኛው መንገድ መሆኑ እርግጥ ነው፡፡ ነገር ግን አሁን እየታየ ያለው አሁንም መድረኮቹ በገዥው ፓርቲ ካድሬዎችና በአንድ ወገን አስተሳሰብ እየተቃኙ፣ ‹‹በድርጅታዊ አሠራር›› መመራታቸው ብዙዎችን እያሳዘነ ነው፡፡ መቼ ነው ኢሕአዴግ አስተማማኝ ማሻሻያ ሊያሳይ የሚችለው የሚለው አጀንዳና ጥያቄም እግሩን እየዘረጋ ነው፡፡

የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በተለይ ሲቪል ሰርቫንቱ በስፋት በሚያነሳው ሐሳብ፣ ‹‹የሕዝብን ቅሬታ፣ ቁጣና ተቃውሞ ባለቤት የሌለው ቅዋሜ እያሉ በመግፋት በውጭ ያሉ ኃይሎችና የሻዕቢያ ቅስቀሳ እንደሆነ የተጀመረው ግፊት አክሰሪ የፖለቲካ መንገድ ነው፤›› እያለ ነው፡፡ ከዚያ ይልቅ ሕዝብ ምን ጎደለበት መባል አለመቻሉም ያሳዘናቸው ቀላል አይደሉም፡፡

ይህን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ስነሳ በአሥር የተለያዩ መሥሪያ ቤቶች የወቅታዊ ጉዳዮች ምክክሮች ላይ የተሳተፉ ሲቪል ሰርቫንቶችን አነጋግሬያለሁ፡፡ በብዙዎቹ ፎረሞች የተነሳው ሐሳብ ግን በሚገርም ሁኔታ ተመሳሳይነት ያለው ብቻ ሳይሆን የተለያዩ አክቲቪስቶች፣ ፖለቲከኞች፣ የውጭ ሚዲያዎችና ብሎገሮች ከሚያነሱት ብዙም የራቀ የሚባል አይደለም፡፡

ቀዳሚው በአገሪቱ ‹‹የታመመ›› ከሚመስለው ፖለቲካዊ ሁኔታና የዴሞክራሲ ምኅዳር ጋር የሚገናኘው ነው፡፡ ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት የነፃነትና የዴሞክራሲ ጥያቄዎች ለመመለስ የታገለ ቢሆንም አሁን ግን የሐሳብ ብዝኃነት ተደፍቋል፣ የፕሬስ ነፃነት ተገድቧል፡፡ መደራጀት፣ መቃወምም ሆነ ነፃ ማኅበር መመሥረት አልተቻለም የሚለው ሙግት እንደ ተራራ ገዝፏል፡፡

እንዲያውም አንዳንዶች፣ ‹‹ሕዝቡ ሐሳቡን በነፃነት የመግለጽ መብቱ መታፈኑም ሆነ ሰላማዊ ሠልፍ በማድረግ ጥያቄውን ማሰማት አለመቻሉ ለሕገወጥ ሠልፍና ነውጥ እንዲነሳሳ ስላደረገው አይፈረድበትም፤›› እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡ ኢሕአዴግ የሚፈልጋቸው ሠልፎች፣ ፎረሞችና ሲምፖዚየሞች በመንግሥት ሀብትና ጥበቃ ታጅበው ሲከናወኑ፣ በየደረጃው የሕዝብ ነፃ ጥያቄዎችና ቅሬታዎች ግን አድማጭ አላገኙም የሚለው ሐሳብ ጎልቶ ተሰምቷል፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ በሽግግር መንግሥቱ ወቅት እንኳን ትልልቅ የአገሪቱ ፖለቲከኞች የዴሞክራሲ ሥርዓቱ ተዋናዮች ነበሩ፡፡ ከዓመት ወደ ዓመት ግን ብዙዎቹ (በተለይ ትምክህተኛና ጠባብ የተባሉቱ) የስደት ፖለቲከኞች ሆነዋል፡፡ በአገር ውስጥ ያለው የተቃዋሚ ድርጅቶች መሪ፣ የማኅበራት ግንባር ቀደም ኃይልና ተዋናይ አንድም ለዘብተኛ አለፍ ሲልም የኢሕአዴግ ተለጣፊ ሆኗል፡፡ በዚህ ምክንያት አገሪቱ ለጥቂቶች የነበረችበትን ያለፈ የታሪክ ካባ መልሳ የምትደርብ መስላለች ነው ያሉት፡፡ ይኼ አስደንጋጭ ዝንባሌ ሁሉንም ሊያሳስብ ይገባል፡፡

የኢትዮጵያ ፖለቲካ የታመመ የሚመስለው በምርጫ ውጤት ብቻ አይደለም፡፡ በምሁራንና ሊያመዛዝኑ ይችላሉ በሚባሉ ዜጐች አድርባይነትም እየተገለጸ ነው፡፡ ለአገርና ለሕዝብ ጥቅም ሲባል ነፃና ሒሳዊ አስተያየትን መሰንዘር የማይችሉ ልጉሞች እየበረከቱ የመጡበት ጊዜ ነው፡፡ አሳዛኙ ነገር ስህተት አለማረም ብቻ ሳይሆን ‹‹በዝምታ ውስጥ የምንቸገረኝ ባህል›› አዳብረው በነፃነት (Comfort Zone) መቀመጣቸው ነው›› በዚህም ምክንያት ጥቂት የሥርዓቱ ‹‹ወገኖች›› ሐሳብ ብቻ እንዲደመጥ የተገደድንበት አገር ተፈጥራለች ይላሉ የመንግሥት ሠራተኞቹ፡፡ ወጣ ያሉ ሐሳቦችን መድፈቅና መግፋት ጭምር በማሳየት፡፡

ሁለተኛው የሕዝብ ቅሬታ ምንጭ የሆነው የመልካም አስተዳደር፣ ፍትሐዊ ተጠቃሚነትና ተሳትፎን የተመለከተው ጉዳይ ነው፡፡ በውጭ ያለው ተቃዋሚ በተለይ ከኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች ሕወሓት ያላግባብ እየተጠቀመና ጠቅላይ እየሆነ ነው የሚለውን ቅስቀሳ በመድረኮቹ ማስተባበል አልተቻለም፡፡

በተለያዩ መድረኮች ተደጋግሞ እንደተነሳው በፌዴራል መሥሪያ ቤቶች፣ በመከላከያና ደኅንነት መዋቅሮች፣ በአዲስ አበባ አስተዳደር መዋቅሮችና በአንዳንድ ድርጅቶች ላይ ለምን ማመጣጠን አልተቻለም? የሚለው ጥያቄ በርትቷል፡፡ ከዚህ ቀደም በተለይ በመከላከያ ኃይልና በደኅንነቱ ውስጥ የሌሎች ብሔር ተወላጆች ‹‹ከነባሩ ታጋይ ልምድ እስኪቀስሙ›› ቢባልም ከ25 ዓመታት በኋላ እንዴት ለውጥ ማምጣት ከበደ? ብሔርና ማንነት ዋነኛ የልዩነት መገለጫ በሆኑበት አገር ውስጥስ ፍትሐዊ ተሳትፎ እንዴት ወደ ጐን ሊባል ይችላል የሚሉ በርክተዋል፡፡

ይህ መሆኑ ብቻውን ባልከፋ፡፡ በዚያው ልክ በሥልጣን መባለግ፣ በሙስና ሕገወጥ ጥቅም መተሳሰር ሲመጣም በቋንቋና በማንነት መሳሳብ እንደሚበረታ የሚሰጉ ተደምጠዋል፡፡ ከመሬት፣ ከገቢዎችና ጉምሩክ፣ ከትራንስፖርት፣ ከኢንዱስትሪና ከኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ አንፃር ‹‹ጥቂቶች እየበለፀጉ ነው›› ለሚለው አሉባልታ ሰፊ በር የከፈተ ጉዳይም ሆኗል፡፡ ስለዚህ ይህን ብዥታ የማጥራትና ፍትሐዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ጉዳይ ወሳኝ ሥፍራ ይዞ መጥቷል፡፡ መልካም አስተዳደርን ለማረጋገጥም እንደ ቀዳሚ ነጥብ እየተነሳ ነው፡፡

ሦስተኛው አነጋጋሪ ጉዳይ የፍትሐዊ ልማትና የሥራ ዕድል ፈጠራው ጥረት ‹‹ያልደረሳቸው›› በሚባሉ ወገኖች ነው፡፡ በእርግጥ እንኳንስ ገና ደሃ በሆነች አገር ውስጥ ይቅርና የትም ቢሆን ያለመርካትና የልማት ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡ መንገድ፣ ትምህርት፣ ጤና፣ ውኃ… ሲሟሉ ኤሌክትሪክ፣ ቴሌኮም፣ ዘመናዊ መኖሪያ ቤት የሚፈልግ ይመጣል፡፡ ይህም ሲሟላ ኢንተርኔት፣ ዓለም አቀፍ ግንኙነት፣ የቅንጦት ዕቃዎችና አገልግሎት… ፍላጐቶች ማብቂያ የላቸውም፡፡

አሁን ባለችው ኢትዮጵያ ግን በተለይ ከሥራ አጥነትና ከኑሮ ውድነት ጋር የተያያዘው የድህነት ጥያቄ ከብዶ እየታየ መሆኑ በመድረኮቹ ተወስቷል፡፡ አዲስ አበባን የሞሏት የደቡብ፣ የአማራና የትግራይ ክልል አርሶ አደሮችና ወጣቶች እንዴትና በምን ምክንያት ፈለሱ? ‹‹ብዙ ሥራ›› ተሠርቷል በሚባልበት ጊዜ እንኳን በሺዎች የሚቆጠሩ የደቡብ፣ የኦሮሚያና የአማራ ክልል ወጣት ስደተኞች ድንበር ተሻግረው ለችግር እየተጋለጡ ያሉት ለምንድነው? በየዓመቱ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ምሩቃን ሥራ አጥተው ምን መፍትሔ ተቀምጦላቸዋል? የሚሉ ጥያቄዎች እንደ መርግ የከበዱ ናቸው፡፡ በተለይ በኦሮሚያና በደቡብ የሥራ አጡ ቁጥር አገር እየፈታ መሆኑ ነው እየተነገረ ያለው፡፡ ለምን?!

መንግሥት በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይሆን በክልሎች የኑሮ ውድነትን ለመመከት የሚያደርጋቸው ጥረቶች አሉ፡፡ የደመወዝ ጭማሪ፣ የመኖሪያ ቤት ግንባታ፣ የአንዳንድ ሸቀጦች ድጎማ… ይጠቀሳሉ፡፡ ነገር ግን አሁንም የዋጋ ግሽበት በተለይ የከተማ ነዋሪዎችን ክፉኛ መፈተኑ ተነስቷል፡፡ የቤት ኪራይ ዋጋ አለመመጣጠን፣ የጤፍ ዋጋ እጅግ በጣም የማይቀመስ መሆን፣ የማጣፈጫ ሸቀጦች ዋጋ መናር… ሕዝቡን ሰቆቃ ውስጥ እየከተቱ መሆናቸው ተወስቷል፡፡

በዚህ ላይ ፍትሐዊነት ሳይረጋገጥና ሕጋዊነት ሲጓደል ችግሩ እንዴት ሊባባስ እንደቻለም ተወስቷል፡፡ ከጐዳና ንግድ፣ ከሰው ሠራሽ ዋጋ ንረትና እጥረት እንዲሁም ከቅሸባና ከባዕድ ነገር ጋር ቀላቅሎ ሽያጭ አንፃር ዜጐች ከመማረር አልፈው ለከፋ የጤና ቀውስ እየተጋለጡ መሆኑ ተቆጣጣሪ አልባ ድርጊት አስመስሎታል፡፡

በዚህ ላይ ሙስናውንና የመልካም አስተዳደር ዕጦቱን በማባባስ ወደ መንግሥት ባለሥልጣናት ተጠግተው በአጭር ጊዜ የሚበለፅጉ ሰዎችን ሕዝብ ይመለከታል፡፡ አዋዋል አኗኗራቸውን ይታዘባል፡፡ ይህ ሁኔታም ኑሮ ውድነቱም ሆነ የዋጋ ግሽበቱ በእርሱ ላይ ብቻ ተፈርዶበት እንደመጣ መቅሰፍት እንዲቆጥር ያደርገዋል፡፡ ለዚህም ነው የሙስና አደጋ ሕዝብንና አገርን የመበተን መዘዝ አለው እስከመባል የሚደርሰው፡፡

አራተኛው የሕዝቡን ቅሬታ ሌላው ያባባሰው በመንግሥት አካላትም ሆነ በየትኛውም የፖለቲካ ማዕቀፍ ውስጥ ተወሽቀው በዘረኝነትና በጠባብነት ሕዝቡን እየነጣጠሉ ያሉ አጥፊዎች ድርጊት ነው፡፡ በፌዴራል መንግሥቱ ሕገ መንግሥት መሠረት ማንኛውም ዜጋ በሕጋዊ መንገድ የትም ክልል ሄዶ ሠርቶና ከሌሎች ጋር ተስማምቶ የመኖር መብት ሰጥቶታል፡፡ በእርግጥ ይኼ መብት ከጥንት ጀምሮ ለዘመናት የኖረ ነው፡፡

አሁን አሁን ግን ይህንን መብት በግላጭ የሚጋፉ ብቻ ሳይሆን በጠባብነት መዶሻ ያደቀቁ ኃይሎች ሚዛን ከብዶ ታይቷል፡፡ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በአንዳንድ የደቡብ ክልሎች በማንነታቸው ብቻ ሀብታቸው ተዘርፎ ባደ እጃቸውን የተባረሩ ዜጐችን አይተናል፡፡ እንዲያውም ግድያና ስቃይ የደረሰባቸውም ነበሩ፡፡ ይህን ድርጊት በእንጭጩ ያላረመው ብሔር ተኮሩ ፌዴራሊዝምና መንግሥት ዛሬ ‹‹አንድ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ተፈጥሯል›› ሲባል ችግሩ ተባብሶ ታይቷል፡፡ እንዲያውም ወደ ሰፋፊዎቹ ክልሎችም ተዛምቷል፡፡

በሰሜን ጎንደር ዞን በታየው ግጭትና በአንዳንድ የኦሮሚያ ከተሞች በተነሳው ተቃውሞ በማንነታቸው ብቻ የተጠቁ ወገኖች አሉ፡፡ ይኼ ለምን ሆነ ብሎ መፈተሽ ካልተቻለ በዚህች በጋራ አገራችን በአንድነት ለመኖር የማንችልበት ሁኔታ መፈጠሩ አይቀርም ሲሉ ነው በርካታ ተወያዮች በጥልቅ ሥጋት ያነሱት፡፡

ክስተቱ የፌዴራል ሥርዓቱ ብዝኃነትን ለማስተናገድ የሚያግዝ ቢሆንም ብሔር ተኮር መሆኑ የፈጠረው ችግር ነው እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡ ዛሬ አማራን ከትግራይ ሕዝብ የሚያጋጨው የወልቃይት ጉዳይ፣ ነገ በሌሎች ክልሎችና ብሔሮችም ላለመታየቱ ዋስትና የለም፡፡ ይኼ ደግሞ በአገራዊው ድንበር እንኳን ቁርጥ ያለ ጠንካራ አቋም ይዞ መሟገት ለማይሻው የኢትዮጵያ መንግሥት ትልቅ ጥያቄ የሚያስነሳበት የውስጥ የመነጣጠል ችግር ነው ተብሏል፡፡

የክልሎች የድንበር፣ የይዞታም ሆነ የወሰን ጭቅጭቅ መበርታት፣ ሕዝቦች ‹‹በማንነት ጥያቄ›› ስም ወደ ዘር ሐረግ መማዘዝ፣ ወረዳና ዞን መሆን መሻት የሚያሳየው አገራዊ ኅብረት አለመፈጠሩን ነው፡፡ ይልቁንም አሁንም ዘራቸውን ወይም ብሔራቸውን መሠረት አድርገው እንዲሚጠቀሙ እንጂ፣ ከአገራዊው ትልቁ ኬክ የድርሻቸውን እያገኙ እንዳልሆኑ የተሰማቸው ዜጐች መበርከታቸውን ያመለክታል የሚሉ ሒሶችም ተነስተዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ በዋናነት እየወቀሱ ያሉት መንግሥትን ነው፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱ በአብዛኛው ማንነትና ብሔር ላይ ያተኮረ፣ ዴሞክራሲያዊም ቢሆን አንድነትን ያላመጣ ነው ይሉታል፡፡ ለአንድ አገርና ሰንደቅ በጋራ ከመሠለፍ ይልቅ ሕዝቦችን በሸረሪት ድር ወደ መተሳሰር የሚያወርድ የላላ ግንኙነት ይከተል እንደሆነም የተለያዩ ተናጋሪዎች አብነቶችን በመጥቀስ ሲያስረዱ፣ በተሻለ አስተሳሰብ ከውድቀት ማዳንና አገርንም መታደግ የዚህ ትውልድ የቤት ሥራ መሆን እንዳለበት ነው የተወሳው፡፡

አምስተኛው ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት አገሪቱን በመራባቸው 25 ዓመታት ውስጥ በተለያዩ ውጣ ውረዶች አልፏል፡፡ የተሻለ ውጤት ያስመዘገበችው መስኮች እንዳሉም ሊካድ አይችልም፡፡ በዚያው ልክ ከፍተኛ ቅሬታ ያላቸውን ዜጎች አበራክቷል፡፡ ያልተሳኩለት አገራዊ አጀንዳዎችም እየታዩ ነው፡፡

እነዚህን ድብልቅልቅ ሁኔታዎች ከሌሎች የፖለቲካ ኃይሎች ጋር ተነጋግሮ ካልፈታቸው አገሪቱን እንዳለፈው ጊዜ ብቻውን ለማስተዳደር መሻት አያወጣም የሚሉ ሐሳብ ሰጪዎችም ተደምጠዋል፡፡ በተለይ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እየተካሄዱ ባሉ ውይይቶች ‹‹የራሳቸው የፖለቲካ ፍላጐት ያላቸውን ኃይሎች አሸባሪ፣ ጽንፈኛ፣ አክራሪ፣ ነፍጠኛ፣ ትምክህተኛ… በሚል ማግለልና መግፋት ብቻ ለመሮጥ ከመሻት ጉደለታቸውንም እየሞሉ መሳብ የመንግሥት ድርሻ ሊሆን ይገባል፤›› ያሉም ነበሩ፡፡

ይህን ሐሳብ የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች ደፍረው አይበሉት እንጂ፣ ‹‹መነጋገርና መወያየት የዘላቂው መፍትሔ ብቸኛ አማራጭ ነው፤›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡ እንግዲህ መንግሥትና ፖለቲከኞች ከዚህ አስተሳሰብ ውጪ ሊቆሙ አይችሉም፡፡ ሕዝቡም ቢሆን (በተለይ የብዙኃኑ) ሁሉም ነገር በሰላምና በዴሞክራሲያዊ መንገድ እንዲፈጸም ነው የሚሻው፡፡ ለዚህም የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይትና ሰፋ ያለ የፖለቲካ ምኅዳር መፈጠር አለበት፡፡ ይኖርበታልም፡፡

ለማጠቃለል

አገር አቀፍ ውይይት በሁሉም ደረጃ መጀመሩ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን አንዱ ሌሎችን የማያዳምጥበት ሊሆን አይገባም፡፡ በየመስኩ በተለይ ሕዝቡ ሊደመጥ ይገባዋል፡፡ የተነገረውን ነገር ወስዶና አንጠባጥቦ መጣል ሳይሆን ደግሞ ፈጣን የማሻሻያ ዕርምጃን አቅም በፈቀደ መጠን መውሰድ ተገቢ ይሆናል፡፡ በዚህ ሒደት ግን መንግሥት ገባ ወጣ የሚለውን የሕዝብ ቅሬታ እንደ መዘናጊያ ቆጥሮ (በተለይ ነገሮች ተረጋግተዋል ብሎ) ተመልሶ ወደ ጭቃው ውስጥ ከገባ የሚያፈጥነው ውድቀቱን ብቻ ነው፡፡ የአገር መዳከምና መበታተንም ሊደርስ እንደሚችል መተንበይ ሟርተኝነት አይደለም፡፡ ስለሆነም ትኩረቱ ለሕዝብ ድምፅ፣ ሐሳብና አገራዊ ውይይት ይሁን እላለሁ፡፡               

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊዋን በኢሜይል አድራሻቸው Hdebebe@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

Standard (Image)

ልብ ያለው ልብ ይበል

$
0
0

በሳሙኤል ረጋሳ

እንደ አገር አሁን እየተጓዝንበት ያለው ሰፊ ጎዳና የት እንደሚያደርሰን ያልገባን ብዙዎች ነን፡፡ የሰላም ዋጋ ርካሽ በመሆኑ ሁሉም ሰው በቀላሉ ሊገዛው ይችላል፡፡ በእጃችን ሲኖር ሰላምን እንደ መዳብ እንቆጥረዋለን፡፡ ሲያመልጠን ግን ዋጋውን መገመት ያስቸግረናል፡፡ መልሶ የማግኛው ዋጋ እጅግ ውድ በመሆኑ ከመጀመሪያው እንዳያመልጠን ያስፈልጋል፡፡

በእጅ ያለው የሰላም ዋጋ ርካሽ የሚሆነው በትዕግሥት፣ በመቻቻልና በመወያየት ብቻ በመሀላችን ያለውን ችግር መፍታት ሳንችል ነው፡፡ ጠንካራ የበሰለ አመራርና አስተዋይ ሕዝብ ያለው አገር ይህንን በቀላሉ የሚተገብረው በመሆኑ የተስፋ እንጂ የሥጋት አገር አይኖረውም፡፡ ነገር ግን ሕዝብና መንግሥት አንድ አካል አንድ አምሳል ሳይሆኑ ቀርተው በ‘እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ’ እልህ ተጋብተው ወደ አላስፈላጊ ቅራኔ ከተገባ የሚከፈለው ዋጋ እጅግ በጣም ውድ ነው፡፡ አሁን አሁን ግን ምንም ያህል ውድ ዋጋ ቢከፈልበት መልሶ ሰላምን ማግኘት ያልተቻለበት አጋጣሚ በጣም ብዙ ነው፡፡ አሁን ያለንበት የዓለም ሁኔታም የሚያሳየን ይኼንን ነው፡፡ ኢራቅ፣ ሶሪያ፣ ሊቢያ… ያጡትን ሰላም ለመመለስ እየከፈሉት ያለው ዋጋ በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ሕይወት እንኳ ሊመስላቸው አልቻለም፡፡

ታዲያ ይኼ በሌሎች ላይ የምናየው ችግር ለጊዜው በሰላም የምንኖር በመሆኑ ብቻ በእኛ አይደርስም ብሎ ማሰብ ከየዋህነትም በላይ ነው፡፡ በኦሮሚኛ አንድ ተረት አለ፡፡ ‹‹ደራሽ ውኃ ሞልቶ ከወንዙ ተርፎ ሜዳ ላይ ወጥቷል፡፡ ውኃው ከደጋው አገር አግበስብሶ ያመጣውን የሰዎችና የእንስሳት አስከሬን እያገላበጠ ሲያልፍ አንዱ መንገደኛ ከዳር ቆሞ ይኼን ጉድ ያያል፡፡ ውኃው እየሞላና እየጨመረ ወደ እግሩ ተጠጋ፡፡ ሰውዬው አሁንም በመገረም ይመለከተዋል፡፡ ታዲያ ወንዙ ለሰውዬው ‘በልቼ አሳየሁህ፣ ጮኼ አሰማሁህ ከዚህ በላይ ማስጠንቀቅ የለም’ ብሎ እሱንም ገፍቶ ከመሀል አስገብቶ ይዞት ሄደ፤›› እኛም አሁን የምንጓዝበት ጐዳና ወደዚያ ላለማምራቱ ምንም መተማመኛ የለንም፡፡ መላ ሳናበጅለት ችግራችንን ከዳር ቆመን ስናይ ከመከራ ባህር ውስጥ እንዳንሰምጥ፡፡

በተለይ መንግሥት ይኼን አስከፊ ጎዳና ሕዝቡ እንዳይጓዝበት ለማድረግ ቀዳሚ ኃላፊነትና ተጠያቂነት አለበት፡፡ ታዲያ መንግሥትም ቢሆን ይኼን የሚያደርገው የጉዞው መጨረሻ ምን እንደሆነ ለራሱም ቢሆን ገብቶት ከሆነ ነው፡፡ የመንግሥት ባለሥልጣናት ሌጋሲያቸውን (ፈለጋቸውን) እንከተላለን የሚሏቸው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አሁን ያለንበትን ሁኔታ የሚገልጽ ምሳሌ ነግረውን ነበር፡፡ ሐሳቡን ቃል በቃል ባልይዘውም መንፈሱ እነሆ፣ ‹‹አንድን እንቁራሪት ቀዝቃዛ ብረት ምጣድ ላይ አድርገው እሳት ላይ ቢጥዷት ሙቀቱ ቀስ በቀስ እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ነገር ግን እንቁራሪቷ የሙቀቱ መጠን በፈለገው ያህል ቢጨምር ለውጡ አይሰማትም፡፡ በዚህ ሒደት ሙቀቱ እየጨመረ እሷም በሒደቱ ሳታውቀው ተጠባብሳ ትሞታለች፤›› የሚል ነው አባባሉ፡፡ አቤት እሳቸውማ ሲያሳምሯት፡፡

በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ አሁን ብረት ምጣዱ የተጣደ ይመስላል፡፡ መንግሥትና ሕዝብም ብረት ምጣዱ ላይ ተጥደዋል፡፡ ሙቀቱ የተሰማቸው ጥቂቶች ካሉ ሳናውቀውና ሳይሰማን ተጠባብሰን ከመሞታችን በፊት ከሁለቱም ወገን መፍትሔ ይምጣ፡፡ ያኔ እንቁራሪት ሳንሆን ሰዎች መሆናችንን ከሰዎችም እንደ ወትሮው አገራችንን ሊታደጓት የሚችሉ ብርቱ ዜጐች ያሏት መሆኑን ለዓለም እናሳያለን፡፡

ብዙ ጊዜ መንግሥት እሱ የማያምንበትንና የእሱን ፖሊሲ የሚጣረስ ምንም ዓይነት ጥሩ ነው የሚባል ሐሳብ ቢሆንም ተቀብሎ በሥራ ላይ ማዋል ቀርቶ መስማት አይፈልግም፡፡ ቢሰማም በፀረ ሕዝብነት ነው የሚፈርጀው፡፡ የኢሕአዴግ መንግሥት ላለፉት 25 ዓመታት ሲከተለው የነበረ በሒደት እንኳ ከወቅታዊ ሁኔታዎች ጋር የማይለወጥ ችክ ያለ አቋም ነው ያለው፡፡ አሁን መመለስ ያለበት አንድ ወቅታዊ ጥያቄ አለ፡፡ መንግሥት ከማንኛውም አቅጣጫ የሚቀርብለትን ጥያቄ እንዴት ለማስተናገድ ተዘጋጅቷል? እስከ መቼ ሁሉም እኔ ባልኩት ይሁን ይላል፡፡ ይኼ ግትር አቋም እንዳለው የሚያውቁ ጠንካሮች አብረው መዝለቅ አይችሉም፡፡ ስለዚህ መንግሥት የአድር ባዮችና የአስመሳዮች፣ እንዲሁም የሙሰኞች ስብስብ ይሆናል፡፡

የሌሎችን ሐሳብ ተቀብሎ ሚዛን የሚደፋውን መተግበርና ያ ሐሳብ የሌሎች መሆኑንም ማሳወቅ መንግሥትን ያስከብረዋል እንጂ አያዋርደውም፡፡ መንግሥት ሁሉንም መንገድ ዘግቶ እሱ በሚያውቃት ጠባብ መንገድ ላይ ብቻ የአንድን አገር ሕዝብ እመራለሁ ማለት የትም እንደማያደርሰው ማወቅ አለበት፡፡ ሰዎች የተለያዩ አማራጮችንና መንገዶችን ማየት ይፈልጋሉ፡፡ ስለዚህ መንግሥት አማራጭ መንገዶቹ ምንም ይሁኑ ምን፣ በተቃዋሚዎችም ሆነ በሌሎች ሲቀርቡለት የሁሉንም ሐሳቦች ተቀብሎ የጋራ ውይይት በሚፈልገው ደረጃ ማድረግ አለበት፡፡ ውጤቱ የሚያለያይም ሆነ የሚያቀራርብ ለሕዝብ በግልጽ መንገርም ይኖርበታል፡፡ ያኔ ፍርዱ የሕዝብ ይሆናል፡፡

ለአብነት የወልቃይትን ጉዳይ በተደጋጋሚ ለመንግሥት ያቀረበ አካል መኖሩን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበውታል፡፡ የቀረበው ጥያቄ ለመንግሥት የማይጥመውና የማይቀበለው ሊሆን ይችላል፡፡ ግን አቅራቢ ኮሚቴዎችን ከመግፋት ይልቅ በክብር ተቀብሎ ጊዜ የወሰደ ውይይት አድርገው በመጨረሻም የሚደርሱበትን ውጤት በጋራ ለሕዝቡ ቢገልጹ፣ ይኼ ጉዳይ አሁን የደረሰበት ደረጃ የመድረስ ተስፋው የመነመነ ነበር፡፡

ኦሮሚያ ውስጥም በተደጋጋሚ ሕዝብና መንግሥት ቅራኔ ውስጥ የሚገቡበት አጋጣሚዎች አሉ፡፡ ነገር ግን ችግሮች በተፈጠሩ ቁጥር የእሳት ማጥፋት ሥራ ነው የሚሠራው፡፡ መንግሥት ችግሮቹን ይፈቱልኛል ብሎ የሚያስበው ችግሩ ከተፈጠረበት አካባቢ መጥተው በሥልጣን ላይ ያሉትን የፌዴራልና የክልል ባለሥልጣናትን ነው፡፡ እነዚህ ባለሥልጣናት ሕዝብ ውስጥ ገብተው የማረጋጋት ሥራ እንዲሠሩ ይነገራቸዋል፡፡ ባለሥልጣን ሆነው አዲስ አበባ ከመኖራቸው ውጪ ከሕዝቡ ጋር ስለማይተዋወቁ የሕዝቡ ተቃውሞ እነሱንም ያጠቃልላል፡፡

እነዚህ ሹመኞች በአካባቢው የሚገኙትን የድርጅታቸውን አባላትና ተገደው እንዲወጡ የሚደረጉ የመንግሥት ሠራተኞችን ሰብስበው ስለተቃዋሚዎች፣ ስለሻዕቢያ አፈጣጠር የተለመደውን ንግግር አድርገው አጨብጭበውና አስጨብጭበው ይመለሳሉ፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይ በምንም ሁኔታ የእነሱን ሐሳብ የሚቃወም መስሎ የታያቸውን ወይም በተቃዋሚ ድርጅትነት የሚጠረጠሩ ሰዎች ድርሽ አይሉም፡፡

ይኼንን ችግር መፍታት የነበረባቸው ትክክለኛ ባለቤቶቹ የዞንና የወረዳ አመራሮች መሆን ነበረባቸው፡፡ አብረው የሚኖሩና በቅርብ ችግራቸውን ያውቃሉ ተብሎ ስለሚገመት፡፡ ለነገሩማ እነሱም የሕዝብ ተመራጭ እኮ ናቸው፡፡ ስለዚህም መሠረታዊ የችግር አፈታት ሥራ ስለማይሠራ በየዓመቱ ችግሩም ሁከቱም ያገረሻል፡፡ ይኼንን ሁከት ለማስወገድ በአንዳንድ አካባቢዎች በቋሚነት በሚመስል ሁኔታ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴውን የሚቆጣጠሩት ከፌዴራል የሚላኩ የፀጥታ ኃይሎች ናቸው፡፡ ይኼ አማራጭ የሌለው ጊዜያዊ መፍትሔ ነው፡፡ ግን እስከ መቼ?

ነገር ግን ይኼን ችግር መፍታት ያለባቸው የአካባቢ፣ የዞንና የወረዳ መስተዳድሮችን ሕዝቡም አያውቃቸው፣ እነሱም መንግሥትን ወክለው እንደሚሠሩ ሆነው ለመታየት አይፈልጉም፡፡ ተወደደም ተጠላ መንግሥት የተቃዋሚንም ሆነ የተራውን ሕዝብ ሐሳብ ተቀብሎ መደራደር የሚገባው ጊዜ ላይ ደርሷል፡፡ ጠንካራ ተቃዋሚዎች የሉም እንጂ ከተገኙ ግማሽ መንገድ ሄደን እንቀበላቸዋለን የተባለው መተግበር ያለበት አሁን ነው፡፡ ነገር ግን በተቃራኒው የተቃዋሚን መኖር ያለመፈለግ አዝማሚያ እየታየ ነው፡፡

በፓርላማው ውስጥ የመንግሥት ዋና ተጠሪ ፓርላማው ተቃዋሚዎች ከነበሩበት ጊዜ ይልቅ አሁን በተሻለ ሁኔታ እየሠራ ነው የሚል ሐሳብ ሰጥተዋል፡፡ ይኼ ገዥው ፓርቲ እኔ ብቻ መግዛት አለብኝ፣ በአገሪቱ (ፓርላማ) ሌላ ተቃዋሚ አስተያየት መኖር የለበትም የሚል ሐሳብ እንዳለው አመላካች ነው፡፡ ፓርላማ የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከት ያላቸው ድርጅቶችና ፓርቲዎች በተለያየ አቋም የሚከራከሩበትና አብላጫው ድምፅ የሚያሸንፍበት እንጂ፣ ከቀድሞው የተሻለ ምርት አግኝቼበታለሁ የሚባልለት ፋብሪካ አይደለም፡፡ መንግሥት የተለመደውን የፖለቲካ አቋሙን ይዞ ምንም ሳያድግ እዚያው ቀንጭሯል፡፡ ስለዚህም የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው ከልማቱ ጋር ሲታይ በተቃራኒ አቅጣጫ እየሄደ ነው፡፡

በሕዝብ በኩልም የመደገፍና የመቃወም መብታችን እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ስለምንቃወመው ነገር ጠለቅ ያለ እውቀትና ባንቃወመው በሕዝብ ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት፣ ብንቃወመው የምናስገኘውን ጥቅም በአግባቡ ማወቅ አለብን፡፡ በተለይም ተቃውሞውን እንደ አጀንዳ የያዘውን ክፍል ማንነትና ከበስተጀርባው ምንም ዓይነት ሕዝባዊ ያልሆነ ተልዕኮ እንደሌለ ማረጋገጥ አለብን፡፡

ተቃውሞዎች በሰላማዊ ሠልፍ ደረጃ መመራት ያለባቸው ሕዝባዊ ወገንተኝነት ባላቸውና በምናውቃቸው ኢትዮጵያውያን ዜጐች ነው፡፡ ስለኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ምንም የማያውቁ ዳያስፖራዎች ውጪ ሆነው በሪሞት የሚቆጣጠሩት መሆን የለበትም፡፡ እኛስ ከእልቂታችንና ከመከራችን ተካፋይ መሆን የማይችሉ ወይም የማይፈልጉ በመሀላችን የማይገኙ ሰዎች በሚያስተላልፉልን የጦር አውርድ ቅስቀሳ የምንመራው እስከ መቼ ነው?

ባለፉት ሳምንታት ከተከሰቱት አደገኛ ሁኔታዎች መማር ያለብን ብዙ ቁም ነገር አለ፡፡ ኦሮሚያን የሚያህል ሰፊ ክልል ውስጥ በአንድ ቀን በሁሉም ቦታ በተመሳሳይ ሰዓት የተቃውሞ ሠልፍ እንዲደረግ፣ በተለያዩ ማኅበራዊ ድረ ገጾች በተወሰኑ ግለሰቦች ሲነገረን ከርሟል፡፡ በተወሰነ ደረጃም ተተግብሯል፡፡

ለመሆኑ ይኼን መልዕክት ሲያስተላልፉ የነበሩት አካላት በአንድ ጊዜ በአጠቃላይ ኦሮሚያ ውስጥ የሚካሄደውን ሠልፍ የሚመራ፣ የሚቆጣጠር፣ ሥርዓት የሚያስይዝና የሚያስከብር ሌላው ቀርቶ በሠልፈኞቹ መካከል እንኳ ችግር ቢፈጠር አመራር የሚሰጥ አካል አስቀምጠዋል? አስቀምጠናል እንኳ ቢሉ በመላው ኦሮሚያ ውስጥ መተግበር እንደማይችል ይታወቃል፡፡ የተቃውሞው አጀንዳስ ምን ነበር? መቅረብ ያለባቸው ጥያቄዎችና መፈክሮች ምንድናቸው? ወይስ የኦሮሚያ ሕዝብ በሙሉ በየግሉ የሚፈልገውን መፈክር ይዞ አደባባይ እንዲወጣና ግርግር ፈጥሮ እንዲማገድ ነው? መንግሥትን በዚህ ዓይነት በአንድ ሌሊት ማስወገድ ፈልገው ከሆነ ትርፍና ኪሳራው ተጠንቷል? እያንዳንዱ ሰው ጊዜ ሰጥቶ ስለሠልፉ ቢያሰላስል በምንም ሁኔታ በትክክል ለኦሮሚያ በሚያስብ ሰው የቀረበ ጥሪ ነው ማለት ይከብዳል፡፡ ከጀርባው ያሉትን አካላት መመርመርና መገመትም አይከብድም፡፡

የአማራው ክልል ሠልፍም ቢሆን ከኦሮሚያው በተሻለ ሁኔታ ተካሂዷል እንኳ ቢባል፣ በአንድ ቀን ሳይሆን በተለያዩ ቀናት በመሆኑና የሠልፉም አጀንዳ በዋናነት ከወልቃይት ጥያቄ ጋር በመያያዙ ነው፡፡ ይኼ ምናልባት ውስን አጀንዳ ስላለው የተለየ ሊመስል ይችላል፡፡ የተነሱት ጥያቄዎች በሰዎች አዕምሮ ውስጥ ያሉ በመሆናቸው መጠየቃቸው ተገቢ ነው፡፡

የሚገርመው ነገር ግን በጉራ ፈርዳና በተለያዩ ቦታዎች በአማራ ብሔረሰቦች ላይ የተፈጸመው እንግልትና መፈናቀል እንዲሁም የንብረት መውደም ሲቃወም የነበሩ ግለሰቦችና ድርጅቶች፣ በአማራ ክልል ውስጥ ያሉ ሌሎች ብሔረሰቦች በአማሮች ሲገደሉ ሲሰደዱና ንብረታቸው ሲወድም ትክክል ነው የሚል ህሊና እንዴት ይኖረናል? እነዚህ የውጭ አገር አራጋቢዎችም ሲሉት የነበረውን ሁሉ ረስተው እንዲህ ዓይነቱን ድርጊት ደግፈዋል፡፡ ለዚህ ሁሉ በዋናነት የዋህ ሕዝብ አግኝተው በፈለጉት መንገድ እየመሩ የራሳቸውንና የዘመናት ጠላቶቻችንን ዓላማ ለማስፈጸም የተዘጋጁ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያዊነታቸውን እንደ እባብ ቆዳ ገፈው ጥለው በትውልድ እዚህ በመፈጠራቸው ትውልደ ኢትዮጵያዊነት ብቻ የቀራቸው ሰዎች የሚያመጡት የእርስ በርሳችን መጠፋፊያ መንገድና የጠላቶቻችንን ድብቅ አጀንዳ ተቀብለው የሚያስተናግዱ መሆኑን ሁላችንም ልናጤነው ይገባናል፡፡ መርዙን የሚረጩልን ዘመኑ በፈጠረው ቴክኖሎጂና ረቂቅ ሚዲያዎች በመሆኑ የሚደርሰን በሪሞት ነው፡፡ እንዳይደርሰን ለመከላከልም ለመቀበልም ያስቸገረ ነው፡፡ የዚህ ሴራ ጠንሳሾች በውጭ የሬዲዮና የቲቪ ፕሮግራሞች መጥፊያችንን አዘጋጅተዋል፡፡

በርካታ የአገራችን ሕዝቦች ሕወሓት/ኢሕአዴግን ሊቃወሙ ይችላሉ፡፡ ለተቃውሞአቸውም በቂ ምክንያት ሊኖራቸው ይችላል፡፡ ተቃውሞአችንን የምንገልጸውና ዓላማችንን የምናስፈጽመው ግን እንደ እንቁራሪት ግለቱ እየጨመረ በሚሄድ፣ ግን የግለቱ መጨረሻ ምን እንደሆነ ሳናውቀው በሚገለን ብረት ምጣድ ላይ ተኝተን መሆን የለበትም፡፡

አሁን እየተካሄደ ያለው ትግል መንግሥትን ከሥልጣን ከማስወገድ በመለስ፣ የቀረቡትን ጥያቄዎች ብቻ በመመለስ የሚያበቃ አይመስልም፡፡ አፄ ኃይለ ሥላሴና ደርግም የብረት ምጣዱ ሙቀት ሳይሰማቸው ነው የከሰሙት፡፡ ለሩብ ምዕተ ዓመት ተደላድሎ ሥልጣን ላይ በመቆየቱና ሕዝቡም በአስተዳደሩ ዝርክርክነትና በመልካም አስተዳደር ዕጦት በመማረር ሌላ መንግሥት ቢፈልግ አይፈረድበትም፡፡ ነገር ግን ይኼ ምኞትና ፍላጐት እንዲፈጸም ከተፈለገ ቀዳሚና ተከታይ ሁኔታዎችን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ጥልቅ ግምትና እውቀት፣ በቂ ጊዜና ሁሉንም የሚያግባባ ድርድር፣ በሁሉም ዘንድ ተቀባይነት ያለው የኢትዮጰያዊነት ትርጉም ቀዳሚና ሁላችንም ልንግባባበት የሚገባን ጉዳይ ነው፡፡

እስከዚያው ግን ከኢሕአዴግ የተለየ አማራጭ አለኝ የሚል ካለ ይንገረን፡፡ መንግሥትም በእስካሁኑ ዓይነት የምርጫ ሒደት መቶ በመቶ አሸንፌ እቀጥላለሁ ካለ የሚያስኬድ አይመስልም፡፡ መጪው ጊዜ ግለቱ እየጨመረ ከሚሄደው ብረት ምጣድ ላይ ወርደን በአዲስ መንፈስ ስለአገራችን አጠቃላይ ሁኔታ የምንወያይበት፣ የምንከራከርበትና መፍትሔ የምናስቀምጥበት መሆን አለበት፡፡ አሁን በሕዝብም ሆነ በመንግሥት እየተኬደበት ያለው የጥፋት መንገድ መሆኑን ልብ ያለው ልብ ይበል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

         

Standard (Image)

ወቅታዊው የአገሪቱ ሁኔታ ዴሞክራሲያዊ ትራንስፎሜሽን ያሻዋል

$
0
0

     በአሳምነው ጎርፉ

ወደኋላ ተመልሰን አመጣጣችንን ስንዳስስ፣

ከካሌብ ዘመን ጀምሮ እስካሁኗ ድረስ፣

ከአፍ እስከ ገደፍ ተሞልቷል ታሪካችን በጀግንነታችን መወድስ፣

በደም የዋጀባት አገሩን አባት ለልጅ አስረክቦ፣

አደራ ብሎ በቃል አስሮ አደራ ብሎ አሳስቦ፣

የተፈጥሮ ግዴታውን ይፈጽማል፣

ከመሬት በታች ይውላል፤ ይላል አንድ ቀደም ባሉት ዓመታት የታተመ መጽሔት ላይ የቀረበ ግጥም፡፡ እነዚህን ስንኞች ለዚህ ትንታኔ መግቢያ ማድረግ የፈለግኩባቸው ዓላማዎች አሉኝ፡፡ አንደኛው አገራችን በረዥም የታሪክ ወንዝ፣ በብዙ ገባሮች ተደላድሎ የሚሄድ ገደል የሞላበት መሆኗ ነው (ይህን አባባል የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ በጥልቀት ሲተነትኑ ሰሞኑን ከከረመ ንግግራቸው አይቻለሁ)፡፡

ሁለተኛው በዚህ አገር ውስጥ የምንኖር ሕዝቦች ታሪክ የውድቀትም ይሁን የድል፣ የዕድገትም ይሁን የክሽፈት በየዘመኑ በነበሩ አባቶች ጥልቅ አገራዊ ስሜት አብሮነት የተገነባ መሆኑ ነው፡፡ በእርግጥ በገዥዎች መካከል በነበረ የግዛት ማስፋፋትም ይባል፣ ርስትና ግብርን የማብዛት ህልም ጦርነቶች እየተካሄዱ የሰውም የንብረትም ጥፋት (በየትኛውም ዓለም የነበረ የኃያልነት ፍልሚያ የወለደው ቢሆንም) ተፈጽሟል፡፡ በዚህ ሒደትም ሕዝቡ እንደ ሕዝብ ተሳስሮና ተባብሮ ከመኖር ያገደው አልነበረም፡፡

ማንም ቢሆን (መሪም፣ ፓርቲም፣ መንግሥትም) ኃላፊ፣ ጠፊና የሚቀያየር ነው፡፡ አገር ግን ቢቻል እንደገና እየተሻሻለ ባይሆንለት ደግሞ ነባር ይዞታውን (በሕዝብም በደንብ) ይዞ ተማምኖና ተሳስቦ እንዲቀጥል ማድረግ ተገቢና አስፈላጊ መሆኑን ለማሳየትም ነው፡፡

ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት ባለፉት ሁለት አሠርት ዓመታት ያለፉትን ፀረ ዴሞክራሲያዊ አገዛዞች በአመለካከትም ሆነ በአወቃቀር እንዲፈራርሱ አድርጓል፡፡ ቢያንስ የዴሞክራሲ ጭላጭል (ከነችግሩ) እንዲታይም ማድረግ ችሏል፡፡ በብዙ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፎ የአገሪቱን መሠረተ ልማቶች፣ የማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ዕድገቶች ለማሻሻል የሄደበት ርቀትም ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም፡፡

በዓለም አቀፍ መረጃዎች ወይም በመንግሥት አኃዞች እንደሚታየው ባለፉት 25 ዓመታት ውስጥ የአገሪቱ ሕዝብ ቁጥር በእጥፍ ጨምሮ 100 ሚሊዮን ተቃርቧል፡፡ ከዚህ ውስጥ 30 በመቶ በትምህርት ላይ እንዲገኝ መደረጉ፣ በ1983 ዓ.ም. 45 ዓመት የነበረው በሕይወት የመኖር አማካይ ዕድሜ አሁን 64 ዓመት መድረሱ፣ የነፍስ ወከፍ ገቢውም አምስት እጥፍ አድጎ ወደ 600 ዶላር በዓመት መጠጋቱ ተጨባጭ የለውጥ ማሳያዎች ናቸው፡፡

እነዚህ መልካም ተስፋዎች ቢኖሩም አሁንም 22 በመቶ የሚደርሰው ሕዝብ ከድህነት ወለል በታች ሲሆን፣ 17 በመቶ ያህሉ ደግሞ ሥራ አጥ ነው፡፡ ይህ ሥራ የሌለው ደሃ የሚባለው ኃይል ወጣትና በትምህርትም ሆነ በግንዛቤ ‹‹የተሻለ የሚባለው›› በመሆኑም አገር ጥሎ ከመሰደድ ጀምሮ የለውጥ ቀዳዳ የሚለውን ፈለግ ሁሉ ጥሶ ከመሄድ ወደኋላ ሊል አይችልም፡፡ በተግባርም እየታየ ያለው ይኼው እውነታ ነው፡፡

ኢሕአዴግ የመሠረተው መንግሥት ከኢኮኖሚያዊ ተስፋዎቹ በተቃራኒ የሚተችባቸው ጉዳዮችም (ገና ከመነሻው ጀምሮ) ትንሽ አይደሉም፡፡ የኤርትራን የነፃነት ጥያቄ የመለሰበት በተለይ የአገሪቱ ወደብ አልባ መሆን፣ ከጎረቤት አገሮች ጋር ለሩብ ክፍለ ዘመን ያልተቋጩ የጋራ ድንበሮች ጉዳይ፣ በአገር ውስጥ ከጎሳ ተኮር ፌዴራሊዝም ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነት መላላቱና አንድነት መሸርሸሩ ይጠቀሳሉ፡፡

ከሁሉ በላይ ሥርዓቱ በግንባር ቀደምነት መርቶ ሥራ ላይ ከዋለው ሕገ መንግሥት ጋር የሚጋጩ ሕግጋትና የአፈጻጸም አቅጣጫዎች መውረዳቸው ዴሞክራሲውን እየጎዱት እንደሆነ ተደጋግሞ መነገር ይዟል፡፡ በተለይ ከመደራጀት፣ ሐሳብን ከመግለጽ፣ የተቃውሞ ሠልፍ ከማድረግ፣ ነፃ ማኅበራትን ከመፍጠር አንፃር ያለው ፈተና የቁጣና የቅሬታ ምንጭ መሆን ጀምሯል፡፡ እዚህ ላይ በሕገ መንግሥቱ ከተጻፈው በተቃራኒ የዴሞክራሲን ምኅዳር እየቀፈደደው የመጣው የኢሕአዴግ ፍልስፍና ከሌሎች አገሮች ተሸራርፎ የተዳቀለ ነው የሚሉም ብዙዎች አሉ፡፡

እ.ኤ.አ. በ1949 የቻይናው አብዮታዊ መሪ ማኦ ዜዲንግ ‹‹አዲሱ ዴሞክራሲ›› ያለውን መርህ ‹‹ሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ የበላይነት›› በሚል ስያሜ የተቃዋሚ ኃይሎች ድምፅ እንዳይሰማ መቆጣጠሪያ ሥልት አድርጎት ነበር፡፡ የሩሲያው ሌኒንም ‹‹ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት›› ሲል ያወጣውን የፍፁም ሥልጣን መሠረት (Democratic Dictatorship) ያለ ጥያቄና ያለ መንገራገር ‹‹በተወስኗል›› ፈሊጥ አድርባይነት እንዲነግሥ አድርጓል፡፡ የእነዚህ አገሮች መሪዎች ተሞክሮ አምሳያ በዚች አገር የፖለቲካ አየር ውስጥ እያረበበ መምጣት አማራጭ ሐሳቦች (በራሱ በገዥው ፓርቲም ውስጥ ሆነ ከውጭ) ቦታ እንዳይኖራቸው አድርጓል የሚለው ሙግት ክብደት እያገኘ መጥቷል፡፡

‹‹ከ25 ዓመታት በኋላ በመነቃቃትና ለውጥ ውስጥ የነበረችን አገር ወደኋላ የሚመልስ ሁከት፣ የሕዝብ ቁጣና ተቃውሞ ያመጣው የፌዴራል ሥርዓቱ አይደለም፤›› የሚሉ ነባር የፖለቲካ ተንታኝ አጋጥመውኛል፡፡ እኝህ ሰው በዓለም ላይ 29 አገሮችና 2.4 ቢሊዮን ሕዝቦች በፌዴራል ሥርዓት መተዳደራቸውን ብቻ አይደለም የሚገልጹት፡፡ ይልቁንም ኢትዮጵያ የምትከተለው ‹‹ብሔር ተኮር›› የሚባለውን ፌዴራሊዝም ግን እንደ ህንድና ናይጄሪያ ያሉት አገሮች እንደተገበሩት ይጠቅሳሉ፡፡

በእነዚህ ሁለት አገሮች ግን የዴሞክራሲያዊነት ጉዳይ ህልውናቸውን ክፉኛ ሲፈትን ታይቷል፡፡ ለአብነት እንኳን ናይጄሪያ ብታድግም፣ ከፍተኛ የተፈጥሮ ሀብት ቢኖራትም የብሔርና የሃይማኖት ፍጥጫን የጋበዘ ኪራይ ሰብሳቢነት (Rent Seeking) እና ፀረ ዴሞክራሲያዊነት ውስጥ ተዘፍቃለች፡፡ በተቃራኒው ከ1,600 በላይ የብሔር ብሔረሰብ ቋንቋዎች የተመዘገቡባት ህንድ ቀስበ በቀስ ከእርስ በርስ ግጭትና መፋጠጥ እየወጣች የበለፀገ ኢኮኖሚና ለሦስተኛው ዓለም ሞዴል የተባለ ዴሞክራሲን በመገንባት ላይ የት ብዝኃነት ያለ ዴሞክራሲ ‹‹ከብት ባልዋለበት ኩበት ፍለጋ›› ነውና፡፡

እንደተንታኙ እሳቤ በብሔርና በቋንቋም ሆነ በጂኦግራፊና በሥነ ልቦና ትስስር ላይ የተመሠረተ ፌዴራሊዝም የዴሞክራሲያዊነት ወፍራም ማገር ካላበጀ ከውድቀት አይድንም፡፡ ከፌዴራሊዝም የዓለም ታሪክ ስንመዝ ጀርመን ፋሺዝም ባስከተለባት ውርደት ምክንያት እ.ኤ.አ. ከግንቦት 9 ቀን 1945 በኋላ መንግሥት አልነበራትም፡፡ በኃያላን አገሮች ወታደራዊ ዕዝ ሥር እስከ 1949 ቆይታለች፡፡ ሕገ መንግሥቱ እ.ኤ.አ. በ1949 ከፀደቀ በኋላ የመጀመርያው የአገሪቱ ቻንስለር በመሆን የተመረጡት ኮንራድ አደናወር (የክርስቲያን ዴሞክራቶች ኅብረት ሊቀመንበር) ግን መሠረታዊ መነሻ ያደረጉ ዴሞክራሲያዊነትን ነበር፡፡ በመሀል ላይ በሥርዓቶች መለዋወጥ፣ በርዮተ ዓለም የቀዘቀዘው ጦርነት ፍልሚያ ጀርመን እስከመለያየት ቢደርስም አንድ ጊዜ መሠረቱን በማይናወጥ አለት ላይ አስፍሯልና የዳበረ ኃያል አገር ለመሆን በቅቷል፡፡

የእንግሊዝ፣ የአሜሪካና የፈረንሣይ ዓይነቶቹን የፓርላማ ዴሞክራሲ ግንባታም ሆነ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ሠለጠነው ፈለግ እየተመሙ ያሉ አገሮች የለውጥ ታሪክ መሠረቱ ልማት ብቻ አይደለም፡፡ ዋነኛው የአገራዊ ጉዞው ምሰሶ ዴሞክራሲ (ነፃነት፣ መደማመጥ፣ ፍትሐዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት፣ የማሻያማ ግልጽነትና ተጠያቂነት. . .) እንደሆነ በግልጽ የሚታይ ነው፡፡

ልማት፣ ድህነት ቅነሳና አገራዊ ዕድገት ብቻውን ምሉዕነት ያለው የሕዝብ እርካታን እንደሚያመጣ ከ60 ዓመታት በፊት የባቡር፣ የግዙፍ መሠረተ ልማትና መሠረታዊ ፍላጎት ያሟሉት ከሁለትና ሦስት አሠርት ዓመታት በፊት መካከለኛ ገቢ አገሮች ተርታ የደረሱ ሊቢያ፣ ግብፅ፣ ቱኒዚያ፣ አልጄሪያ. . . የለውጥ ማዕበል ባልተቀሰቀሰባቸው ነበር፡፡ እነ ኢራቅ፣ አፍጋኒስታን፣ ሶሪያና የመንም ዕልቂት የሚጋብዝ ውጥንቅጥ ውስጥ ባልገቡም ነበር የሚለውን መከራከሪያ አለመፈተሽ ሞኝነት ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝብ ገና ብሔራዊ መግባባትን ፈጥሮ በዴሞክራሲያዊ አንድነት ያልቆመባቸው ጉዳዮች ብዙ ናቸው፡፡ ቀዳሚው አሻሚው የታሪካችን እውነታ ነው፡፡ አንዱ ድል፣ ስኬትና አገራዊ ማንነት የሚለውን ጉዳይ ሌላው ሽንፈት፣ ጥቃት ወይም ጥፋት ይለዋል፡፡ አንዱ ‹‹የአገሪቱ አባት›› የሚለውን ቀደምት መሪ፣ ሌላው ‹‹ጠላት›› እያለ ለትውልድ የሚተላለፍ ሐውልት ይሠራበታል፡፡ . . .

ያለመግባባቱ ከሕገ መንግሥቱ አናቅጽትም ጋር ይገናኛል፡፡ አንዱ አንቀጽ 39 ‹‹ይበትነናል›› ሲል ሌላው ‹‹ዋስትናችን ነው›› ይላል፡፡ በቡድንና በግል መሻት፣ በመንግሥት ሦስቱ ክንፎች የሥልጣን መለያየት፣ በፌዴራል ሥርዓቱ አከላለል፣ በማንነት ጥያቄ አመላለስ. . . ቀላል የማይባል አለመተማመንና መጠራጠር እንደተጋረጡ ናቸው፡፡

ከሁሉ በላይ ገዥው ፓርቲ ፖሊሲ አውጥቶ እየተገበራቸው ባሉ የልማት ሥራዎች፣ የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ ግንባታ ተግባራት ላይ እንኳን የተሞላ አጋርነት የማያሳዩ የፖለቲካ ኃይሎች አሉ፡፡ ለአብነት ያህል ታላቁ የህዳሴ ግድብን ያህል ግዙፍና ወሳኝ ፕሮጀክት ‹‹የሚያልቅ ሥራ አይደለም፣ በአነስተኛ ፕሮጀክቶች ሊተካ ይገባ ነበር፣ ከጎረቤት አገሮች ጋር የሚያፋጥጥ ሥራ ነው፣ አገሪቷን ለከፍተኛ ብድር ያጋልጣል፤ ኢሕአዴግ ለፖለቲካ ትርፍና የሕዝቡን አመለካከት ለማስየቀር ነው. . .›› እያሉ ሲተቹት ተደምጧል፡፡ ይኼ በልማት ሥራዎች ላይ ሳይቀር ያለው ልዩነት መስፋቱን ያሳያል፡፡

ብሔራዊ መግባባትን በተመለከተ በአንድ እውነት መስማማት ተገቢ ነው፡፡ ሁሉም የአገሪቱ የፖለቲካ ኃይሎችና ዜጎች በሁሉም ጉዳዮች ላይ ላይስማሙ ይችላሉ፡፡ የመግባባት ምልዑነት የትም አገር ቢሆን የለምና፡፡ ይሁንና ዴሞክራሲያዊ ባህልን በመገንባት አገሪቷን ወደፊት ለመግፋት እንደሚመኝ መንግሥትና ሕዝብ በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ መግባባትና መተማመን መፍጠር የግድና አስፈላጊ ነው፡፡

ለአብነት ያህል ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ አስፈላጊና ወሳኝ በሚባሉት ተቋማት ገለልተኝነት፣ ፍትሐዊነትና ብቃት ላይ ብቻ ሳይሆን የባለቤትነት ስሜት ላይ የተራራቀ ማኅብረሰብ አንድ የጋራ እሴት ለመገንባት አይቻልም፡፡ በዚህ ረገድ በምርጫ ቦርድ፣ በእንባ ጠባቂ፣ በሰብዓዊ መብት ኮሚሽንና በመንግሥት ሚዲያዎች ላይ እየወረደ ያለው ትችትና ‹‹አናምናቸውም›› ቅዋሜ በአንድ ዕርምጃ ሊሻሻልና ሊታረም ግድ ይላል፡፡

በተመሳሳይ የመከላከያ ኃይሉ፣ የፖሊስ፣ የደኅንነት ኃይሉና የሥርዓቱ መለያየት (ገለልተኝነት) ጉዳይም አዲስ ዓይነት ዕርምጃ ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡ በዚሁ ጋዜጣ ላይ ሂሳዊ አስተያየት እንደሰነዘሩት የቀድሞው የኢፌዴሪ አየር ኃይል አዛዥ ሜጀር ጄኔራል አበበ ተክለ ሃይማኖት (ጆቤ) እምነት፣ የመከላከያና የፀጥታ ኃይሉ ከአብዮታዊ ዴሞክራሲ የኢሕአዴግ ርዕዮት ካልተለቀቀ እስከመቼውም ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሽግግርን ማምጣት አይቻልም፡፡ እንዳለፈው ሥርዓት ወደ ዜሮ ድምር ፖለቲካ መውረድንም ያስከትላል፡፡

በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የዴሞክራሲ ሽግግር (Transformation) ያስፈልጋል የሚባልበት ሌላው ምክንያት፣ ሲቪል ሰርቪሱና የኢሕአዴግ ድርጅታዊ መዋቅር የተሰናሰሉበትን ገመድ የመበጠሱ ተግባር ነው፡፡ በየትኛውም ዓለም የገዥው ፓርቲ ፖሊሲና ስትራቴጂዎች ሳይበጣጣሱ በሲቪል ሰርቪሱ መተግበር አለባቸው፡፡ በእኛ አገር ሁኔታ ግን ትስስሩ ከፖሊሲ ማስፈጸም በላይ ነው፡፡

የገዥው ፓርቲ ተሿሚዎች ሲቪል ሰርቪሱን ይመራሉ፡፡ የኢሕአዴግና አባል ድርጅቶቹ አባላት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ‹‹ሠራዊት›› ናቸው›› የፓርቲ አባላት ምልመላ፣ ስብሰባና መዋጮ በቢሮክራሲው ውስጥ ያለገደብ ይከናወናል፡፡ የመንግሥት የጽሕፈት ቤት መሣሪያ፣ ተሽከርካሪ፣ አዳራሽ፣ አለፍ ሲልም በጀት ለፓርቲ ሥራ ማዋል እየተለመደ መጥቷል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ የሚደበቅና የሚያስወቅስ ሳይሆን የሚያስመሰግን በመሆኑ በተለይ በክልሎች በእጅጉ ተስፋፍቷል፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን በሲቪል ሰርቪሱ ውስጥ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል ወይም አመራር ሆኖ የተገኘ የሚደርስበት ውግዘት ነው፡፡

ከዚህ አንፃር ኢሕአዴግም ሆነ ሁሉም የአገሪቱ የፖለቲካ ኃይሎች የፓርቲና የመንግሥት መደበላለቅን ለማስቀረት ትኩረት መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎንም የተገዳዳሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ሰላማዊና ሕጋዊ መንገድን እስከተከሉ ድረስ በመላው አገሪቱ በነፃነት ያለሥጋት እንዲንቀሳቀሱ የማድረግ ጉዳይ ለነገ የሚባል ተግባር አይደለም፡፡ እንደስከዛሬው ‹‹የትም አይደርስ›› የተባለውን ለቅቆ፣ ሕዝብ የሚደግፈውን ለጉሞ ለማቆም መሞከር ትርፉ የሕዝብ ቁጣን መጋበዝ ነው፡፡

በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታም ሆነ ሕዝባዊ አንድነት መጠናከር ረገድ የተጀመሩ ሥራዎች አሉ፡፡ በትምህርት ቤቶች የሲቪክ ትምህርት፣ የሕፃናት ፓርላማ፣ የሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌዎች መተግበር (የሕፃናት፣ የሴቶችና ሌሎች ሰብዓዊ መብቶችን) መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከአሥር ዓመታት ወዲህ የብሔር ብሔረሰቦች፣ የባንዲራ ቀን፣ የመከላከያና የፖሊስ ቀን. . . የታዩ መልካም ምልክቶችም አሉ፡፡

ከዚህም በላይ ግን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ አገራዊ ስሜቶችን የሚገነቡ ሥራዎች ያስፈልጋሉ፡፡ አንደኛው ልማቱን በፍጥነትና በፍትሐዊነት ማስቀጠል ነው፡፡ ሁለተኛው ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ማስወገድ ነው፡፡ ሦስተኛውና ዋናው ግን ግልጽነትና ተጠያቂነትን የመሳሰሉ የዴሞክራሲ እሴቶችን የመተግበር ሥራ ሊሆን ይገባል፡፡ አሁን እየታየ እንዳለው ገዥው ፓርቲ በልማቱ መስክ ያሳየው ዓይነት ውጤት በሌሎች መስኮች አለማሳየቱ ውድቀት እያሳየ ነው፡፡

በተለይ የፌዴራል መንግሥት የጋራ እሴቶች በማጠናከር በኩል ያለው ክፍተትም ሊፈተሽ ይገባዋል፡፡ እንደ አገር ያለን የጋራ የሥራ፣ ቋንቋ፣ የጋራ ሰንደቅ ዓላማችንና የወል ተቋማት እንዴት እየተከበሩና እየተጠበቁ ነው? ሥነ ጥበቡና መንፈሳዊ ቅርሶች እንዴት የጋራ ሀብት እየሆኑ ነው? ከሃይማኖት ነፃነት በተጨማሪ የአማኞች አብሮነትና መተሳሰብ እንዴት እየተገነባ ነው? በብሔርና ብሔረሰቦች መካከል የነበረውን ታሪካዊና ባህላዊ ትስስር (መዋለድ፣ መጋባት፣ ማኅበር፣ ዕቁብና አክሲዮን መመሥረት. . .) እንዴት እያበረታታ ነው? . . . የሚል ሙግትና ውይይት ያስፈልጋል፡፡

እነዚህ በዕለት ተዕለት ሕይወታችን ውስጥ የሚፈጸሙ ማኅበራዊና ልማዳዊ ክስተቶች ከዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ጋር ምን አስተሳሰራቸው? የሚል ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ዛሬ ከ50 በላይ ራሳቸውን የቻሉ ግዛቶች ያቀፈችው ዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካ አገራዊ ልዕልና (Hegmomy) ከዜጎችም አልፋ በዓለም ሕዝብ አዕምሮ በማንገሷ ነው፡፡ ያውም አሜሪካ የራሱ ባህልና ግልጽ ማንነት ያለው ሕዝብ የሚኖርባት እንዳልሆነ እየታወቀ፡፡

በእኛ ሁኔታ ደግሞ ገና ከኋላ ቀርነትና ድህነት ሙሉ በሙሉ ባልተላቀቀ ማኅበረሰብ ውስጥ ከአንድነትና አብሮነት ይልቅ ልዩነትን በማንቀሳቀስ፣ ከጋራ እሴቶች በበለጠ የተናጠል መገለጫዎችን እያሟሟቁ የጋራ ቤት መሥራት ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ ‹‹በልዩነት ውስጥ ያለ አንድነት›› የሚለውን መፈክር ገልብጦ ዴሞክራሲያዊ አንድነትና ኅብረትን ማስቀደም ካልተቻለ አሁን እየታየ ያለውን ሥጋት ማስቀረት በቀላሉ የሚቻል አይደለም፡፡

ለማጠቃለል ለኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ትራንስፎርሜሸን ለማምጣት እንነሳ ሲባል በአንድ ወገን (በመንግሥት) ጥረት ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች፣ ምሁራን፣ የሃይማኖት አባቶች፣ መገናኛ ብዙኃንና የተለያዩ ሲቪክ ማኅበራትን ጨምሮ ዜጎችንም የሚመለከት ነው፡፡ የዴሞክራሲ ባህል ስርፀትና ትግበራ ከእነዚህ ተዋናዮች ውጪ ዕውን ሊሆን እንደማይችል ተገንዝቦ መትጋት ያስፈልጋል፡፡

የአገራችን ዴሞክራሲ ሽግግራዊ ለውጥ ማምጣት ወይም በአሳታፊነቱና የሕዝብ ተጠቃሚነቱ ማደግ ለሁሉም ተግባራት ወሳኝ መሆኑን መፈተሽም ግድ ይላል፡፡ ለተጀመረው ልማት ወይም ለሰላምና ለአገራዊ ደኅንነት ትልቁን ሚና የሚጫወት ነው፡፡ ካልሆነ ግን አንዱ የቤት ልጅ፣ ሌላው የእንጀራ ልጅ፣ አንዱ ዋነኛ የአገሩ ባለቤት ሌላው አኩራፊና ‹‹ጠላት››፣ አንዱ ተሽቆጥቁጦ አዳሪ ሌላኛው ሰማይ ልቧጥ ያለ፣ አንዱ ደሃና ዋስትና ቢስ ሌላኛው በጥቂት ዓመታት የናጠጠ ቱጃር. . . እየተሆነ የወል አገር መገንባት የሚታሰብም የሚሆንም አይደለም፡፡

እንግዲህ ይህን አሁን የምንወተውተውን ጉዳይ ነው አሜሪካኖቹም ሆኑ ሰሞኑን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ ጋር የተወያዩ የአውሮፓ አገሮች አምባሳደሮች በግልጽ የተናገሩት፡፡ ‹‹ሕዝብ በመግደል የሚመጣ ለውጥ አይኖርም፡፡ ችግሮቻችሁን ሁሉን አሳታፊ በሆነ የጋራ ውይይት መፍታት ይኖርባችኋል፡፡ ቅድሚያ ግን መንግሥት የራሱን ችግር መፈተሽ አለበት፤›› ሲሉ እቅጩን ምክረ ሐሳብ የሰነዘሩት፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው agorfoo@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

Standard (Image)

‹‹በመስተዋት ቤት ውስጥ የሚኖር ሰው መጀመርያ ድንጋይ ወርዋሪ መሆን የለበትም››

$
0
0

 በሚዛኑ አደራ

ከላይ የተመለከተው ምሳሌያዊ አነጋገር ወደ ጆሮዬ የገባው የሁለተኛ ደረጃ ትምህር ቤት ተማሪ እያለሁ ከዛሬ 40 ዓመታት ገደማ በፊት ነው፡፡ ጊዜው የደርግ መንግሥት የንጉሡን ሥርዓት ገርስሶ ሥልጣን የያዘባቸው የመጀመርያዎቹ ዓመታት አካባቢ ይመስለኛል፡፡ በወቅቱ በዚህ ምሳሌያዊ አነጋገር ርዕስ ሥር ከደርግ የተሰጠ መግለጫ ነበር፡፡ እንደማስታውሰው መግለጫው የተሰጠው ደርግ ኢዲ አሚን ዳዳ ይመሩት ከነበረው የኡጋንዳ መንግሥት ጋር ገብቶበት ለነበረው የዲፕሎማሲ ፍጥጫ የኡጋንዳን መንግሥት የተቸበት ነበር፡፡ የመግለጫው ቁልፍ ይዘትም ኡጋንዳ ራሷ በችግር ውስጥ ሆና እያለ ትንኮሳ ውስጥ መግባት እንደሌለባት የሚያስገነዝብ ነበር፡፡

ይህ ምሳሌያዊ አነጋገር ከዚያ በፊትም ከዚያ በኋላም አንብቤውም ሰምቼውም አላውቅም ነበር፡፡ እነሆ ዛሬ እኔው ራሴ ከ40 ዓመታት በኋላ ምሳሌያዊ አነጋገሩን በርዕስነት መርጬ በወቅታዊ አገራዊ ጉዳይ ላይ ልጽፍበት ወሰንኩ፡፡

ከጥቂት ሳምንታት በፊት ጀምሮ በሰሜን ምዕራብ የአገራችን ክፍል በተለይም በጎንደርና በባህር ዳር ከተሞች እንዲሁም አካባቢዎቻቸው ሕዝባዊ አመፅና ረብሻ ተቀስቅሶ ለብዙ ሰው ሕወይትና ንብረት ጉዳት ምክንያት መሆኑ፣ በመንግሥትም ሆነ ከመንግሥት ውጪ ያሉ ወገኖች ዘግበውታል፡፡ ከደረሰው የሰው ሕይወት ጉዳት ውስጥ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና የሲቪል የማኅበረሰብ አባላት እንደሚኙበት ታውቋል፡፡ በንብረት ጉዳቱም የመንግሥት፣ የድርጅቶችና የግለሰቦች ሀብት እንደሚገኝበት ተመልክቷል፡፡

ይህ ሁሉ ጥፋትና ውድመት መፈጸም ያልነበረበትና አሳዛኝ ነው፡፡ የበለጠ የሚያሳዝነው ግን የሕይወትም ሆነ የንብረት ጉዳት ከደረሰባቸው ውስጥ ሁከት በመፍጠርም ውስጥ ያልነበሩ፣ በፀጥታ አስከባሪነትም ያልተሰማሩ፣ ጉዳቱ እቤታቸው ድረስ ሄዶ ያጠቃቸው ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች የጉዳትና የጥቃት ሰለባ የሆኑበት ጥፋትና ምክንያት ደግሞ የመጡበት ብሔር እንደሆነ ተዘግቧል፡፡ እንዲያውም ከጥቃት የተረፉትም በአስቸኳይ አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ በርካታ በራሪ ወረቀት እየተበተነባቸው እንደሆነ ይሰማል፡፡

በእርግጥ አንዳንድ ወገኖች (ተምረናል የሚሉት) ብሔርን መሠረት አድርገው ጥቃት የፈጸሙትን ያህል ይህንን ድርጊት በፅኑ አውግዘው ንብታችሁን ለመከላከል ከአቅማችን በላይ ቢሆንም ሕይወታችሁን እናድን ብለው፣ ተጠቂዎቹን ዋናው መኝታ ቤታቸው ሳይቀር ለእነሱ ለቀው ከሞትና ከድብደባ የተከላከሉ (ፊደል ያልቆጠሩት) ወገኖች እንዳሉም እየተነገረ ነው፡፡ የእናት ሆድ ዥንጉርጉር መሆኑ ነው፡፡

በጎው ነገር የኢትዮጵያዊነት መገለጫ በመሆኑ ይበል የሚባል ተግባር ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን ሰዎችን በዘራቸውና በብሔር ምንጫቸው ፈርጆ የጥቃት ዒላማ ማድረግና ለቀው እንዲወጡ መመርያ መስጠት የት ያደርሰናል? የአማራን ሕዝብስ ይጠቅመዋል ወይ?  ብሎ በሰከነ መንገድ መመርመሩ ተገቢነት አለው፡፡

ሲጀመር ይህንን ‹‹አካባቢን ካልተፈለገ ዘር የማጥራት›› ዕርምጃ እያስተላለፉና እያስፈጸሙ ያሉት የሃይማኖት አጥባቂ አማኞች፣ ለሰብዓዊ መብት ተቆርቋርቋሪና የአማራ ሕዝብ ጥቅምና ክብር ጠባቂ ነን የሚሉ ወገኖች መሆናቸው ይሰማል፡፡ ጥያቄው ነን የሚሉትን እየሆኑ ነው ወይ? የሚል ነው፡፡

እንደሚታወቀው ሃይማኖት በፈጣሪ አምሳል የተፈጠረን የሰው ልጅ ክብር ሊሰጠው እንደሚገባ ይሰብካል፡፡ ታዲያ ይህ ድርጊት ከሃይማኖት አንፃር ምን ማለት ነው? ከሰብዓዊ መብት መርህም አንፃር ሲታይ ሰዎች ሁሉ እኩል መሆናቸው፣ እኩል ክብርና አያያዝ ሊሰጣቸው እንደሚገባ፣ እንዲያውም በዘራቸው፣ በሃይማኖታቸው፣ በፖለቲካ አመለካከታቸው፣ ወዘተ ምክንያት መድልኦና መገለል ሊደርስባቸው እንደማይገባ በግልጽ የተቀመጠ ጉዳይ ነው፡፡

የጥቃት ዒላማ የሆኑት ወገኖች ብሔራቸውንም ሆነ ዘራቸውን መርጠው የያዙት አይደለም፡፡ ሊለውጡትም የሚችሉት ነገር አይደለም፡፡ ይህ እንደ ጥፋት ተቆጥሮ ለጥቃት ሲዳርጋቸው እጅግ ያስቆጫል፡፡ ለሰብዓዊ መብት እቆረቆራለሁ የሚል ወገን ሊፈጽመው አይገባም ነበር ብቻ ሳይሆን ድርጊቱን ጮክ ብሎ ሊያወግዘው በተገባም ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ሰብዓዊ መብት ሲደፈር ያንገሸግሸናል ባዮቹ እነ ፕሮፌሰር መስፍን፣ እነ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ጉባዔ፣ እነ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ምነው በዚህ ወቅት ብዕራቸው ደረቀ? ልሳናቸው ተዘጋ?  አልሰማንም እንዳይሉ በአልጄዚራ ሳይቀር ሽፋን የተሰጠው ጉዳይ ነው፡፡

የሃይማኖት አጥባቂነትና ለሰብዓዊ መብት መቆርቆርን ጉዳይ በዚህ ትተን ዕርምጃው ለአማራ ሕዝብ ይበጃል ወይ? ጥቅሙንስ ያስከብራል ወይ? የሚለውንም ማየቱ ተገቢ ነው፡፡ በታሪክ ሒደትና አጋጣሚ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ካንዱ የአገሪቱ ጫፍ ወደ ሌላው እየተዘዋወሩ ጎጆ ቀልሰው፣ ወልደው ከብደው መኖር ከጀመሩ ብዙ ዓመታት አስቆጥረዋል፡፡ በተለይም የአማራ ሕዝብ ከጫፍ እስከ ጫፍ በሚባል ደረጃ እንደ ጨው ተዘርቶ የሚኖር ሕዝብ ነው፡፡ በምዕራቡም በምሥራቁም፣ በሰሜኑም በደቡብም ቁጥሩ ይለያይ እንደሆነ እንጂ የአማራ ሕዝብ ያልሰፈረበት የኢትዮጵያ ክልል የለም (1999 የቤቶችና ሕዝብ ቆጠራ ማየት ይጠቅማል)፡፡ በጎንደርና በተወሰነ መልኩም በባህር ዳር እየተተገበረ ያለው አካባቢን ከሌላ ብሔር የማፅዳት ዕርምጃ በሌሎች ክልሎችም ተግባራዊ እንዲደረግ ዕድል ከተሰጠው ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል ከወዲሁ መገመት ይገባል፡፡ የዕርምጃችን ምንነትና ሊያስከትለው የሚችለው ውጤት አማትሮ ማየት ብልህነት ነው፡፡

ለነገሩ በተወሰነ የአማራ ክልል በጥቂት በጭፍን ጥላቻ በተሸበቡ ጉልበተኞች አርቆ አሳቢነት የጎደለው ዕርምጃ በማየት በሌላው የአገሪቱ ክፍል በሰላም ጥሮና ግሮ በሚኖረው የአማራ ተወላጅ ላይ የአፀፋ ዕርምጃ መውስድ ከመርህ አንፃር ተቀባይነት የለውም ብቻ ሳይሆን፣ ጥላቻን በጥላቻ መመለስና በጉልበተኞቹ ደረጃ ወርዶ ማሰብ ይሆናል፡፡ ከዚህም አልፎ ይህንን ኢሃይማኖታዊና ኢሰብዓዊ ተግባር በምሬት እየተቃወመ ላለው ለአብዛኛው የአማራ ሕዝብም ተገቢ ክብርና ዕውቅና መንፈግም ይሆናል፡፡ እዚህ ላይ ለማሳየት የተፈለገው ዋናው ነገር አካባቢን ከሌላ ብሔር የማፅዳት ፕሮጀክት በአገር ደረጃ ተግባራዊ ከተደረገ፣ ቆመንለታል ለሚሉት የአማራ ሕዝብ አይጠቅምም ብቻ ሳይሆን ከማንም በላይ ተጎጂ የሚሆነው እሱ ነው፡፡

በተጨማሪም የእኛ ያልሆነ ለቆ ይውጣልን የሚለው አመለካከት ልዩነትን አለመቀበል ስለሆነ ሌላ ጣጣም አለበት፡፡ ልዩነት ያለመቀበል ሲመጣ ማቆሚያ የለውም፡፡ የአማራ ሕዝብ አንድ የሆነውን ያህል ልዩነትም አለው፡፡ የሃይማኖት ልዩነት አለው፣ የፖለቲካ አመለካከት፣ የኢኮኖሚ አቅም ልዩነት አለው፡፡ ሌሎች የልዩነት መሠረቶችም አሉት፡፡ በመሆኑም ተሳክቶለት የሌላውን ብሔር ጠራርጎ ክልሉን ካፀዳ በኋላም ቢሆን ትግሉ አያበቃም፡፡ ወደ ውስጡ ተመልሶ የሃይማኖትም ሆነ ሌሎች ልዩነቶችን በማሳደድ መተራመሱ አይቀርለትም፡፡ ልዩነትን መቀበል እንጂ ማስወገድ አይቻልም፡፡ ስለዚህ ይህ አካሄድ በሌላ ክልል ውስጥ ለሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ብቻ ሳይሆን፣ በክልላቸው ውስጥ ለሚኖሩትም ቢሆን ዘላቂ ሰላምና እርጋታ የሚሰጥ አይሆንም፡፡ በመጨረሻም በተለያዩ ክልሎች በብዛትና በስፋት የሚኖር ሕዝብ፣ በውስጡም የሃይማኖትና ሌሎች ልዩነቶችን ይዞ የሚኖር ሕዝብ ሆኖ እያለ ክልሉን ከሌላ ብሔር ለማፅዳት መነሳትና መሞከር በመስተዋት ቤት እየኖሩ ሌላው ላይ ድንጋይ የመወርወር ያህል እንዳይሆን፣ አርቆ አሳቢ ወገኖች ቢገቡበት ይበጃል ባይ ነኝ፡፡ ሳይቃጠል በቅጠል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

 

 

 

Standard (Image)

ይድረስ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም

$
0
0

በሀብተሥላሴ ለይኩን (ዶ/ር)

በአዲሱ ዓመት መግቢያ ላይ ቆሜ እንደ አንድ የአገር ተቆርቋሪ ዜጋ ይህን መልዕክት ለማድረስ የወደድኩት ወቅታዊው የአገራችን ሁኔታ አሳሳቢ ስለሆነብኝ ነው፡፡ እንደ አቅሜ መንግሥት በሚፈጥራቸው ብዙዎቹ የምክክር መድረኮች እየተገኘሁ ያመንኩበትና የመሰለኝን ከመግለጽ ወደኋላ ባልልም፣ ‹‹ኢሕአዴግ አፍ እንጂ ጆሮ የለውም›› እንዲሉ እምብዛም ሰሚ ማግኘት አልቻልኩም፡፡

በመሆኑም ቢያንስ ለታሪክ መመዝገብ ስላለበትና ለክቡርነትዎ በተጨማሪ ሪፖርተር ጋዜጣን የሚያነብ ‹‹ወዳጅ››፣ ‹‹ጠላትም›› ሆነ መሀል ሠፋሪ ስለሚመለከተው ሐሳቤን ለመግለጽ ወድጃሁ፡፡ ማስተናገድ ያለማስተናገድ የሪፖርተር ጋዜጣ ፈንታ ሆኖ በግሌ ግን ያለንበት ሁኔታም ሆነ መደረግ ስላለበት ከአቻ የሥራ ጓደኞቼ፣ ከኢመደበኛ ወዳጆቼና በተለያየ አጋጣሚ ከማገኛቸው ሰዎች ጭምር የተረዳሁትን አጠናቅሬ ላቀርብልዎት ሞክሬያለሁ፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር!

በቅርቡ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴና የኢሕአዴግ ምክር ቤቶች ያደረጉዋቸውን ግምገማዎች አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ከመላው አገሪቱ ‹‹የተውጣጡ ናቸው›› ከተባሉ ሦስት ሺሕ ገደማ የሚደርሱ ወጣቶች ጋር ያደረጉትን ውይይትም አይቻለሁ፡፡ በእነዚህ ንግግሮች በልበ ሙሉነት ስለአገሪቱ ቀጣይነት እያሰቡ፣ በነባሮቹ የኢሕአዴግ ፖሊሲዎች ሕዝቡን መልሰው ለመምራት እንደተዘጋጁም ሁኔታዎች ያሳብቃሉ፡፡

በእኔ እምነት ግን አሁን አገሪቱ ክፉኛ ታማለች፡፡ እርስዎ ‹‹ግምገማ›› ባሉት መድረክና በወጣቶች ውይይት ላይ እያሉ እንኳን በተለይ በጎጃም፣ በጎንደርና በምሥራቅ ሐረርጌ ዞኖች ከ100 በላይ ንፁኃን ወጣቶች በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው ተሰምቷል፡፡ በእነዚሁ ቀናት የወደመው ንብረትም በደሃ አገር ኢኮኖሚ ሲሰላ እጅግ የሚያስቆጭ ነው፡፡

አሁን ባለው ግርድፍ የፖሊስ መረጃ መሠረት በባህር ዳር፣ ዳንግላ፣ ፍኖተ ሰላም፣ ደምበጫ፣ ቡራዩና መሰል ከተሞች በርካታ የአበባ እርሻ ልማቶችን ጨምሮ የግል ኢንቨስትመንቶች፣ የሕዝብ መገልገያ ተቋማት፣ የግለሰቦች ቤቶችና ተሽከርካሪዎች ውድመት እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ሊደርስ ይችላሉ መባሉን ሰምተናል፡፡ ይህ ጉዳት ከጎንደርና ለወራት ከዘለቀው የኦሮሚያ ሁኔታ ጋር ተዳምሮ ሲታይ ምንኛ አገሪቷን እንዳከሰረ መገመት አያዳግትም፡፡

እንደ አገር ፈጣን ልማት ያመጣች፣ በርካታ ስደተኞች ተቀባይ፣ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋነኛ አፍሪካዊት ሰላም አስከባሪ የተባልን ነን፡፡ ይሁንና ዘንድሮ ከዳር እስከ ዳር በታየው ቀውስ፣ የመልካም አስተዳደርና የዲሞክራሲ ዕጦት ተምሳሌት ሆነናል፡፡ የፌዴራል ሥርዓቱ ጎሳ ተኮርነትም እንኳን አንድነትን ሊያመጣ በቀበሌና በወረዳ ድንበር አገር ሊበትን የሚችል ውዝግብ ውስጥ የምንገባ መሆናችን ታይቷል፡፡ ይህንን አምነስቲ ኢንተርናሽናልን ጨምሮ በርካታ የሰብዓዊ መብት ተማጋቾች፣ ዋና ዋና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሚዲያዎችና ምዕራባውያን እየገለጹት ነው፡፡ (አንዳንድ መንግሥታትም በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ምክንያት ለዜጐቻቸው ማስጠንቀቂያ እስከ መስጠት ደርሰዋል) ይህን ያፈጠጠ ሀቅ ደግሞ ሻዕቢያና ግብፅ የሠሩት ሴራ ነው እያልን ራሳችንን ልናታግልበት አንችልም፣ አይገባምም፡፡

ክቡርነትዎ!

በእርግጥ ያሳለፍነው ዓመት ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ጥሩ ጊዜ የሚባል አልነበረም፡፡ በአገሪቱ ከ50 ዓመታት ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ ድርቅ መታየት፤በጋምቤላ ክልል በደቡብ ሱዳን የጎሳ ታጠቂዎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ሕልፈት፣ የበርካታ ሕፃናት ተጠልፎ መወሰድና ሌሎችም ሥጋቶች ተከሰቱ፡፡ በአገሪቱ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ የፀረ ስደት ግብረ ኃይል ቢቋቋም ሕገወጡ ስደቱ ከመባባስ አልተገታም፡፡ እንዲያውም በደቡብ በኩል በሚደረግ የቡድን ስደት በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች በየኮንቴነሩ ሞተው ተገኙ፡፡ በኬንያ፣ በሱዳንና በታንዛኒያ እስር ቤቶች የሚማቅቁት ‹‹ሕገወጦችም›› የውድቀት ማሳያ ናቸው፡፡ ታዲያ የአገሪቱ ለውጥና ዕድገት እምኑ ላይ ነው? ያስብላል፡፡

ያጠናቀቀነው ዓመት ከስኬት ይልቅ የችግርና የቀውስ ነው የሚባልበት ሌሎች ማሳያዎችም አሉ፡፡ ቀዳሚው እርስዎ የሚመሩት መንግሥትና አጋሮቻችሁ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱን ያለምንም ተቀናቃኝ ከያዛችሁ በኋላ የዲሞክራሲ ምኅዳሩ ይበልጥ መጥበቡ ነው፡፡ በተለይ ኢሕአዴግ እምብዛም ሕዝቡ ድጋፍ የማይሰጣቸውን ‹‹ተቃዋሚዎች›› ለጨዋታው ማሟሟቂያ ያህል ይዞ ቢንቀሳቀስም በነፃ መደራጀት፣ ሐሳብን በነፃነት መግለጽ፣ የፖለቲካ ድጋፍም ሆነ ተቃውሞ ማድረግ ቅንጦት መሆኑ የውድቀት መጀመሪያ ነበር፡፡

በድርጅትዎ አሥረኛ ጉባዔ ላይም ቢሆን ‹‹ዲሞክራሲያዊ ሥርዓቱ ይጠናከራል፣ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦቱም እየተባባሰ ስለሆነ እንገታዋለን፤›› የሚል ቃል ኪዳን ተገባ፡፡ ከዚያ በኋላ በ‹‹ጥናት›› ላይ የተመሠረተ ውይይትም ተካሄደ፡፡ ሕዝቡም አጀንዳውን ከአደባባይ አልፎ በየጓዳው አብላላው፡፡ ይሁንና ከውይይትና ‹‹ግምገማ›› ያለፈ እዚህ ግባ የሚባል ዕርምጃ አልታይ አለ፡፡ ለምሳሌ አዲስ አበባን ጨምሮ በታችኛው የመንግሥት እርከን ላይ ያሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ‹‹የኢሕአዴግ›› አመራሮች ከሥራቸው ተነሱ ተባለ፡፡

ከእነዚህ ብዙዎቹ ተነሽዎች ወደ ትምህርት ቤት፣ መልሶ ወደ ሌላ ሹመትና የንግድ ሥራ እንደገቡ ይነገራል፡፡ አስገራሚው ነገር በአቅም ማነስና በትምህርት ዝግጅት መጓደል የተነሱት ምንም አይደል፡፡ ‹‹ሙሰኛ›› የተባሉት ግን በሕግ የሚጠየቁበትም ሆነ ያጋበሱት የሕዝብ ሀብት የሚመለስበት ምልክት እንኳን አለመታየቱ ነው፡፡ ጭራሽ የመንግሥትዎ ሙሰኛና ሕገወጥ ካድሬዎች ገንዘብ እየተቀበሉ ከማስተር ፕላን ውጪ የሕዝብ መሬት ሲሸነሽኑ የከረሙበት ቦታ ላይ የሠፈሩ ዜጎች በግፍ ተፈናቀሉ፡፡ ከነልጆቻቸውም ወደ ጎዳና ተበተኑ፡፡

‹‹ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትን ለመታገል ኢሕአዴግ ወኔ የለውም፤›› የሚሉ ተቺዎች ለመብዛታቸው ማረጋገጫው የክራሞቱ ሁኔታ ነው፡፡ በትልልቅ ባለሥልጣናት ደረጃ በየብሔራዊ ድርጀቱ የሚነሳው ሐሜት፣ በተለይ በዋና ዋና ከተሞች በአንድ ጀንበር የበለፀጉ ጥቂት የሥርዓቱ ነቀዞች ጉዳይ በቸልታ መታለፉ ሕዝቡን ተስፋ አስቆርጦታል፡፡ ሊሸሽግ ያልቻለው የዋና ኦዲተር ሪፖርት፣ የሜጋ ፕሮጀክቶች መጓተት፣ እንደ ‹‹ሜቴክ›› ባሉ የመንግሥት ካምፓኒዎች ላይ የሚነሳ ቅሬታ ሁሉ መንግሥት ሊለወጥ አይችልም የሚል ድምዳሜ እያስያዘ መጥቷል፡፡

በዚህ መሀል እርስዎም ሆኑ የካቢኔ አባላትዎ ‹‹የመልካም አስተዳደርና የሪፎርም ሥራዎ ውጤት እያጣ ነው፤›› ወደሚል ያልተጨበጠ ፕሮፓጋንዳ ገባችሁ፡፡ በምክር ቤት ሪፖርት ሳይቀር ይኼው ተገለጸ፡፡ ግን አሁንም ያለብቃት፣ በትውውቅና በዝምድና መሾሙ ቀጥሏል፡፡ በአገራቸው ጉዳይ ተቆርቋሪ የሆኑና ሊያገለግሉ የሚችሉ ዜጎች በማንነታቸው ብቻ ይጠረጠራሉ፡፡ ይገፋሉም፡፡ ታዲያ ይህ ምንን ያሳያል? መታበይና እብሪትን ካልሆነ፡፡

በአዲስ አበባ የመሬት ካርታ ማውጣት፣ ማሳደስ፣ ውኃና መብራት ማስቀጠል፣ በትራንስፖርት መስክ ሊብሬ፣ ታርጋ ወይም የተሽከርካሪና የአሽከርካሪ ብቃት ማውጣት መሠለፍንና የቀጠሮ ርዝማኔን ብቻ አይደለም የሚጠይቁት፡፡ ጉቦ የሚያስገፈግፉም ናቸው፡፡ ሌላው ቀርቶ ዜጎች ግዴታቸውን ለመወጣት አስበው ለግብርና ለታክስ ጉዳይ ሲሄዱ ጉቦና ሙስና የሚጠየቁበት አሳዛኝ አገር እየተፈጠረች ነው፡፡

በየአካባቢው ያሉ የቀበሌ አስተዳደር አካላትና ደንብ አስከባሪ ተብዬዎች የየመንደሩ ሽፍቶች ሆነዋል፡፡ ‹‹ሕገወጥ›› በሚሉት ግንባታ፣ የቤት እድሳት፣ ገበያ፣ ንግድ… ስም ወደ ሕጋዊነት እንዲሄዱ ከማድረግ ይልቅ ጉቦ እየተዋጣ እንዲሰጣቸው መድፈር ጀምረዋል፡፡ በእርግጥ እዚህ ላይ ጉቦኛን የሚያፋፋው ሕዝብም ሥርዓቱን እያገዘው ባለመሆኑ በእጅጉ ያሳዝናል፡፡ በትራፊክ ፖሊሶችና ሌሎች ፖሊሶች አካባቢ የሚታየው የሥነ ምግባር መጓደልም በሥርዓት ደረጃ ያለው ብልሽት ውጤት ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ጉድ ታዲያ ሕዝብን አያስቆጣም?

በ2008 ዓ.ም. ሌላኛው አሳዛኝ ሁኔታ የተከሰተው በአገሪቱ ሕዝባዊ እምቢተኝነትና ይህን ተከትሎ የተስተዋለው የንፁኃን ሕልፈትና የንብረት ውድመት ነው፡፡ በተለይ በኦሮሚያ ክልል ለወራት በዘለቀው ሠልፍና ግጭት ከ450 በላይ ንፁኃን ዜጎች ሕይወት አልፏል፡፡ በአማራ ክልልም ቀስ በቀስ እየተስፋፋ በሄደ ግምት ተመሳሳይ የሚባል ቁጥር ያለው ሕይወት አልፏል፡፡ የአካል መጉደሉና የጅምላ እስሩም ቢሆን ሕዝብና መንግሥትን የሚያቃቅር ነው፡፡

ክቡርነትዎ!

በሁለቱ ትልልቅ ክልሎች የተነሳው ግጭት ‹‹ሕዝባዊ እምቢተኝነት ነው›› የሚባልበት ግልጽ መገለጫ አለው፡፡ የተለያዩ የአገሪቱ የፖለቲካ ተንታኞችና ምሁራን እንደሚሉት በኦሮሚያ መነሻው ‹‹የአዲስ አበባና የፊንፊኔ ዙሪያ የጋራ ማስተር ፕላን›› በአማራ ክልልም ‹‹የወልቃይትና አካባቢው የማንነት ጥያቄ›› ይሁኑ እንጂ፣ የተጠራቀሙ የሥርዓቱ ድክመቶች ድምር ውጤት የፈነቀለው ቀውስ መሆኑን ነው፡፡

ቀዳሚው ጉዳይ ከሁለቱ ሰፋፊ ክልሎች የወጡና በማንነታቸው የተደራጁ የተቃዋሚ የፖለቲካ ኃይሎች ከሌሎችም በባሰ ደረጃ ተገፍተዋል (Marginalized ሆነዋል)፡፡ በዚህም ብዙዎቹ ፓርቲዎቻቸውን በትነው ተሰደዋል፡፡ አሊያም በእስር ቤት የመማቀቅ ዕጣ ገጥሟቸዋል፡፡ ይህ በሌሎች አናሳ ብሔረሰቦች ውክልና ያላቸው የፖለቲካ ኃይሎች ያልታየ ግፉአንነት መሠረቱ መንግሥት ጽንፈኛ ከሚላቸው ኦነግና ግንቦት ሰባት ጋር ሊያያዝ ቢችልም፣ በአገር ውስጥ ያሉትም ከመድቀቅና ከመበታተን አልዳኑም (መኢአድ፣ አንድነት፣ ኦፌኮን፣ ወዘተ ያሉበትን ሁኔታ ይመለከቷል)፡፡

እነዚህ የፖለቲካ ኃይሎች ደግሞ መጠኑ ይብዛም ይነስ ደጋፊ የላቸውም ሊባሉ አይችሉም፡፡ አሁን አንዳንድ ታዛቢዎች እንደሚሉት ማንነትን ዋነኛ ጉዳዩ እያደረገ በመጣ ማኅበረሰብ ውስጥ ብሔር ተኮር ድርጅቶችን ማዳከም፣ ተወላጁን ቅር ማሰኘት እንደሆነ መንግሥት ያለመጠርጠሩ ውጤት ነው፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር!

ሌላኛው ጉዳይ በእርስዎ ካቢኔ ብቻ ሳይሆን ባለፉት ሩብ ክፍለ ዘመናትም ያልታዩና እንደ ዋዛ ሥር እየሰደዱ የመጡ የፓርቲዎና የመንግሥት ችግሮች ናቸው፡፡ ለምሳሌ እርስዎ በቅርቡ የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ በ‹‹ጥልቀት›› ገምግሞታል ያሉት የወልቃይት የማንነት ጥያቄና ግጨው አካባቢ ያለ የሁለቱ ክልሎች ድንበር ጉዳይ እስካሁን ለምን ከረመ?! ቢባል መልሱ ግልጽ ነው፡፡ ሕዝብን ያለማዳመጥና አድርባይነት (ፍርኃት) ይመስለኛል፡፡

ሰሞኑን በአንድ ታዋቂ ድረ ገጽ ላይ ቃለ መጠይቅ ያደረጉት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ሳይቀሩ፣ ‹‹ጉዳዩን ገፍተን ሄደን በሕዝበ ውሳኔ አንፍታው እንጃ ድርጅቶቹ በትጥቅ ትግል ላይ ከነበሩበት ከ1976 ዓ.ም. ጀምሮ ይነሳል፡፡ አወዛግቦንም ያውቃል፤›› ብለዋል፡፡ እንግዲህ ዛሬ ለዓባይ ወልዱና ለገዱ አንዳርጋቸው ካቢኔ ጦስ ለአገሪቱም መዘዝ ያስከተለ ጣጣ እዚህ ደረጃ የደረሰው መቶ በመቶ በመንግሥትዎ ድክመት ነው፡፡

በተመሳሳይ በኦሮሚያና በፊንፊኔ ዙሪያ የጋራ ማስተር ፕላን፣ ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ስለምታገኘው ሕገ መንግሥታዊ ጥቅምና የአርሶ አደሩ ካሳ ጉዳይ መንግሥት ሕዝቡን ያሳመነ ዕርምጃ አለመውሰዱ እምነት ያልጣለባቸውን ካድሬዎች ብቻ ይዞ እየወሰነ፣ ትልልቅ ጉዳዮችንም ሕዝብን ሳያሳምን ይቅርና ሳይገልጽ እንኳ እንዳሻው እያደረገ ‹‹ልማት›› ለማምጣት ይፈልጋል፡፡ በሌላ በኩል ሰፊው የሕዝብ መሬትም ሆነ ለተነሽ ካሳ የሚባለው ገንዘብ በሥልጣን ላይ ባሉና ግብረ አበሮቻቸው እንደሚዘረፍ በግላጭ እየታየ ነው፡፡ ታዲያ ነገሩ እንዴት ቀላል ሊሆን ይችላል?!

ክቡርነትዎ!

በእኔ እምነት ኢሕአዴግን በተለይ ከእነዚህ ሁለት ትልልቅ ሕዝቦች (Majority) ጋር እያቃቃረው የመጣው ሌላኛው ጉዳይ በድርጅትዎ ውስጥ ካላቸው የሥልጣን ውክልና ማዘቅዘቅ አንፃር ነው፡፡ ዛሬ ኢሕአዴግና መንግሥት ይህቺ አገር ከገባችበት ቀውስ ውስጥ የእኩልነትና የውስጠ ዲሞክራሲ ሥርዓትን አጠናክሮ መዘርጋት ይኖርበታል፡፡ ግድም ይለዋል፡፡

በአገሪቱ ያሉ ሁሉም ክልሎች ራሳቸውን በራሳቸው ቢያስተዳድሩም በፌዴራል መንግሥቱ ላይ ብዙኃኑ ያላቸው ሚና እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ አንዳንዶች ይህን የተዛባ አካሄድ ኢሕአዴግ ‹‹ብዙኃኑ በመጠኑ ልክ ሥልጣን ከወሰደ አናሳውን (Minority Group) ይጨቁናል›› የሚል የስታሊን ፍልስፍና ስለሚከተል እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ብሔርና ማንነት የሁሉ ጉዳይ ጫፍ እየሆነ በመጣበት የአሁኒቷ ኢትዮጵያ ግን፣ የሥልጣን ብሔራዊ ምጥጥን መዘንጋት ያውም ብዙኃኑን ማግለል የትም ሊያደርስ የሚችል አይደለም፡፡

ከዚህ አንፃር ቀዳሚው ተጠቃሽ የኢፌዲሪ መከላከያ ሠራዊት፣ የብሔራዊ መረጃ ደኅንነትና የመሳሰሉ ተቋማት ናቸው፡፡ ይኼ በትግል የተገኘ ልምድን ለመጠቀም ሲባል የቆየ መከራከሪያ ዛሬም ድረስ አገራዊ ገጽታ አለመላበሱ ያለጥርጥር ለመተማመን ችግር ነው፡፡ በተመሳሳይ በብዙዎቹ የፌዴራል መሥሪያ ቤቶች (በተለይ ኤጀንሲዎችና ቢሮዎች የብዙኃን ወካይ መሪዎችን ማግኘት ይከብዳል) እዚህ ግባ የሚባል ብቃትና ዕውቀት ሳይኖር የፓርቲ አባል በመሆኑ ብቻ ቁልፍ ቦታዎችን ማስያዝስ የት ያደርሳል?

ሌላ አብነትን ለመጠቆም ለምሳሌ አዲስ አበባ በአዲስ አበቤዎች እንድትመራ ማድረግ አልተቻለም፡፡ እንዲያውም በቀበሌና በወረዳ ደረጃ በአብዛኛው በአንደኛው ድርጅት ካድሬዎች መመራቷ ነው የሚታየው፡፡ ይህ ሁኔታም ሥርዓቱ ምንም ያህል የተጠያቂነት ዘዴ ቢዘረጋ ለሙስና፣ ለመድልኦም ሆነ ለሐሜት መጋለጡ አይቀርም፡፡ በመሠረቱ በተጨባጭም እየታየ ያለው የተደራጀ ሥርዓት አልበኝነት ከዚህ እንዳይመነጭ ያስጠረጥራል፡፡ ስለዚህ አንዱ የትኩረት ነጥብ መሆን ያለበት ይህ የሥልጣን ድልድል ጉዳይ ነው፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር

የትግራይ ሕዝብና ሕወሓት ለአሁኒቷ ኢትዮጵያ መፈጠር (በተለይ ፊውዳላዊና አምባገነን ሥርዓቶችን በማስወገድ) ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ይህን አገራዊ ውለታ በሌሎች ዘንድ ቅቡል ማድረግ የሚቻለውም ሆነ አብሮነታችን ተከባብሮ ለዘመናት የሚዘልቀው ግን፣ በአገሪቱ የሚታይ እኩልነትና ፍትሕ ሲረጋገጥ ነው፡፡

አሁን እየታየ እንዳለው ‹‹የትግራይ ሕዝብ በከፈለው መስዋዕትነት ልክ ሕወሓት የጠቅላይነት ሚና ይኑረው›› የሚል አስተሳሰብ ግን መታረም ያለበት ነው፡፡ ይህን የተዛባ የኢፍትሐዊነት አካሄድም በቀዳሚነት ራሱ ሕወሓትና ኢሕአዴግ ካላረሙት ሌላውም ወገን ታግዬ ካልመጣሁ ሥልጣን አላገኝም ወደሚል ጀብደኝነት እንደሚያማትር የሚያደርግ ነው፡፡ በመሠረቱ የባለታሪኩንና የሃይማኖተኛውን የሰሜኑ ሕዝብን የሚመጥን ተግባርም ሊሆን አይችልም፡፡

ዛሬ ዛሬ በአገሪቱ ሥልጣን የመጨረሻው ደረጃ ላይ ያሉትን እርስዎን እንኳን ‹‹መወሰን አይችሉም!›› የሚሉ ታዛቢዎች እየበዙ ነው፡፡ ይህ የሆነው ደግሞ ቢሆንም ባይሆንም የእኩልነት መልክ ያለው ስብጥር ባለመኖሩ ነው፡፡ ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ስመለስም አማራና ኦሮሚያን በመሰሉ ሰፊ ክልሎች ውስጥ ያሉ ተወካዮችን እኮ ከማንነትም በላይ የአውራጃና የክፍለ አገር አጥር በማበጀት ዕውቅና የማይሰጡም ትንሽ አይደሉም፡፡

ከዚህ አንፃር የአማራ ክልልን እየመራ ያለው ብአዴን (ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ) በቀዳሚነት ይጠቀሳል፡፡ በዚህ ድርጅት ውስጥም ሆነ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ያሉ ዘጠና በመቶና ከዚያ በላይ የሚሆኑት ‹‹የአማራ ተወካዮች›› የወሎና የሰቆጣ አካባቢዎች ተወላጆች ናቸው፡፡ ይህ አኳኋን ቀደም ሲል እንደተጠቀሰው በትጥቅ ትግሉ ወቅት ከነበራቸው ልምድና ከሥርዓቱ አጋርነት አንፃር የመጣ ነው ቢባል እንኳን፣ እንዴት ኢሕአዴግ 25 ዓመታት ሙሉ ከጎጃም፣ ከጎንደርና ከሸዋ አካባቢዎች አመራሮችን መፍጠር አልቻለም ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ እንግዲህ ይህን ሁሉ የዘርና የመንደር አጀንዳ እየመዘዝን ጎራ እንድንሸነሽን ያደረገንን መሠረታዊ ምክንያትም መለየት ያስፈልጋል፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር!

አገራችን ፌዴራላዊ ሥርዓት ማራመዷ እኔን ጨምሮ ብዙዎቹ የአገሪቱ ዜጎች ተቀብለውታል፡፡ ነገር ግን ሥርዓቱ በቋንቋ ላይ ብቻ የተመሠረተ መሆኑ፣ ለማንነትና ለቡድን መብት እጅግ የተለጠጠ ዕውቅና መስጠቱና አገራዊ ማንነትን እየቀበረ ለመሆኑ አልጠራጠርም፡፡ ለዚህም ነው ዛሬ መሪዎቻችንን ከብሔር ማንነትም ወርደን የተወለዱበትን አውራጃና መንደር ወደ መጠየቅ የደረስነው፡፡ እንዲያው ለነገሩ አገራዊ ስሜቱ የጎላ ‹‹ናሽናሊስት›› የሚባል መሪስ አለን እንዴ?!

እንዲያው ድፍረት ካልሆነብኝ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ይህን የጎሳ ፌዴራሊዝም ቀስ በቀስ እያዳከሙ ወደ ጠንካራ ዲሞክራሲያዊ አንድነት እየመጡ እንደነበረ ለማስታወስ እወዳለሁ፡፡ በተለይ ከኢትዮጵያ ሚሊኒየም መባቻ አንስቶ በንግግራቸው የሦስት ሺውን ዓመት ድምር የአገሪቱ ታሪክ ዕውቅና ሰጥተው ነበር፡፡

የባንዲራ ቀን፣ የብሔር ብሔረሰቦች ቀን፣ የአርብቶ አደር ቀን፣ የአርሶ አደር ቀን፣ የመከላከያ ቀን… በሚል አገራዊ በዓላትና ኢትዮጵያዊ መልክ ያላቸውን ሁነቶችም መፍጠር ተጀምሮ ነበር፡፡ ከሁሉ በላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአማራና የኦሮሚያ ክልሎችን ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች እየተገኙ ሕዝቡን በማነጋገር፣ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች ጎልተው በመታየት በውጭ የሚኖሩ ዜጎችን በመጋበዝና በማወያየት ‹‹ናሽናሊስት›› ወደመሆን መጥተው ነበር፡፡ ለዚህም ነው በሰውዬው ሕልፈት ወቅት ዜጎች ከጫፍ ጫፍ በአንድ ዓይነት ስሜት (የሚቃወሟቸው ጭምር) ያዘኑት፡፡

ክቡርነትዎ!

እንዳለመታደል ሆኖ ግን እርስዎና የእርስዎ ካቢኔ ይህንን ጅምር ማስቀጠል አልቻላችሁም፡፡ እንዲያውም አቶ መለስ ቀስ በቀስ እያጠበቡት የመጡትን የብሔር ፖለቲካ በማስፋት ዜጎች በመንደርተኝነት ኔትወርክ እንዲተሳሰሩ ተደርጓል፡፡ ይቅርታ ይደረግልኝና በአሁኒቷ ኢትዮጵያ እኮ አክሲዮንና ማኅበር ብቻ ሳይሆን ዕቁብና የሰንበቴ ትስስር በተወላጅነት ሆኗል፡፡ ለሙስናው መባባስም ሆነ ለዴሞክራሲው አለመጎልበት ጠባብነቱ የፈጠረው ደንቃራም ቀላል የሚባል አልሆነም፡፡

አሁን በአገሪቱ እየታየ ላለው ትርምስም ቀደም ሲል በኅብረ ብሔራዊነትና በጠቅላይ አስተሳሰብ (ትምክህተኝነት) ሲታማ የነበረው ትግል ላይ ነኝ የሚለው ኃይል ሁሉ ጠባብነትና ዘረኝነትን ማራመዱ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ‹‹ውሻ በቀደደው…›› እንዲሉ ጽንፈኛው ተቃዋሚ የአገሪቱን መዳከም በሚሹ ኃይሎች ጭምር እየታገዘ በዘረኝነት ላይ ተመሥርቶ በማኅበራዊ ድረ ገጽ ያራመደው የጥላቻ ዘመቻ አገር የሚበትን ነው፡፡ ወትሮም ሕዝቡ ወደ አንድነት የሚያመጣው የተጠናከረ ሥራ ባለመሠራቱም ፍጥጫው ይበልጥ ጎልቶ እንዲታይ አድርጓል፡፡

አሁን ባለችው ዓለም ከየትኛውም ጫፍ ይምጣ የሰው ልጅ ሕጋዊ ይሁን እንጂ የትም አገር ሠርቶ መኖር ይችላል፡፡ ለዚህ አባባል ጥሩ ምሳሌ የምትሆነው አሜሪካ ነች፡፡ በእኛ አገር ግን አሁን አሁን እየታየ እንዳለው አማራው በኦሮሚያ ወይም በደቡብ፣ የትግራይ ተወላጅም በኦሮሚያ ወይም በአማራ ክልል በነፃነት ሠርቶ መኖር የሚችልበት ልበ ሙሉነት ጠፍቷል፡፡ ያለሥጋት ለመንቀሳቀስም ዋስትና ያለው አይመስልም፡፡ ታዲያ ይህ ‹‹አንድ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ የተፈጠረበት አገር›› ለማለት ይቻላልን?! በእኔ እምነት ይህ ክስተት ከድህነትም በላይ የከፋ ውርደትና ውድቀት ነው፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር!

እንግዲህ ሐሳቤን ባጠቃልለው ሳይሻል አይቀርም፡፡ ይህቺ አገር ያለጥርጥር የልማትና ዕድገት ለውጥ እያመጣች ነው፡፡ ነገር ግን ውስብስብ ችግሮች የተበተቧትና የሕዝቡን ግንዛቤና ብልህነት ያላገናዘበ ፖለቲካዊ ሥሪት የቀፈደዳት መሆኗን ማጤን ይገባል፡፡ ለሌላው ዓለም ለይስሙላ ‹‹ዴሞክራት›› ወይም ‹‹ትልቅ መንግሥት›› ነን ማለቱ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ ይህን ሰፊና ውስብስብ አገር እንደሚመራ መንግሥት ከሕዝቡ ጋርም መተማመን የሚያስፈልግበት ወሳኝ ወቅት ላይ እንዳላችሁ ልትመዝኑ ይገባል፡፡ ከዚህ አንፃር እነዚህን ምክረ ሐሳቦች ለመጠቆም እወዳለሁ፡፡

መንግሥትም ይበልጥ ሕዝባዊ ሆኖ አገሪቱን ለአጭርም ሆነ ረጅም ጊዜ ለመምራት ሙስናን በርትታችሁ ታገሉ፡፡ በተለይ በሕገወጥ ኔትወርክና በብሔር መሳሳብ እየበለፀጉ ያሉ ካድሬዎችዎን አደብ አስገዙ፡፡ ለዚህ ደግሞ ካቢኔዎንም ሆነ በደረጃው ያለውን መዋቅር አሁን እንዳላችሁት ብዙዎችን የሚያሳትፍ ማድረግ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ ይልቁንም በስም ብቻ ተቋቁመው፣ በጀት ተመድቦላቸው ሙት የሆኑ ሕገ መንግሥታዊ ተቋማት (ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ እንባ ጠባቂ ኮሚሽን፣ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽንን…) ከእስር ቤት ነፃ አውጥቶ ሕይወት እንዲኖራቸው ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡

ኢሕአዴግ ‹‹ልማት አምጥቻለሁ›› በሚል አጉል ጀብደኝነት ዲሞክራሲያዊ ምኅዳሩን ማዳከም ብቻ ሳይሆን ገድሎታል፡፡ በአገሪቱ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ተገዳዳሪ የለም፡፡ ነፃ ፕሬስ ብልጭ ብሎ እየጠፋ ነው፡፡ በነፃነት መሰብሰብና ሠልፍ ማድረግ ‹‹ወንጀል›› ሆኗል፡፡ የመንግሥትም (የሕዝብ) ሚዲያዎችና የኢሕአዴግ የፓርቲው ልሳኖች (አዲስ ራዕይ፣ ህዳሴ፣ አብዮታዊ ዴሞክራሲ) የሚለያያቸውን አጥር አፈራርሰዋል፡፡ የመንግሥትና የገዥው ፓርቲ ሥራ ተደበላልቆ ቅጥ አምባሩ ጠፍቷል፡፡

እነዚህ ፀረ ዴሞክራሲያዊ አሠራሮች ቀስ በቀስ ሥር እየሰደዱ ባህል የሆኑት በተለይ እርስዎ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ነው፡፡ እንግዲህ ይህን አለመቀየር ውድቀትን ከማፋጠን ውጪ ምንም ትርፍ አይኖረውም፡፡ በር የተዘጋበት ሕዝብ እንኳን በድህነት ውስጥ ሆኖ ፍላጎቱ ቢሟላም ደረማምሶ እንደሚወጣ ሊቢያና ሶሪያን ብቻ ማየት ብቻ በቂ አይደለም፡፡ እኛም አገር የሚያቆመው እንደሌለ አይተናል፡፡

የፌዴራል ሥርዓቱ በአገሪቱ በተለይ በአናሳ ብሔረሰቦች ላይ የፈጠረው መነሳሳትና የእኩልነት ተሳትፎ ቀላል አይደለም፡፡ ይሁንና ግን የቀደመውን የአንድ ወገን የበላይነት አስወግዶ አሁንም የሌላ ወገን የበላይነት እንዳይነግሥ መደረግ አለበት፡፡ ይህቺ አገር የሁሉም ዜጎች የጋራ ቤት ልትሆን የምትችለው በመተማመን ላይ የተመሠረተ አንድነት መገንባት ሲቻል ነው፡፡ በመሠረቱ ኢሕአዴግ በአገር አንድነትና በሕዝቦች አብሮነት ላይ የሠራው ሥራ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም፡፡ ዛሬ በማንነት ስም፣ በመንደርና በወንዝ ልጅነት መፈላለግ የሚብላላው መብዛት አንድነት የሌለው ሕዝብ ምልክት ነው፡፡ በዚህ ላይ የጥላቻ ንግግርና ዘረኝነት ሲጨመርበት ያለጥርጥር የሚጋብዘው ጥፋት ነው፡፡

ክቡርነትዎ ይህን እውነት ክዶ ዓይንን ከመጨፈን፣ ፊት ለፊት ተጋፍጦ ብሔራዊ መግባባትም በሉት ብሔራዊ እርቅን ማሰብ ግድ ይላል፡፡ በመሠረቱ እኮ የትም ይኑሩ የት የዚህች አገር ዜጎች ሁሉ ኢትዮጵያ የጋራ ቤታቸው ነች፡፡ ታዲያ ስለምን አንዱ የሌላውን መጥፋት እየተመኘ ሊኖር ይችላል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደታየው በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በሚነሱ ሁከቶች ከፍተኛ መጠን ያለው ሀብት እየወደመ ነው፡፡ ሰሞኑን በአማራ ክልል በስምንት የአበባ እርሻዎች ላይ 600 ሚሊዮን ብር የሚገመት ሀብት መውደሙን መገንዘብ ተችሏል፡፡ በኦሮሚያም ተመሳሳይ ነው፡፡ ይኼ ለምን ሆነ ብሎ መጠየቅ የእናንተ ድርሻ ነው፡፡

በእኔ እምነት ግን በአንድ በኩል ሕዝቡ ያላመነበትና ያልተቀበለው ልማት ይመስለኛል፡፡ በሌላ በኩል ለአርሶ አደሩ ለመሬት ይዞታው የተከፈለው ካሳ ዝቀተኛ ነው ወይም ተመዝብሯል፡፡ ምናልባት እንደ ሦስተኛ ምክንያት የሚነሳው ይኼው ለዓመታት የተሠራበት ጠባብነት የፈጠረው ባለሀብቱን የሩቅ ሰው ከማድረግ ይመነጫል፡፡ (ይህ እንግዲህ ዓለም አንድ መንደር በሆነበት የሉላዊነት ዘመን ሊሰሙት የሚቀፍ ውርደት ነው፡፡ ግን ምን ይደረግ እውነቱ እሱ ሆኗል)

የሕዝቡ ቁጣ የተገለጸበት ሌላው መንገድ ከማረሚያ ቤት እስከ ፍርድ ቤቶችና አስተዳደር ጽሕፈት ቤቶች ያሉ የሕዝብ መገልገያ ተቋማትን ማውደሙ ነው፡፡ እነዚህን የቢሮክራሲው መሣሪያዎች ‹‹የእኔ አይደሉም!›› ብሎ ያወደመበትን ሚስጥር ከሕዝብ ጋር በግልጽ መወያየት መለየት ያስፈልጋል፡፡ ሥርዓቱ መቶ በመቶ ምርጫ አሸነፍኩ እያለ ራሱን ሲደልል ከዳር እስከ ዳር ሕዝብ እየተነሳ እሳት የሚለቅበት ተቃርኖን ፊት ለፊት ተጋፍጦ አለመፍታት ዕረፍት የሚሰጥ ሁኔታን አይፈጥርም፡፡

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ያሉበት ሁኔታ የሚያስጨንቅና ከባድ ጊዜ መሆኑን እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን የዚህች አገር ሁኔታ ሁሉ በእርስዎና በባልደረቦችዎ ትከሻ ላይ መውደቁን አውቃችሁ ልትነሱ ይገባል፡፡ ከውሸት ሪፖርትና ከአስመሳዮች ንግግር ወጥቶ ሀቀኛና አብዮተኛ ትውልድን በድርጅትዎ ውስጥ መፍጠርና አገር ሳይፈርስ ለሌሎቹ ዕድል መስጠትም ብልህነት ነው፡፡ ፈጣሪ ይርዳዎት፡፡ ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር ብዬ ልሰናበት፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው lhabt@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

የሕዝብን አደራ መብላት ካልቆመ አገርን እንደ ማዕበል ጠራርጎ ይወስዳል

$
0
0

በዳዊት ወልደየሱስ

በየታክሲው፣ በየካፌው፣ በየስብሰባዎችና በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴያችን ቃሉን እንሰማለን፡፡ ሚዲያዎችም በየዕለቱ ከሚዘግቧቸው ዜናዎችም ሆነ መጣጥፎች ዙሪያም አይጠፋም፡፡ ገዥው ፓርቲም የሥርዓቴ አደጋ ነው ብሎ ፈርጆታል - ኪራይ ሰብሳቢነትን፡፡

ኪራይ ሰብሳቢነት በተደጋጋሚ እንደምንሰማውና እንደምናነበው ሕግን ተከትሎ ከመሥራት ይልቅ ሥልጣንና ኃላፊነትን መከታ በማድረግ ሕግና ሥርዓትን በመጣስ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብትን መስረቅ፣ መዝረፍ፣ ማጭበርበርና እንዲሁም በጉቦ፣ በዝምድና፣ በትውውቅ፣ በጎሰኝነት፣ በፖለቲካ ወገንተኝነትና በሃይማኖት ትስስር ላይ በመመርኮዝ አድሎአዊ በሆነ አሠራር ፍትሕን እያዛቡ የግል ጥቅምን ማካበትና ሌላን ወገን ተገቢ ባልሆነ መንገድ መጥቀም መጉዳት ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአገር ዕድገት ላይ ከሚያደርሰው ተፅዕኖ ባሻገር ለእርስ በርስ ግጭትና መተላለቅ ምክንያት ይሆናል፡፡

አንዱ ሕግና ሥርዓትን ሲከተል፤ ሌላው ደግሞ ሕግና ሥርዓትን አስከብራለሁ ብሎ በሕዝብ ወንበር ላይ ተቀምጦ አገርንና የሕዝብን ሀብት ሲዘርፍ ይስተዋላል፡፡ አንዱ የሕዝብን አደራ ሲጠብቅ ሌላው ደግሞ አደራ ይበላል፡፡ አንዱ ለአገር ዕድገት ሲቆረቆር ሌላው በግዴለሽነትና በራስ ወዳድነት አገሩን ሊቀብር ተዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ ለምን በሕዝብ መካከል ግጭት አይቀሰቀስ? ለምን በአንድ ሕዝብ መካከል መከፋፈል አይፈጠር? ለምንስ ሰው በአገሩ ባይተዋርነት አይሰማው?

በተለይ አገሪቱ ከፍተኛ ሀብት እየፈጠረች በሄደች ቁጥር ኪራይ ሰብሳቢነት ሥልቱን እየለዋወጠ፣ መልኩን እየቀያየረና አቅሙን እያሳደገ ፈተና የመሆኑ እውነታም በተጨባጭ እየታየ ነው፡፡ የዘራፊው ፍላጎትም አቅምም አብሮ እያደገ መጥቷል፡፡ እየተዘረፈ ያለው የሕዝብና የአገር ሀብትም በዛው መጠን እየጨመረ ሄዷል፡፡ መከላከል ካልተቻለ ደግሞ ማዕበሉ አገርን ጠራርጎ ይወስዳታል፡፡ ስለሆነም ከቃላት ያለፈ ትርጉም ያለው ሥራ ይጠበቃል፡፡

በመድረክ ስለኪራይ ሰብሳቢነት በቁጣ ይናገር የነበረ ኃላፊ ከመድረክ ጀርባ ግን በኪራይ ሰብሳቢነት ሐይቅ ውስጥ የሚዘፈቅ ከሆነ፣ በመድረክ እንደሳቸው ያለ መሪ አይገኝም እያለ ይሰብክ የነበረ ፈጻሚም መሪውን ተከትሎ የሚጠፋ ከሆነ፣ አንዳንዱ ደግሞ እኔስ ድርሻዬን ለምን አልወስድም? በማለት በእኩይ ተግባር ተባባሪነቱ ከቀጠለ፣ አገሪቱ የጋራ ሆና እያለ ስግብግቦች ግን ተቀራምተው ይጨርሷታል፡፡ የወላድ መካንም ትሆናለች፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትን ታግሎ ማሸነፍም ከባድ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ይናገሩ የነበሩ አንደበቶችም ይዘጋሉና! ይሟገቱ የነበሩ ሰዎችም ሽባ ይሆናሉና! በተግባር የሚገለጥ ታማኝነት ከሌለ ደግሞ ደመወዙ ይኼው ይሆናል፡፡

አሁን አሁን “እከከኝ ልከክልህ” ዓይነት ተግባር እየተንፀባረቀ በመሆኑ የኪራይ ሰብሳቢውን ኮቴውንም ሆነ ጥላውን ለማወቅ አስቸጋሪ እስከሚሆን ድረስ ዕድገትን እየተፈታተነ ይገኛል፡፡ ዝርፊያውም በተደራጀ መንገድ የሚከናወን በመሆኑ ምንጩን ለማወቅና ማንነትን ለመለየት አስቸጋሪ እየሆነ እንደመጣ በዘርፉ የተደረጉ ጥናቶች ያረጋግጣሉ፡፡ ቀደም ሲል ይታገሉ የነበሩ ወገኖችም በጥቅማ ጥቅም አፋቸው ተይዞ እንዳይናገሩ ተከልክሏል፡፡ ችግሩ ተደረሰበት ተብሎ የሚጋለጠውም በትናንሾች እንጂ ትላልቅ ዝሆኖችን አይነካም፡፡

አሁን ችግሩ እየገነነ መጥቷል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነት ይጎላባቸዋል ተብለው ከተለዩ ዘርፎች በላቀም መልኩ የአደጋው መናገሻ ቦታውም በዝቷል፡፡ በዚህ ጊዜ ነው አገር እንደ አገር የማትቀጥለው፡፡ ወደ መፍረስ አዝማሚያም የምታመራው፡፡ ስለዚህ ይህንን አዝማሚያ በአስቸኳይ ማቆም ግድ ይላል፡፡ የቀጣይ ህልውና ጉዳይ ነውና፡፡ ለዚህ ደግሞ የሁሉንም ታማኝነትና ቁርጠኛ ትግል ይፈልጋል፡፡ ምንም እንኳ እልህ አስጨራሽ ቢመስልም፡፡

መንግሥትም ይህን አደጋ ለማጥመድ መረብ ዘርግቷል፡፡ ከፍተኛ የሆነ ዘመቻም ከፍቷል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢው ኃይል ደግሞ በከፍተኛ ደረጃ ሀብት ያካበተ እንደመሆኑ፣ በገንዘቡ በመደለል እየመጣበት ያለውን ዘመቻ ለማምከን ከሚሠራው በላይ ጤናማው ዜጋ በንቅናቄው መስመር እንዳይገባም በጥቅማ ጥቅም በመደለል የራሱን ስትራቴጂ ቀይሷል፡፡ ስለሆነም ምንም እንኳ የተለያዩ የአሠራር ሥርዓቶች ቢዘረጉም፣ ኪራይ ሰብሳቢው አካል መረቡን ለመበጣጠስ ጉልበት የሚያንሰው አይሆንም፡፡ እየተደረገበት ካለው እያደረገው ያለው ይበልጣልና፡፡

ምክንያቱም ኪራይ ሰብሳቢው ኃይል አድማሱን ከውስጥ እስከ ውጭ በመዘርጋት የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ዘመቻውንና ትግሉን የማደናቀፍ፣ ኃይሉን የማዳከምና ተስፋን የማስቆረጥ ተግባራትን በዚህም በዚያም በመፈጸም የተካነ መሆኑን በየጊዜው በተለያዩ ሥፍራዎችና የመነሻ ጉዳዮች እየተከናወኑ ያሉ ግጭቶችም ሆነ፣ በአገርና በሕዝብ ሀብት የሚደረጉ ዘረፋዎች ማሳያዎች ናቸው፡፡ ስለሆነም አገር ከመበታተኗ በፊት አሁን እየተደረገ ካለው በላይ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል፡፡

በዚህ ረገድ የመጀመርያውና ቀዳሚው ተግባር መንግሥትና ሕዝብ ተባብረው የኪራይ ሰብሳቢውን ኃይል ራስን የመከላከል ሥልቶችና ማምታቻ መንገዶች አውቀው እነሱን መገደብ ነው። በተደራጀ መልኩ የመጣን ጠላት እንደ አመጣጡ ለመመከትና ለማስተካከል ሕዝብና መንግሥት ተደራጅቶ መንቀሳቀስ ይገባቸዋል፡፡ ሕዝብን ያላሳተፈ ማንኛውም ተግባር ውጤታማ ሊሆን እንደማይችል ይታመናል፡፡ ቀጥሎም በተመሳሳይ ትብብር ይህን ኃይል የማጋለጥ በተከታታይና በማያባራ ዘመቻም ይህንን የግንኙነት መረብ መበጣጠስ ነው፡፡ ከሕዝብ የሚደበቅ ነገር የለምና፡፡ በግለሰብ ደረጃ በኪራይ ሰብሳቢነት ተግባር የታመመውን ደግሞ ያለምንም አድልኦ፣ አድርባይነት፣ ዝምድናና ትውውቅ ትርጉም ያለውና አስተማሪ የሆነ ፍትሕ ባልተዛባበት መልኩ ቅጣቱን ማግኘት ይኖርበታል፡፡

ስለሆነም በየሥርቻው ያላግባብ በዘመድ አዝማድ ስም ሀብት ያካበተውን፣ በመጠቃቀምና በጎሰኝነት ካባ ተከናንቦ የአገርንና የሕዝብን ሀብት የዘረፈውን ከየጎሬው እያወጣ ማጋለጥ ከሕዝቡ የሚጠበቅ ኃላፊነትና ግዴታ ይመስለኛል፡፡ ይህንን የንቅናቄ ፍኖት መንግሥት ያላንዳች መዘንጋትና መዘናጋት በአግባቡ መምራት ይኖርበታል፡፡ መሪው ድርጅትም ከሕዝብ በሚያገኘው መረጃና በራሱም የተለያዩ መንግሥታዊ መዋቅሮች በሚያገኛቸው መረጃዎች ላይ ተመሥርቶ ውስጠ ድርጅት ትግሉን የበለጠ አፋፍሞ ለሕዝብ ጥያቄ ተግባራዊ ምላሽ የሚሰጥ ዕርምጃ ውስጥ መግባት ይጠበቅበታል፡፡ ንቅናቄው በዚህ መልኩ ከተመራ ማንም አያቆመውም፡፡ ራሱን እያጠናከረ መሄድ ይችላል፡፡ በሒደትም በኪራይ ሰብሳቢነት ላይ ወሳኝ ድል መጎናፀፍ ይቻላል፡፡

እስኪ ሁላችንም አሮጌውን የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ተግባርን ልብስ አውልቀን በአዲሱ ዘመን በአዲስ መንፈስና አስተሳሰብ የልማታዊ፣ የአገራዊ፣ የመተሳሰብና የዕድገትን ልብስ እንልበስ፡፡ የስግብግብነትን አመለካከትን አርቀን የጋራ ዕድገትን እናስብ፡፡ የዘረፋን ልቦና አስወግደን የመተሳሰብን ልብ እንትከል፡፡ በአጠቃላይ መላው አመለካከታችንን ለአገር፣ ለሕዝብ፣ ለመተሳሰብና ለዕድገት እንለውጥ፡፡ ዘረፋ፣ ሌብነት፣ ስግብግብነትና ሆዳምነት ይብቃ፤ በመልካም አመለካከትና ተግባር አገራችንን እንገንባ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ማዕበሉ አገሪቱን ጣራርጎ ይወስዳታል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dawit.keha@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

 

 

Standard (Image)

ለውጥ መምራት ወይም በለውጥ መገፋትና መገለል?

$
0
0

ወቅቱ ለኢሕአዴግ ያቀረበለት ምርጫ ነው

በሞላ ዘገዬ

ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚጠይቅ አገራዊ ፈተና ገጥሞናል። በአገራችን በበርካታ አካባቢዎች የብዙ ኢትዮጵያውያንን ሕይወት የቀጠፉ ግጭቶች ተከስተዋል፡፡ በሚያሳዝን ሁኔታ ግጭቶች ከመፈታት ይልቅ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተወሳሰቡና የአገራችን የፖለቲካ ሁኔታ ወደከፋ ደረጃ እየወሰዱት ነው፡፡ አገራችን የገባችበት እጅግ አስቸጋሪ ሁኔታ እከሌ ከከሌ ሳይባል ሁላችንም ሊያሳስበን ይገባል፡፡ ይህንን አሳሳቢ ሁኔታ ስለተረዱ ይመስላል፣ የቀድሞ የሕወሓት ባለሥልጣናት ሳይቀሩ በመገናኛ ብዙኃን በመቅረብ የችግሮቹን መንስዔዎች ማንሳትና የመፍትሔ ሐሳብ የሚሉትን መጠቆም ጀምረዋል። እኔም በዛሬው ጽሑፌ ሌተና ጄኔራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ ሪፖርተር ጋዜጣ (ሐምሌ 17 እና 24 ቀን 2008 ዓ.ም.) ላይ በሁለት ክፍል ባቀረቡት ጽሑፍ ላይ ተንተርሼ፣ ለገጠሙን አገራዊ ፈተናዎች መንስዔ ናቸው የምላቸውን ጉዳዮች እገልጽና እነዚህን አንገብጋቢ ችግሮች ለመፍታት ያስችላሉ የምላቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች ለመጠቆም እሞክራለሁ።

ሌተና ጄኔራል ፃድቃን በአገራችን ያለው የፖለቲካ ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ መሆኑን ገልጸው፣ ይህ አስቸጋሪ ሁኔታ የከፋ ጉዳት ከማድረሱ በፊት “በሠለጠነ መንገድ ተወያይተን እንፍታው” ሲሉ በሥልጣን ላይ ለሚገኙት ወገኖች፣ ለተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና የአገራቸው ሁኔታ ለሚያሳስባቸው ኢትዮጵያውያን ሁሉ ጥሪ አቅርበዋል።

በእኔ አስተያየት ሌተና ጄኔራል ፃድቃን ገብረ ትንሳዔ አገራችን የገባችበት እጅግ አስቸጋሪ ሁኔታ አሳስቧቸው በሥልጣን ላይ ያሉት አካላት፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ሌሎች አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን በሰከነ መንገድ እንዲወያዩና መላ እንዲመቱ ጥሪ ማቅረባቸው የሚያስመሰግናቸው ነው። እኔም የአገራቸው ሁኔታ ከሚያሳስባቸው ወገኖች አንዱ ነኝ ብዬ ስለማምን፣ የጀኔራሉን ጥሪ ተቀብዬ ይህን ጽሑፍ አቅርቤያለሁ፡፡  

ጽሑፉ ሁለት ክፍሎች ይኖሩታል። በመጀመርያው ክፍል ጄኔራል ፃድቃን ያለንበትን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁኔታ በተመለከተ ያቀረቧቸውን ትንታኔዎች ተቀብለን፣ “አሁን ወዳለንበት ሁኔታ እንዴት ገባን?” በሚል ንዑስ ርዕስ ሥር ባቀረቧቸው ነጥቦች ላይ ስለማልስማማ፣ የራሴን ምልከታ እገልጻለሁ። በሁለተኛው ክፍል ፃድቃን ያስቀመጧቸውን ቢሆኖች (Scenarios) ተቀብዬ፣ ነገር ግን የመፍትሔ ሐሳቦች ብለው ባቀረቧቸው አስተያየቶች ላይ የሚጎድል ነገር ያለ ስለሚመስለኝ፣ በሁለት ንዑስ ርዕሶች ከፍዬ መጨመር አለባቸው የምላቸውን ነጥቦች እሰነዝራለሁ።

የችግሩ ምንጭ ምንድነው? 

እኔም እንደ ጄኔራል ፃድቃን አገራችን ያለችበት የፖለቲካ ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ነው እላለሁ። በአገራችን የተለያዩ አካባቢዎች የሚቀሰቀሱትና የበርካታ ኢትዮጵያውያንን ሕይወት የሚቀጥፉት ሕዝባዊ ተቃውሞዎች ምላሽ ያስፈልጋቸዋል። በበኩሌ ለሕዝብ ጥያቄዎች አፋጣኝ የሆነና የጉዳዩን ባለቤት (ሕዝቡን) ያሳተፈ ምላሻ ካልተሰጠ በስተቀር አገራችን ወደከፋ ሁኔታ ልትገባ ትችላለች የሚል ከፍተኛ ሥጋት አለኝ። ብሔረሰባዊና ሃይማኖታዊ መልክ ያላቸው የሕዝብ ልዩነቶች፣ የሕዝብ ቁጥር መጨመርና በደሃውና በሀብታሙ መካከል ያለው የሀብት ክፍፍል መራራቅ፣ በወጣቱ አካባቢ የሚታየው ከፍተኛ የሆነ ሥራ አጥነትና ተስፋ ማጣት፣ በአገራችን የሰፈነው መረን የለቀቀ ሙስናና ሕዝብ ያማረረ የመልካም አስተዳደር ችግር እርስ በርሳቸው እየተመጋገቡ፣ ችግሮች መፈታት ከማይችሉበት ደረጃ ላይ እንዳይደርሱ እሰጋለሁ። በመንግሥት በኩል መሠረታዊ የሆነውን ችግር ወደ መልካም አስተዳደር ችግር ለማውረድ የሚደረገው የተለመደው አካሄድ ጨርሶ መፍትሔ እንደማይሆን እረዳለሁ፡፡ ሕዝብንና አገርን ውድ ዋጋ ያስከፍላል ብዬም አምናለሁ። በሚያሳዝን ሁኔታ ሕዝቡ የሚጠይቀው ሌላ፣ በመንግሥት ሥልጣን ላይ ያሉት ኃይሎች የሚሰጡት ምላሽ ሌላ እየሆነ፣ በሕዝቡና በመንግሥት መካከል ትልቅ ገደል እየተፈጠረ ነው፡፡ በሥልጣን ላይ ያሉት አካላት በኩል አሁንም እንደተለመደው የሚበጅህን የምናውቅልህ እኛ ነን የሚል አደገኛ አካሄድ እየተራመደ ነው፡፡ ሕዝቡ የሚበጀውን እንደማያውቅ፣ ሁልጊዜም ሞግዚት እንደሚያስፈልገውና እኛ የምንልህን ብቻ ተቀበል እየተባለ ነው፡፡ ይህ ነው የበሽታው ሁሉ ምንጭ፡፡

በእኔ አስተያየት የችግሮች ሁሉ ምንጭ ከፖለቲካ ባሕላችን ጋር የተያያዘ ነው። ጄኔራል ፃድቃን ኢሕአዴግ የመንግሥት ሥልጣን እስኪይዝ ድረስ ዴሞክራሲያዊ እንደነበር ጠቅሰው ሲያበቁ፣ የመንግሥት ሥልጣን ከያዘ በኋላ የድርጅቱን ዴሞክራሲያዊነት የሚፈታተኑ ሦስት ትልልቅ ክንዋኔዎች መፈጸማቸውን ይነግሩናል። ፃድቃን እንደሚሉት “ኢሕአዴግ አንደኛ ከኦነግ ጋር የነበረውን ልዩነት የፈታበትን መንገድ፣ ሁለተኛ በሕወሓት ውስጥ የተፈጠረው የውስጠ ፓርቲ ቀውስ የተፈታበት ሒደትና ሦስተኛ የ1997ቱን ምርጫ ተከትሎ የተፈጠረው ቀውስ የተፈታበት መንገድ የኢሕአዴግን ፀረ ዴሞክራሲያዊነት ያጎሉ ብቻ ሳይሆኑ፣ ፀረ ዴሞክራሲያዊነት ተቋማዊ እንዲሆን ያደረጉ ክንዋኔዎች ናቸው፤” እኔ በዚህ አልስማማም። በእኔ አስተያየት ችግሩ የሚያያዘው ከድርጅቱ ተፈጥሮ ጋር ነው። ላብራራው።

ችግሩ የሚጀምረው ከሕወሓት መንታ ማንነት ነው ብዬ አስባለሁ። ሕወሓት ሲመሠረት በአንድ በኩል ማርክሲስታዊ ሌኒኒስታዊ፣ በሌላ በኩል የትግራይ ብሔርተኛ ሆኖ ነው የጀመረው፡፡ እነዚህ ድምር ማንነቶች ዴሞክራሲያዊ ቁመና እንዲኖረው አይፈቅዱለትም።

ሕወሓት እንደ ሌሎች በኢትዮጵያ አብዮት ዘመን እንደተመሠረቱ ድርጅቶች፣ ሌኒኒስትና ስታሊኒስት በሆኑ አስተምህሮዎች የተገነባ በመሆኑ ቅራኔዎችንና የቅራኔዎችን አፈታት በዚሁ ርዕዮተ ዓለም መነጽር የሚያይና የሚፈታ ድርጅት ነው። በዚህ አስተምህሮ መሠረት አንድ ሁሉን አውቃለሁ የሚል፣ ወይም ለሁሉም ችግሮች መፍትሔው እኔ ነኝ የሚል ድርጅት እንዳለ ስለሚታመን፣ ከዚያ ውጪ ያለው ኃይል ሁሉ ወይ የዚህ ድርጅት ደጋፊ ይሆናል፣ ካልሆነ ደግሞ ጠላት ነውና መደምሰስ አለበት ይባላል። ልዩነት አይከበርም። ልዩነትን ለዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት መገበር ያስፈልጋል። በፓርቲ አባላት መካከል ውይይትና ክርክር ይደረጋል ቢባልም፣ በአብዛኛው ውይይቶችና ክርክሮች የሚደረጉት ጥቂት የፖሊት ቢሮ አባላት ወይም የፓርቲው ዋና ጸሐፊ ባሳለፈው ውሳኔ ላይ ሲሆን፣ የተወያዮች ሚና የውሳኔ ሐሳቡን ወይም ሰነዱን ማፅደቅ ወይም ማዳበር ብቻ ነው። ከሌሎች ድርጅቶች ጋር የሚደረጉ ድርድሮችም ቢሆኑ የችግር መፍቻና የዘላቂ ሰላም መፍጠሪያ መንገዶች ሳይሆኑ፣ ማዘናጊያና ጊዜ መግዣ ናቸው። እነዚህ ድርጀቶች መቶ በመቶ ማሸነፍን እንጂ፣ የዴሞክራሲ እሴቶች የሆኑትን ከልብ መወያየትን፣ መደራደርንና ሰጥቶ መቀበልን አይቀበሉም። ለምሳሌ ያህል ሕወሓት በረኻ በነበረበት ወቅት ዴሞክራሲያዊ ነበረ ቢባልም፣ በትግራይ ሕዝብ ስም ከተደራጁ ድርጅቶችና በአካባቢው ይንቀሳቀሱ ከነበሩ ኅብረ ብሔራዊ ንቅናቄዎች ጋር የነበረውን ቅራኔ የፈታበት መንገድም ሆነ፣ የመንግሥት ሥልጣን ከያዘ በኋላ ከኦነግና ከቅንጅት ጋር የነበረውን ቅራኔ እንዲሁም በራሱ በድርጅቱ ውስጥ የተፈጠረውን ክፍፍል የፈታበት መንገድ ሁሉ ይህንን መቶ በመቶ አሸናፊ የመሆን ባሕርይ የሚያሳዩ ናቸው እንጂ፣ ዴሞክራሲያዊ ባሕሪውን የሚገልጹ አልነበሩም፣ አይደሉም፡፡

በመሠረቱ ሁሉም በበ1960ዎቹ ዘመን የተፈጠሩ ስታሊኒስትና ማኦይስት ድርጅቶች አንድ ብቸኛና ያለቀለት መፍትሔ እንዳላቸው አድርጎ የማቅረብ በሽታ ነበረባቸው፣ አለባቸው። እነሱ ከሚያቀርቡት የመፍትሔ ሐሳብ ውጪ የተለየ አስተያየትና የተለየ አቀራረብ ሊኖር አይችልም የሚለው፣ ወይም ደግሞ ከዚህ ውጪ አማራጭ የለም የሚለው አመለካከት ምርጫ የሚያሳጣ ብቻ ሳይሆን፣ በከፍተኛ ደረጃ የአዕምሮ ነፃነትን የሚጋፋ አካሄድ መሆኑ ግልጽ ይመስለኛል። በማንኛውም ዘዴ ቢሆን ትልቅ ጫና የሚፈጥረውና ነፃነት ገፋፊ የሚሆነው አማራጮችን ዘግቶ ልክ አንድ ብቸኛ መፍትሔ እንዳለ አድርጎ የማቅረብ አካሄድ ነው ለማለት ይቻላል። ‹ወይ እኔን ትደግፍና የጥቅም ተካፋይ ትሆናለህ፣ ካልሆነ ግን በኅልውናዬ ላይ መጥተሃልና ትደመሰሳለህ› በሚል ፀረ አማራጭና ፀረ ነፃነት አስተሳሰብ መመራት ትልቅ መከራ ነው።

በሁለተኝነትና በሦስተኝነት፣ የድርጅቱ ኢዴሞክራሲያዊነት የሚገለጸው ሕወሓትዎች (ኢሕአዴግአውያን) በ1983 ዓ.ም. የመንግሥትን ሥልጣን ሲቆጣጠሩ ያዋቀሩት የሽግግር መንግሥት ሁሉንም ወገን ያላሳተፈ መሆኑ፣ ከዚያም በኋላ ሕገ መንግሥቱ ሲረቀቅም አሁን የሚነገርለትን ያህል ሕዝቡን ያላሳተፈ መሆኑ ነው። ለዚህ ነው ጄኔራል ፃድቃን የዘረዘሯቸው ችግሮች የድርጅቱ ኢዴሞክራሲያዊነት ውጤቶች እንጂ መንስዔ ናቸው ብዬ የማልቀበላቸው፡፡

ፖለቲካችን ከተለመደው የሴራ ፖለቲካ ሊፈወስ ይገባል

ከፍ ብዬ እንደገለጽኩት ጄኔራል ፃድቃን  የኢሕአዴግን ዴሞክራሲያዊነት የተፈታተኑ ያሏቸው ክንዋኔዎች በሙሉ ከድርጅቱ ተፈጥሮ አንፃር የሚጠበቁ እንጂ ጨርሶ እንግዳ ነገሮች አይደሉም። አሁን የሚታየው ችግርም የዚህ አስተሳስበ ውጤት ነው፡፡ ይህ አስተሳሰብ ከዴሞክራሲ ጋር የተጣላ መሆኑን ተቀብሎ በዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብና አሠራር እስካልተቀየረ ድረስ፣ ለይስሙላ ስለመድበለ ሐሳብ (Pluralism) እና መድበለ ፓርቲ ሥርዓት መስበኩ ችግር እንጂ በጎ ውጤት አያስገኝም። እስከዛሬም አላስገኘም፡፡ ውሳኔ ከወሰኑ በኋላ ሕዝብን ማወያየት፣ የተለየ ሐሳብ ያላቸውን ወገኖች (አሁን እንደሚታየው) በፀረ ልማት፣ በፀረ ሰላምነትና በውጭ ኃይሎች ጉዳይ አስፈጻሚነት መፈረጅም ቢሆን በችግር ላይ ችግር ይፈጥራል እንጂ፣ የሚጠቅም አካሄድ አይደለም።

ከገባንበት አሳሳቢ ሁኔታ እንድንወጣ ካስፈለገ የመቶ ሚሊዮን ሕዝብ ዕጣ ፈንታ በአንድ ድርጅት፣ ከዚያም ውስጥ በጥቂት የፖሊት ቢሮ አባላት የሚወሰንበት ሒደት መለወጥ ይኖርበታል። ሌሎችም ስለአገራቸው እንደሚቆረቆሩ፣ የሌሎችም ሐሳብ ሊጠቅም እንደሚችል ከልብ መቀበል ያስፈልጋል። ለዚህ ነው ከሁሉ አስቀድሞ ከዚህ የሴራ ፖለቲካ በሽታ መፈወስ ያስፈልጋል የምለው። የእኛ ትውልድ (ኢሕአዴግን ጨምሮ) ራሱን ከዚህ ድርጅታዊ አሠራርና የሴራ ፖለቲካ መፈወስ ካልቻለ፣ ቢያንስ ይህን አጥፊ አካሄድ ለተተኪው ትውልድ ማውረስ የለበትም። ወጣቱ ትውልድ በዚህ አስተሳሰብ ያልተበከለ፣ ልዩነትን የሚያከብርና ለውይይት ዝግጁ የሆነ ኃይል እንዲሆን ሁኔታዎችን ማመቻቸት ያስፈልጋል። አሁን እንደሚታየው ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው ጽንፈኛ የጎሳ ብሔርተኝነት፣ ከነባሩ የሴራና የመጠፋፋት ፖለቲካ ጋር ተገናኝተዋል፡፡ ይህ ደግሞ በሒደት የሚያስከትለው ጥፋት የትየለሌ ነው፡፡

እዚህ ላይ ለበርካታ ዓመታት አምኜበት ስታገልለት የኖርኩትን አስተሳሰብ በተመለከተ ያለኝን አስተያየት ግልጽ ላድርግ። ደጋግሜ ከሴራ ፖለቲካ እንፈወስ፣ ከሚስጥራዊ ድርጅታዊ አሠራር እንላቀቅ፣ ዜጎች የመሰላቸውን ነገር ሳይፈሩና ምን ይደርስብኛል ሳይሉ የሚናገሩበትና የሚከራከሩበት መንገድ ይዘርጋ፣ ወዘተ. እያልኩ ስከራከርና ለዚህ ዴሞክራሲያዊ አሠራር ትልቅ መሰናክል የሆነውን ሌሊኒስት፣ ስታሊኒስትና ማኦይስት አስተምህሮ ስተች፣ በመድበለ ሐሳብና በመድበለ ፓርቲ ሥርዓት የሚያምኑ፣ ለማኅበራዊ ፍትሕ የሚታገሉና ዝቅተኛ ገቢ ላለው የኅብረተሰብ ክፍል ወገንተኛ የሆኑ፣ ዴሞክራሲያዊ ሶሻሊስት ፓርቲዎች (Democratic Socialists) መኖር የለባቸውም ወይም አያስፈልጉም እያልኩ እንዳልሆነ እንዲታወቅልኝ እፈልጋለሁ።

የእኔ ክርክር በተለምዶ ‹ያ ትውልድ› እየተባለ የሚጠራው የእኔ ትውልድ የተጠመቀበትን፣ ለብዙዎች ሞት ምክንያት የሆነውንና አስካሁንም ድረስ በሁሉም አቅጣጫ ማዕከላዊ ቦታ ይዞ የፖለቲካ ባሕላችን እንዳይሻሻል አንቆ የያዘውን አስተሳሰብ የተመለከተ ነው። ትናንትና ጥያቄዎችን በውይይትና በድርድር ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ ፋሽስት፣ አናርኪስት፣ ወንበዴ፣ የዓረብ ተላላኪ፣ ወዘተ እየተባባልን የተለየ ሐሳብ ያላቸውን ወገኖች እየፈረጅን ምን ላይ እንደደረስን እናውቃለን። አሁንም ቢሆን ከታሪክ ትምህርት ቀስሞ ፍረጃውን ማቆምና ለውይይት መዘጋጀቱ ነው የሚበጀው። እንዲያውም በእኔ አስተያየት አገራችን አሁን ከገባችበት እጅግ አሳሳቢና ፈታኝ ሁኔታ እንድትወጣና ዘላቂ የሆነ ሰላምና ልማት እንዲመጣ ካስፈለገ፣ መንግሥት በሰላማዊ መንገድ ከሚታገሉት የፖለቲካ ኃይሎች ጋር ብቻ ሳይሆን የትጥቅ ትግል ከሚያደርጉት ድርጅቶችም ጋር ለመወያየት መዘጋጀት ይኖርበታል።

በመንግሥት በኩል የሕዝብን ጥያቄ ያለመቀበል፣ መሠረታዊ ምላሽ የሚያስፈልጋቸውን ጥያቄችን ወደ ተራ የመልካም አስተዳደር ጥያቄነት የማውረድና ጥያቄው የጥቂቶች እንጂ የሕዝብ ጥያቄ አይደለም እየተባለ ሌላ የቤት ሥራ የማስቀመጥ አካሄድ ይስተዋላል። ይኼ አካሄድ መታረም ይኖርበታል። የሕዝብ ጥያቄዎችን በጥይትና ወጣቶችን በገፍ በማሰር ለመመለስ የሚደረገው ሙከራም ጥያቄውን ለጊዜው ያዳፍነው እንደሆነ እንጂ ችግሩን ጨርሶ አይፈታውም። መፍትሔው ሀቁን መቀበል ነው፣ መፍትሔው የሕዝብን ብሶት ከምር ማዳመጥ ነው፣ መፍትሔው ሕዝብ የሚበጀውን መምረጥ እንደሚችል ከልብ ማመን ነው፣ መፍትሔው ብሔራዊ መግባባት የሚፈጠርበትን መንገድ መቀየስ ነው፡፡

የሕገ መንግሥት ‘ሪፎርም’ እና ብሔራዊ መግባባት

ሌተና ጄኔራል ፃድቃን፣ “አገራችን አሁን ካለችበት ቀውስ እንድትወጣ፣ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጡትን ሰብዓዊና ፖለቲካዊ መብቶች ያለምንም መሸራረፍ ተግባር ላይ በማዋል ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ያለምንም ተፅዕኖ በሰላማዊ ፖለቲካዊ ውድድር የሚሳተፉበትን ሁኔታ ማመቻቸት መጀመር አለበት፤” ሲሉ ጽፈዋል። ተገቢ አስተያየት ነው። ስለኅብረተሰብ የፖለቲካ ተሳትፎ፣ ስለመተማመን፣ ስለነፃና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ባነሷቸው ነጥቦች ላይም እስማማለሁ። ከሁሉ በላይ ደግሞ የአገር መከላከያ ሠራዊት በሕገ መንግሥቱ መሠረት የተሰጠውን ተልዕኮ ብቻ እንዲፈጽም እንጂ ከየትኛውም ድርጅት ጋር ወገንተኛ ሆኖ እንዳይቆም፣ ይልቁንም “የፀጥታ ኃይሎች እንደ ሌሎች የመንግሥት ሥራ አስፈጻሚ አካላት በማንኛውም ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ከመግባት ሙሉ በሙሉ መቆጠብ ይኖርባቸዋል። ዋናው ሥራቸው የአገር ዳር ድንበርና ሉዓላዊነት ማስጠበቅ ነው፤” ያሉት ሊሰመርበት የሚገባው ነጥብ ነው።

የገለልተኝነታቸው ሁኔታ ብዙ ጥያቄ ስለሚነሳበት ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽንና የመንግሥት ሚዲያ ቦርድ ያቀረቡት አስተያየትም በጣም ጥሩ ነው። ሌሎችም ያልጠቀስኳቸው ጠቃሚ ነጥቦች ተነስተዋል። በአጠቃላይ በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጡት ሰብዓዊና ፖለቲካዊ መብቶች በሥራ ላይ መዋል አለባቸው የሚለው አስተያየት የሚደገፍ ነው።

ሕዝብ ነፃነቱ ተጠብቆ ሳይፈራና ሳይሸማቀቅ የመሰለውን እንዲናገር ካስፈለገ የአገር መከላከያ ሠራዊት፣ የደኅነት ተቋማትና ሌሎች የፀጥታ ኃይሎች በተግባር ገለልተኛነታቸው የተረጋገጠ እንዲሆን ያስፈልጋል። መገናኛ ብዙኃንና የፍትሕ አካላት (ፍርድ ቤት፣ ፖሊስ፣ ዓቃቤ ሕግና ማረሚያ ቤት) ገለልተኛነትም እንዲሁ ሕገ መንግሥቱ በሚለው መሠረት በተግባር መረጋገጥ አለበት። እስከዚህ ድረስ ከሌተና ጄኔራል ፃድቃን ጋር እስማማለሁ።

ሆኖም ሕገ መንግሥቱ የዜጎችን መብት ለመጠበቅና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ለመገንባት የሚያግዙ በርካታ ድንጋጌዎች ቢኖሩትም፣ ከብዙ አቅጣጫዎች ጥያቄ የሚነሳበትና ከፍተኛ የሆነ የቅቡልነት (Legitmacy) ችግር ያለበት ሰነድ መሆኑን መካድ አይቻልም። ራሳቸው ሌተና ጄኔራል ፃድቃን ሕገ መንግሥቱን አስመልክተው ሲገልጹ፣ “ሕገ መንግሥቱ በሕዝባዊ የትጥቅ ትግሉ ውስጥ አብዮታዊና ዴሞክራሲያዊ መንፈስ የተላበሰ፣ ኢሕአዴግ በሚመራው መንግሥት እንዲኖር የሚፈለገውን የመንግሥት አሠራርና ባሕርይ መለኪያ (Standard) ይሆናል ብለን ያስቀመጥነው የትጥቅ ትግሉ ድሎች መቋጫ ነበር እላለሁ፤” ያሉት፣ ሰነዱ ሕዝቡ አስተያየቱን ያልሰጠበትና በበቂ ያልመከረበት መሆኑን የሚጠቁም ነው። “ሁኔታው በፈቀደው መጠን ሕዝብ እንዲመክርበትና አስተያየቱን እንዲሰጥበት ተደርጓል፤” የሚለው አስተያየት አሳማኝ አይመስለኝም። የማያከራክረው ሀቅ ሰነዱ ምንም ያህል ጠቃሚ ድንጋጌዎች ያካተተ ሕገ መንግሥት ቢሆንም፣ ከፍተኛ ሆነ የቅቡልነት ችግር ያለበት ሰነድ መሆኑ ነው። በሕገ መንግሥቱ ውስጥ የተካተቱ ክፍፍል የፈጠሩ አንቀጾች መኖራቸውም እውነት ነው። ስለሆነም ከሁሉ በፊት ይህን ሕገ መንግሥት አንድ በትጥቅ ትግል ያሸነፈ ኃይል የጫነው ሰነድ ነው ከመባል ለማዳን፣ ወዲያውም በእነዚህ የሕዝብ ክፍፍል በፈጠሩ አንቀጾች ላይ አስተያየት እንዲሰጥና በሰነዱ መካተት ሲገባቸው ሳይካተቱ የቀሩ ሌሎች አንቀጾችን ለማካተት፣ እንዲሁም የሕገ መንግሥቱን ተቀባይነቱን ለመጨመር፣ የሕገ መንግሥት ሪፎርም የተሻለ አማራጭ ነው የሚል እምነት አለኝ።

ከዚህ ቀደም በውይይት መጽሔት (ከቁጥር 01 እስከ 03 በተከታታይ) ባቀርብኳቸው ጽሑፎች ለመጠቆም እንደሞከርኩት፣ የሕገ መንግሥት ‹ሪፎርም› ሒደት መንግሥትና  ሕዝብን ለማቀራረብ፣  በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ውይይት ለመክፈት፣ ከሁሉ በላይ ደግሞ የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ሕዝብ የአገሪቱን የበላይ ሕግ በማመንጨትና በማፅደቅ፣ ዘመን ተሻጋሪ የሆነ ሕገ መንግሥት ለመፍጠር ትልቅ ዕድል ይከፍታል። በሒደቱ በርካታ አገራዊ ጥያቄዎች እየተነሱ ውይይትና ክርክር ስለሚደረግባቸው፣  የሕዝቡ የፖለቲካ ተሳትፎ ይጨምራል፤ ዴሞክራሲ ይለማመዳል፣ በኅብረተሰቡ መካከል መቀራረብና መተማመን እንዲፈጠር ምቹ ሁኔታ ይፈጠራል፣ ወዘተ።

በመጨረሻም ኢሕአዴግ ለውጥ የመምራትን አማራጭ ለመውሰድ ከፈለገ የሚከተሉትን ዕርምጃዎች ሳይውል ሳያድር ሳያድር ተግባራዊ ሊያደርግ ይገባል፡፡ አንደኛ በየወህኒ ቤቱ የታጎሩትን የፖለቲካ ሰዎች፣ ጋዜጠኞች፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች፣ አክቲቪስቶች፣ ወዘተ. ያላንዳች ቅድመ ሁኔታ ሊፈታቸው ይገባል፡፡ ሁለተኛ ከ1960ዎቹ ጀምሮ በተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ታቅፈው እርስ በርስ የተጋደሉትና እስካሁን ድረስ በጠላትነት የሚፈላለጉት ሁሉ ኢሕአዴግን ጨምሮ ላለፉት የፖለቲካ ድርጊቶቻቸው ምሕረት የሚያደርግ የምሕረት አዋጅ (Blanket Amnesty) ሊውጅ ይገባል፡፡ ሦስተኛ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሙያና የሲቪል ማኀበራት፣ የሃይማኖት ተቋማት፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወዘተ. የሚሳተፉበት ሁሉን አቀፍ የሆነ ብሔራዊ የንግግር ጉባዔ ሊጠራ ይገባል፡፡

ደጋግሜ እንዳልኩት ኢሕአዴግ ይህን ካደረገ አገሪቱን ከጥፋት፣ ራሱንና ደጋፊዎቹንም በአገራችን እንደተለመደው መንግሥት በተቀያየረ ቁጥር ከሚደርስ የበቀል ዕርምጃ ይታደጋቸዋል፡፡ በአጭሩ የተለመደው የመፈራረጅና የመጠፋፋት ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ተዘግቶ በአዲስ ተስፋ መጓዝ እንድንጀምር መሠረት ይጥላል፡፡

ይህን ምርጫ ወደጎን ካለ ግን ለውጥን መምራት አንዳልፈለገ ተቆጥሮ በለውጡ ሊገፋና ሊገለል ይችላል፡፡ ስለዚህ ምርጫው አንድም ከፍ ሲል የተጠቀሱትንና ሌሎችንም ለሰላማዊና ለዴሞክራሲያዊ ሽግግር ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ ዕርምጃዎችን ወስዶ የለውጥ መሪ መሆን፣ አንድም እነዚህን ዕርምጃዎች ባለመውሰዱ ምክንያት በለውጥ መገፋትና መገለል ይሆናል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው ከንጉሠ ነገሥቱ ዘመን ጀምሮ በውትድርና፣ በፖለቲካና በአስተዳደር የመንግሥት ሥራ ያገለገሉ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የሕግ አማካሪና ጠበቃ ናቸው፡፡ ጽሑፉ የሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው molla.zegeye@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

ኢሕአዴግን በማደስ አገርን ማዳን ወይስ…?

$
0
0

   በገመቹ ዘለዓለም

ከ2008 ዓ.ም. ማጠቃለያ ቀናት አንስቶ አሁን እስካለንበት ጊዜ ድረስ በመላው አገሪቱ ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ››፣ ስብሰባና ግምገማ ተቀጣጥሏል፡፡ ከአገሪቱ ከፍተኛ የሥልጣን አካል (የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ) አንስቶ ከፍተኛ፣ መካከለኛና ዝቅተኛ አመራር፣ መምህራንና የትምህርት ዘርፍ አመራሮች፣ ወላጆችና የተማሪ ተወካዮች በስብሰባ ተወጥረዋል፡፡ ሲቪል ሰርቪሱም ቢሆን በመስከረም መጨረሻ የሚካሄደውን የመንግሥት ማዋቅር ማሻሻያ ከመጠበቅ ባለፈ በውስጥ ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ላይ መጠመድ መጀመሩ በስፋት እየተወራ ነው፡፡

ግን ይህ ሁሉ ከፍተኛ የአገር ሀብት ወጥቶ ድካሙ ሁሉ ፍሬ የሚያፈራ ካልሆነ ዋጋ የለውም፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት በተመጣበት መንገድ ለማሻሻል መሞከር የሚቻል አይሆንም፡፡ በተለይ አሁን በሁሉም መድረኮች በድፍረት እየተነሱ ካሉ መሠረታዊ ጭብጦች አንፃር፣ የራሱ የድርጅቱ አባላትና አመራሮች ጭምር በድፍረት አደባባይ ያወጡትን ችግር ወደ ጎን ማለት ከወድቀት አያድንም፡፡

ከዚህ አንፃር በዚህ ጸሐፊ እምነት እንደ ሕዝብና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የኢሕአዴግን ጥልቅ ተሃድሶ በዝምታ ልናልፈው አንችልም፡፡ አቅማችን በፈቀደው መጠንም አገሪቱን ከቀውስ፣ ሕዝቧንም ከችግር የሚያወጣ ፖለቲካዊ ሥነ ምኅዳር ለመፍጠር የየድርሻችን መወጣትም ይኖርብናል፡፡

ግን ሁላችንም የየድርሻችን የምንወጣው ‹‹ኢሕአዴግን በማደስ አገርን ማደስ? ወይስ ኢሕአዴግን በማፍረስ አገርን ማንገራገጭ? አልያም ሁሉንም የፖለቲካ ኃይሎች ያሳተፈ መፍትሔ በማፈላለግ የጋራ መፍትሔ ማምጣት?›› የሚለውን ማጤን ተገቢና አስፈላጊ ይሆናል፡፡ ከዚህ አንፃር ለውይይት የሚረዱ ነጥቦችን በአሁኒቷ ኢትዮጵያ ልዩ ልዩ መድረኮች ከሚነሱባት ገጽታ አንፃር ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡

ሙስናና ጥገኝነትን እንደምን መግታት ይቻላል?

ራሱ ገዢው ፓርቲ ላለፉት ተከታታይ ዓመታት እንደገለጸው በሥርዓቱ ውስጥ ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› የሚባለው አስተሳሰብ በተለይ በከተሞች እየጎመራ መጥቷል፡፡ ለዚህ ያልሠሩበትን የማጋበስ አስተሳሰብና ተግባራዊው መነሻ ደግሞ ሥልጣንና የ‹‹ሕዝብ አደራ›› እንደሆነ ይታወቃል፡፡

ኢሕአዴግ በአገሪቱ ለማስፈን የሚፈልገው ‹‹ልማታዊ መንግሥት›› የተባለው የምሥራቅ እስያ ተሞክሮ እንደመሆኑ መንግሥት ዋነኛው የማኅበረ-ኢኮኖሚው ተዋናይ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ ይህም በየትኛውም የመንግሥት እርከን ላይ የተቀመጠ ኃላፊም ሆነ ባለሙያ ከመቼውም ጊዜ በላይ ትልቅ በሚባል የአገር ሀብት ላይ የማዘዝና የመወሰን ዕድል አለው፡፡ ደርግ አገሪቱ እንዳትሆን አድርጎ ትቶ ሲሸሽ በመንግሥት ካዝና ውስጥ የተገኘው ከ33 ሚሊዮን ዶላር ያነሰ ገንዘብ ነበር፡፡ አሁን ግን ለአንድ ሜጋ ፕሮጀክት (ታላቁ የህዳሴ ግድብን መውሰድ ይቻላል) እስከ 4.5 ቢሊዮን ዶላር መበጀት የቻለች አገር ተገንብታለች፡፡

ይህ ነገር ታዲያ ባለሥልጣናትና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሙያዎች በቢሊዮን ብር የሚገመት ተጫራጮችና የውጭ ኩባንያዎችን እንዲደራደሩ ይላካሉ፡፡ በከፍተኛ ሀብት የመንግሥት ግዢም ሆነ ሽያጭ ይፈጸማል (በተለይ የኮንትራት ግዢ ከሚገመተው በላይ ነው)፡፡ የጉምሩክና የግብር ሥርዓቱ፣ መሬትን ዋነኛ የሀብት ማዕከል ያደረገው ኃይል የሚራኮትበት ሁኔታ ሁሉ ለሙስናና ለብልሹ አሠራር ተጋልጦ ቆይቷል፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወይም በፌዴራል የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ተቀምጦ ሳይፈርም በስልክ ትዕዛዝ ብቻ ሀብት ሲያካብት የከረመው ኃይል ቁጥሩ ትንሽ አይደለም፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ ዙሪያ ያለ የሕዝብ መሬት ተቀራምቶ፣ ሕንፃና ዘመናዊ ቪላ እስከ መገንባትና የንግድ ድርጅት እስከ ማቋቋም የደረሰው፤ ከዚያም አልፎ የውጭ አገር ባንኮች ውስጥ ዳጎስ ያለ ገንዘብ ያስቀመጠው የመንግሥትና የኢሕአዴግ ሰው ቁጥሩ ትንሽ እንዳልሆነ እየተደመጠ ይገኛል፡፡

አሁን በተለያዩ መድረኮች ተሳታፊዎች እየተነሳ እንዳለው ‹‹ሌባ›› ከየትኛውም ብሔር ቢመጣ የመጣበትን ሕዝብ ሊወክል አይችልም፡፡ በግላዊ ፍላጎት የሕዝብ መስብን ገልብጦ የበላ ቀማኛ እንጂ፡፡ ይሁንና ስንቶች መስዋዕት ሆነውበታል የሚባለውን ኢሕአዴግ መከታ አድርገው የዘረፉ፣ ያዘረፉና ያቀባበሉም መጠየቅ እንዳለባቸው ጥርጥር የለውም፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአንድ ብሔር ላይ ያነጣጠረ ቅሬታ እንዲፈጠር የሚያደርጉ ዝንባሌዎች በግልጽ ታይተዋል፡፡ በተለይ ከመከላከያ፣ ከደኅንነትና ከቢሮክራሲው የወጣ አብዛኛው ጥገኛ በተለያዩ ክልሎች፣ ውስጥ በመግባት በላቡ ከመሥራትም ባለፈ የአቋራጭ ተጠቃሚ ሆኗል፡፡ በተለይ በምዕራብ ኢትዮጵያ ‹‹በእርሻ ሥራ›› ስም ተሰማርቶ ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ የሚሊዮኖች ብር ብድር ተመቻችቶለታል፡፡

በዚህም አገርን ለልማት (በተለይ በማካናይዝድ እርሻ) አሳድጎ ወደ ልማታዊነት ከመቀየር ይልቅ በጥገኝነት የተገኘን የሕዝብ ሀብት ሕንፃ ሠርቶ ለማከራየት፣ የግንባታ ማሽነሪ ከታክስ ነፃ አስገብቶ ኪራይ ለመሰብሰቢያ መሣሪያ ማድረግ የለየለት ሌብነትና ጥገኝነት ነው፡፡ ያለጥርጥርም ዘረፋ ነው፡፡

አዲስ አበባን ጨምሮ በአገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች ላይ በርካታ ባለሀብቶች (በዘኢኮኖሚስት መጽሔት ሚሊየነሮች እየጎረፉባት ያለች አገር ተብለናል) ተፈጥረዋል፡፡ ይሁንና እነዚሁ ወገኖች ሕንፃም ይሥሩ የንግድ ኩባንያ በምን መንገድ ተለወጡ የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡ ምንም እንኳን የሚሸማቀቁበትና የሚደናገጡበት ሁኔታ ይፈጠር ባይባልም፣ በተለይ በሥልጣን ላይ ከነበረው ጥገኛ ኃይል ጋር ተጣብቀው የሕዝብ ሀብት ዘርፈው የከበሩ ካሉ ሊጋለጡና ሊገቱ የግድ ይላል፡፡ በመሠረቱ ከአንዳንድ ባለሀብቶች ስም ጀርባ ሕዝብ የሚያነሳቸው ሕንፃዎችና ኩባንያዎች ወይም የንግድ ድርጅቶች ጉዳይም ተፍረጥርጦ መታወቅ ይኖርበታል፡፡

በድምር ‹‹የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን›› የሚባለው ልግመኛ መሥሪያ ቤት የባለሥልጣናትንና የተመራጮችን ሀብት መዝግቦ ተኝቶበታል፡፡ ቢያንስ አሁን ግን በእንዲህ ዓይነቱ የተሃድሶና የጥልቅ መሻሻል ለሚባልላት ጊዜ መረጃው ሊያግዝ ይገባል፡፡ በተጨባጭም ሥርዓቱ ሙስናን የሚፀየፍና ሕዝባዊ መሆኑን ሊያረጋግጥ የሚችለው፣ ይኼ አገርና ሕዝብ ያወቀውን ወቅታዊ ፈተና አብዮታዊ በሆነ ዕርምጃ መሻገርና ከሕዝብ ጋር መተማመንን ሲፈጥር ብቻ ነው፡፡

መንግሥታዊ ቸል ባይነትና የፈጠረው የቅንጦት ገደል

ይኼ መንግሥት መታደስና እውነተኛ መሻሻል ማድረግ ካለበት በዋናነት፣ በገዢው ፓርቲና በመንግሥት መዋቅሩ ውስጥ ያለው ስንፍና፣ ሕዝባዊነት ማጣትና የጥቅም መካፈል አደጋ በግልጽ መታወቅ አለበት፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በቅርቡ እንደተናገሩት፣ የመንግሥትን ሥልጣን የግል ጥቅም ማካበቻና ምቾት ማረጋገጫ ያደረጉ ብዙዎቹ ሹመኞች፣ በተለይ ብሔርንና የውሸትም ቢሆን የድርጅቱ አባልነትን ተጠቅመው ተገልግለውበታል፡፡

እነዚህን አባባሎች በማሳያ ለማብራራት ለምሳሌ የአገሪቱ ባለሥልጣናት የሚጠቀሙባቸው ተሽከርካሪዎች ጉዳይ ወዳልሆነ ፉክክር የተገባባቸውና ጥቅም ማስከበሪያ ሆነዋል፡፡ ትናንት በሚኒስትሮች፣ በሚኒስትር ዴኤታዎች፣ በአማካሪዎች፣ በኮሚሽነሮች፣ ወዘተ እጅ ያየናቸው  (እስከ ስምንት ሚሊዮን ብር ያወጣሉ) ዛሬ በአዲስ አበባ የክፍለ ከተማ አስተዳዳሪ እጅ ደርሰዋል፡፡ ዘመናዊ ላንድክሩዘርና ዘመናዊና ራዶ ተሽከርካሪን ያልያዘ የመንግሥት ባለሥልጣንም ፈጽሞ ማግኘት አይቻልም፡፡

እንግዲህ አስቡት ገና የሕዝቡ አማካይ የነፍስ ወከፍ ገቢ ከ600 ዶላር በታች በሆነባት አገር፣ 22 ሚሊዮን ሕዝብ ከድህነት በታችና ከዚህ ውስጥ 17 ሚሊዮን ሥራ አጥ ለተሸከመ አገር ይኼ ምን ማለት ነው!? ሌላው ይቅር ልመናው፣ ሴተኛ አዳሪነቱ፣ ስደቱ፣ ድርቁና ችግሩ አልቆጠቁጣችሁ ያለን ለምንድነው!? መባል አለበት፡፡ በአገሪቱ ሁሉም ክልሎች ያለው የተሽከርካሪ የቅንጦት አጠቃቀም የሚያስገርም ነው፡፡ አንዳንዱ የካቢኔ አባልም ካለልምምድ ላሽከርክር እያለ በሚሊዮን የሚገመት ሀብት ዶጋ አመድ ሲያደርግ ማየት ተራ ነገር ሆኗል፡፡ ይኼ ሁሉ እንዝህላልነት ገደብና ጣሪያ ሊበጅለት ግድ ይላል፡፡ ቢያንስ የደርግን ያህል እንኳን ደረጃ ማውጣትና ሕዝባዊ ተቆርቋሪነትንም ማሳየት ያስፈልጋል፡፡ በነገራችን ላይ እነ ህንድ፣ ቻይናና ኮሪያን የመሳሰሉ አገሮች ደግሞ ለመንግሥት ኃላፊዎቻቸው ከአገር ውስጥ ምርት ውጪ እንዲጠቀሙ አያስደርጉም፡፡

የእኛ አገር አስፈሪ የባለሥልጣናት ባህሪ ደግሞ ከወረዳ አመራር ጀምሮ ተሽከርካሪውን በጥቁር ስቲከር እየሸፈነ ከሕዝብ ተደብቆ መውጣትና መግባቱ ነው፡፡ ሚኒስትሩና ሥራ አስፈጻሚው እሺ ‹‹ለደኅንነቴ›› ይበል እንዲያው የክፍለ ከተማ ካቢኔና ስሙ እንኳን በአግባቡ የማይታወቅ የጽሕፈት ቤት ኃላፊን ማን እንዳይነካው ይሆን!? ነው ሕዝብን ሽሽት? አገልጋይነትን መግፋት? ወይም ራስን ከፍ ከፍ ለማድረግ? በነገራችን ላይ ባለሥልጣናቱ የሚጠቀሙበት በር፣ የቢሮ ዕቃዎችና የቅንጦት ዕቃዎች ሁሉ የተገልጋይነት ፊውዳል ባህሪ የፈጠረው የቢሮ ትምክህተኝነት መሆኑ ሊመረመር ግድ ይለዋል፡፡

አሁን የሕዝቡ ቁጣ ጣሪያ ነክቶ ኢሕአዴግን እንደ ሥርዓት ከዳር ዳር መቃወም ሲጀምር ‹‹መንግሥታዊ ሥልጣንን ለኑሮ ማመቻቻና ለመጠቃቀሚያ ያደረጉ ኃይሎች አሉ›› እያለ ነው፡፡ ለዚህ ጥሩ አብነት የሚሆኑት የአዲስ አበቤዎቹ አስተዳዳሪዎች ኔትወርክ ነው፡፡ ብዙዎቹ በኔትወርኩ አማካይነት በቤተሰብ ጭምር ተሳስረዋል፡፡ አንዳንዱ የአስተዳደሩም ሆነ የድርጅቱ ተሿሚ በተለያየ መንገድ የያዘውን ሁለትና ሦስት የመንግሥት ቤት በሕገወጥ መንገድ ጨብጦ ኪራይ እየለቀመበት ነው፡፡

በብልጣ ብልጥ ሙያተኞች (አንዳንድ አመራሮች) የተመቻቸን የውጭ ጉዞ ያለምንም ዓላማ መመላለሻ ያደረጉ ‹‹ተሿሚዎች›› ጥቅማቸው እየጎለበተ ነው፡፡ ኢሕአዴግ የዓላማ ሰዎችና የሕዝብ ጥቅምን ያስቀደሙ ጀግኖች የሞሉበት እንዳልነበረ፣ እየተሞዳሞደ የአገር ሀብት የሚከፋፈል በእጅጉ እየከበበው መጥቷል፡፡ እንግዲህ ይቺ የተፈጠረችውን የተሃድሶ የመጨረሻ ዕድል የሚታዩ ግልጽ ዝርክርክነቶችን ለማረም መጠቀም ግድ ይለዋል መባሉም ለዚሁ ነው፡፡

አገር እያስጨነቀ ያለ ጠባብነት

ኢሕአዴግና መንግሥት በአገሪቱ ጠባብነት አለ ሲል የማይነጥለው ትምክህትም ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ዝንባሌዎች በሌሎች አገሮችም ያሉና የነበሩ ናቸው፡፡ በኢትዮጽያ ሁኔታም ምንም እንኳን ለዘመናት የዘለቁ ቢሆኑም፣ ከፌዴራል ሥርዓቱ መጀመር ጋር ተያይዘው ብቅ ጥልቅ እያሉ መምጣታቸው አይካድም፡፡

በእኔ እምነት አሁን የአገሪቱን አየር የሞላው ግን በዚያም ሆነ በዚህ እየተቀጣጠለ ያለው ጠባብነት (Narrow Nationalism) እና መንደርተኝነት ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲስ አንዳንዶች በአገራቸው ጉዳይ ለመጠቀምና ለመሳተፍ ከመሻት ይልቅ ‹‹ምንነቴ›› በሚሉት ብሔር ቋንቋና ሠፈር ዙሪያ መኮልኮል ይዘዋል፡፡ ለዘመናት አብሯቸው የኖረውን የተጋቡትንና የተወለዱትን የሌላ ብሔር ሳይቀር እንደ ባዕድና የሩቅ ሰው መቁጠሩንም ገፍተውበታል፡፡ (ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የእገሌን ቤት ማፍረስ፣ እነእገሌ ይውጡልን ምን ያህል እየበረታ እንደመጣ መገንዘብ አያዳግትም፡፡)

ለዚህ ጠባብነትም ቢሆን ዋነኛ ተጠያቂዎቹ የገዢው ፓርቲ መሪዎች መሆናቸው ግን ግልጽ ነው፡፡ ገና ከመነሻው ከፌዴራልም ሥርዓት ባህሪ ልዩነትን እንጂ አንድም የጋራ እሴትን ማስገንዘብ አልተቻለም፡፡ ትውልዱ በራሱ ቋንቋ መማሩና መዳኘቱ ጥሩ ሆኖ ስለሌለው ቋንቋና ማንነት ያለው አረዳድ የተዛባ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ (ኦሮሚያ ክልል አማርኛን ‹‹የገዢ መደብ›› ቋንቋ አስመስሎ በእነዚያ ኋላቀርነት የተሞላበት ቅስቀሳ አማርኛ ችሎ የሚናገር ወጣት ጠፍቷል፡፡ ይህም የክልሉ ምሩቃን በፌዴራል መንግሥቱ የመቀጠር ዕድላቸውን ጎድቶታል፡፡)

ኢትዮጵያውያን ለጋራ ሰንደቃቸውና ኢትዮጵያዊ ማንነታቸው ያላቸው ክብርና ፍቅርም የተደበላለቀ ነው፡፡ ምንም እንኳን ለ25 ዓመታት ‹‹አንድ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ተገንብቷል›› ሲባል ቢከርምም በአንዲት ቃል ወይም ኅትመት ስህተት ጥቅሜ ተነካ ብሎ ድብልቅልቅ የሚያወጣ ትውልድ መጥቷል፡፡ ከ40 ሺሕ ሔክታር በማትበልጠው የግጮውና አካባቢው ይዞታ መዘዝ ለዘመናት የኖሩት የጎንደርና የምዕራብ ትግራይ ነዋሪዎችን ቅያሜና ቅሬታ ውስጥ ከትቷል፡፡ በክልሎቹ አስተዳዳሪዎች ማናለብኝነትና ችግር የመፍታት ድክመት የልዩነት ደውሉ ከልክ በላይ ጮኾ ተደምጧል፡፡

ኢትዮጵያውያን አገራችን ከድህነት ወጣች፣ ዜጎች ሀብት እያፈሩ ነው ሳይሆን የሚያስጨንቃቸው ‹‹እነእገሌ በለፀጉ›› የሚለው ጉዳይ ሆኗል፡፡ የአንድ አገር ዜጎች ተባብረውና ተሳስበው ሌባውን እየነጠሉ እንዳይመቱ የሚያደርግ መደበቂያ የብሔር ባርኔጣ ውስጥ እየተበጀ ነው፡፡ እንኳን የአክሲዮን ማኅበር ይቅርና ዕድርና ሠፈር በብሔር የሚደራጅበት አገር መፈጠሩ ባለፉት 25 ዓመታት ጠባብነት ይበልጥ እንዲባባስ በር ከፍቷል፡፡ ይህን መጥፎ በሽታ ደግሞ መንግሥትና መዋቅሩ አለመከላከላቸው አደጋውን ይበልጥ አስፈሪ ያደርገዋል፡፡

አብዮታዊነት የራቀው ኢሕአዴግ

የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) በትጥቅ ትግል የቀድሞውን አምባገነን ሥርዓት አሸንፎ በአገሪቱ አዲስ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ሥርዓት የዘረጋ ነው፡፡ በዚህም ሥር ነቀል ለውጥ የማምጣት ባህሪ እንዳለው ይታመናል፡፡ ይሁንና ድርጅቱ በአንድ በኩል እስካሁን ድረስ ኅብረ ብሔራዊ ፓርቲ መሆን አልቻለም፡፡ እሱ ብቻ ሳይሆን ከጊዜ ወደጊዜ ደግሞ የአራቱ አባል ፓርቲዎቹ አብዮታዊነት ሲዳከምና ሲሸረሸር ታይቷል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገሪቱ ለተፈጠሩት ቀውሶች እየተነገሩ ያሉ ምክንያቶችን ለሚመረምር በአብዛኛው ከጋራ መርህ ውጪ መንቀሳቀስ የፈጠራቸው ናቸው፡፡ አንዱ ጋ ሙስና ሲበረታታ፣ ሌላው ዘንድ ጠባብነት ወይም ትምክህት ይጎላል፡፡ በውስጥ መደማመጥና መከባበር የለም፡፡ የእኩልነት መንፈስ እየተዳከመ ከመሄዱም ባሻገር፣ የአንዱ ድርጅት አባል የሌላውን የሚያበጠለጥል ኃይል እየሆኑ ነው፡፡

የአብዮታዊነት አንዱ መገለጫ ሕዝባዊነት ነው፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ገዢው ፓርቲ ፈጥኖ ካላስተካከለው ከሕዝቡ የተነጠለባቸው የተለያዩ ምልክቶች አሉ፡፡ በአንዳንዱ አካባቢ የመልካም አስተዳደር መጓደል፣ በሌላው የዴሞክራሲ መሸራረፍ፣ ወይም ሥራ አጥነትና ድህነት ቅር የሚያሰኛቸው ዜጎች ቁጥር ትንሽ አይደሉም፡፡ ባሳለፍነው ዓመት ደግሞ በተለያዩ ምክንያቶች በጣም በርካታ ዜጎች ተገድለዋል፡፡ እነዚህ ሳንካዎች ደግሞ ድርጅቱ ይቅርታ ጠይቆ ወደ ሕዝቡ እንዲወርድ ያስገድዱታል፡፡

ወደ ሕዝቡ ለመውረድ መሠረታዊው ጉዳይ ደግሞ የተሿሚዎች ቀለም መቀየር ወይም ወንበር ማዟዟር ብቻ በቂ አይደለም፡፡ ይልቁንም ሌባና ሕገወጡን በሕግ መቅጣትና የሕዝብ ሀብት ማስመለስ፣ በፖለቲካ መዘዝ የታሰረን መልቀቅ፣ የዴሞክራሲ ምኅዳሩን ማስፋት ብሎም ወደተጠናከረ የልማትና የሥራ ዕድል ፈጠራ ተግባር መግባት ይኖርበታል፡፡

በአጠቃላይ ኢሕአዴግን በማሻሻልና በማደስ የአገሪቱን ጉዞ አጠናክሮ ማስቀጠል ይቻላል ባይ ነኝ፡፡ የብዙኃኑ የአገሪቱ ሕዝብ ፍላጎትም ቢሆን ከዚህ የተለየ ይሆናል ብዬ አላስብም፡፡ ምክንያቱም ከሰላማዊና ከዴሞክራሲያዊ መንገድ ውጪ በኃይል የሥርዓት ለውጥ ለማምጣት መሞከር አገርን የሚበታትን ነው፡፡ በተለይ አሁን የአገሪቱ ሕዝቦች ላይ ባንዣበበው ጠባብነትና የመለያየት ስሜት ውስጥ አገርን ለመገነጣጠልም ያጋልጣል፡፡ ስለዚህ የመጨረሻው የማስጠንቀቂያ ደወል ተሰጥቶትም ቢሆን ኢሕአዴግ በጥልቀት እንዲታደስ ዕድል እንስጠው፡፡ የአቅማችንንም እንተባበረው ለማለት እወዳለሁ፡፡ ይህ ሲሆን ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታና ለሰብዓዊ መብት መከባበርና ለሌሎች ዘርፈ ብዙ ችግሮቻችን መፍትሔ ለማምጣት መንገዱን መጥረግ ይቻላል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

Standard (Image)

አራቱ የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳዎች

$
0
0

   በዘለዓለም እሸቴ (ዶ/ር)

ዛሬ ኢትዮጵያ አስከፊ ችግር ውስጥ ወድቃለች፡፡ ነገር እይተባባሰና የሰው ሕይወት እየተቀጠፈ ባለበት በዚህ ወቅት፣ ኢትዮጵያ ልጆቿ አደጋ ላይ ሳይወድቁ ይህን ክፉ ጊዜ የምታልፍበት መውጫ ቀዳዳ ያጣች ትመስላለች፡፡ መውጫ ቀዳዳዎች ከአንድም አራት አሉላት ይባል ይሆናል፡፡ መውጣትም አይቀሬ ነው፡፡ ሁሉም ነገር ያልፋልና፡፡ ግን ዋናው ጉዳይ በአንደኛው መውጫ ቀዳዳ እንደምንም ብሎ መውጣቱ አይደለም፡፡ ይልቁንስ ልጆቿ ኖረውላት፣ ፍቅርን አትርፈውላት፣ ታሪክን ሠርተውላት፣ በዓለም አንገቷን ቀና እንድታደርግ አድርገውላት፣ በድልና በክብር ካለችበት አደጋ የሚያስፈተልካት መውጫ ቀዳዳው የትኛው እንደሆነ ለይቶ ማወቁና መተግበሩ ላይ ነው፡፡

ታዲያ ለዚህ ፈውስን በሚያመጣው መውጫ ቀዳዳ በኩል ኢትዮጵያን የሚያስመልጡ ጀግናዎች ያስፈልጉናል፡፡ ለመሆኑ ታዲያ ኢትዮጵያ የጀግና አገር ናትን? መልሱ አንድ ሳይሆን ሁለት ነው፡፡ ያውም ተቃራኒ የሆኑት አዎና አይ ናቸው፡፡ እንግዲህ የዚህን ጭብጥ ለመረዳት ወደ ዝርዝሩ እንለፍ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ ‹‹ዕርምጃ እንዲወሰድ!›› እያሉ ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ተቃዋሚዎች ሽምግልና ቦታ የለውምና ‹‹አትደራደር!›› እያሉ ሲጮሁ ይሰማል፡፡ በዚህ መሀል ሽምግልና ቦታ ይሰጠው ብለን የምናቀነቅን ሰዎች ሁለቱም ወገን እንዲሰማን ስንሟገት እንገኛለን፡፡ በዚህ ግርግር ቆም ብለን ‹‹የኢትዮጵያ ሕዝብ ምኞትና ፍላጎት ምን ይሆን?›› ብለን እንድንጠይቅ ግድ ሊለን ይገባል፡፡

ሽምግልና መፈለግ የደካማነት ምልክት ሳይሆን የእውነተኛ ጀግንነትን ጥበብ የሚያመላክት ነው፡፡ ምክንያቱም ማሸነፍን ብቻ ሳይሆን ከማሸነፍ በስቲያም ማሸነፍን ያረጋግጣልና፡፡ ይህች ቀጭንና ጠባቧ መንገድ ናት፡፡ እንደሚታወቀው ሁለት ዓይነት የሽምግልና አካሄዶች አሉ፡፡ አንድም አድሏዊ የሆነ ከኃይለኛው ጋር የወገነ የይስሙላ ሽምግልና ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ አድሏዊ ያልሆነ ከማንም ያልወገነና እውነተኛ ሽምግልና ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ላይ የምናየው ሽምግልና ፋይዳ የማይሰጠውን የይስሙላ ሽምግልና ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን ካለችበት አጣብቂኝ እንድትወጣ ድልድይ የሚሠራውን እውነተኛውን ሽምግልና ነው፡፡ የዚህ እውነተኛ ሽምግልና ግብና ዓላማ በውይይትና በመግባባት አገሪቱን በሰላማዊ መንገድ ወደ ዘላቂ ዴሞክራሲ፣ ፍትሕ፣ እኩልነትና ዕድገት የሚያመራውን ሒደት ለመፍጠር ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው፡፡

ሽምግልናን በተመለከተ መንግሥት ሁለት ምርጫዎች አሉት፡፡ አንድም በመግባባት መንገድ መሄድ፣ አለበለዚያ በእንቢተኝነት ዘራፍ ብሎ ‹‹ደምስሰው!›› እያለ መገስገስ፡፡ አማራጭ ኃይሎችም ሁለት ምርጫዎች አሉዋቸው፡፡ አንድም በመግባባት መንገድ መሄድ፣ አለበለዚያ ዘራፍ ብሎ ‹‹ገርስሰው!›› እያሉ መጓዝ፡፡ መንግሥትና ተቃዋሚዎች የሚመርጡዋቸው ምርጫዎች ኢትዮጵያን ከአራቱ አንዱን አካሄድ እንድትያዝ ያደርጋታል፡፡ እያንዳንዳቸውን በየተራ ለመመልከት እንድንችል እነዚሁ አራቱ የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳዎች ከዚህ በታች ተዘርዝረዋል፡፡

  1. ተቃዋሚ ሽምግልናን ፈልጎ መንግሥት ግን ሽምግልናን ባይፈልግ፣
  2. መንግሥት ሽምግልናን ፈልጎ ተቃዋሚ ግን ሽምግልናን ባይፈልግ፣
  3. ሁለቱም ወገን ሽምግልናን ባይፈልጉ፣
  4. ሁለቱም ወገን ሽምግልናን ቢፈልጉ፣

አንደኛው የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳ

መንግሥት ሽምግልናን ባይፈልግና ተቃዋሚዎች ሽምግልናን ቢመርጡስ?

አንድም ዘርፈ ብዙ የሆኑትን አማራጭ ኃይሎችን መግባባት እርስ በርስ ያቀራርባቸዋል፡፡ አንድ ድምፅ ይሰጣቸዋል፡፡ ልዩነታቸውን እንዲያጠቡ ያበረታታቸዋል፡፡ አንድነት ኃይል ይሆንላቸዋል፡፡ ጥያቄው ሕዝብ ያሸንፋል ወይ? አይደለም፡፡ ሕዝብ ሁልጊዜ አሸናፊ ነው፡፡ ግን እንዴት ያሸንፋል? ነው ጥያቄው፡፡ መግባባትን ለመረጠ አማራጭ ኃይል፣ ሕዝብ ሥልጣኑን ቢሰጠው የሕዝብ መንግሥት ለመሆኑ የተረጋገጠ ይሆናል፡፡ ቁምነገሩ እዚህ ላይ ነው፡፡ ከማሸነፍ ባሻገር ማሸነፍ አለ የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡ ከማሸነፍ ባሻገር ያለው ማሸነፍ ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ማየት ነው፡፡ ይህም ይቻላል፡፡ ኢትዮጵያ መከራ ይበቃታል፡፡ እርስዋ እየደማች ተራ በተራ ንጉሦች የሚፈራረቁባት ጊዜ ያክትም፡፡ ልባችንን መጣል ያለብን ኢትዮጵያ ታሸንፍ ዘንድ ነው፡፡ ስለዚህም ነው ‘ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ’ እንዳይሆን መግባባትን ዛሬውኑ ጓደኛ ማድረግ የሚበጀው፡፡

ደግሞም አማራጭ ኃይሎች መግባባትን ዕድል ቢሰጡትና መንግሥት እንቢ ብሎ ኃይሉን ብቻ ማፈርጠም ቢቀጥል፣ ይህ አካሄድ መግባባትን እንቢ ያለውን መንግሥት ብቻውን እንዲቀር ያደርገዋል፡፡ ሕዝብን ሁሉ አንድ ወገን አድርጎ እምቢተኛውን መንግሥት ያጋልጠዋል፡፡ እንቢተኝነቱ እርሱን የሚደግፉት ሁሉ እንዲክዱት ያደርጋል፡፡ ይህን አደጋ ለማምለጥ ምንም መላ አያገኝም፡፡ ሌላውን አጥፍቶ ሳይሆን እንዲሁ ብቻውን ራሱ ራሱን አጥፍቶ ታሪክ አልባ ሆኖ ሥፍራውን ይለቃል፡፡

ሁለተኛው የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳ

መንግሥት ሽምግልና ቢፈልግና ተቃዋሚዎች ለሽምግልና ቦታ ባይሰጡትስ?

መንግሥት መግባባትን በሥራ ላይ ለማዋል መድረኩ በእጅ ነው፡፡ እንደሚገባ ኃላፊነቱን በዚህ ረገድ መወጣት የመሪነቱ ግዴታ ነው፡፡ ጊዜ ከወሰደ ዕድሉ ከእጁ እያፈተለከ እንደሆነና ኢትዮጵያን አደጋ ላይ እየጣላት እንደሆነ ማወቅ አለበት፡፡ ነገር ግን ነገ ሳይል ዛሬ ሽምግልናን ቢቀበል ታሪክ ሠሪ መንግሥት ሆኖ በታሪክ መዝገብ ሊታወስና አዲስ ጅማሬን ለኢትዮጵያ የማውረስ አጋጣሚ አለው፡፡ መንግሥት መግባባትን ሲመርጥ፣ ለሚያልፍ ጊዜ ሥልጣን ላይ መቆየት ላይ ያነጣጠረ ራዕይ ሳይሆን፣ ራዕዩን አስፍቶ ፈር ቀዳጅ ድርጊትን አድርጎና ለታሪክ የሚቀር አሻራ ትቶ እንዲያልፍ ያሳስበዋል፡፡ ሕዝብ ብሎ በሥልጣን ቢቆይም በክብር፣ ሕዝብ ብሎ ሥልጣን ቢለቅም በክብር ይሆንለታል፡፡ ላስተዋለው እንዲህ ያለ ታሪክ ሠሪነትን በጀማሪነት የሚታደል አንዱ ጀማሪ ብቻ ነው፡፡ ይህን ዕፁብ ድንቅ የሆነውን ዕድል የሚቀናጀው የመግባባትን ጥሪ በእውነት ሲቀበል ነው፡፡

በሌላ በኩል መንግሥት የመግባባትን ሰላማዊ ጥሪ ለሁሉም ቢያቀርብና ተቃዋሚዎች ለሰላሙ ጉዞ ሥፍራና ቦታ ካልሰጡ፣ ጉዳያቸው ስለኢትዮጵያ ሳይሆን መንግሥትን አውርዶ ራስን ዙፋኑ ላይ የማስቀመጥ ሩጫ መሆኑ ይታወቅባቸዋል፡፡ ተሳክቶላቸው እንኳን መንግሥት ቢለቅ፣ መግባባትን ንቆ በዘራፍ ቤተ መንግሥት የደረሰ አማራጭ ኃይል ሁሉ አንድነትን ፈጥሮ ለመጓዝ ያስቸግረዋል፡፡ ባሳለፍነው ታሪክም ያየነው እንደማይቻል ነው፡፡ በመግባባት የዛሬውን ልዩነት ዛሬ መፍታት እንቢ ብሎ ለይደር ያስቀመጠ፣ ያኔ ሥልጣኑ ተይዞ ልቡ ከየት ይመጣል? ያው አንዱ እንደተለመደው ደግሞ ሥልጣኑን ይይዝና ‹‹ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም›› እንዲሉ ለኢትዮጵያ ጠብ የሚል ምንም ነገር ላይፈጠር ይችላል፡፡ እንዲያውም ‘ከድጡ ወደ ማጡ’ እንዲባል የባሰ ቢመጣ ምን የሚያስገርም ነገር አለ?

ሦስተኛው የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳ

ሁለቱም ወገን ሽምግልናን ዓይን ላፈር ብለው በዘራፍ ጎዳና መንገድ

ለዚህ ምንም ማብራሪያ መስጠት አያስፈልገውም፡፡ ሁሌም ለዘመናት ያየነው ታሪካችን ነው፡፡ ለውጭ ጠላት ያሳየነው ‹‹እውነተኛ ጀግንነት›› ብዬ ስጠራ፣ ለእርስ በርስ ባለብን ግጭት አፈታት ላይ ያሳየነው ዘራፍነት ‹‹የክስረት ጀግንነት›› ብዬ እፈርጃለሁ፡፡ ምክንያቱም በውጭ ጠላት ላይ ባሳየነው ዘራፍነት ኢትዮጵያ አሸንፋለችና እውነተኛ ጀግንነት ነው፡፡ በሌላ በኩል እርስ በርስ ባለን ግጭት ላይ ያሳየነው ዘራፍነት ኢትዮጵያ ከስራለችና የክስረት ጀግንነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ በምን ከሰረች ቢባል፣ ዴሞክራሲና እኩልነት ለሕዝቡ ያላስገኘ ድርጊት ስለነበረ ነው፡፡ ለዚህም ነው እርስ በርስ ባለው የውስጥ ችግር ኢትዮጵያ እውነተኛ ጀግንነትን ለማየት እስካሁን አልታደለችም ብሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ የሚቻለው፡፡

አራተኛው የኢትዮጵያ መውጫ ቀዳዳ

ሁለቱም ወገን ሽምግልና ቢፈልጉስ?

ጉዳዩ በእውነት ስለኢትዮጵያ እንደሆነ ቁልጭ ብሎ ይታያል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ መሪዎች ከራሳቸው የሥልጣን ጥማት ይልቅ የሕዝቡን የልብ ትርታ አዳመጡ ይባላል፡፡ ቁምነገሩ መንግሥትን በሥልጣን ማቆየት ሳይሆን፣ ወይም ደግሞ መንግሥትን ከሥልጣን ማውረድ ሳይሆን፣ የሕዝብ መሻት እንዲሆን ሁለቱም ወገኖች ራሳቸውን ለሰላም መንገድ መስዋዕት አድርገው ሊሰጡ መወሰናቸው ነው፡፡

ሁለቱም ወገኖች በሥልጣን ላይ ያለውም ሆነ፣ ወደ ሥልጣን ልምጣ ባዩ ቁጭ ብለው የሚደራደሩት ስለየራሳቸው የሥልጣን ዕጣና ፈንታ ሳይሆን፣ ስለሕዝብ ስንል ምን እናድርግ? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ነው፡፡ የመደራደሩ ውጤት የሕዝብን የበላይነት ለማረጋገጥ ነው፡፡ ይህ ነው እውነተኛ ጀግንነትን የሚጠይቀው፡፡ ይህ ነው ጥበበኛ የሚያሰኘው፡፡ ይህ መንገድ ነው እስካሁን በእውነተኛ ጀግንነትን የሚጠይቀው፡፡ ይህ ነው ጥበበኛ የሚያሰኘው፡፡ ይህ መንገድ ነው እስካሁን በኢትዮጵያ ረዥም ታሪክ ውስጥ ያልታየው፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው ethioFamily@outlook.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

 

Standard (Image)

‹‹የመንግሥት የዓመቱ አቅጣጫ›› ከተሃድሶው አንፃር

$
0
0

  በፀሐዬ መንበር

የመስከረም 2009 ዓ.ም. የመጨረሻዋ ሰኞ የፌዴራሉ መንግሥት የሕዝብ ተወካዮችና ፌዴሬሸን ምክር ቤቶች ስብሰባ በጋራ የተከፈተበት ዕለት ነው፡፡ በዚሁ ቀንም የዓመቱ የትኩረት አቅጣጫ በኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ከአንድ ሰዓት በላይ ይፈጀ ንግግር ተንፀባርቋል፡፡ መንግሥት (ሕግ አውጭው፣ ሕግ ተርጓሚውና አስፈጻሚው) ከዚህ መነሻ ተነስተው የራሳቸውን ዝርዝር ዕቅድና ተግባሮች በማውጣት ወደ ሥራ እንደሚገቡም ይጠበቃል፡፡

በዚህ ጸሐፊ እምነት ግን በንግግሩ የቀረቡ ዕቅዶች አሁን ካለው ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር የሚገጥማቸው ፈተና አለ፡፡ በተለይ ገዥው ፓርቲ ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ብሎ ከጀመረው ሥራ አኳያም ሽግግራዊ ተሃድሶ ማስመዝገብ ካልቻለ፣ ንግግሩ መና ላለመቅረቱ ዋስትና የለም በሚል ለመሞገት እወዳለሁ፡፡ በዚሁ አቅጣጫ ወይም በሌላ ዕይታ የሚመለከተው ካለም ልንወያይበት እንችላለን፡፡ የፕሬዚዳንቱን ንግግር ዋና ዋና ትኩረቶች አንድ በአንድ በመምዘዝ በራሴ አመንክዮ ለመሞገት እሞክራለሁ፡፡

ወጣቶችን ከነውጥ ወደ ለውጥ ለማውጣት እንዴት?

ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት በሚያወጣው መረጃ መሠረት ከ65 ሚሊዮን በላይ ታዳጊዎችና ወጣቶች በአገሪቱ ይኖራሉ፡፡ ከወጣትነት ዕድሜ በታች ያሉ ሕፃናትን ጨምሮም እስከ 27 ሚሊዮን ዜጎችም ከመዋዕለ ሕፃናት እስከ ድኅረ ምረቃ ትምህርት ተሰማርተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ ባለሥልጣን የቅርብ ጊዜ መረጃ መሠረትም በአገሪቱ ከድህነት ወለል በታች ከሆኑ ከ22 ሚሊዮን በላይ ዜጎች መሀል 17 ሚሊዮን የሚደርሱ ሥራ አጥ ወጣቶች እንዳሉ ይታወቃሉ፡፡

ይህ ከፍተኛ መጠን ያለው ወጣት ሥራ አጥ ሆኖ የሚገኝበት የገጠሩ ክፍል መሆኑ ደግሞ ገጽታውን ሌላ መልክ ያስይዘዋል፡፡ የአርሶ/አርብቶ አደሩ ልጆች በገጠር መሬት የላቸውም፡፡ የሚቀጠሩበትም ሆነ የሚሰማሩበት በቂ የሥራ ዕድልም የላቸውም፡፡ በቅርቡ በተካሄደው የአፍሪካ ኅብረት መደበኛ ስበሰባ ላይ ‹‹ወጣቱ ኃይል እንደ ማዕበል እየመጣ ያለ የአኅጉሩ ፈተና›› የሚል አጀንዳ ተነስቶ የተመከረበት ለኢትዮጵያ ይሠራል፡፡

ይህንን ማዕበል ቀድሞ የተረዳው የኢትዮጵያ መንግሥት ‹‹ወጣት ተኮር ፓኬጆችን›› በመንደፍ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ማድረጉ ይታወቃል፡፡ የተባለለትን ያህል ውጤታማ ባይሆንም ጥቃቅንና አነስተኛ ልማት በተባለው መርሐ ግብር በተለይ በአንዳንድ ክልሎች (አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋና ትግራይ) የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ትንሽ አይደሉም፡፡ በሌላ አካባቢ ጥረቱ ቢኖርም ያሳተፋቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ የተመናመኑና በአስፈጻሚው የውሸት ሪፖርት ሲሰለቅ የከረመ ነው፡፡

በዘንድሮው የፕሬዚዳንቱ ንግግር በዓመቱ ‹‹የወጣች ፈንድ›› የሚባል መሥሪያ ቤት በሁሉም ወረዳዎች ይከፈታል፡፡ ለዚህም የአሥር ቢሊዮን ብር በጀት ተመድቧል ብሏል፡፡ ፈንዱ ምን? እንዴትና የት ይሠራል? የሚለው ገና በዝርዝር ዕቅድ የሚመለስ ነው፡፡ ነግር ግን ፈንዱን አደራጅቶ፣ አሠራር ዘርግቶ፣ ሀብት አደላድሎ ወደ ተግባር መግባት በራሱ ረዥም ጊዜና ብዙ ሥራ የሚፈልግ ነው፡፡ ለአብነት ያህል የተባለው በጀት በአገሪቱ ለሚገኙ 900 ወረዳዎች በአማካይ 10.5 ሚሊዮን ብር ሊደርስ ነው የሚችለው፡፡ ይህ ገንዘብ ሥርዓት ባለው መንገድ ካልተመራ ደግሞ ከጽሕፈት ቤት ማቋቋሚያ የሚያልፍ አይደለም፡፡

ከዚህ ሁሉ በላይ በወጣቶች ላይ የሚሠራው ሥራ የገጠመው ፈተና የፍትሐዊነት ችግር ነው፡፡ በብዙዎቹ ከተሞችና የገጠር ቀበሌዎች ‹‹ተደራጅተው ውጤታማ ሆኑ›› የተባሉ ወጣቶች ለመንግሥት ፖለቲካ ቅርብ የሆኑ፣ ለባለሥልጣናትና (በታችኛው ደረጃ) ጭምር የዝምድና፣ የብሔርና የሃይማኖት ቅርበት ያላቸው ናቸው፡፡ በበርካታ ወጣቶች ስም ተደራጅተው (በተለይ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ) የማምረቻና የመሸጫ ቦታ በነፃ አግኝተው፣ ብድርና ሥልጠና ተሰጥቷቸው፣ ገበያ ተመቻችቶላቸው በጥቂት ቤተሰቦች የተያዙ ‹‹ማኅበራትን›› ብቻ ማየት በቂ ነው፡፡

ከዚህ ሁሉ በላይ በአዲስ አበባ ከመኪና እጥበት ጀምሮ፣ በግንባታ ምርት፣ በኮንስትራክሽን ዘርፍና በደረቅ ምግብ ምርት መሰክ የተሰማሩ ወጣቶች ተወላጆች ሳይሆኑ ከሌላ አካባቢ መጥተው የተመቻቸላቸው ናቸው፡፡ ሌላው ይቅርና ባለፈው ዓመት የጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፍ ያለበትን ደረጃ የሚመረምርና ቆጠራ የሚያካሂድ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ያገኘው ውጤት እጅግ የሚያሳፍርና የሚያስደነግጥ ነበር፡፡ ታዲያ ይህን የተዝረከረከና ፖለቲካዊ ጩኸቱ የበዛ ሥልት ወደምን ቀየሮ ይሆን ወጣቱን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚቻለው? የሚለው ጥያቄ መመለስ አለበት፡፡

ሌላው የፕሬዚዳንቱ ንግግር ስለወጣቶች ተጠቃሚነት ያወሳው ጉዳይ በሜካናይዝድ እርሻና በመካከለኛ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ወጣቶችን የማሰማራቱ ሥራ ነው፡፡ በእርግጥ ይህ ዕቅድ በፍትሐዊነትና በግልጽነት ከተሠራበት የነቻይና፣ ኮሪያና ጃፓንም መንገድ ነው፡፡ እዚህም ላይ ያለው ፈተና ግን ሀብቱ (Resource) ያለበት ቦታና ሥራ አጡና አማራጩ ኃይል በብዛት የሚገኝበት ክልል የተጣጣመ አለመሆኑ ነው፡፡ ይህን አቀራርቦ ለላቀ ውጤት ለመብቃት ደግሞ ቋንቋና ብሔር ተኮሩ ፌዴራሊዝም ዜጎችን ከአንዱ ክልል ወደ ሌላው ክልል ከመሄድ ይልቅ በረሃ ቆርጠው፣ ባህር ተሻግረው ቢሰደዱ እንዲመርጡ አድርጓቸዋል፡፡ ሁሉም ከፈለሰ ወደ ዋና ከተማዋ ብቻ ሆኗል፡፡ ይህ ከባድና አደገኛ ዝንባሌ በምን ይገታል?

በመንግሥት ሜጋ ፕሮጀክቶች በግል ባለሀብቶች እየተፈጠሩ ያሉ የሥራ ዕድሎች ተስፋ ሰጪ ናቸው፡፡ አሁን ከተደቀነው ልማትን ዋስትና የሚያሳጣ የሰላምና የመረጋጋት ጉዳይ ገና ብዙ ሥራ የሚፈልግ ነው፡፡ ስለሆነም መንግሥት አሁን በቀላሉ ወደ ‹‹ነውጥ›› እና ሁከት ወይም የሥርዓት ለውጥን ወደ ማማተር የገባውን ወጣት ኃይል ለመያዝ የሚጠብቀው ፈተና ከባድና ውስብስብ መሆኑ ሊታመንበት ይገባል፡፡

የዴሞክራሲ ምኅዳሩን ለማስፋት ቁርጠኝነት አለ?

      አሁን ያለውን የኢትዮጵያ መንግሥት ‹‹ዴሞክራሲያዊ አይደለም›› የሚሉ ወገኖች ሥር ነቀል ለውጥ ካልመጣ በስተቀር ጥገናዊ ለውጥ ሊቀይረው አይችልም ይላሉ፡፡ ሥርዓቱ በተለይ ካወጣው ሕገ መንግሥት ጋር የሚጋጩ የተለያዩ ሕግጋትን

(የፀረ ሽብር ሕግ፣ የመረጃና መገናኛ ብዙኃን አዋጅ፣ የሲቪክ ማኅበራት ማቋቋሚያ አዋጅና የፖለቲካ ፓርቲዎች ማቋቋሚያ አዋጅ) ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ ማውጣቱ ክፉኛ ጎድቶታል የሚሉም አሉ፡፡

ባለፉት አሥር ዓመታት በአገሪቱ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ መጎዳቱም ሆነ የፖለቲካ ምኅዳር መጥበቡ በግልጽ ታይቷል፡፡ ምንም እንኳን ችግሩ በተለያዩ ወገኖች ሲነሳ መንግሥት ባይቀበለውም አሁን ግን በየአካባቢው ለተነሳው ቀውስና ሁከት ‹‹የሰላም በር መጥበቡ ያመጣው ጣጣ ነው›› የሚለው አመክንዮ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ የፕሬዚዳንቱ ንግግርም ይህንኑ ያሳያል፡፡

ያም ሆኖ አሁንም የተነገረው ተስፋ ምን ያህል በመስኩ ሽግግራዊ ለውጥ ለማምጣት እንደሚያስችል አልታወቀም፡፡ በቀዳሚነት የተጠቀሰው ‹‹የምርጫ ሕጉን የማሻሻል›› ጉዳይ ነው፡፡ ያውም ከሦስት ዓመታት በኋላ በሚካሄደው ምርጫ ላይ፡፡ ነገር ግን በምን ያህል መጠን ይሻሻል? የምርጫ ቦርድ ገለልተኝነት ወሳኝ ጥያቄ እንዴት ይፈታል? የዜጎች የመደራጀትና ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት፣ ፖለቲከኞች በሁሉም አካባቢ ያለሥጋት የመንቀሳቀስ ነገር. . . እንዴት ይሆናል? ብሎ በአንክሮ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡

ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ወሳኝ ድርሻ ያለው የፕሬስ ነፃነትና የማኅበራዊ ድረ ገጽ ነፃነትና በሥርዓት የመመራት ጉዳይም በጥልቀት መታየት አለበት፡፡ በተለይ መንግሥት በሞኖፖል የያዘው የቴሌቪዥን ጣቢያ ባለቤትነት፣ የዴሞክራሲ ውይይትን የሚፈሩት የአገሪቱ የኤፍኤፍ ሬዲዮ ጣቢያዎች መነሾነት፣ ጭልጭል የሚለው የግል ፕሬሱ በሥርዓትና ማኅበራዊ ኃላፊነት ቅኝት የዴሞክራሲ ባህሉን ለመገንባት ካላገዙ ንግግሩ ዋጋ አይኖረውም፡፡

ከፕሬዚዳንቱ ንግግር አንፃር ተስፋ የተጣለበት የዜጎች አማራጭ ሐሳብን የማዳመጥ ተግባር ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ መንግሥት ‹‹ብዝኃነት›› ሲነሳ የሚናገረው ስለብሔር፣ ሃይማኖትና ፆታ ብዝኃነቶች ብቻ ነበር፡፡ ትልቁ የልዩነት ምንጭ ግን የፖለቲካ አመለካከት ጉዳይ ነው፡፡ ይህን እውነት እንደሌለ ቆጥሮ ሁሉንም ‹‹በአብዮታዊ ዴሞክራሲ›› ለማጥመቅ መቋመጥ ያለጥርጥር የሚጋብዘው ውድቀትን ብቻ ነበር፡፡

መንግሥት ይህን ችግር ዘግይቶም ቢሆን በመገንዘብ የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከቶች የሚደመጡባቸው ምክር ቤቶችና መንግሥታዊ ፎረሞች ይፈጠራሉ ብሏል፡፡ በእውነት መተግበር ከተቻለ! ለዚህ ተግባር በርካታ አብነት ያላቸው የአፍሪካም ሆኑ የዓለም አገሮች በወሳኝ አገራዊ አጀንዳዎች ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማኅበራትና ምሁራንን እስኪደክሙ ያወያያሉ፡፡

በዚህ አገር ከላይ የተጠቀሱትን አካላት እንደ ባለድርሻ ቆጥሮ ለማወያየት የሚሞከረው አንድም በምርጫ ወቅት ካልሆነም በቀውስ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ያኔም ቢሆን ‹‹እንዴት እናድርግ? ምን ትመክሩናላችሁ?›› በሚል ሳይሆን፣ ‹‹ይህን አድምጡና ተቀበሉ›› በሚል ከላይ ወደታች በሚለቀቅ አጀንዳ ላይ ለማጥመቅ እንደሆነ ዘንድሮ የመምህራንና የተማሪዎች ‹‹ውይይት›› ጥሩ ማሳያ ነው፡፡

ከእነዚህ ነባራዊ ሀቆች አንፃር በአገሪቱ የዴሞክራሲ ሥርዓትን ለመገንባትና የፖለቲካ ምኅዳሩን ለማስፋት የመንግሥት ቁርጠኝነት ሊኖር ግድ ይላል፡፡ ከትምህርት ቤቶች አካዳሚክ ነፃነት አንስቶ፣ የሲቪል ሰርቪሱን ገለልተኝነት፣ የዴሞክራሲ ተቋማትና ልዩ ልዩ ማኅበራትን ነፃነት የመጀመር ሥራ መታየት አለበት፡፡ ሕዝቡ ‹‹የሰላም በር አልተዘጋም›› ሊል የሚችለው በዚሁ መንገድ ብቻ ነው፡፡

‹‹የዴሞክራሲ አንድነትን እንገነባለን›› በየትኛው ተግባር?

ፕሬዚዳንቱ በንግግራቸው ወቅታዊውን የአገሪቱ አሥጊ ሁኔታ በመዳሰስ በየአካባቢው ዜጎች ከጠባብነትና ‹‹ፀረ ዴሞክራሲያዊ ብሔርተኝነት›› ወጥተው አገራዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት እንገነባለን ብለዋል፡፡ ሐሳቡ መልካምና ለድርድር የማይቀርብ ነው፡፡ ግን እንዴት ሊሳካ ይችላል?  የሚለው ጥያቄ ብዙዎችን ያሳስባል፡፡

ባለፉት 25 ዓመታት በጎሳና በማንነት ላይ ብቻ ያተኮረው ፌዴራላዊ ሥርዓቱ የተለያዩ ብሔረሰቦች እንዲታወቁና መብታቸው እንዲከበር (ቢያንስ በማንነት) አድርጓል፡፡ ግን ያለጥርጥር አንድነትና አገራዊ ብሔርተኝነትን ማምጣት አልቻለም ብል ማጋነን አይመስለኝም፡፡

በዚህ ረገድ መንግሥት የሚጠየቅበት ስለልዩነት ድምቀት ያወራውን ያህል ስለአንድነትና ኅብረት፣ ስለኢትዮጵያዊነት ያልሠራ መሆኑ ነው፡፡ የጋራ ባንዲራ፣ የጋራ የሥራ ቋንቋ፣ በታሪክ አጋጣሚ የጋራ ባህልና ወግ፣ የጋራ ሃይማኖቶች. . . ያሏቸው የአገራችን ሕዝቦች ለመለያየትና ለመገፋፋት ቅርብ ሆነዋል፡፡ በተለይ ደግሞ አዲሱ ትውልድ በመንደርተኝነት እየተነዳ ከዚህ ውጣ፣ ያ የኔ ብቻ ነው. . . የሚል ጎጠኛ አጀንዳ እያራገበ ነው፡፡ ባሳለፍናቸው ወራት በኦሮሚያ፣ በአማራ ክልልና በደቡብ (ዲላና ኮንሶ) እንደታየው የሕዝቦች አብሮ የመኖር ገመድ ክፉኛ ላልቷል፡፡ ዋስትናም ህሊናና የጋራ ማንነት ሳይሆን መሣሪያ መስሏል፡፡

መንግሥት ይህን አደገኛ ችግር ተረድቶ ከሆነ ‹‹የሕዝቦችን ዴሞክራሲያዊ አንድነት እንገነባለን!›› ያለው መልካም ነው፡፡ ይህ ግን ከራሱ ከገዥው ፓርቲ መጀመር እንዳለበት ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ ገዥው ፓርቲ ራሱ ለሁለት አሥርት ተኩል ዓመታት ከብሔር ፓርቲ ወጥቶ ኅብረ ብሔራዊ ድርጅት መሆን አልቻለም፡፡ በእሱ አምሳል የተፈጠሩት የተቃዋሚ ማኅበራትም ቢሆኑ ከመንደር አስተሳሰብ አልወጡም፡፡ ኅብረት በሌለው ፖለቲካ ምን ዓይነት የሕዝብ አንድነት ይጠበቃል ማለት የሚበጀውም ለዚህ ነው፡፡

በርዕሰ ብሔሩ ቃል ‹‹የሥነ ዜጋና የሥነ ምግባር ትምህርትን በስፋት ማስረፅ›› ሲባል አንዱ የዜጎችን ሥነ ምግባር፣ ተነሳሽነትና አገራዊ ስሜት መገንባት እንደሆነ ይታመናል፡፡ ለዚህ ደግሞ የትምህርትና የእምነት ተቋማት፣ እንዲሁም ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎችና መገናኛ ብዙኃንም ኃላፊነት አለባቸው፡፡ በመሠረቱ ጠባብነትና መንደርተኝነት የኋላ ቀርነት ጥሩ መገለጫ ነው፡፡ ዓለም አንድ መንደር ሆኖ ሳለ እኛም ዜጎች ጭምር ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ ‹‹በለው! አሳደው!›› ማለትን ካላራገፍን የትም ልንደርስ አንችልም፡፡

ከዚህ አንፃር በአገሪቱ አንዳች ዓይነት አብዮታዊ ኅብረ ብሔራዊነት እስኪፈጠር ሳንጠብቅ የኅብረትና የአንድነት መንገድን መጀመር አለብን፡፡ መንግሥት ‹‹አንድ ፖለቲካና የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ፈጥረናል›› የሚለውን ምዕተ ዓመት የሚወስድ መላምት ትተን፣ ከተዛባው የታሪክ መጓተትና መፈላቀቅ ወጥተን የምንከባበርና የምንተማመን የአንዲት ኢትዮጵያ ሕዝቦች መሆናችን በገቢር ማሳየት አለብን፡፡ መንግሥት ሆይ እንደ ንግግርና ዕቅድ ይኼም ተግባር ቀላል አይደለምና አስብበት ማለት ይሻላል፡፡

መንግሥታዊ ሥርዓቱን በማስተካከል መልካም አስተዳደር ማስፈን

ከሞላ ጎደል አንድ ዓመት ገደማ ያስቆጠረው በተለያየ መንገድ የተነሳ ሕዝብ ጥያቄ መነሻው የመልካም አስተዳደር ዕጦት ነው፡፡ መንግሥትም ከቀደሙት ዓመታት ጀምሮ ኪራይ ሰብሳቢነትና ሙስና፣ እንዲሁም የመልካም አስተዳደር ዕጦት ሕዝቡን እንዳማረረ ሲገልጽ ቆይቷል፡፡ ይህን ለመቅረፍ እንደሚሠራ በድርጅቱ ጉባዔና በጥናት ጭምር ተናግሮ በተግባር ግን ለውጥ ሲጀምር አልታይ አለ እንጂ፡፡

እንደ ኦሮሚያ ባሉት ክልሎች ከመሬት ካሳ፣ ከይዞታ ማስተላለፍ፣ ከሥራ ዕድል ፈጠራ ጋር በተያያዘ፣ በሌሎች ክልሎችም ከፍትሐዊ የሥራ ዕድል ፈጠራና ከአገልግሎት ጋር በተያያዘ ብዙ ቅሬታ ተነሳ፡፡ በአዲስ አበባ አብዛኛው አገልግሎት በጉቦና በእጅ መንሻ ብቻ የሚፈጸም ሆነ፡፡ ለዚህ ደግሞ በየደረጃው ያለው ተሿሚና ተቀጣሪ ግልጽነትና ተጠያቂነትን እየሸሸ በሥልጣን የመጠቀምና ሀብት የማካበት ልድም ውስጥ ተነከረ፡፡ ይህ ለአሁኑ ተሃድሶም ዋነኛ ማጠንጠኛ ሆኗል፡፡

በሙስና ደረጃም በየጉልቱ ችርቸራ ከምትገባዋና ባጃጅና ታክሲ ነድቶ ከሚውለው ጀምሮ እስከ ቱባው ባለሀብት ደረጃ የዕለት ቋንቋ ሆነ፡፡ በእርግጥ ለሙስና መባባስ ራሱ ማኅበረሰቡ የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት ተሸካሚ መሆኑ የፈጠረው ጫና ቢኖርም፣ መንግሥትም ችግሩን ለመታገል የፖለቲካ ቁርጠኝነትን አጣ፡፡

በተለይ የመንግሥትን ሥልጣን የያዙ ቱባ ባለሥልጣናትና ሕገወጥ ደላሎች  (ኪራይ ሰብሳቢ ባለሀብቶች) በፈጠሩት መስተጋብር ንፋስ አመጣሽ ሀብታሞች በየቦታው ተቀፈቀፉ፡፡ ግብር ከመደበቅ፣ የጉምሩክና የቀረጥ ነፃ አሻጥር (በብረታ ብረት ማስገባት ብቻ 112 ሕገወጦች ተከሰው ለዓመታት የሕዝብ ጥቅም ማጥፋታቸው እየታወቀ ዕርምጃ መወሰድ እንዳልተቻለ ይነገራል) ጥቂቶች ከልክ በላይ በለፀጉ፡፡ ይህን ሕገወጥ ውድድር መቋቋም ያልቻሉ ነባር ባለሀብቶችም ደቀቁ ወይም ተሰደዱ፡፡

የኦሮሞን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን መላውን የአገሪቱን ሕዝቦች ‹‹ለምን?›› እያስባለ ያለው የአዲስ አበባና የፊንፊኔ ልዩ ዞን ያለው የአገር ይዞታም በሙስና ተቸበቸበ፡፡  በየከተሞች የተመደቡ ‹‹ከንቲባዎች›› በሺዎች የሚቆጠሩ ካርታዎችን ከአሻጥረኞች ጋር ሆነው ሸጡ፡፡ ለዘመድና ወዳጆቻቸው አስተላለፉ፡፡ አርሶ አደሩም ላይቀርልኝ እያለ በጥቂት ገንዘብ እየሸጠ (ካሳ እየተቀበለ) ተፈናቀለ፡፡ ጊዜው ሲደርስም ድርጊቱ ተጠራቅሞ አገር የሚያፈርስ የሕዝብ ቁጣን ቀሰቀሰ፡፡

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከትልልቅ ሀብቶች ጀርባ ስማቸው የሚነሳ ባለሥልጣናትና ሸሪኮቻቸው አሉ፡፡ በሥርዓቱም ስም ነግደው ባለሕንፃና ድርጅት የሆኑትም ትንሽ አይደሉም፡፡ አንዳንዱ የደኅንነትና የፀጥታ አካልም የግል ጥቅሙን እያስቀደመ ከብሯል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን አብሮ ሲሰርቅ የነበረው ወይም በፍርኃትና በአድርባይነት ድምፁን አጥፍቶ የከረመው ቀሪው ደግሞ ‹‹የእዕገሌ ሀብት›› እያለ ጣቱን እየቀሰረ ነው፡፡

እንግዲህ ይህ የገዘፈ ፈተና ባለበት ወቅት ነው የከረመ ቆሻሻ በረት ለመጥረግ ‹‹ሙስናን እታገላለሁ›› የሚል የመንግሥት ጩኸት የሚሰማው፡፡ ፈተናው ግን ‹‹ማን ማንን?›› ለመታገል ይችላል ሲባል ነው፡፡ በእርግጥ መንግሥት በእውነት የሕዝብን ድጋፍና አጋርነት ከፈለገ ግን የሚከፈለውን መስዕዋትነት ሁሉ ከፍሎ ዋና ዘራፊዎችን ማጋለጥ፣ ከዚህም በላይ የመልካም አስተዳደር መሠረት ለመገንባት የዴሞክራሲና የፍትሕ ተቋማትን ነፃነትና ጥንካሬ መፍቀድ ያስፈልጋል፡፡ የሚዲያ ነፃነትም መጠናከር አለበት፡፡

አሁን ኢሕአዴግ ሥልጣን የግል ጥቅምን ማባረሪያ አይደለም እንደሚለው ሁሉ፣ በተግባርም የማይነቃነቅ መርህ ያስፈልጋል፡፡ በገዥው ፓርቲ ውስጥ በመንደር ልጅነት፣ በኔትወርክና በታዛቢነት መሿሿም ሊቆም ግድ ይለዋል፡፡ ብቃት፣ ሥነ ምግባርና አገር ወዳድነት ቀዳሚ የሕዝብ ኃላፊነት መመልመያ መሆንም አለባቸው፡፡

ይህ መሆን ሲጀምር ደግሞ ሲቪል ሰርቪሱና ሕዝቡን በቀጥታ የሚያገለግለው ኃይልም የባለቤትነት ስሜት ይኖረዋል፡፡ ‹‹እነ እገሌ እየበሉ. . .›› እያለ ከመቆዘም ወጥቶም ለህሊናውና ለሕዝቡ መሥራትን ያስቀድማል፡፡ መርህ ሲከበርም ተደፋፍሮ ሌብነትን ያጋልጣል፡፡ ኪራይ ሰብሳቢነትንም ‹‹እሺ!›› ብሎ ከመቀበል ይላቀቃል፡፡

በዚሁ እሳቤ መንግሥት ‹‹መዋቅሩን ላስተካክል›› ሲል ከመዲናዋ መጀመር አለበት፡፡ በሺዎች የሚቆጠር ሕገወጥ ገንቢ መሬት ወሮ መብራትና ውኃ እንዲገባለት እየተደረገ ለዓመታት ከተበዘበዘ በኋላ ‹‹ይፈረስ›› እያለ ሕዝብ የሚያስለቅስ ቡድን መራገፍ አለበት፡፡ በትልልቅ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክቶችና የመንገድ ሥራዎች ያለ ጨረታና በድርድር በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ሲፈቅድ የከረመ ተጠርጣሪ ሁሉ ሊፈተሽ ግድ ይለዋል፡፡ እንደ ወርቅ የተወደደውን የአገሪቱ መሬት የቸበቸበና ያስቸበቸበም እንዲሁ. . .

በአጠቃላይ የዶ/ር ሙላቱ ተሾመን የመራሔ መንግሥት ንግግር በተስፋ ማየት ጥሩ ሆኖ ከፊት ያለው ገደል ሲታይ ግን ትግበራው መክበዱ አይቀሬ ነው፡፡ ስለሆነም መንግሥትም ሆነ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነት ተነስተው ለለውጥ መነቃነቅ አለባቸው፡፡ ካልሆነ ግን ንግግሩን ወደ ተግባር ለመውሰድ የሚገጥመው ተቃርኖ ከውቅያኖስም የሰፋ ነው ባይ ነኝ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው menbertt@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡  
 

Standard (Image)

ሕግ የፍትሕ ማስገኛ መሣሪያ እንጂ የኢፍትሐዊ ዓላማ ማስፈጸሚያሊሆን አይገባም!!

$
0
0

በሞላ ዘገዬ፣ የሕግ አማካሪና ጠበቃ

ግልጽ አቤቱታ (ጥቆማ)

  1. ለክቡር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር

(ከአገር እንዲወጡ ተደርገው የነበሩ ኤርትራውያን ንብረት አስመላሽ ዓብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ) 

  1. ለክቡር የገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ሚኒስትር

(የዓብይ ኮሚቴ አባል)

  1. ለክቡር የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር

(የዓብይ ኮሚቴ አባል)

  1. ለክቡር የፌዴራል ፖሊስ ዋና ዳይሬክተር

(የዓብይ ኮሚቴ አባል)

የዚህ ግልጽ ጥቆማ (አቤቱታ) ዓላማ

  • ዳኞች ሕግን ተከትለው ካልሠሩና ፍትሕን ካዛቡ ከአደባባይ ትችትና ወቀሳ እንደማይድኑ ለማሳወቅ፣
  • የሕግ የበላይነትን በግንባር ቀደምትነት ማክበር የሚገባቸው የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና የሥራ ኃላፊዎች አዋጅን ደንብንና መመርያን ተከትለው ካልሠሩና በዜጎች ላይ በደል ከፈጸሙ በአደባባይ እንደሚጋለጡና ከተጠያቂነት እንደማይድኑ ለመግለጽ፣
  • ለፍትሕ ሥራ መሳለጥ ከፍተኛ ሚና ያላቸውና በሙያው ሥነ ምግባር ደንብ ሊገዙ የሚገባቸው ጠበቆች ሙያቸውን ለሕገወጥ ዓላማ መሣሪያ ካደረጉ ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ ለማሳየትና በዚህ ግልጽ አቤቱታ (ጥቆማ) መነሻነት የተፈጸመው ግፍና በደል ከአገር እንዲወጡ ተደርገው የነበሩ ኤርትራውያን ንብረት አስመላሽ ዓብይ ኮሚቴና ጉዳዩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በሚመለከታቸው የፍትሕና የሕግ የበላይነት ተቆርቋሪ ወገኖች እንዲታረም ጥቆማ ለመስጠት ነው፡፡

የጉዳዩ አመጣጥ በአጭሩ

ደንበኛዬ አቶ ብሩክ በቀለ ከፍተኛው የአክሲዮን ድርሻ ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑበት “ባይሴሌክስ ኢትዮጵያ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር” በሚል ስያሜ የሚታወቅ ድርጅት አላቸው፡፡ ይህ ድርጅት ቀደም ሲል አቶ ገብረየሱስ ገብረ ልዑል በሚባሉ ግለሰብ ባለቤትነትና ዋና ሥራ አስኪያጅነት ሲመራ ቆይቶ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ምክንያት ግለሰቡ ከአገር እንዲወጡ ሲደረግና በድርጅቱ የነበራቸውን አክሲዮን “ለእነ አቶ ብሩክ በቀለ” ሲሸጡ በሕጋዊ መንገድ የተላለፈላቸው ነው፡፡ የአክሲዮን ሽያጩ የተከናወነው ኬንያ ናይሮቢ ስለነበር በናይሮቢ የኢትዮጵያ ኤምባሲና በኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተረጋግጦ በሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ ጽሕፈት ቤት ተመዝግቦና ተረጋግጦ፣ በንግድ ቢሮ ትዕዛዝ በጋዜጣ ታውጆና በቢሮው ዋና መዝገብ የተመዘገበ በመሆኑ የአክሲዮን ሽያጩና ዝውውሩ በሕጉ መሠረት የተከናወነ ነው፡፡

ድርጅቱ በዚህ ዓይነት ባለቤትነቱ ለእነ አቶ ብሩክ ተላልፎ ከአሥራ ሦስት ዓመታት በላይ ሲሠሩበት ከፍተኛ ሀብትና ንብረት አፍሰውበታል፡፡ ከዚህ ሁሉ በኋላ የቀድሞው የድርጅቱ ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ግለሰብ ከዓመታት በፊት በሕጋዊ መንገድ ባስተላለፉት ንብረት ላይ አንዳችም የንብረት መብት የሌላቸው መሆኑ አጠያያቂ ባይሆንም፣ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው “ድርጅቴን አስረክበኝ” በማለት እነአቶ ብሩክን ጠየቁ፡፡ አቶ ብሩክም ድርጅቱን በሕጋዊ መንገድ እንዳስተላለፉላቸው ገልጸው ጥያቄያቸውን በቀና መንፈስ በማየት አቶ ገብረየሱስ በባንክ የተቀመጠላቸውን የአክሲዮን ሽያጭ ገንዘብ ጨምሮ አለኝ የሚሉት መብት ካለ በመግባባትና በድርድር እንዲጨርሱ ጠየቁ፡፡ በመሀሉም አቶ ገብረየሱስ ይህን የእርቅ፣ የድርድርና የመግባባት ጥያቄ አሻፈረኝ ብለው በከፍተኛው ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 125295 አቶ ብሩክ ንብረቶቹን ሊያስረክቡኝ ይገባል በሚል የባለቤትነት ክስ መሠረቱ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ እኚሁ ግለሰብ በጉዳዩ በፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደበት መሆኑን ደብቀው በፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደባቸው ያሉት ተመሳሳይ ንብረቶች እንዲመለሱላቸው በኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰብሳቢነት ለሚመራው ለኤርትራውያን ንብረት አስመላሽ ንዑስ ኮሚቴ አቤቱታ አቀረቡ፡፡

ንዑስ ኮሚቴውም፡- የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባወጣው የአፈጻጸም መመርያ አንቀጽ 6(2) መሠረት፣

ሀ.   ጉዳዩ በፍርድ ቤት የተያዘ መሆኑንና አለመሆኑን ሳያጣራ፣  

ለ. ንብረቱ በሽያጭ ለሦስተኛ ወገን የተላለፈ መሆን አለመሆኑን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የንግድ ሚኒስቴርና የሰነዶች ማረጋገጫ ጽሕፈት ቤት ጠይቆ ሳያጣራ፣

ሐ.  ንብረቱ በሕግ አግባብ የተላለፈላቸውን እነ አቶ ብሩክ በቀለን አስቀርቦ ሳይጠይቅ ፈጽሞ ኢፍትሐዊ በሆነ ሕገወጥ መንገድ በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/89/05 በፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደበት ያለውን ንብረት ከእነ አቶ ብሩክ በቀለ ላይ ነጥቆ አቶ ገብረየሱስ ገብረልዑል እንዲያስተዳድሩት ወሰነ፡፡ ይህንኑ ሕገወጥ ውሳኔ ለማስፈጸምም በቀን 15/6/2005 ዓ.ም በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/89/05 ንብረቱ ለሚገኝበት ወረዳ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ በተጨማሪም “በገብረየሱስ ገብረልዑል አስመጪ ኩባንያ” ስም በካርታ ቁጥር 29758 ተመዝግቦ የነበረው ይዞታ በግለሰቡ ስም እንዲዛወር ለቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር የይዞታ አስተዳደር የሽግግር ጊዜ አገልግሎት በቁጥር 3-1/129/317/05 በተጻፈ ደብዳቤ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ እዚህ ላይ እጅግ የሚገርመው ነገር በቦሌ ክ/ከተማ ወረዳ 02 የካርታ ቁጥር 29758 ቀደም ሲል የተሰጠው ኤርትራ ለተመዘገበ ለገብረየሱስ ገብረ ልዑል ኩባንያ ሆኖ ሳለና ይህም የስም ለውጥ ጥያቄ ሲቀርብ የኩባንያው የንግድ ምዝገባና ፈቃድ የተሰረዘ ስለመሆኑ ለንዑስ ኮሚቴው የቀረበ ማስረጃ ሳይኖር፣ በኩባንያው ስም ተመዝግቦ የሚኘው ካርታ በግለሰቡ በአቶ ገብረየሱስ ገብረልዑል ስም እንዲዛወር መታዘዙና በዚሁ ሕገወጥ ትዕዛዝ መሠረት አዲስ የካርታ ቁጥር 9/16/1/7/29758/22062/22823/02 በአቶ ገብረየሱስ ስም የተሰጠ መሆኑ ነው፡፡

አቶ ብሩክም በተለይ ንዑስ ኮሚቴው በሕገ መንግሥቱ የተዘረጋላቸውን የመሰማት መብት በመግፈፍ እሳቸውን ሳይጠራና ሳይሰሙ ውሳኔውን መስጠቱን፣ በአገሪቱ የተዘረጋውን ሕግና ሥርዓት ጠብቀው የባይሴሌክስ ኢትየጵያ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር አክሲዮኖች በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ በተደረጉ ሕጋዊ ውሎች የገዙና ይኼውም በንግድ መዝገብ የተመዘገበ መሆኑን፣ በእነዚሁ ተመሳሳይ ንብረቶች ላይ አቶ ገብረየስ ባቀረቡት ክስ መሠረት በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክርክር ላይ መሆናቸውን ገልጸው በመመርያው መሠረት ለተዋቀረውና በክቡር የኢፌድሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ለሚመራው ዓብይ ኮሚቴ ያመለከቱ ቢሆንም፣ የንዑስ ኮሚቴው ውሳኔ የፀና መሆኑን በጽሕፈት ቤታቸው በኩል በቃል ተነገራቸው፡፡ ይሁን እንጂ የንዑስ ኮሚቴው አሠራር ግልጽነት ስለሚጎድለው ጉዳዩ ለክቡር ሚኒስትሩና ለዓብይ ኮሚቴው ስለመቅረቡ የሚያውቁት ነገር የለም፡፡

በዚህ ረገድ በንዑስ ኮሚቴው የተሰጠው ውሳኔ ራሱ የተቋቋመበትን መመርያ ለማስፈጸም የወጣውን መመርያ አንቀጽ 6(2) በግልጽ የተጻረረ በመሆኑ አቶ ብሩክ ወደ ፍርድ ቤት በመሄድ የተወሰዱት ንብረቶች ይመለሱላቸው ዘንድ ውሳኔውን በሰጠው ንዑስ ኮሚቴ ላይ የሁከት ይወገድልኝ ክስ መሠረቱ፡፡ አቶ ገብረየስም በዚሁ መዝገብ በሌሉበት የሚሰጥ ውሳኔ መብታቸውን ሊነካ የሚችል መሆኑን በመግለጽ በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 41 መሠረት በክርክሩ ውስጥ ጣልቃ ለመግባት እንዲፈቀድላቸው አቤቱታ ያቀረቡ ቢሆንም፣ ያቀረቡት ምክንያት አጥጋቢ ስላልነበር ፍርድ ቤቱ አቤቱታውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡ በዚሁ ብይን ቅር በመሰኘት እስከ ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ይግባኝ ያሉ ቢሆንም በየደረጃው የሚገኙት ፍርድ ቤቶች ይግባኙን ባለመቀበል የሥር ፍርድ ቤቱን ብይን አፅንተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ጉዳዩን እያየ የነበረው የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የኮሚቴው ውሳኔ የኤርትራውያንን ንብረት ለማስመለስ የወጣውን መመርያ ማስፈጸሚያ መመርያ አንቀጽ 6 (2)ን የጣሰ በመሆኑ ውሳኔው ተሽሮ ንብረቶቹን እነ አቶ ገብረየሱስ በተረከቡበት አኳኋን ለእነ አቶ ብሩክ እንዲያስረክቡ በሚል ፍርድ ሰጠ፡፡ በወቅቱ ንዑስ ኮሚቴውን በመወከል ተከሳሽ የነበረውም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውሳኔውን በፀጋ የተቀበለው ሲሆን ያቀረበውም ይግባኝ አልነበረም፡፡ እነ አቶ ብሩክም በፍርድ ቤቱ ውሳኔ መሠረት ንዑስ ኮሚቴውን ንብረታቸውን እንዲያስረክባቸው የጠየቁ ቢሆንም ኮሚቴው ከሕግ በላይ ሆኖ እንቢ በማለቱ ውሳኔው እንዲፈጸምላቸው ለፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአፈጻጸም ችሎት አቤቱታ አቀረቡ፡፡ ነገር ግን ይህ የአፈጻጸም ፍርድ ቤት “ውሳኔው ግልጽ አይደለም” በማለት መዝገቡን ስለዘጋባቸው ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኝ አቅርበዋል፡፡ የአፈጻጸም ይግባኙ የቀረበለት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሥር ፍርድ ቤትን ውሳኔ ሽሮ ባይሴሌክስ ኢትዮጵያ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር በይዞታው ሥር አድርጎ ሲያስተዳድራቸው የነበሩ ንብረቶች ምን ምን እንደሆኑ አጣርቶ ሀ. በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/89/05 እና

ለ. በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/317/05 በኮሚቴው ውሳኔ አቶ ገብረየሱስ የተረከቧቸውን ንብረቶች ለነአቶ ብሩክ (ለባይሴሌክስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ) እንዲያስረክብ ለፍርድ አፈጻጸም ዳይሬክቶሬት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡

በዚህ ትዕዛዝ መሠረትም አንደኛውን ሕንፃ የተረከቡ ሲሆን፣ በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/89/05 የተወሰደው ሕንፃ ግን በሕገወጡ የኮሚቴው ውሳኔ ከእነ አቶ ብሩክ የተነጠቀ መሆኑ እየታወቀ ለፍርዱ የተሳሳተ ትርጉም በመስጠትና ውሳኔ አላረፈበትም በሚል ሰበብ፣ አቶ ገብረየሱስ የፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 358ን ጠቅሰው የፍርድ አፈጻጸምን እየተመለከተ በነበረው ችሎት ጣልቃ በመግባታቸው በጉዳዩ እስከ ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ክርክር ከተደረገ በኋላ፣ የሰበር ሰሚው ችሎት አቶ ገብረየስ በሕንፃው ላይ በሥር ፍርድ ቤት ክርክር ያልተካሄደበት መሆኑን ገልጸው  ያቀረቡትን ክርክር በመቀበሉ፣ ይኼው ንብረት ለባይሴሌክስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር (ለእነ አቶ ብሩክ) ሳይመለስ ቀርቷል፡፡ ከሕግ አግባብ ውጪ የተሰጣቸው ካርታም በአቶ ገብረየሱስ ስም እንደሆነ ይገኛል፡፡

በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ምክንያት ከአገር እንዲወጡ ተደርገው የነበሩ ኤርትራውያን በኢትዮጵያ ውስጥ ያላቸውን ንብረት ማግኘትና ማልማት እንዲችሉ የወጣውን የሚኒስትሮች ምክር ቤት መመርያ ለማስፈጸም የወጣው የአፈጻጸም መመርያ አንቀጽ 6 (2) መሠረት፣ “በፍርድ ቤት በመታየት ላይ ባሉ ወይም በተሸጡ ንብረቶች (ጉዳዮች) ቅሬታ ሊቀርብ እንደማይችል ይደነግጋል፡፡” በመሆኑም የማኅበሩ አክሲዮኖች በሕጋዊ መንገድ ለእነ አቶ ብሩክ የተላለፉ በመሆናቸው፣ እንዲሁም አቶ ገብረየሱስ ለኮሚቴው አቤቱታ ባቀረቡባቸው ተመሳሳይ ንብረቶች ላይ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደባቸው የነበሩ በመሆኑ ኮሚቴው ንብረቶቹን አቶ ገብረየሱስ እንዲረከቡ ሲል የሰጠው ውሳኔ፣ ከላይ የተመለከተውን የመመርያውን አንቀጽ 6(2) ግልጽ ድንጋጌ የጣሰ ፈጽሞ ሕገወጥ ተግባር በመሆኑ በአገሪቱ የሕግ የበላይነትንና ፍትሕን ከማስፈን አኳያ  ውሳኔው ዛሬም ቢሆን ሊታረም የሚገባው ነው፡፡

እነ አቶ ብሩክ የንዑስ ኮሚቴውን ውሳኔ በመቃወም ለፍርድ ቤት ክስ ሲያቀርቡ ኮሚቴው በተከሳሽነት ቀርቦ የተከራከረና የተፈረደበት ቢሆንም፣ ውሳኔውን በፀጋ የተቀበለ ሲሆን ለበላይ ፍርድ ቤትም ያቀረበው ይግባኝ የለም፡፡ ይህም ፍርዱን እንደተቀበለ የሚያስቆጥረው በመሆኑ ንብረቶቹን ለአቶ ገብረየሱስ ባስረከበበት አኳኋን መልሶ ለነአቶ ብሩክ እንዲያስረክብ አቤቱታ ሲቀርብለት፣ ከሕግ በላይ ሆኖ እንቢተኛ መሆኑ አግባብ አይደለም፡፡ የመጨረሻውን ፍርድ የሰጠው የጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎትም በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት መ.ቁ. 11032 በነበረው ክርክር “በሕንፃው ላይ የቀረበ ክስም ሆነ ክርክር የለም፣ ፍርድም አላረፈበትም” ከማለት ውጪ በጉዳዩ አንኳር ነጥብ ላይ ውሳኔ ያላሳረፈ ከመሆኑ አንፃር ውሳኔው ዓብይ ኮሚቴው፣ ንዑስ ኮሚቴው መመርያውን በመፃረር አስቀድሞ የሰጠውን ሕገወጥ ውሳኔ እንዳያርም የሚከለክለው አይደለም፡፡ ስለዚህ እነ አቶ ብሩክ ሳይጠሩና ሳይሰሙ በሕጋዊ መንገድ በተካሄደ የሽያጭ ውል የተጎናፀፉትን ንብረታቸውን በሕገወጥ መንገድ ተቀምተው እስከዛሬ ድረስ በንብረቱ ቢገለገሉ ኖሮ ሊያገኙት ይገባ የነበረውን በብዙ ሚሊዮን ብር የሚገመት የገንዘብ ጥቅም ተነፍገው በርካታ ዓመታት ለፈጀ ሙግትና ክርክር ተዳርገው፣ እንዲሁም ሕገ መንግሥታዊ የንብረት መብታቸውን ተነፍገው ሊቀጥሉ ስለማይገባ ዓብይ ኮሚቴው ጉዳዩን በመመርመር ሀ. በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/89/05፣ ለ. በደብዳቤ ቁጥር 3-1/129/317/05 የሰጣቸውን ውሳኔዎች በመሻር አቶ ገብረየሱስ በሕገወጥ መንገድ በእጃቸው የገባውንና የካርታ ቁጥሩ 9/16/1/7/29758/22062/22823/02 የሆነውን ንብረት በሽያጭ ለሌላ ሦስተኛ ወገን ለማስተላለፍ እየተሯሯጡ መሆኑን ተረድቶ፣ ንብረቶቹን ለእነ አቶ ገብረየሱስ ላስረከቡት ለቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደርና ንብረቱ ለሚገኝበት ወረዳ 2 ጽሕፈት ቤት ለእነ አቶ ብሩክ መልሰው እንዲያስረክቡ ትዕዛዝ በመስጠት፣ በዚህ ጥቆማና አቤቱታ መነሻነት የንዑስ ኮሚቴውን ጥፋት በማረም የሕግ የባላይነት እንዲያስከብርልንና የፍትሕ ጥማታችንን እንዲያረካልን እንለምናለን፡፡

የእነ አቶ ገብረየሱስ ጠበቆችን ሥነ ምግባር የጎደለው ድርጊት በተመለከተ

አቶ ገብረየሱስ ገብረልዑል በአንድ በኩል ኤርትራዊ ነኝ በማለት ንብረቴ ይመለስ ብለው ለፍርድ ቤት ክስ ማቅረባቸውንና በሌላ በኩል ደግሞ ይህን ደብቀው ለኤርትራውያን ንብረት አስመላሽ ኮሚቴ ተመሳሳይ አቤቱታ ማቅረባቸውን ገልጸናል፡፡ ይህንን ሲያደርጉም ኤርትራዊ ነኝ እያሉ ሲሆን ለአገር ደኅንነት አስጊ ናቸው ተብለው ከአገር ከወጡም በኋላ እዚሁ ተመልሰው መጥተው ኢትዮጵያዊ ነኝ በማለት በ25/11/2004 ዓ.ም በቁጥር ዋ/መ/2000/1/2004 የውክልና ሥልጣን ሰጥተዋል፡፡ ይህም የውክልና ሥልጣን የተሰጠው ወኪልም ለጠበቃቸው ውክልና ሰጥቷል፡፡ ጠበቃውም የአቶ ገብረየሱስን “ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ” የሚል የተጠቀሰበትን የውክልና ሥልጣን ተቀብለው ኤርትራዊ ናቸው እያሉ መከራከሩን ቀጥለውበታል፡፡ በሌላ ሰነድም እንዲሁ ዜግነቴ ኬንያዊ ነው በማለት ውክልና የሰጧቸው ሁለት ጠበቆች “ኤርትራዊ ናቸው” እያሉ በተመሳሳይ ሁኔታ እንደሌላኛው ጠበቃ በክርክሩ ቀጥለዋል፡፡

ከዚህ በላይ ካለው ሁኔታ የምንረዳው እኚህ ሰው ኤርትራዊም፣ ኢትዮጵያዊም፣ ኬንያዊም ሁነው ባለሦስት ዜግነት ናቸው ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ ሊጤን የሚገባው ነገር ኤርትራዊ ከሆኑ እንዴት ኢትዮጵያዊ ነኝ በማለት ውክልና ሰጡ? በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያዊና ኬንያዊ ነኝ ካሉ እንዴት ኤርትራዊ ነኝና ንብረቴ ይመለስ ብለው አመለከቱ? በተጨማሪም በተለይ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብለው ውክልና የሰጧቸው ጠበቃ ይህ በፍፁም ሊደረግ እንደማይችል እያወቁ በዚህ ዓይነት ውክልና እንዴት ግለሰቡ ኤርትራዊ ናቸውና ንብረታቸው ይመለስ እያሉ ክርክሩን ሊያካሂዱ ቻሉ? ምንም እንኳ ዜግነት መለወጥ መብት ነው ተብሎ ቢወሰድም ቅሉ ዜግነታቸውን ከኤርትራዊነት ወደ ኬንያዊነትና ኢትዮጵያዊነት ስለመለወጣቸው በፍርድ ቤት በመሠረቱት ክስም ሆነ ለኤርትራውያን ንብረት አስመላሽ ኮሚቴው ባቀረቡት ማመልከቻ ያያያዙት ማስረጃ ባለመኖሩ፣ ጠበቆቹ ይህንን እያዩና እያወቁ በዚህ ዓይነት ውክልና እንዴት ክርክሩን ሊያካሂዱ ቻሉ?

ከዚህም በላይ ጠበቆቹ በአንድ በኩል በፍርድ ቤት ክስ መሥርተው ጉዳዩ በመታየት ላይ እያለ ዘግይተው ደግሞ የኤርትራውያንን ንብረት ለማስመለስ የወጣውን መመርያ ለማስፈጸም በወጣው መመርያ አንቀጽ 6(2) ድንጋጌ መሠረት አቤቱታ ማቅረብ እንደማይቻል እያወቁ እንዴት ለኮሚቴው ማመልከቻ አቀረቡ? እንዴትስ እስከ ሰበር ችሎት ድረስ ኮሚቴው ጉዳዩን ማየቱና መወሰኑ ትክክል ነው እያሉ ሲከራከሩ ቆዩ? ጠበቆቹ ጣልቃ እንግባ ብለው ለሰበር ችሎት ባቀረቡት የይግባኝ አቤቱታ ላይ የሥር ፍርድ ቤት በሰጠው ውሳኔ አሁን አከራካሪ የሆነውን ሕንፃ ጭምር እንድናስረክብ ፈርዶብናል ብለው ካረጋገጡ በኋላ፣ እንደገና ተመልሰው ደግሞ ለከፍተኛው ፍርድ ቤትና ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ባቀረቡት ይግባኝ አከራካሪ የሆነውን አንዱን ሕንፃ በተመለከተ የሥር ፍርድ ቤት ውሳኔ አላረፈበትም እያሉ እንዴት ፍርድ ቤቱን የሚያሳስትና ፍትሕን የሚያዛባ አቤቱታ አቀረቡ? ጠበቆቹ ዳኞች የአገሪቱ ከፍተኛ የሥልጣን አካል በሆነው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚሾሙት ከማናቸውም ተፅዕኖ ነፃ ሆነው በህሊናቸው እየተመሩ በሕግ መሠረት እንዲወስኑ መሆኑን ያውቃሉ፡፡ ስለሆነም ክብራቸው ዝቅ ተደርጎ በማናቸውም ሁኔታ ሊዘለፉ እንደማይገባም ይረዳሉ፡፡ በተለይም በፍርድ ቤት በሚቀርብ አቤቱታ ላይ የዚህ ዓይነት ድርጊት ሲፈጸም በሥነ ምግባር እንደሚያስጠይቅም ያውቃሉ፡፡

እውነቱ ይህ ሆኖ ሳለ ጉዳዩን የተመለከቱትንና የሥር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በሕግ አግባብ በማስፈጸም ንብረቶቹ እንዲመለሱ የወሰኑትን ዳኛ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ያቀረቡት የችሎት ይነሳልኝ ጥያቄ በሁለት የተለያዩ ችሎቶች ውድቅ ከተደረገና የቅጣት ውሳኔ ከተወሰነባቸው በኋላ፣ ጠበቆቹ የፈለጉትን ውሳኔ ስላልሰጧቸው ብቻ እንዴት “የሥነ ሥርዓት ሕግ አያውቁም” እና “የራሳቸውን ታሪክ ፈጥረዋል” እያሉ ሊዘልፏቸው ቻሉ? ጠበቆቹ ተከራካሪ ወገን (እነ ብሩክ) ባልነበረበት የችሎት ቀጠሮ ያቀረባችሁትን የይግባኝ ማመልከቻ አሻሽላችሁ አቅርባችሁ የተሻሻለው ለፍርድ ቤቱና ለተከራካሪ ወገን (ለእነ ብሩክ) ይድረሰው ተብሎ በችሎት ትዕዛዝ ተሰጥቷቸው ሳለ፣ ትዕዛዙን ባለማክበር እንዴት አሻሽለው ለችሎት ሳያቀርቡና ያልተሻሻለውን ይግባኝ ለተከራካሪ ወገን በማድረስ ከአንድ ዓመት በላይ መልስ ተሰጥቶ ክርክር እንዲደረግበት አድረጉ? እንዴት ቀድሞ በተሰጠው ትዕዛዝ መሠረት እናሻሽለው ብለው ለችሎቱ ጥያቄ አቀረቡ? ችሎቱስ የትኛውን ሕግ መሠረት አድርጎ እንዲያሻሽሉ ፈቀደላቸው? ክቡር የፌዴራል ጠቅላይ ዋና ዓቃቤ ሕግ ይህንን ጥቆማና አቤቱታ መነሻ በማድረግ አስፈላጊውን ውሳኔ እንዲሰጡበት በአክብሮት እንለምናለን!! 

ጉዳዩን በተመለከቱት የጠቅላይ ፍርድ ቤትና የሰበር ችሎት ላይ የቀረበ ቅሬታ   

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤትን በተመለከተ

የፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እነ አቶ ብሩክ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የመ.ቁ. 11032 በንብረቶቹ ላይ ያቀረቡትን አቤቱታ እንደ ባለቤትነት ክስ አድርጎ በመውሰዱ ባይሰሌክስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበርንና ይኼው ማኅበር ለዓመታት በእጁ አድርጎ ሲያስተዳድረው የነበረውን በካርታ ቁጥር 9/16/1/7/29758/22062/22832/02 የተመዘገበውን ሕንፃ በመለያየት፣ ሕንፃው ላይ ቀድሞውንም ክስ ያልቀረበበትና ፍርድም ያላረፈበት ነው ሲል የተሳሳተ አተረጓጎምና ድምዳሜ ላይ ሊደርስ ችሏል፡፡ በተጨማሪም የእነ አቶ ገብረየሱስ የፍርድ አፈጻጸምን እየተመለከተ ላለ ችሎት በፍ/ብ/ህ/ስ/ስ/ቁ 358 ያቀረቡትን አቤቱታ አከራካሪ ቢሆንም፣ በውጤት ላይ የሚያመጣው ለውጥ የሌለ መሆኑን በመጥቀስ ያላንዳች ተጨባጭ ሕጋዊ ምክንያት የእነ አቶ ብሩክን ሰፊ ክርክር በአንድ ዓረፍተ ነገር አልፎታል፡፡ በሌላ በኩል እነ አቶ ብሩክ በሌሉበት ቀጠሮ አቶ ገብረየሱስ ያቀረቡትን የይግባኝ አቤቱታ ተሻሽሎ እንዲቀርብ ለጠበቆቹ ትዕዛዝ ሰጥቶ ሳለ፣ የተሰጣቸውን ትዕዛዝ ባለማክበር የተሻሻለውን የይግባኝ ቅሬታ ለፍርድ ቤቱ ካለማቅረባቸውም በላይ ያልተሻሻለውን ቅሬታና መጥሪያ ለተጠሪ (ለነአቶ ብሩክ) አድርሰው መልስና የመልስ መልስ ተሰጥቶ ለአንድ ዓመት ያህል ክርክር ሲካሄድ ከቆየ በኋላ፣ ጉዳዩ ለውሳኔ በተቀጠረበት ቀን ፍርድ ቤቱ ጠበቆችን ለምን አቤቱታቸውን አሻሽለው እንዳላቀረቡለትና ለምን ያልተሻሻለውን አቤቱታ ለተጠሪ (ለነአቶ ብሩክ) እንዲሰጡ ጠየቀ? በዚሁ ዕለት ሳይጠሩና በሌሉበት የተሰጠውን ትዕዛዝ ለመጀመሪያ ጊዜ ያወቁት ተጠሪ (እነአቶ ብሩክ) የአቶ ገብረየሱስ ጠበቆች ድርጊት ሕገወጥ መሆኑን ጠቅሰው ከአንድ ዓመት በኋላ በድጋሚ አሻሽለው ሊያቀርቡ ስለማይገባ መዝገቡ እንዲዘጋ ያቀረቡለትን አቤቱታ ወደ ጐን ብሎ አቤቱታው እንዲሻሻል መፍቀዱና ክርክሩ እንዲቀጥል ማድረጉ፣ አልፎ ተርፎ በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 358 መሠረት በአፈጻጸሙ መዝገብ ጣልቃ ሊገቡ ይችላሉ በማለት አንዱ ሕንፃ ፍርድ አላረፈበትም ሲል መወሰኑ ታይቶ ተሰምቶ የማያውቅ የሥነ ሥርዓት ሕግ ግድፈት ነው፡፡ ሌላው እጅግ አስገራሚ ድርጊት ደግሞ የአቶ ገብረየሱስ ጠበቆች ባቀረቡት አቤቱታ ይግባኝ ያሉበትን ፍርድ የሰጡት የከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ ላይ የሰነዘሩት “የሥነ ሥርዓት ሀሁን አያውቁም” እና “የራሳቸውን ታሪክ ፈጥረዋል” በማለት በይግባኝ አቤቱታቸው ላይ የሰነዘሩትን ዘለፋና ስድብ ሰምተው እንዳልሰማ፣ ዓይተው እንዳላየ በዝምታ ማለፉ እጅግ የሚያሳዝን ነው፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ሰሚ ችሎትን በተመለከተ

ከላይ እንደተመለከተው እነ አቶ ብሩክ በመ.ቁ. 11032 ለፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክስ የመሠረቱት ኮሚቴው የአፈጻጸም መመርያውን አንቀጽ 6(2) በመተላለፍ በፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደባቸው በነበሩት ንብረቶች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ ሕገወጥ የሁከት ድርጊት በመሆኑ፣ ሁከቱ በፍ/ብ/ህ/ቁ 1149 መሠረት ተወግዶ ንብረቶቹ ተመልሰው ሁኔታዎች ከኮሚቴው ውሳኔ በፊት ወደነበሩበት ሁኔታ እንዲመለሱ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ በንብረቶቹ ላይ የቀረበ የባለቤትነት ክስ አልነበረም፡፡ ይህም የሆነው በአጋጣሚ ሳይሆን በእነዚሁ ተመሳሳይ ንብረቶች ላይ ከእነ አቶ ገብረየሱስ ጋር በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክርክር እየተካሄደባቸው የነበሩ በመሆኑ ነው፡፡ አቶ ገብረየሱስም በዚሁ መዝገብ ላይ የሚሰጥ ውሳኔ መብታቸውን ሊነካ የሚችል መሆኑን ጠቅሰው፣ በፍ/ብ/ሕ/ስ/ስ/ቁ 41 መሠረት ወደ ክርክሩ ጣልቃ ለመግባት እንዲፈቀድላቸው አቤቱታ ያቀረቡ ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ በተለይም በዚሁ መዝገብ እየተካሄደ ያለው ክርክር ከይዞታ ጋር የተገናኘ መሆኑን እሳቤ በማድረግ አቤቱታውን ውድቅ አድርጎታል፡፡ እነ አቶ ገብረየሱስም በዚህ ረገድ በፍርድ ቤቱ በተሰጠው ብይን ላይ እስከ ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ይግባኝ ያሉ ቢሆንም፣ በየደረጃው የሚገኙት ፍርድ ቤቶች ይግባኙን ሳይቀበሉት ቀርተዋል፡፡ በመሆኑም ከዚህ ሁሉ በኋላ አቶ ገብረየሱስ የፍርዱን አፈጻጸም እየተመለከተ ለነበረው ይግባኝ ሰሚ ችሎት በፍ/ብ/ሕ/ስ/ስ/ቁ 358 መሠረት መቃወሚያ እንዲያቀርቡ የሚያስችላቸው የሕግ መሠረት የሌለ መሆኑን ጠቅሰን ለተከበረው የሰበር ሰሚ ችሎት ያቀረብነውን መሠረታዊ የሥነ ሥርዓት ክርክር ፍርድ ቤቱ አንዳችም ምክንያትና ትችት ሳይሰጥ በዝምታ አልፎታል፡፡

ከዚህ ነጥብ ጋር ተያይዞም በተለይ እነ አቶ ገብረየስ ጣልቃ አትገቡም ተብሎ በተሰጠው ብይን ላይ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኛቸውን ባቀረቡበት ወቅት የተመዘገበው ሕንፃ በእርግጥም ፍርድ ያረፈበት መሆኑት ጠቅሰው ሲከራከሩ የነበሩ ከመሆኑ አንፃር፣ አሁን እንደ አዲስ ወደ ኋላ ተመልሰው ይኼው ሕንፃ ክስ ያልቀረበበትና ፍርድ ያላረፈበት መሆኑን በመግለጽ የሚያቀርቡት ክርክር ፈጽሞ ተቀባይነት ሊያገኝ የማይገባ መሆኑን ገልጸው እነ አቶ ብሩክ ያቀረቡትን ክርክር የሰበር ሰሚ ችሎቱ በእጅጉ ግራ በሚያጋባ መልኩ አንዳችም ትችት ሳይሰጥበት በተመሳሳይ መልኩ በዝምታ አልፎታል፡፡ በመሆኑም የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበር ሰሚ ችሎት እነ አቶ ብሩክ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የመ.ቁ. 11032 ያቀረቡት ክስ የይዞታ ይመለስልኝ (Possessory Action) ሆኖ እያለ፣ በንብረቶቹ ላይ የባለቤትነት ክርክር እንዳቀረቡ በማስመሰልና በዚሁ የተሳሳተ አረዳድ መነሻነትም በካርታ ቁጥር…. በተመዘገበው ሕንፃ ላይ ቀድሞውንም ክስ ያልቀረበበትና ክርክር ያልተካሄደበት እንዲሁም ፍርድ ያላረፈበት ነው ሲል የደረሰበት ድምዳሜ የንብረት መብታቸውን ከሕግና መመርያ ውጪ በግፍ የተነጠቁትን እነ አቶ ብሩክን በእጅጉ ያሳዘነና ወደፊት ዓመታትን ሊወስድ ለሚችል ተጨማሪ ሙግትና እንግልት የሚዳርግ ነው፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን በሰበር አጣሪ ችሎቱ ያስቀርባል ተብሎ በተያዘው ጭብጥ መሠረት ለምርመራ የቀረቡት ውሳኔዎች፣

ሀ.    የከፍተኛው ፍ/ቤት በአፈጻጸም መዝገብ የሰጠው ፍርድ (የፍ/ሕ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 358ን ጭብጥ በሚመለከት)፣

ለ.    የሰበር ችሎት የሰጠው ፍርድ (ጠበቆቹ “የአሁን አመልካቾች የተጠቀሱትን ሁለት ሕንፃዎች ለአሁን ተጠሪዎች ለባይሰሌክስ ኩባንያ (ለእነአቶ ብሩክ) እንድናስረክብ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ሰጥቷል” ያሉበት)፣

ሐ.    የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሰጠው ፍርድ (አከራካሪው ሕንፃ ፍርድ አርፎበታል ወይስ አላረፈበትም” የሚለውን ጭብጥ በሚመለከት) ቀርቦ ከመዝገቡ ጋር ተያይዞላቸው ሳለ የአቶ ብሩክን ቁልፍ ክርክር የሚመለከተውን የፍ/ሥ/ሕ/ቁ 358ን እና የጠበቆቹን ተዓማኒነት ጥያቄ ውስጥ የሚከተውን የሰበር ውሳኔ ሳይመረምሩና ሳይተቹ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትን መዝገብ ብቻ መሠረት አድርገው ፍርድ መስጠታቸው፣ እንኳን የሕግ ማኅበረሰቡን ይቅርና ነገር ለመከታተል አደባባይ የሚውሉ ሰዎችንም ጭምር የሚያስገርም ነው፡፡ በመሠረቱ ክርክር የሚመራውና ዳኝነት የሚሰጠው በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕጉ መሠረት ነው፡፡ በሥነ ሥርዓት ሕጉ ከተዘረጋው የክርክር አመራርና የዳኝነት አሰጣጥ ውጪ ክርክር የመምራትና ዳኝነት የመስጠት አካሄድ የዳኝነት ሰጪ አካሉን ገለልተኝነት ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ነው፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን እንዲህ ዓይነቱ ድርጊት በዳኝነት አካላቱ ላይ ዜጎች እምነት እንዳይኖራቸው የሚያደርግ ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳዩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚመለከታቸው ወገኖች በጥልቅ ሊያስቡበትና ሊታረም የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡

  •  

ለዚህ ሁሉ አለመግባባት መነሻ የሆነው ነገር ከነአቶ ብሩክና ከነአቶ ገብረየሱስ አቅም በላይ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ምክንያት ከአገር እንዲወጡ ተደርገው የነበሩ ኤርትራውያን በኢትዮጵያ ውስጥ ያላቸውን ንብረት ማግኘት እንዲችሉ ሲባል የኤፌዴሪ መንግሥት ያወጣውን መመርያ እደግፋለሁ፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን መመርያውን መሠረት በማድረግ ብቻ መብታቸውን ለሚያስከብሩ ኤርትራውያን በሕግ ባለሙያነቴ ዕገዛ ማድረግ እንደሚገባኝም አውቃለሁ፡፡ ይህ ጉዳይ እንደተጀመረም ከፍርድ ቤት ውጪ በእርቅና በስምምነት እንዲያልቅ ደንበኛዬን አቶ ብሩክን በማሳመን የበኩሌን ጥረት አድርጌአለሁ፡፡ አቶ ገብረየሱስ የሰላሙን መንገድ ረግጠው በጠበቆቻቸው ዕገዛና ግፊት ሕግን ለኢፍትሐዊ ዓላማ መሣሪያ ለማድረግ ሲጥሩም በሕግ አግባብ ሞግቼአቸዋለሁ፡፡ ያገኙት ጊዜያዊ ውሳኔም (ድል) ቢሆን በዚህ ግልጽ አቤቱታና ጥቆማ እንደሚታረም ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ በሌላ በኩል ይህ በእሳቸውና በደንበኛዬ በአቶ ብሩክ መካከል የተፈጠረው አለመግባባት ለልጅ ልጅ እንዳይተላለፍ ስል ጉዳዩ በእርቅና በስምምነት የመጨረሻ እልባት እንዲያገኝ አቶ ብሩክን ለማሳመን የበኩሌን ጥረት እንደማደርግ ቃል እገባለሁ፡፡ አቶ ገብረየሱስም በፈጸሙት ሕገወጥ ድርጊት ተፀፅተው ወደ እርቅና ሰላም መንገድ እንዲመለሱ ጥሪ አቀርብላቸዋለሁ፡፡ በመጨረሻም ከዚህ አቤቱታና ጥቆማ ጋር አግባብነት ያላቸውን ማስረጃዎች ከተጠየቅሁ ምንጊዜም የማቀርብ መሆኔን እየገለጽኩ አቤቱታና ጥቆማዬን በዚሁ አጠቃልላለሁ፡፡ ለተጨማሪ ማብራሪያ በስልክ ቁጥር 0911233892 እገኛለሁ፡፡  

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው molla.zegeye@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

 

 

Standard (Image)

የልደቱ ምልከታዎችና አገርን ከቅርቃር የማውጫ አማራጮች

$
0
0

በመኮንን ቢምር

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሕዝብ መረጃ ክፍል “Africa Renewal” የሚባል ተወዳጅ መጽሔት ያሳትማል፡፡ የመጽሔቷ እ.ኤ.አ. የኖቬምበር 2016 ዕትም ደግሞ “Africa Democracy Coming of Age” የሚል በሳል ትንታኔ በዓምደኛው ኪንግስሊ ኩበር አማካይነት ይዞ ወጥቷል፡፡

ዘገባው የአፍሪካ አገሮችን ሕዝቦች ፖለቲካዊና ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች መፍቻ ወሳኙ ጉዳይ መልካም አስተዳደር እንደሆነ በግልጽ አስቀምጧል፡፡ መልካም አስተዳደርን በማረጋገጥ የማኅበረሰቡን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ ደግሞ ግልጽነትና ተጠያቂነት፣ አሳታፊነትና አገልጋይነት፣ ወዘተ የመሳሰሉትን የዴሞክራሲ እሴቶች እያጎለበቱ መሄድ ወደኋላ ሊባሉ አይችሉም፡፡ ይህ ሲሆን ነው በአኅጉሩ ያሉት 1.2 ቢሊዮን ሕዝቦች ሙሉ ብርሃን የሚወጣላቸው ሲልም ያትታል፡፡

በአኅጉሩ አጀንዳ 2063 የስምምነት አንቀጽ 3 መሠረት ‹‹መልካም አስተዳደር የሚሰፍንበት፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚከበሩበትና የሕግ የበላይነት የሚረጋገጥበት አኅጉር ይሆናል፤›› የሚለው ይገኝበታል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከወዲሁ መዋቅራዊ ለውጥ ማምጣትና ሕዝቡን ያሳተፈና ተጠያቂነት የተላበሰ መንግሥታዊ ሥርዓት በየአገሩ እንዲኖር ይጠበቃል፡፡

እስካሁን በታየው መረጃ ጋና፣ ቦትስዋና፣ ኬፕቨርዲ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ናሚቢያና ሲሸልስ በአርዓያነት ሲጠቀሱ፣ የመጨረሻዋ ደረጃ ላይ ያለችውን ሶማሊያን ጨምሮ ደቡብ ሱዳን፣ ማዕከላዊ አፍሪካ፣ ሱዳን፣ አንጐላ፣ ሊቢያና ጊኒ ቢሳኦ የመጨረሻዎቹ ተርታ ላይ ናቸው፡፡ ይህ አምነስቲ ኢንተርናሽናልን ጨምሮ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተቋማት የተስማሙበት መለኪያ የእኛን አገርም ባለፉት 13 ወራት እያሽቆለቆሉ ከመጡ አገሮች ተርታ ከመመደቡም ባሻገር፣ የተደጋጋሚ ግጭቶች (በሕዝብና በፀጥታ ኃይሎች) መቀጠሉ ወደ ቀውስ እንዳያመራንም ሰግቷል፡፡

የኪንግስሊ ኩበርን ትንታኔ ዘርዘር አድርጌ የተመለከትኩት ወድጄ አይደለም፡፡ ይልቁንም በቅርቡ በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን አመቻችነት በሸራተን አዲስ ‹‹በኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ግንባታ ፈተናዎችና መልካም ዕድሎች›› ኮንፈረንስ ላይ የተመለከትኩትን ትዝብት ለማስተሳሰር በመፈለጌ ነው፡፡

በተለይ ከአራቱ የመወያያ ጽሑፍ አቅራቢዎች አንዱ የሆኑት በ1997 ዓ.ም. የምርጫ ትኩሳት ወቅት ‹‹ማንዴላ›› የተባሉት፣ የአሁኑ የኢዴፓ አማራጭ መንገዶች ፋና ወጊ የነበሩት ልደቱ አያሌው ናቸው፡፡ በነገራችን ላይ እኚህን የአዲሱ ትውልድ ፖለቲከኛ የተወሰኑ ወገኖች ‹‹የከዱ፣ አድርባይ፣ አስመሳይ…›› ቢሏቸውም፣ በግሌ የማደንቅላቸው የተለያዩ መለኪያዎች አሉኝ፡፡

አንደኛው በፍጥነት አቅማቸውን እያሳደጉ የመጡ ፖለቲከኛ መሆናቸው ነው፡፡ በዚህ ላይ አንደበተ ርቱዕና ጠንካራ ሐሳብ በማራመድም ‹‹ከ30 ሚኒስትር አንድ ልደቱ›› የተባለላቸው ናቸው፡፡ ከ1997 ዓ.ም. ምርጫ ማግሥት ምንም እንኳን በሥልጣን ሽሚያ ተናቁረው ቅንጅትን ካፈረሱት ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና ኢንጂነር ኃይሉ ሻወል (ነፍሳቸውን ይማረውና) ግሰለቦች ተርታ በመሠለፍ ከታሪክ ተጠያቂነት ባያመልጡም፣ በኢሕአዴግ ጐራም ቢሆን የሚፈሩ ፖለቲከኛ እንደሆኑ አውቃለሁ፡፡ ይህ የግል አስተያየቴ ነው፡፡

ከሁሉ በላይ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በሁለት ጫፍና ጽንፍ ተለጥጦ የሚብላላውን አክራሪ ፖለቲከኝነት በማፍረስ ‹‹ሚዛናዊ ቅዋሜና መሀል ላይ ያረፈ የሰላማዊ ትግል ብቸኛ ሥልት›› ይዞ ብቅ ያለውን የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) በመሥራችነትም ይታወቃሉ፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ፀረ ዴሞክራሲያዊና የከፊል ወገን ፖለቲካ አራማጅ ብቻ ሳይሆን በቡድን መብት ስም የግለሰቦችን መብት መዘንጋቱ፣ በማንነት ፌዴራሊዝም ሳቢያ ኢትዮጵያዊ አንድነትና አገራዊ ብሔርተኝነትን አደጋ ላይ መጣሉ፣ ብሎም የአገሪቱ ወደብ አልባነትና መሰል ችግሮችን የፈጠረ ነው፤›› የሚሉትን ያህል፣ ባለፉት 25 ዓመታት አመርቂ የማኅበረ ኢኮኖሚ ልማት ማስመዝገቡን አይክዱም፡፡ ቀውስ በበዛበት ቀጣና ከሽብርተኞች አገርን መጠበቁና አንፃራዊ ሰላም እንዲሰፍን ማድረጉንም ዋጋ ይሰጡታል፡፡

በሰሞኑ አገር አቀፍ ኮንፈረንስም ላይ ቢሆን ከኢሕአዴጉ በረከት ስምዖን (ጊዜ ያለፈባቸው አስተያየቶች) ሆነ ከዶ/ር መረራ ጉዲናና ኢንጅነር ፀደቀ ይሁኔ የከረሩና የአገም ጠቀም አካሄዶች በበለጠ የኢዴፓው ልደቱ አያሌው ሐሳቦች አገርን ከቅርቃር ለማውጣት የሚበቁ ይመስለኛል፡፡ ‹‹ኢሕአዴግን ከውጭ እንደመጣ ባዕድ ጠላት ከሚመለከት ጽንፈኛ አተያይ በመውጣት አሁን በተፈጠረው አገራዊ ቀውስ ውስጥ የሕዝቡን ፍላጎትና ስሜት ተቀብሎ የመፍትሔው አካል መሆን እንዳለበት ፓርቲ ማየት አለብን፤›› የሚሉት አቶ ልደቱ፣ ይህ ሲሆን ከሰላማዊና ከዴሞክራሲያዊ መንገድ ውጪ ያለውን አፍራሽ የኃይል ዕርምጃም በጥንቃቄ ማየቱ የሚበጀው ከኢሕአዴግም አልፎ አገር የሚበትን ስለሆነ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡ ለሁሉም የልደቱ አተያይም ሆነ የኢዴፓ ሐሳብ በወቅቱ የተነሱ ነጥቦችን ከሌሎች ትንታኔዎች ጋር በማጣቀስ ለመወያያነት ማቅረብን መርጫለሁ፡፡

ኢሕአዴግ የደፈቀው የዴሞክራሲ ዕጦት የፈነቀለው ሕዝብ

ባሳለፍናቸው ወራት በኢትዮጵያ የሕዝቦች ትግል ውስጥ ትልቅ ግምት የሚሰጠውና ከሞላ ጎደል ለ12 ወራት የዘለቀው ሕዝባዊ እንቢተኝነት አሁንም አገሪቱ ብሔራዊ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንድታውጅ አስገድዷታል፡፡ አቶ ልደቱ ይህን የሕዝብ ቅሬታ የሚመለከቱት የዴሞክራሲ ምኅዳሩ ጠቦ፣ የአንድ አሸናፊ ገዢ ፓርቲ አስተሳሰብ ብቻ ምድርን በመሙላቱ የተፈጠረ መሆኑን ያምናሉ፡፡ ይህንኑ ሲያስረዱም፣

‹‹…በተለይ ከ1997 ዓ.ም. አገራዊ ምርጫ ውጤት በኋላ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ከፍተኛ የዴሞክራሲ ዕቀባ አድርጓል፡፡ በቀዳማዊነት ምኅዳሩን የሚያጠቡና አፋኝ ሕጎችን አውጥቷል፡፡ (የፀረ ሽብር ሕጉ፣ የመገናኛ ብዙኃንና የመረጃ ነፃነት ሕጉ፣ የሲቪክ ማኅበራት ሕግ) መላውን የአገሪቱ ሕዝብ (በተለይ አርሶ አደሩንና ሲቪል ሰርቫንቱን) በአንድ ለአምስት አደረጃጀት አዲስ ‘ሥልት’ ጠርንፎታል፡፡ በአጭር ጊዜ በሁሉም አባል ድርጅቶቹ የገፋ አባላት ምልመላ አድርጎ ከስድስት ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ‘አባል’ አድርጓል፡፡ ልማትን የሞት ሽረት አጀንዳ እያለ ዴሞክራሲና ፖለቲካን ከአየር አስወጥቶታል…›› (ቃል በቃል ባይሆንም) ብለዋል፡፡

ከእነዚህ እውነታዎች ባሻገር የመንግሥት መገናኛ ብዙኃንን ጠቅልሎ በሞኖፖል በመያዝ የፕሮፓጋንዳ መሣሪያ አደረገ፣ የግል መገናኛ ብዙኃንም (የራሳቸው ችግር እንዳለ ሆኖ) ተበተኑ፣ ተዘጉ፡፡ ሌሎች የገዥው ፓርቲ የፕሮፓጋንዳ ተቋማትም ተስፋፍተው ተከፈቱ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን በአገሪቱ የሰላማዊ ዴሞክራሲያዊ አማራጭ የነበራቸው የፖለቲካ ኃይሎች ተበታተኑ፣ ተዳከሙ፣ ቀላል ግምት የማይሰጣቸውም ተሰደዱ፡፡ በምርጫ 97 መዘዝ በአገሪቱ በታየው እስራት፣ ግድያና ማሳደድም ሕዝቡ ‹‹ፖለቲካና ኮረንቲ›› እንዲልና ደግሞ ወደ ቆፈኑ እንዲመለስ አድርጎት ነበር፡፡

አቶ ልደቱ፣ ‹‹ይህ አገራዊ ሁኔታ የሰላማዊ ፓርቲዎችን ትግል ትርጉም አልባ ከማድረግ ባለፈ በፌስቡክ አራማጆችና በየአካባቢው ካሉ የመንደር የጐበዝ አለቆች ያነሰ ተሰሚነት ላይ ጣለው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ አክራሪ ፖለቲከኝነትና ኢሕአዴግን በመጣበት የጦርና የኃይል መንገድ ካልሆነ አይሆንም የሚለውን ኃይል ተደማጭነት አጠናከረ፤›› ባይ ናቸው፡፡

ለዴሞክራሲያዊ አፈናው ተጨባጭ ማሳያም በኢሕአዴግ ዘመን በተካሄዱ ምርጫዎች በ1987 ዓ.ም. 21 ወንበሮች የነበራቸው ተቃዋሚዎችና የግል ተወዳዳሪዎች ቢያንስ በ1992 ዓ.ም. 25 ወንበሮች፣ በ1997 ዓ.ም. አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉና 173 የፓርላማ ወንበሮች የተቃዋሚ ጐራ ሲያገኝ ነበር፡፡ ከምርጫ 97 በኋላ ግን በ2002 ምርጫ ኢሕአዴግ 99.6 በመቶ ሲያሸንፍ ‹‹በቴክኒክ ስህተት›› አንድ የግልና አንድ ተቃዋሚ ፓርላማ ገቡ (ተሳታፊውን ያሳቀ ገለጻ ነበር)፡፡ በ2007 ዓ.ም. መቶ በመቶ ገዥው ፓርቲ በተመሳሳይ ውድድር አልባ ፀረ ዴሞክራሲያዊ መንገድ አሸነፍኩ አለ፡፡ በወራት ዕድሜ ‹‹መረጠኝ ያለው ሕዝብ›› በገጠር ሳይቀር ድንጋይ መወርወርና እሳት መጫር ጀመረ ብለዋል፡፡

እነሆ አሁን ከ25 ዓመታት በኋላ አገሪቱ ወደ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የገባችው፣ በየአካባቢው የንፁኃን ሕይወት መርገፍ፣ የሰላማዊና የዴሞክራሲያዊ ትግል መዳከሙ (የፓርቲዎች የራሳቸው ችግር እንዳለ ሆኖ)፣ ብሎም ጽንፈኛ ዳያስፖራ የቀሰቀሰው የኃይል ዕርምጃ ብዙዎችን እያሳሰበ ያለውና አገርንም ለአደጋ ያጋለጠው የኢሕአዴግ የቻይና ፀረ ዴሞክራሲ መንገድ መከተል ሲሉ ደምድመዋል፡፡ ስለዚህ በቀዳሚነት በድርጊቱ ተፀፅቶ ከእንቅልፉ መንቃት ያለበት ራሱ ኢሕአዴግ ሊሆን ግድ ሆኗል ማለት ነው፡፡

ዘመኑን ያልመጠነ የተቃዋሚ ፖለቲከኝነት የበታተነው ሕዝብ

የኢዴፓው ሰው ልደቱ አያሌው በአጭሩ በመወያያ ጽሑፋቸው በአገሪቱ ውስጥም ሆነ በውጭ ያለውን የፖለቲካ ኃይልም ዳስሰዋል፡፡ በተለይ እሳቸው ‹‹የ1990ዎቹ ፖለቲከኞች›› ያሏቸውን ኦነግ፣ ሻዕቢያ፣ ኢሕአፓ፣ ኢሠፓና ኢሕአዴግ ጭምር የተጠናወታቸው የግራ ፖለቲካና አክራሪ ባህል ለውይይትና ለሰጥቶ መቀበል መርህ ዝግ እንደሆነ ሒሰዋል፡፡ በድርድር የማያምን፣ መቆጣጠርን ብቻ የሚሻና አሸናፊነትን ብቻ የተቀበለ ትውልድም ሲሉ ገልጸውታል፡፡

ከዚህ አንፃር ከኢዴፓና ከሰማያዊ ፓርቲ በስተቀር አብዛኞቹ የአገሪቱ ፓርቲዎች በዚያ ትውልድ መመራታቸውና ተፅዕኖ ሥር መውደቃቸው ሒደቱን ጐድቶታል ባይ ናቸው፡፡ ከዚህ እውነት በላይ በውጭ ያሉ የዳያስፖራ ፖለቲከኞች ቀስ በቀስ ጽንፈኛና አክራሪ መንገድን እየመረጡ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ትግልን መሸሻቸው፣ በአገር ውስጥም የሰላማዊና የኃይል አማራጭን ለማጣቀስ የሚሹ ፓርቲዎች መኖራቸው ለኢሕአዴግ ክስና ጫና ምኅዳሩን አጋልጦታል፡፡

የአቶ ልደቱ ሌላው ተጨባጭ ግምገማ በአገር ውስጥ ያለው የፖለቲካ ኃይል ከኅብረ ብሔራዊነት ይልቅ በብሔር የተደራጀ፣ ተጠናክሮ የሕዝብን ድጋፍ የሚያገኝበት አማራጭ ፖሊሲ የሌለው፣ በዕውቀትና በቁርጠኝነት ሊመሩት የሚችሉ የፖለቲካ ልሂቃንን ያላቀፈ ሆኗል፡፡ በዚህ ምክንያት የተቃዋሚው ጐራ የኢሕአዴግን ተፅዕኖና ጫና መሸከም ካለመቻሉም በላይ ሕዝቡን ተስፋ እያስቆረጠው ይገኛል፡፡ አሁን በአገሪቱ በተጨባጭ እንደታየውም በየአካባቢው ሕዝቡን ብሶት አነሳሳው እንጂ ሕዝቡን የመራው አስተሳሰብ አልታየም፡፡ መፈክሩ ‹‹ለውጥ! ለውጥ! ለውጥ!›› ብቻ ሆኗል፡፡

በኢትዮጵያ የተቃዋሚ ፖለቲካ መዳከምና እርባነ ቢስ መሆን ረገድ ገዥው ፓርቲ በተለይም መንግሥት ተጠያቂ ነው፡፡ የማያፈናፍን ሕግ በማውጣት፣ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን በማሳደድ፣ እንዲሁም በፓርቲዎች መጠናከር ላይ ሕገ መንግሥታዊ ድጋፍን ባለማድረግ ይጠየቃል፡፡ ከዚህም በላይ ግን ተቃዋሚ ፓርቲዎቹና መሪዎቻቸው የሚወቀሱባቸውን ድክመቶች በጥልቀት መለየት እንደሚያስፈልግ በውይይቱም ተነስቷል፡፡ ‹‹አገራዊ አጀንዳ አለመኖር፣ ቢያንስ ሕዝቡ ኢሕአዴግ ቢወርድ ማን ይተካዋል የሚለውን ሥጋት እንዲቀንስ የሚያደርግ መደማመጥና አሠራር፣ አደረጃጀትና የሰው ኃይል ዘርግቶ አለመታገል…›› የሚሉት መሠረታዊ ነጥብ ሆነው ወጥተዋል፡፡

ከዚህ በመነሳትም ነው በአቶ ልደቱ ትንታኔ ‹‹ሕዝቡንና ዘመኑን ያልመጠነ የተቃውሞ ፖለቲካ ትግል›› እንደተንሰራፋ የተገለጸው፡፡ ይህን አተያይ የሚጋሩ አንዳንድ ታዛቢዎች ለተቃውሞው ጐራ አለመጠናከር በተለይ ምሁሩንና የግል ባለሀብቱንም ይነቅፋሉ፡፡ ምሁሩ በፍርኃትና በአድርባይነት ‹‹አብዛኛው ምን ቸገረኝ ብሏል›› ይላሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው የፖለቲካ ምሁር ዶ/ር ካሳሁን ብርሃኑ፡፡ የግል ባለሀብቱም ባለመጠናከሩና ከመንግሥት ጥገኝነት ባለመላቀቁ ከአጐንባሽነት እንዳይወጣ ሆኗል፡፡ ስለዚህ የተቃውሞ ጐራው በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ ትግል ሕይወት ኖሮት እንዲንቀሳቀስ ሁሉም ታሪካዊ ኃላፊነቱን መወጣት አለበት ነው እየተባለ ያለው፡፡

መሪ አስተሳሰብ ያላገኘው ሕዝብና ያልተፈለገ መስዋዕትነት

የኢትዮጵያ ሕዝቦች ለዘመናት አገራቸውን በነፃነት ያኖሩ፣እርስ በርሳቸውም ተሳስበውና ተከባብረው የዘለቁ ናቸው፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ሀቀኛ ዴሞክራሲንና ብሔራዊ ክብርን ባይቀናጁም ልማትንና ‹‹አስመሳይም›› ቢሆን ዴሞክራሲም አይተዋል ይላሉ አቶ ልደቱ አያሌው፡፡ ይሁንና በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ መንገድ የሚፈልጉትን ኃይል ወደ ሥልጣን ማውጣትም ሆነ ባለው አገዛዝም መብትና ጥቅማቸውን ለማስከበር የሚታይባቸው ጉድለት እንዳለ ተናግረዋል፡፡

አንደኛው የአገሪቱ ሕዝቦች ባላቸው የግንዛቤ ደረጃ ልክ የፖለቲካው የለውጥ ኃይል (በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በዕውቀት፣ ካስፈለገም በመስዋዕትነት አስፈላጊውን ለመክፈል የተዘጋጁ) መሆን አለባቸው፡፡ እዚህ ላይ መሪም ሆነ ፓርቲ ከሕዝብ የሚፈጠር እንደመሆኑ፣ ከታሪክ እየተማሩና ዓለማዊ ሁኔታውንም እየመረመሩ ሁለንተናዊ ተሳትፎ ማድረግ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም፡፡

ሁለተኛው የኢትዮጵያ ሕዝቦች ወደውና ፈቅደውም ሆነ በኢሕአዴግ ጫና የተቀበሉትና በሥራ ላይ ያለ ሕገ መንግሥት አላቸው፡፡ ይሁንና በመሠረታዊነት የሕገ መንግሥቱ አንቀጾች ሲሸራረፉና የዴሞክራሲ መርሆዎች ጥርስ ሲወላልቅ ሕዝቡ በየአደረጃጀቱም ሆነ በተናጠል ‹‹ለምን?›› ማለት አለበት፡፡ ይኼ ረዘም ላለ ጊዜ በዝምታ የቀጠለ ሲሆን፣ አሁን አሁን (ምንም እንኳን ድንጋይ መወርወርና የንብረት ጥፋት ቢደመርበትም) መጠየቅና መሞገት እየጀመረ ነው፡፡ (ይህንን የሕዝብ መነሳሳትም ቢሆን ኢሕአዴግ ጠያቂ ማኅበረሰብ (Demanding Society) በመፍጠራችን ነው ቢለውም)

ሦስተኛው ሕዝቡ አሁን እየታየ እንዳለው መሪ አስተሳሰብ ባለማግኘቱና የተደራጀ ሰላማዊ ትግል ባለማግኘቱ አላስፈላጊ መስዋዕትነት እየከፈለ ነው፡፡ ለሠልፍ የወጡ ዜጐች ንብረት ያወድማሉ፣ አገር ትጎዳለች፡፡ በዚህ መዘዝም በሚወሰድ ዕርምጃ ወጣቶች ይገደላሉ፣ አገር ትበደላለች፡፡ ማንም አሸናፊና አትራፊ በሌለበት በዚህ አካሄድ ወደኋላ መመለስ ያጋጥም እንደሆነ እንጂ ወደፊት መራመድ የሚታሰብ አይደለም፡፡

በእርግጥ ለዚህ ዓይነቱ ችግር መቀስቀስ የመንግሥት ድክመትና ፈጣን ምላሽ ያለመስጠት፣ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ ከሕዝብ ፍላጎት ጋር የማይሄድ አጀንዳ በማራመድ ሁከትና አመፅ እንዲቀጣጠሉ የየራሳቸውን ድርሻ አበርክተዋል፡፡ እንደሚባለውም የአገሪቱ የቆዩና የቅርብ ጊዜ የውጭ ጠላቶችም ቢሆኑም ከተረጋጋና የውስጥ ሰላም ካለው አገር ይልቅ፣ የተዳከመና የሚበጣበጥ ባላንጣ ስለሚቀላቸው የበኩላቸውን ሚና ይጫወታሉ፡፡

ሕዝቡ ግን ከሁከትና ከስሜታዊ የለውጥ ፍላጐት ወጥቶ ዴሞክራሲያዊና ሰላማዊ ትግልን ብቻ ማስቀደም አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ የአገርን ጥቅም ማስቀደም፣ ከጥላቻና ከጽንፈኛ ፖለቲካ መውጣት፣ ከዘረኝነት መላቀቅ ይኖርበታል የሚለውን ምክረ ሐሳብ አቶ ልደቱ ጠቃቅሰዋል፡፡

በአጠቃላይ ለ25 ዓመታት አገሪቱን የመራው ኢሕአዴግ በርካታ ጠቃሚ ተግባራትን ቢያከናውንም አገሪቱን የፖለቲካ ቅርቃር ውስጥ እንዳስገባት ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡ ማሳያው ሁከቱ፣ ግድያው፣ የወደመው ንብረት፣ ኩርፊያውና በየአካባቢ የወታደር ካምፕ መፈጠሩ ብቻ ሳይሆን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁና ኢንተርኔት መዘጋቱም ነው፡፡ ኢሕአዴግ ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ሲለው የከረመው ጉዳይም መያዣና መጨበጫው አለመታየቱ ሌላው ሥጋት ሆኗል፡፡

እዚህ ላይ አቶ ልደቱ እንደ መፍትሔ ያስቀመጡትን መቋጫዬ ላድርገው፡፡ ኢሕአዴግ ‹‹ድልን›› ብቻ መስበኩን ትቶ እስካሁን የተሠሩ ስህተቶችን አምኖ መቀበል፣ ወደፊት 30 ዓመታት እቀጣጥላለሁ ከሚል የከሸፈ ፕሮጀክት ወጥቶ መደራደር፣ የገፈፈውን የሚዲያ፣ የማኅበራትና የዴሞክራሲ ተቋማትን ነፃነት መመለስ አለበት፡፡ እነዚህ ባለመደረጋቸው በአገሪቷ የተፈጠረውን አለመተማመን ለማስወገድም፣ እንዳስፈላጊነቱ ገለልተኛ ኮሚሽን በማቋቋም መቃቃርን የሚያስቆም ድርድር መጀመር አለበት፡፡      

በተቃዋሚ ጎራም ቢሆን የአገሪቱን ሕዝብ ብዛትና ስፋት የሚመጥን ፓርቲ መፍጠር አስፈላጊ ነው፡፡ የነበሩትን ድክመቶች አርመው በመርህና በአማራጭ ላይ ኅብረት እንዲፈጥሩ፣ ካልሆነም አዲስ ጠንካራ ፓርቲ ማዋቀር፣ አልያም በተናጠልም ጠንካራ ተወዳዳሪ በመሆን መነሳት ይችላል፡፡ እንደ አገራዊ ፖለቲከኛ ከጥላቻና ከዘረኝነት አስተሳሰብና ድርጊት በመውጣት ለብሔራዊ ዕርቅና መግባባት የበኩላችንን ድርሻም ማበርከት አለብን ብለው፣ ትግሉን ከውጭ አገር ይልቅ አገር ውስጥ ሆኖ መምራትም አስፈላጊ መሆኑን አስምረውበታል፡፡

ለዚህ ደግሞ ‹‹ሥራው ከዛሬ መጀመር አለበት፤›› ሲሉም በአጽንኦት ተናግረዋል፡፡ በተለይ ከፊታችን ላለው የ2010 ዓ.ም. የአዲስ አበባ ከተማ ምርጫና በ2012 ዓ.ም. ለሚካሄደው ብሔራዊ ምርጫ ስኬት የጋራ ኃላፊነት አለብን፡፡ አሁን ያለው የኢሕአዴግ የፖለቲካ መዳከምና የሕዝቡ የለውጥ ፍላጐት መጨመር ደግሞ ብቸኛውን አማራጭ ይኼ እንደሆነ ያደርጉታል፡፡

እነዚህን ዕድሎች እንደ አገር አለመጠቀም ሥርዓቱን እንደ ሻዕቢያ የለየለት አምባገነን እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ በተያዘው መንገድ ከቀጠለም ኢትዮጵያን ሩዋንዳን እናደርጋታለን (ያውም እንደነሱ ማገገማችንም አይታወቅም)፡፡ ከጐበዝን ግን ሁላችንም የምንወዳትና የምናከብራትን አገር ቢያንስ ወደ እነ ጋና ደረጃ ከፍ ማድረግ አይሳነንም ሲሉ የኢዴፓው ሰው ሐሳባቸውን ቋጭተዋል፡፡ ብዙዎቹ ተሳታፊዎች (ያውም መድረኩ የመንግሥት ሰዎች ይበዙበታል) በስሜት ያስጨበጨበም ንግግር ነበር፡፡

እንግዲህ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የዴሞክራሲ መለኪያና በእነ ጋና ደረጃ ተንደርድሬ የአቶ ልደቱን ሐሳብ ለመቃኘት የሞከርኩት ለዚሁ ነበር፡፡ ሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሎች፣ ራሱ ኢሕአዴግና መንግሥትም ይሁኑ ሕዝቡ አገራችን እንደ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳንና ሊቢያ እንዳትወድቅ እንደ ጋና፣ ቦትስዋና ደቡብ አፍሪካ፣ ኬፕቨርዲ… በዴሞክራሲ ስሟ እንዲጠራ ማድረግ አለብን፡፡ የልደቱም ዓይነት ይብዙ፣ ይጠናከሩ፡፡

  ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

    

Standard (Image)

የማንነት መቶ ገጽታዎች

$
0
0

በመታሰቢያ መላከ ሕይወት ገብረ ክርስቶስ

የሰው ልጅ በምድር ላይ መኖር ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ማንነት ምንጊዜም ቢሆን ትኩረት ተነፍጎት አያውቅም፡፡ እንኳን ሰዎች ወፎች እንኳን ብዙ ጊዜ ቀለማቸው በእጅጉ ተመሳሳይ የሆኑ ናቸው አብረው የሚበሩት፡፡ ነገር ግን ዋናው ጥያቄ በብዙ መቶ ከሚቆጠሩት ማንነቶች ትልቁ ነገር ለኑሮ የሚበጀን፣ የተሻለ ኑሮ ለመምራትና ለወደፊቱ ትውልድ በዚህ ፉክክር በሞላበት ዓለም ውስጥ ለመኖር የሚጠቅመው ማንነት የትኛው ነው የሚለው ጥያቄ ነው፡፡

ስለማንነት ስናወራ የቋንቋ ማንነት፣ የመልክዓ ምድራዊ ማንነት፣ የሃይማኖት ማንነት፣ የቆዳ ቀለም፣ ማንነት፣ ወዘተ እያልን እንደፈለግን መለያየት እንችላለን፡፡ ማንነት ደግሞ በሌላ መልኩ ጥንታዊ ማንነት፣ በመሀል ዘመን የነበረ ማንነት፣ አሁን ያለ ማንነት እያልንም መከፋፈል እንችላለን፡፡ በመሆኑም ይህ ሒደት ማለቂያ የሌለው ጨዋታ ነው፡፡ ለምሳሌ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የአማራ ሕዝብ ሴማዊ ማንነት እንዳለው ስንማር ከርመናል፡፡ አሁን ደግሞ ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶለሳ እንዳስተማሩን አማራ የኩሽ ሕዝብ አካል ነው ብለው ከአሳማኝ ምክንያቶች ጋር አስነብበውናል፡፡

በመሆኑም ማንነት የሚለው ጨዋታ መጀመሪያ እንጂ መጨረሻ የሌለው ገመዱ ተመዞ ተመዞ የማያልቅ ነው፡፡ በመሆኑም እኛ አትዮጵያውያን አሁን ባለን ማንነታችን ላይ ተመሥርተን ዓለም በሚያውቀን ግዛታችንና ቅርፃችን መንቀሳቀሳችን የአሁኑን ዘመን አስቸጋሪ ሁኔታ ለመሻገር የሚጠቅመን ብቻ ሳይሆን፣ ወደፊትም የተሻለ ሕይወት ለመምራት የሚረዳን መንገድ መሆኑን መገንዘብ መቻል የግድ አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡

ኢሕአዴግ የኢትዮጵያን ሕዝብ በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፌዴራሊዝም እመሠርታለሁ ብሎ ዘጠኝ ቦታ ቢከፋፍልም፣ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሕዝቦች ግን ከሰማኒያ በላይ በመሆናቸው ኢትዮጵያን 85 ቦታ ቢከፋፈል የዓለም መሳቂያ እሆናለሁ ብሎ በማሰብ ይመስላል፣ ሌሎቻችሁ አንድ ላይ ተዳመሩ ብሎ ጉዞውን ያቆመው፡፡ ይህ ችግር አሁንም ወደፊትም የሰላምና የመረጋጋት ችግር ምንጭ ሆኖ ከመቀጠል ባለፈ፣ የአገራችንና የሕዝባችንን ህልውና የሚያስፈራ አደጋ ላይ መጣሉ አሁን አሁን ለሁሉም ግልጽ እየሆነ የመጣ ይመስላል፡፡ ከሁሉም በላይ ይህ አስተሳሰብ የፓን አፍሪካኒዝም ጽንሰ ሐሳብ ተቃራኒ መሆኑ ደግሞ ከሁሉም በላይ ለመላው አፍሪካውያን ታላቅ አደጋ ነው፡፡

በተለይ ደግሞ በአንድ ቦታ ጥቅም የሚያስገኝ የተፈጥሮ ሀብት ተገኘ ሲባል፣ ማንነት ከሚገባው በላይ ጎልቶ ሊስተጋባ የሚችልበት ጉዳይ መከሰቱ የማይቀር ነው፡፡ በዚህ ወሳኝ ወቅት መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በማንነት ጥያቄ ላይ ግልጽ የሆነና ወደኋላ ሊመልሰን የማይችል አቋም ለመያዝ የጋራ መግባባት ላይ መድረስ የሚባን ወሳኝ ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ ይህንን የማንነት ጥያቄ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ግልጽ አድርገን ትኩረታችንን ልማትና ሰላም ላይ ብቻ አድርገን መጓዝ ምንም አማራጭ የሌለው ነው፡፡

በሌሎች አገሮችም ቢሆን በአንድ ወቅት የማንነት ጥያቄ ለበርካታ ዓመታት የሕዝቦች የጦርነት፣ ያለመረጋጋት፣ የኢኮኖሚ ድቀት ምንጭ ሆኖ የኖረ ጉዳይ ሲሆን እኛ ኢትዮጵያውያን ይህንን ወቅት በአሸናፊነት መንፈስ መወጣት ይጠበቅብናል፡፡

ለምሳሌ ዛሬ በአሜሪካ የሚኖር ከጀርመን፣ ከኢጣሊያ፣ ከእንግሊዝ፣ ወዘተ የመጣው ሁሉ ማንነቱ አሜሪካዊነት ነው፡፡ እንኳን በበለፀጉት አገሮች ይቅርና በቅኝ በተገዙ የአፍሪካ አገሮች እንኳን ይህ ጥያቄ በአግባቡ ተመልሶ ዛሬ ሁሉም ትኩረታቸው የዕለት ተዕለት ኑሮአቸው ላይ ብቻ ነው፡፡

ለምሳሌ ደቡብ አፍሪካን ብንመለከት ከአውሮፓ የመጡት ነጮችም ነባር ነዋሪዎቹ ጥቁሮችም ሁሉም ዜግነታቸው ደቡብ አፍሪካዊነት ነው፡፡ ይህ ጥያቄ እስኪመለስ በርካታ መስዋዕትነት የተከፈለበት ቢሆንም በመጨረሻ አዋጭና ጠቃሚ ሆኖ የተገኘው ይኸው ብቻ በመሆኑ፣ አሁን አገሪቱ በዓለማችን አስደናቂ ዕድገት ካስመዘገቡ አገሮች ተርታ ተሠልፋ እናገኛታለን፡፡

በዓረቡ ዓለም በአሁኑ ወቅት እየተመለከትን ያለነው እጅግ አሳፋሪና ጥቅም ለሌለው ማንነት ነው፡፡ ማለትም ሱኒ ሙስሊምና ሺአ ሙስሊም በመባል ጎራ በመለየት እጅግ ደም አፋሳሽ ግጭቶች እንመለከታለን፡፡ በእነዚህ ሁለት የሃይማኖት አስተሳሰቦች መካከል ያለው ልዩነት ግን እንኳን ደም ለማፋሰስ ለጠብ እንኳን ማብቃት አልነበረበትም፡፡ ሁለቱም እስላም ወንድማማቾች ናቸው፡፡ በሁለቱ እስልምና ተከታዮች ያለው ልዩነት በእጅጉ የጠበበ ነው፡፡

ስለማንነት መጻፍና መናገር ካለብን ብለን ብለን ልንጨርሰው የማንችለው ጉዳይ በመሆኑ፣ በተቻለ ፍጥነት ቶሎ እልባት ተፈልጎለት ወደ መደበኛ ሕይወታችንና ወደ ልማት መግባት በእጅጉ ብልህነት ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ብዙ ሰዎች ማንነትን ከመሬት ጋር ያያይዙታል፡፡ ይህ ሙሉ በሙሉ ስህተት የሆነ ጉዳይ ነው፡፡ ምድር ለሰው ልጆች፣ ለአእዋፋት፣ ለዱር እንስሳት፣ ለእፅዋት፣ ወዘተ የተሰጠች የጋራ ሀብት እንጂ ይኼ መሬት የእከሌ ነው እነ እከሌ ከዚህ ውጡ የሚባለው አስተሳሰብ ያረጀ፣ ያፈጀና ሙሉ በመሉ ሊወገድ የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡

እዚህ ላይ ግን እነ እከሌ ይህንን ቦታ ቢያስተዳድሩት የተሻለ ነው ማለት ለልማትም ለዕድገትም በእጅጉ ጠቃሚ በመሆኑ፣ አስተዳደራዊ ክልል ወይም ፌዴራላዊ አስተዳደር መመሥረት በእጅጉ ዘመናዊነት ነው፡፡ በተረፈ እነ እከሌ እዚህ መብት የላችሁም ይህ መብት የተፈቀደው ለእነ እከሌ ብቻ ነው ማለት የሚያስከትለው አደጋ እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ ሁላችንም በጋራ ልንዋጋው ይገባል፡፡

ለምሳሌ ብንወድ የደቡብ ሱዳን ሕዝቦች ልዩነታቸውን ወደ ጎን ትተው ተፈጥሮ የሰጣቸውን የነዳጅ ሀብታቸውን እየሸጡ በሰላም መኖር ሲችሉ በማይረባ የሥልጣን ሽኩቻ ሕዝባቸውን ለረሃብና ለስደት ዳርገው አገሪቱ ወደ አስፈሪ መንገድ እየተጓዘች ትገኛለች፡፡ ያስከተለውም ችግር ለእኛና ለሁሉም ጎረቤት አገሮች እየተረፈ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለደቡብ ሱዳን ችግር በዋናነት ተጠያቂ የማደርገው የኢጋድ አባል አገሮችንና ኃያላን መንግሥታትን ነው፡፡ ደቡብ ሱዳን እንደተመሠረተች የኢጋድ አባል አገሮችና ኃያላን መንግሥታት ቶሎ ቶሎ መንግሥታዊ መዋቅር እንዲመሠረትና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት እንዲመሠረት በቂ ግፊትና ጥረት ባለማድረጋቸው ነው፡፡ ደቡብ ሱዳን ለዚህ ብጥብጥ ያበቃችው እስቲ አስቡት በምን ሁኔታ ነው? አንድ አገር በሁለት ኃያል መሪዎች የሚመራው፣ አንድ አገር የፈለገውን ያህል ብሔር ሕዝብ ይኑራት የግድ አንድ ጠንካራ አመራር የሚሰጥ ሰው ወይም ኃይል ነጥሮ መውጣት አለበት፡፡ አለበለዚያ ጭቅጭቅና አለመግባባት ስለሚኖር የመንግሥት ሥራ በምንም ሁኔታ መተግበር አይቻልም፡፡ በመሆኑም ከላይ የተጠቀሱት አካሎች ይህ እንዲሆን መጎትጎትና ከፊት መምራት ሲገባቸው ይህንን ባለማድረጋቸው፣ አሁን ያለው የደቡብ ሱዳን አሳዛኝ ችግር ሊከሰት ችሏል፡፡

ዛሬ ዓለማችን አንድ መንደር እየሆነች ባለችበት ጊዜ ኢሕአዴግ ላለፉት 25 ዓመታት ለማንነት የተጋነነ ትኩረት በመስጠቱ፣ አሁንም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ድህነትና ኋላ ቀርነት መገለጫ እንደሆነ ቀጥሏል፡፡ በመሠረቱ አንድ ጉዳይ በየጊዜው በሬዲዮና በቴሌቪዥን እየተጋነነ ሲነገር በተለይ ባልተማረው ሰፊ ሕዝብ ዘንድ እንደ ጥሩ ነገር እየተወሰደ፣ ሕዝቡም ያንን እያስተጋባ የሚቀጥልበት ሁኔታ መፈጠሩ የግድ ነው፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት በርካታ ስህተቶች ተሠርተዋል፡፡ ለአገራችንም ሕዝቦች በተለይ ለወጣቱ ትውልድ የማይጠቅመውን ነገር ነው ስናስተምረው የኖርነው፡፡ ውጤቱንም አሁን እያየነው ነው፡፡ በእኔ እምነት ብሔርተኝነት በእጅጉ ቅንጦት ነው፡፡ በምንም ሁኔታ መሠረታዊ ጉዳይ አይደለም፡፡ እንኳን ብሔርተኝነት ሃይማኖት፣ ፍልስፍና፣ ወዘተ ቅንጦት ናቸው፡፡

ለምሳሌ አንድ የክርስትና ወይም የእስልምና እምነት ተከታይ ቤቱ የሚበላ ሳይኖረው ወደ ቤተ ክርስቲያን ወይም ወደ መስጊድ አይሄድም፡፡ የሰው ልጅ ስለተለያዩ ነገሮች መፈላሰፍ የጀመረው ሰው ከተፈጠረ ከብዙ ሚሊዮን ዓመታት በኋላ ነው፡፡ የሰው ልጆች እንደ ሰው በምድር ላይ መኖር ከጀመርን ከሦስት ሚሊዮን በላይ ዓመታት ነው ያሳለፍነው፡፡ ቋንቋ መናገር ግን ከጀመርን ገና 100,000 ዓመት ብቻ ነው፡፡ ይህ በቅርቡ የወጣ አንድ ጥናት ያረጋገጠው ነው፡፡ የሰው ልጆች ቋንቋን ለመናገር የሚያስችለን አውታረ ድምፅ (Vocal cord) በዝግመተ ለውጥ ሒደት ውስጥ አልፎ ቋንቋ መናገር እንድንችል ያደረገን ከላይ ከተጠቀሰው ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ ሃይማኖት ደግሞ በተለይ ሰማያዊ አምላክ አለ ብለን ማመን ከጀመርን ገና ሦስት ሺሕ (ሦስት ሺሕ) ዓመታት እንኳን አልሞሉም፡፡ በመሆኑም የመላው ዓለም ሕዝቦች አንድ ዓይነት ማንነት ኖሮን ለብዙ ሚሊዮን ዓመታት ኖረናል፡፡ ስለዚህ በዚህ ከቀጠልንበት የተሻለ ነው ብዬ ነው የማምነው፡፡

በተለይ ደግሞ እንደ ኢትዮጵያ ባለ እጅግ ኋላ በቀረ ማኅበረሰብ ውስጥ እየኖርን፣ ይህንን ቅንጦት የሆነውን ማንነት ለማጉላት መንቀሳቀስ የለየለት ስህተት መሆኑን በአስቸኳይ ልንገነዘበው ይገባል፡፡ ለልዩነት ቦታ እየሰጠን አላስፈላጊ ምኞት ውስጥ እየገባንና ንብረት እያወደምን ወደ ኋላ ስንሄድ ተጠቃሚ የሚሆኑት፣ የበለፀጉና ለአገራዊ ማንነት ትልቅ ቦታ የሰጡ መንግሥታት ብቻ መሆናቸውን ተገንዝበን ስህተታችንን ለማረም ብቃቱ ሊኖረን ይገባል፡፡

ዓባይን የምንገድበው እኮ በኢትጵያዊነት ስሜት ነው፡፡ ወደፊትም እንደ ዓባይ ያሉ በርካታ ተግባሮችን መፈጸም የሚያስችለንን ኢትዮጵያዊነት ከምንም በላይ ከፍ አድርገን ቦታ ልንሰጠው ይገባል፡፡

መንግሥት ደግሞ እንደ መንግሥት ከማንም በላይ ለመረጃ ቅርብ እንደመሆኑ መጠን ሰፊውን ሕዝብ የሚጠቅመውን መሞከር ይገባዋል እንጂ፣ ኋላ ቀር አስተሳሰብን በምንም ሁኔታ የመንግሥት አጀንዳ መሆን የለበትም፡፡ ከዓይን ቀለም፣ ከቆዳ ቀለም፣ ከሰውነት ቅርፅ፣ ከቋንቋ፣ ከሃይማኖት፣ ወዘተ መቶ ዓይነት ማንነቶችን በመፈለግ ችግር መፍጠር ይቻላል፡፡ ነገር ግን አንዳቸውም ጠቀሜታ የላቸውም፣ ለእኛ የሚጠቅመን ማንነት አያቶቻችን ያቆዩልንን ወፍራም ዳቦ የሚያበላን ኢትዮጵያዊ ማንነታችን መጠበቅና መንከባከብ ብቻ ነው፡፡

እዚህ ላይ ሊታወቅ የሚገባው ሌሎች የአፍሪካ አገሮችና ኢትዮጵያ የሚለዩበት አንዱና ትልቁ ጉዳይ፣ ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ቅኝ ገዢዎች የለጠፉባቸው ማንነት ለአንድነታቸውና ተቻችለው ለመኖር ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሞዛምቢካዊ፣ ‹‹እኔ ሞዛምቢካዊ ነኝ ቋንቋዬም ፖርቹጊዝ ነው፤›› ይላል፡፡ አንድ ጋናዊ ደግሞ፣ ‹‹እኔ ጋናዊ ነኝ ቋንቋዬም እንግሊዝኛ ነው፤›› እያለ አዲሱን ማንነቱን ለአንድነቱ መሠረት አድርጎ ለልማት ብቻ ይሠራል፡፡ ወደ ኤርትራ ደግሞ ስንመጣ ዛሬ ለኤርትራዊነት የተጋደሉት የቀድሞው ኢትጵያውያን የግንዛቤ እጥረት ሆኖ ነው እንጂ፣ እነዚህ ሕዝቦች በግንባር ቀደምትነት ኢትዮጵያዊነትን ለመፍጠርና ለመጠበቅ ታላቅ መስዋዕትነት የከፈሉ ናቸው፡፡ በጉርዓ፣ በጉንዲትና በዶጋሊ በተካሄዱ ጦርነቶች በወቅቱ ማንነትን መሠረት አንድም ኦሮሞ፣ አማራ ወይም ሌላ ብሔረሰብ ባልተካፈለበት ጦርነት ተዋግተው ኢትዮጵያ ለመጠበቅ አንፀባራቂ ድል ተጎናጽፈዋል፡፡

ታዲያ ያ ሁሉ ታሪክ ተረስቶ ዛሬ ኢትዮጵያዊነትን የሚያረክሱ አስተሳሰቦች በአንዳንድ የአገራችን ክፍልና በኤርትራ መንፀባረቁ በእጅጉ አሳዛኝ ነው፡፡ ጣሊያኖች ኤርትራ የምትባለውን ምድር ፈጥረው ለማስተዳደር የወሰኑበት ዋናው ዓላማ በወቅቱ የስዊዝ ቦይ ተከፍቶ የነበረ በመሆኑ፣ ያ መስመር በእስያና በአውሮፓ መሀል የሚደረገው ዋነኛ መንገድ ሆኖ በመገኘቱና ‹‹ኤርትራ›› የሚለውም ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የቀይ ባህር ስም በመሆኑ ነው፡፡ በተጨማሪም መላው ኢትዮጵያን ለመቆጣጠር እንደ መረማመጃ ለመጠቀም፣ እንዲሁም የመሀል አገር ነገሥታት ከዓለም አቀፍ መንግሥታት ጋር እንዳይገናኙ ለማድረግ በነበራቸው ዓላማ ምክንያት ነው፡፡

በመጨረሻም ማንነትን በተመለከተ በዚህ አጭር ጽሑፍ ብዙ ማለት ባይቻልም፣ በቅርቡ አንድ የወጣ ጥናት በሚቀጥሉት ከሃምሳ እስከ መቶ ዓመታት በዓለማችን ከሚገኙ ቋንቋዎች ከ50 በመቶ በላይ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እንደሚጠፉ ይጠቁማል፡፡ ይኼ ጥናት እንደሚያመለክተው ከእንግዲህ ወዲህ ቋንቋዎች ራሳቸውን ከጊዜው ሥልጣኔና ዕድገት ጋር እያሳደጉ መጓዝ ካልቻሉ የመጥፋት ዕድላቸው በእጅጉ የሰፋ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ማንነት ይፈጠራል፣ ያድጋል፣ ይጠፋል፡፡ ይህ ማለት ለሁላችንም የሚጠቅመን ከላይ እንደተጠቀሰው ለእኛና ለልጆቻችን የተሻለ ኑሮ ሊያኖረን የሚችል፣ በዓለም መድረክ ላይ ታዋቂ መንግሥት ሊያዳርገን የሚችለውን ማንነት መንከባከብ፣ መጠበቅና ማሳደግ በእጅጉ ብልህነት ነው፡፡ 

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

Standard (Image)

በተሃድሶው የተንቆረቆሩ ‹‹ሒሶች›› ማረፊያቸው የት ነው?

$
0
0

(ክፍል አንድ)

በልዑል ዘሩ

ገዥው ፓርቲና መንግሥት (ብዙ ጊዜ በተደበላለቀ ስያሜ ይጠራሉ) ተሃድሶ ያውም ʻጥልቅʼ የሚባለውን ማድረግ ከጀመሩ ከራርመዋል፡፡ ምንም እንኳን ኢሕአዴግ ላለፉት ሦስት ጉባዔዎቹ (ከስድስት ዓመታት) ወዲህ ጀምሮ የመልካም አስተዳደር ችግርና ሙስና ‹‹የሥርዓቱ አደጋ ነው›› ሲል ቢቆይምና ስለቁርጠኝነቱ ደጋግሞ ቢያወሳም ሥጋቱ የከራረመ ነበር፡፡

አንዳንድ ውስጥ አዋቂዎች ሥርዓቱ አሰፍስፎ የመጣውን ችግር እያወቀ ፈጥኖ ለማሻሻል ያልቻለባቸውን ምክንያቶች ያስቀምጣሉ፡፡ አንደኛው ከ2003 ዓ.ም. ወዲህ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ መታቀዱና እንደ ባቡር፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብና የስኳር ፕሮጀክት ዓይነት ግዙፍ ፕሮጀክቶች መጀመራቸው ግንባሩ ውስጡን ከማጥራት ይልቅ ወደፊት ብቻ እንዲያይ ማድረጉ ነው፡፡ እዚህ ላይ መንግሥትም ሆነ ገዥው ፓርቲ ከአቅም በላይ የተለጠጡ ዕቅዶችን ይፋ ሳያደርጉ በፀደይ ሕዝባዊ አብዮት ሲመቱ ከነበሩት የሰሜን አፍሪካና መካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ዕጣ ፈንታ አንፃርም ለማምለጥም ነበር ያሉ ነበሩ፡፡

ሁለተኛው በሥርዓቱ ውስጥ ተፅዕኖ ፈጣሪ የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ መሞታቸው የፈጠረው ከውስጥ ይልቅ ወደ ውጭ የማየት ዝንባሌ ነው፡፡ እዚህ ላይ በአንድ በኩል የእሳቸው ሕልፈተ ሕይወት ሥርዓቱን ለብተና አገርንም ለአደጋ ያጋልጣል የሚል ሥጋት የነበራቸው ሰዎች ነበሩ፡፡ በሌላ በኩል በግንባሩ ውስጥ የኃይል ሚዛኑን በመቀየርና በማመጣጠን በብዙኃኑ ተቀባይነት ያለው መንግሥታዊ ሥርዓት እንደሚዋቀር ተስፋም የነበራቸው፣ በውስጥም በውጭም ቁጥራቸው ትንሽ አልነበረም፡፡

እነዚህ ትልልቅ ክስተቶች የሥርዓቱን የተሃድሶ ጊዜ ከማራዘም ባሻገር አጉል መታበይና መዘናጋት ውስጥ የከተቱበት ሁኔታም ነበር፡፡ በተለይ በትልልቆቹ ዕቅዶችና በህዳሴው ግድብ፣ በመሀልም በአቶ መለስ ሕልፈት ወቅት የሕዝቡ ንቅናቄና ድጋፍ ከመቼውም ጊዜ በላይ ከፍ እያለ መምጣቱ ታይቷል፡፡ በተለይ ገዥው ፓርቲ ሀብትና ጊዜ በብዛት እያባከነባቸው ባሉ ልዩ ልዩ በዓላትና ሥነ ሥርዓቶች ላይ የተለያዩ ደጋፊ አደረጃጀቶች (ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የነዋሪ ፎረሞችና ሊጎች) የሕዝቡን ፍላጎት ጋርደው አረበረቡ፡፡ ከወረዳ እስከ ክልሎች የሙሉ ጊዜ ሠራተኛ ሆነው በደመወዝ የተቀጠሩ የየብሔረሰቡ የባህል ቡድኖችና ኪነቶች ብሔረሰብ እየወከሉ በየመድረኩ አሸበሸቡ፣ ብዙ ተናገሩ….፡፡

ከዚህ ሁሉ በላይ በድርጅቱም ሆነ በመንግሥት መዋቅሩ አድርባይነትና ኪራይ ሰብሳቢነት ተስፋፋ፡፡ በብሔረሰብ፣ በሃይማኖትና በጥቅም ዙሪያ መሰባሰብና አገራዊ እሴትን መግፋት ‹‹ትክክለኛ›› ተግባር መሰለ፡፡ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና አሳታፊነትን የመሳሰሉ የመልካም አስተዳደር እሴቶች የወረቀት ጌጥ ብቻ ሆነው ቀሩ፡፡ በኢሕአዴግ ስም መነገድ፣ መሞዳሞድና የግል ጥቅምን ማካበት መጠኑ ይለያይ እንጂ ዋነኛው የዘመኑ መገለጫ መሰለና አረፈው፡፡ በዚያው ልክ ሥርዓቱን ሊገዳደሩ የሚችሉ የዴሞክራሲ ተቋማትና የፖለቲካ ድርጅቶች ተሽመደመዱ፣ ተዳከሙ፡፡

ሁለተኛው ተሃድሶ መደረግ ከነበረበት ቢያንስ ስድስትና ሰባት ዓመታት ባክነዋል ብያለሁ፡፡ በእነዚህ ጊዜዎች ውስጥ በአገሪቱ ሰላም ነበር፡፡ ልማትም (መንገዶች፣ የከተሞች የቤት ግንባታዎች፣ ባቡርና ኃይል ማመንጫዎችን ጨምሮ፣ ዩኒቨርሲቲዎችና የጤና ተቋማት) ተስፋፍተዋል፡፡ በመንግሥት ተሠርቷል፡፡ በፍጥነትና በአቋራጭ የበለፀጉትን ጨምሮ ሕይወታቸው የተቀየረ ዜጎችም ቁጥራቸው ትንሽ አይደለም፡፡ ስለዚህ አገሪቱና ሕዝቦቿ ‹‹አድገዋል›› የሚለው በምጣኔ ሀብት መመዘኛ ቢያወዛግብም የልማት መፋጠኑን መደበቅ ፈጽሞ አይቻልም፡፡

በዚህ መልካም እውነታ ውስጥ ግን ሌላ መጥፎ እውነትም እየተብሰከሰከ ከፍ ያለ ቁጣ ቀስቅሷል፡፡ አንዱና ዋነኛው ፀረ ዴሞክራሲያዊነት በሥርዓቱም ሆነ በአገሪቱ ውስጥ ጥርስ እያወጣ መምጣቱ ነው፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች መዳከም፣ የአማራጭ ሐሳቦች መንጠፍ፣ የመገናኛ ብዙኃን መድቀቅና መበተን፣ የመደራጀት፣ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ከወረቀት አለማለፍ፣ ብዝኃነት በሞላበት አገር ገዥው ፓርቲ ‹‹መቶ በመቶ›› ምርጫ ማሸነፍ … የለየለት የፀረ ዴሞክራሲ ማሳያ ሆኑ፡፡ ይህም የዴሞክራሲን በር ወደ መዝጋት አቀረበው፡፡

በሌላ በኩል በሥርዓቱ ውስጥ የነገሠው የመልካም አስተዳደር ዕጦትና ሙስና (በዚህ ላይ አሉባልታው ተጨምሮበት) ሕዝቡን ክፉኛ አሳዘነው፡፡ በየመሥሪያ ቤቱ ነፍሰ በላው ተሰገሰገ፡፡ በየመሥሪያ ቤቱ በተሾመ ኃላፊ ስምና በቡድን በተደራጀ ኃይል  አዛዥነት ሌብነት ተጧጧፈ፡፡ እንደ መሬት፣ ኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ ኮንትሮባንድና የገንዘብ ዝውውርን በመሳሰሉ ከፍ ያለ የአገር ሀብት የያዙ መስኮች ተዋናዮቹ ጥቂቶች ጥገኞች ሆኑ፡፡ ተገልጋዩም ሕዝብ ከዚህ በመነሳት ሥርዓቱ ‹‹የእነ እገሌ ነው›› የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሶ እርሙን አወጣ፡፡ በእጅ መሄድ ብቻ የዜግነት መብትም መሰለ፡፡

ከላይ ካነሳኋቸው ሁለት ሕገወጥነቶች ተነጥለው የማይታዩ የሕዝብ ቅሬታ ቆስቋሾች በከተሞች በመልሶ ማልማትና በሕገወጥ ግንባታ ስም ሰፋ ያለ መፈናቀል ታየ፡፡ በዚያው ልክ አዳዲስ በሚመስሉ ሠፈሮች በአብዛኛው በሥርዓቱ ውስጥ የተሰገሰጉ ጥገኞች ባለ ሕንፃና የትልልቅ ሆቴል ባለቤት ሆኑ፡፡ ሠርተውም ይሁን ተመቻችቶላቸው ሰፋ ያለ ሀብት በጥቂቶች እጅ የገባ መሰለ፡፡ ከዚህ በተቃራኒ በሌላ አመለካከት ወገን የሚጠረጠሩ ባለሀብቶች ተሰደዱ፣ ወይም እየከሰሙ መጡ…፡፡

ጤነኛ ለማይመስለው የሀብት ክፍፍል ሌሎች ማሳያዎችን ለመጠቃቀስ ያህል በቢሊዮን ብሮች የሚያንቀሳቅሱ ከፍተኛ ኮንትራክተሮችና ብዙዎቹ የመስኩ ባለሀብቶች በአንዴ የከበሩ ዘመነኞች ሆኑ፡፡ በሶማሌ፣ በጋምቤላ፣ በቤንሻንጉልና በሁመራ አካባቢ በሰፋፊ እርሻ ‹‹የተሰማሩ›› አብዛኞቹ ሥርዓቱ ውስጥ ለመሸጉ ሙሰኞች ቅርበት ያላቸው ግለሰቦች ናቸው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ለዘርፉ የተመደበውን ከፍተኛ ብድር ለከተማ ቤት፣ ለማሽነሪ ኪራይና ለንግድ ሥራ ያዋሉትም ትንሽ እንዳልሆኑ ታወቀ፡፡ ‹‹ሜካናይዝድ እርሻም›› የተወራለትን ያህል ሳይሆን ቀረ፡፡

በአዲስ አበባና በዙሪያው ባሉ የኦሮሚያ ታዳጊ ከተሞች መሬት ተቸበቸበ፣ ተሸነሸነ፡፡ በዚህም ውስጥ በተለይ ካድሬዎችና የሥራ ኃላፊዎች በገፍ ሀብት አግበሰበሱ፡፡ ቢዘገይም ቡራዩ፣ ሰበታ፣ ለገጣፎና ሱሉልታን የመሳሰሉ ከተሞች ከንቲባዎችና የመሬት ላይ ኃላፊዎች ተጠያቂ ተደረጉ፡፡ ግን ከደረሰው ጥፋትና የሕዝብ ሀብት ንጥቂያ ጋር ፍፁም ሊጣጣም የማይችል ዕርምጃ ነበር፡፡

በገቢዎችና ጉምሩክ መስክም ተመሳሳይ ነው፡፡ ዋነኛው ኮንትሮባንዲስት ከመንግሥት መዋቅር ውስጥ የወጣው ወይም የተሻረከው ሆነ፡፡ የቀረጥ ነፃ ውንብድናን ጨምሮ የታክስ ማጭበርበርና ሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር ለጥቂቶች የተፈቀደ ‹‹ሕጋዊ ወንጀል›› መሰለ፡፡ በ2005 ዓ.ም. በሕገወጥ መንገድ የግንባታ ብረት አስገብተው በፀረ ሙስና ተከሰው የነበሩና ጉዳያቸው እስካሁን ለሕግ ያልቀረበ 112 የሚደርሱ ‹‹ጮሌዎች›› ውስጥ ብዙዎቹን የኮሚሽኑ ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል›› መጽሔትም አቅርቦዋቸው አይተናል፡፡

ከእነዚህ ትልልቅ ዘረፋዎች በላይ አነስተኛ ሙስናው ዜጎችን እያማረረ ነው፡፡ የኤሌክትሪክ ኃይል ቢስፋፋም መብራት ለማግኘት ‹‹ጉቦ›› ተፈለገ፡፡ የመጠጥ ውኃ፣ ቴሌኮምና የውስጥ ለውስጥ መንገዱም ያው ሆነ፡፡ ፖሊስ፣ ትራፊክ ፖሊስ፣ ፍርድ ቤት የሚሰማው ድምፅ ቀስ በቀስ ርትዕና ፍትህን እየተወ ‹‹የነጋዴ ባህሪ መሰለ››፡፡ የጤና፣ የባህልና ቱሪዝም፣ የንግድ ቢሮዎች ከብቃት ማረጋገጫ፣ ፈቃድ ከመስጠትና ከማደስ ጋር መሞዳሞድን ለመዱ፡፡ ደንብ ማስከበር እንኳን በጥቅም የሚደለል መዋቅር ሆነ፡፡ ሕዝብ የሚገለገል ሳይሆን አገልጋይ እየሆነ የመጣበት ፖለቲካዊ ኢኮኖሚ አንሰራራ፡፡

ይህ ችግር መጠኑና ዓይነቱ ይለያይ እንጂ በሁሉም አካባቢዎች እንደተንሰራፋ መንግሥት አውቋል፡፡ ገዥው ፓርቲም በጉባዔ ጭምር ደጋግሞ እያነሳ ተማምሏል፡፡ ግን ፈጣንና ሥር ነቀል ለውጥ አልመጣም፡፡ እንዲያውም መንግሥታዊ ማናለብኝነት እያቆጠቆጠ መጣ፡፡ ኃፍረትና ሕዝብ ማዳመጥም ተረሳ፡፡

ለአብነት ያህል በመልካም አስተዳደር ዕጦትና በሥራ አጥነት የተንገሸገሸውን ወጣት ብሶቱን አዳምጦ ችግሩን ከመፍታት ይልቅ፣ በጋራ ማስተር ፕላን ስም ከቦታው የሚፈነቀልበት ሥጋት ተደቀነ፡፡ እዚህ ላይ ፕላኑ ምንም ያህል አገራዊ ፋይዳ ቢኖረውም ሕዝቡ ከገባበት ሥጋትና ውዥንብር ሳይወጣ ለመተግበር መመኮሩ ‹‹የመንግሥታዊ ማናለብኝነት›› ውጤት ነው፡፡ በዚህ ላይ በአገርም ውስጥ ሆነ በውጭ ያለው ተቃዋሚ ኃይል የተደረገውንም ያልተደረገውንም እየጨማመረ ሕዝቡን ‹‹መሬትህ ተዘረፈ›› ሲል ቀስቅሶታል፡፡ ያኔ ከተማ፣ ገጠር ሳይል ለጥቅሙና ለመብቱ ተነሳ (በነገራችን ላይ በቀዳሚው የሕዝብ እምቢተኝነት አብዛኛው ሕዝብ ተሳትፏል ማለት ይቻላል)፡፡

በአማራ ክልልም ሕዝቡ ‹‹የተገፋ›› እንዲመስለው የሚያደርጉ ብርቱ ዘመቻዎች በራሱ በገዥው ፓርቲና በመንግሥት እንዝላልነት (አውቆ የተኛ አካሄድ) ተፈጸመ፡፡ ለአብነት በሰሜን ጎንደር የተነሱ የማንነት ጥያቄዎች፣ የክልልና የወረዳ የወሰን ጉዳዮች ሲድበሰበሱ ከርመው የቀውሱ ዋነኛ ክብሪት ሆኑ፡፡ በሚያሳፍር ደረጃ በአፍሪካ ትልቅ የሚባሉ ተራራና ኪነ ሕንፃ ለሕዝብ በተበተኑ ሰነዶች የሚገኙበት ቦታ እየተቀየረ ተሠራጩ፡፡ ብሔርና ክልል የአሁኒቷ ኢትዮጵያ ዋነኛ መገለጫ በሆኑበት ጊዜ የልማት ሥርጭቱ ለኢፍትሐዊነት ማጣቀሻ ሆነ፡፡

እነዚህና ሌሎች ጥቃቅን የሚመስሉ ክፍተቶች ሕዝብና መንግሥት እንዲቃቃሩ አደረጉ፡፡ ምንም እንኳን ይህንን ክፍተት ተጠቅመው አክራሪ የዳያስፖራ ፖለቲከኞችና ማኅበራዊ ድረ ገጾች ሕዝባዊ እምቢተኝነቱን ለማባባስ ቢሠሩም፣ የቀውሱ መነሻም መድረሻም የመንግሥት የተሃድሶና የለውጥ መንቀርፈፍና ቁርጠኝነት ማጣት ነው ለማለት ይቻላል፡፡

ከላይ በስፋት የተንደረደርኩባቸው መሠረታዊ ጉዳዮች ልቦለዶች አይደሉም፡፡ ወይም በግል እምነት የተቀጣጠሉ የሥርዓቱ ጉድለቶች እንዳልሆኑም ለማረጋገጥ እወዳለሁ፡፡ ይልቁንም ራሱ ገዥው ፓርቲና መንግሥት ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ ያስፈልገናል፣ ተሃድሶውን ወቅቱን ጠብቀን በእንጭጩ ባለማረማችን በሕዝብ ግፊት ተገደን የገባንበት ሆኗል፤›› ካሉ በኋላ በተለያዩ መድረኮች የተነገሩ ናቸው፡፡ ብዙዎቹም በትልልቁ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ጭምር ተቀባይነት አግኝተው ‹‹እውን እስካሁን የት ነበርን?!›› እስከማለት አድርሰዋል፡፡

ከሥርዓቱ ሰዎች ውጪም በአንድ ወቅት በኃላፊነት ላይ በነበሩ ሰዎች፣ ሚዛናዊ በሆኑ ታዛቢዎችና በምሁራን በቃልም በጽሑፍም የተነሱ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ሥርዓቱን ከድተው ወይም ተነጥለው የሄዱ የ‹‹ቀድሞ›› ባለሥልጣናትም ቢሆኑም ምንም እንኳን ለራሳቸው ወቅታዊ የፖለቲካ ትርፍ ሲሉ የሚለጥጡት ጉዳይ ቢኖርም፣ ችግሮቹን በተጨማሪ ማስረጃዎች እያደመቁ የሕዝቡን መከፋት አባብሰውታል፡፡

ይህ ሁሉ በመሆኑ መንግሥት ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ላይ ነኝ እንኳን ቢል ያልረገበው የሕዝብ ቁጣ (በኋላ የጥፋት አካሄድ መላበሱ ባይቀርም) ተቀስቅሶ ብዙ ጥፋት ደረሰ፡፡ በግርድፍ መረጃ በ11 ወራት ብቻ ከ1,500 በላይ ዜጎችና የፀጥታ ኃይሎች ሕይወት አለፈ፡፡ በኦሮሚያ (ሰበታ፣ አምቦ፣ አርሲ ነገሌ፣ ሻሸመኔ፣ ባቱ፣ ነቀምት፣ ምሥራቅ ሐረርጌ፣ ደቡብ ምዕራብ ሸዋ…) በሰሜንና ደቡብ ጎንደር፣ በባህር ዳርና በምዕራብ ጎጃም ወረዳዎች፤ በደቡብ ክልል ኮንሶና ዲላ አካባቢ በሺዎች የሚቆጠሩ የግለሰብ ቤቶችና ድርጅቶች ወደሙ፡፡ የመንግሥት መዋቅሮችና ግምታቸው በቢሊዮን ብር የሚሰላ ኢንቨስትመንቶችና ኩባንያዎችም እንዳይሆኑ ሆኑ፡፡

ይኼ ጥፋት መንግሥትን በአገር አቀፍ ደረጃ እስከ ስድስት ወራት የሚዘልቅ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ (State of Emergency) ለማውጣት አስገደደ፡፡ ሕገ መንግሥቱን የተካ ‹‹ወታደራዊ›› የሚመስል የመንግሥት አስተዳደር በመዘርጋት ጥፋትና ሞቱ ቢቆምም፣ አሁንም ግን በአገሪቱ ላይ አሉታዊ ገጽታ እንዳረበበ ነው፡፡ በተለይ በሕዝቡ ውስጥ የፀጥታ ኃይሎች አዋጁን ለጥጠው እንዳይጠቀሙ፣ የዜጎች የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳይፈጸም የሚታይ ሥጋት አለ፡፡ በፖለቲከኞች በኩልም የመሰብሰብ፣ በሕጋዊ መንገድ የቅስቀሳ ሥራ መሥራትና የሐሳብ ነፃነት መገደብ እንደ ጉዳት ይነሳል፡፡ ከሁሉ በላይ ምንም እንኳ ሰሞኑን ማሻሻያ ተደርጎ ዕገዳ ቢነሳም፣ ዲፕሎማቶችና ቱሪስቶች ከዋና ከተማዋ 40 ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውጪ መሄድ እንደማይችሉ ተደርጎ መነገሩ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሮ ነበር፡፡

ይህ ነባራዊ ሀቅ ባለበት ሁኔታ አሁንም ገዥው ፓርቲና መንግሥት የ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ጉዳያቸውን የዘነጉት አይመስልም፡፡ በቅርቡ እንዳየነው ለማሻሻያና ለለውጥ ዕርምጃው አንድ ጅምር ሊባል የሚችል ሹም ሽር ተካሂዷል፡፡ በተለይ በኦሮሚያ ክልልና በፌዴራል መንግሥት ደረጃ በተካሄደ የካቢኔ አባላት ሹመት አዳዲስና በፖለቲካው ውስጥ ያልሰለቹ ፊቶች ታይተዋል፡፡ ምሁራን በርከት ብለው መሾማቸውም በሕዝቡ ውስጥ የተደበላለቀ ስሜትን ፈጥሯል፡፡ በቀጣዮቹ ቀናትም አማራ፣ ትግራይና ደቡብ ክልሎች እንዲሁም ታዳጊዎቹ ቆላማ ክልሎችም የሚያደርጉት ሹም ሽር እንደሚኖር ይጠበቃል፡፡

አሁን በሕዝቡ እየተነሳ ያለው ‹‹ተጠየቅ›› ግን አንዱ ይህ ሹም ሽር እስከ ታችኛው የመንግሥት እርከን ታስቦበት ይወርዳል ወይ? የሚለው ነው፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርን በመሰሉ በአድርባይነትና በሙስና የተለወሱ ብሎም ሕዝብ ያማረሩ መዋቅሮች እንዴት ሊታደሱ ይችላሉ? የሚል ጉጉት አለ፡፡ በሌላ በኩል እስካሁን በተካሄዱ ግምገማዎች፣ ለሕዝብ ጭምር ይፋ በተደረጉ የብልሹ አስተዳደሮች መፈጠር ማሳያ ጥናቶች የተነሱ ኃጢያቶችና የተንቆረቆሩ ‹‹ሒሶች›› ማረፊያቸው የት ነው? ባለቤታቸውስ እነማን ናቸው? እንዴት ተጠየቁ? ምን ዕርምጃና እርምትስ ተወሰደ? … የሚል ብርቱ ጥያቄም ይነሳል፡፡

በቀጣዩ ክፍል ሁለት ምልከታዬ በተለይ ኢሕአዴግን በመሠረቱት አራቱ ብሔራዊ ድርጅቶች ውስጥ ከተነሱ ሒሶች አንፃር ተሃድሶውን ራሱ ለመገምገም እሞክራለሁ፡፡ ሊወሰዱ የሚችሉትን ዕርምጃዎች ለማመልከትም ይሞከራል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው Zeru@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡  

         

         

Standard (Image)

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ወዴት ነው ያለኸው?!

$
0
0

በይትባረክ ምሥጋናው

የግል የባንክ ኢንዱስትሪው ኢትዮጵያ እንደ አገር እያስመዘገበች ላለችው ፈጣን ዕድገት እንደ አንድ መታያ አድርገው የሚዘክሩት በርካታ ምሁራንና የዓለም የገንዘብ ድርጅቶች እንዳሉ ከተለያዩ መጣጥፎችና መረጃዎች መመልከት ይቻላል፡፡ የእኔም ግምገማ በአብዛኛው ከእነዚህ ምሁራን ጋር ይመደባል፡፡

በእርግጥም የግል ዘርፉ ኢኮኖሚ እጅግ አመርቂ እመርታ ካሳየባቸው መስኮች መካከል የባንክ ኢንዱስትሪው ተጠቃሽ ነው፡፡ ዘርፉ በአሁኑ ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩ የሥራ ዕድሎችን ክፍት በማድረግ፣ በአገሪቱ ውስጥ ከሚገኙ ዋነኛ ከሚባሉ ቀጣሪ ተቋማት መካከል ግንበር ቀደም ሆኗል፡፡ የአገሪቱ የቁጠባ ባህል እንዲዳብርና እንዲያድግ በርካታ ቅርንጫፎችን በመክፈት ተደራሽነቱን ከማረጋገጡም በላይ፣  በተለያዩ የግንዛቤ ፈጠራዎችና የውድድር መንፈስን በሚያነቃቁ ሽልማቶች አማካይነት የቁጠባ ባህል እንዲሰርፅ ከፍተኛ ሥራ አከናውኗል፡፡ በመንግሥት ባንኮች አማካይነት የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ሽፋን የማያገኙ የንግድ እንቅስቃሴዎች ብድርና የውጭ ምንዛሪ እንዲያገኙ በማድረግ ድርጅቶቹ ቀጭጨው እንዳይቀሩ ከማድረጉም በላይ፣ እነዚህ ድርጅቶች እንዲስፋፉና በተራቸውም ተፈላጊውን አገልግሎት ለማኅበረሰቡ እንዲያቀርቡ፣ በተጓዳኝም መጠነ  ሰፊ የሆነ የሥራ ዕድል እንዲፈጠሩ ድጋፍ አድርገዋል፡፡

ወደፊት የአገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት በከፍተኛ መጠን በማሳደግና በአገራችን እየተካሄደ ያለውን ልማትና ዕድገት ሁለንተናዊ በሆነ መንገድ በመደገፍና የኃይል ቅርበቱን አስተማማኝ በማድረግ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ለተረጋገጠለት የታላቁ የዓባይ ግድብ ኃይል ማመንጫ፣ የግል ባንኮች ዝቅተኛ ወለድ በመክፈል ከፍተኛውን መዋጮ በማድረግ ጥቅማቸውን አሳልፈው በመስጠት የሕዝብ አጋርነታቸውን በተግባር አሳይተዋል፡፡

የግል ባንኩ ዘርፍ የአገሪቱ ልማት ብሎም ዕድገት ይበልጥ እንዲጎለብትና የዜጎች ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ ሰፋፊ ዕድሎችን  በማመቻቸት መጠነ ሰፊ የሆነ ገንቢ ሚና  የመጫወቱን ያህል፣ ከዕለት ወደ ዕለት እየጠነከረ የመጣውን ውድድር መቋቋም ያቃታቸው አንዳንድ ባንኮች የአሠራር ሥልታቸውን በማዘመንና አዳዲስ አሠራርን በመቀየስ ከመወዳደር ይልቅ፣ ሕገወጥ ድርጊት በመፈጸም አንዱስትሪው ያሳየውንና ወደፊትም ለማሳየት የሚችለውን መልካም ዕድል የሚያጨነግፍ ተግባር ውስጥ በመዘፈቅ ላይ መሆናቸውን የሚጠቁሙ ድርጊቶች እየተንፀባረቁ ነው፡፡

ይህንን ተግባር በእንጭጩ ለመግታት በብሔራዊ ባንክ የባንኮች ቦርድ አባላት እስከማገድና የአንዳንድ ባንኮችን ፕሬዚዳንቶች እስከማባረረር የደረሱ አንዳንድ ጠንካራ ዕርምጃዎች የታዩ ቢሆንም፣ በተለይ ጀማሪ ባንኮች ውድድሩ የፈጠረውን ጫና በሕጋዊ ውድድር ተቋቁሞ ተፈጥሮአዊ ዕድገታቸውን ጠብቀው ከማደግ ይልቅ፣ አቋራጭ ሥልቶችን በመጠቀም ዘለቄታ የሌለው ትርፍ ማስመዝገብን እንደ መፍትሔ ይዘው እንደቀጠሉ በግላጭ እየታ ነው፡፡

ከዚህ ቀደም አንድ የግል ባንክ ይህንኑ የውድቀት መንገድ በመከተል የሌለውን የውጭ ምንዛሪ እንዳለው በማስመሰልና የራሱ ያልሆኑ ደንበኞችን በማሳሳት ሌተር ኦፍ ክሬዲት በጨበጣ እንዲከፍቱ በማድረግ በኢንዱስትሪው ውስጥ የፈጠረው ሕገወጥ እንቅስቃሴ ከፍተኛ የሆነ መናጋት ከመፍጠሩም በላይ፣ የተለያዩ የውጭ አገር ባንኮች ከኢትዮጵያ ባንኮች ጋር ላለመሥራት ውሳኔ ላይ የደረሱበት፣ አንዳንድ ምርት አቅራቢ አገሮች የንግድ አታሼዎቻቸውን ወደ ኢትዮጵያ ልከው ከመንግሥት ጋር እስከመጋጨት የደረሱበት ሁኔታ መፈጠሩ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

ይህ ተግባር እንደ ቋያ እሳት በመቀጣጠል ከጥቂት ባንኮች በስተቀር አብዛኛዎቹ ባንኮች ደንበኞቻቸውን ለመከላከልና ከራሳቸው ጋር ለማቆየት ሲሉ፣ በገቡበት የግዴታ ውዴታ ጦርነት በኢንዱስትሪው ውስጥ በርካታ ጉዳቶች ተከስተዋል፡፡ ቁጥራቸው በርካታ የሆኑ ነጋዴዎችም ለዘመናት ደክመው ከተጎዳኙዋቸው የውጭ ዕቃ አቅራቢዎቻቸው ጋር የነበራቸውን ውል እንዲያቋርጡ ተገደዋል፡፡ ብሔራዊ ባንክ ዘግይቶም ቢሆን ተጠያቂ ባላቸው የባንክ አመራሮች ላይ ዕርምጃ ባይወስድ ኖሮ፣ ከግለሰብ ነጋዴዎች ጉዳይነት አልፎ በአገሪቱ ላይ አንዣቦ የነበረው በመልካም አፈጻጸም ላይ የተመሠረተው የውጭ ምንዛሪ እንቅስቃሴ አደጋ ላይ ይወድቅ አንደነበር ጥርጥር የለውም፡፡  

ኢንዱስትሪው ለአገሪቱ ኢኮኖሚ መሳለጥ፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ እንዲሁም ለቁጠባ ባህል ያለው ወሳኝ ሚና ይህን ያህል የገዘፈ ከሆነና ውድቀቱም የበርካቶችን ሕይወት ከማተረመስ አልፎ የአገሪቱን ንግድ ሚዛን በማዛባትና ተዓማኒነትን በመሸርሸር ከዓለም አቀፍ ባንኮች ጋር ያለውን በመልካም ግንኙነት (In Good Faith) ላይ የተመሠረተ የግብይት ሥርዓትን እንደሚንድ ከታወቀ፣ ችግሩ በአፋጣኝና ገጽታውንም ከመቀየሩ በፊት በወቅቱ መፍትሔ ሳያገኝ ለምን ቀረ የሚለው ጥያቄ የበርካቶች ራስ ምታት እንደሆነ ቀጥሏል፡፡

ከላይ የተዘረዘረው ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቼ የኢንዱስትሪውን ውድቀትና ኪሳራውን አሊያም ተስፋውን እንደ መነሻ እንድተነትን፣ ብሔራዊ ባንክም በተራው ራሱንና በሥሩ የተኮለኮሉትን ባንኮች በጥንቃቄ እንዲፈትሽ የሚያመላክት ጥያቄ እንዳጭር ያደረገኝ አሳሳቢ ሁኔታ ላይ እንድደርስ ያስገደደኝ አሥጊ ሁኔታዎችን ለመታዘብ በመብቃቴ ነው፡፡

ዛሬ ኢንዱስትሪው በተለይም ደግሞ ትንንሽ አቅም ይዘው የተነሱት ባንኮች ካለፈው ስህተት ተምረዋል ወይ ቢባል? ከሚታየውና ከሚሰማው አኳያ የእኔ መልስ አልተማሩም ነው፡፡ ይህ ግን ጀማሪዎችም ሆኑ ነባር ባንኮች በኢንዱስትሪው ውስጥ ሕግና ሥርዓትን ጠብቀው በገበያ ሥርዓትና በውድድር የሚመሩ ባንኮችን የማይመለከት መሆኑን ግንዛንቤ እንዲወሰድልኝ በአክብሮት አሳስበለሁ፡፡

ችግሩ ፈርጀ ብዙ ነው፡፡ ከችግሮቹ መካከል በተለይ ተጠቃሽ የሆነው፣ ትንንሾቹ ባንኮች ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት ያለአቅሟ ውኃ ተግታ ዝሆንን ለማከል እንደተወጣጠረችው እንቁራሪት ያገኙትን ሁሉ በመሰልቀጥ ትልልቆቹን ለማከል ውጥረት ውስጥ መግባታቸው ነው፡፡ በዓመታዊ ስብሰባዎቻቸው ላይ ለባለቤቶቻቸው የሚገቡት ቃል አዙሪት እየሆነባቸው፣ ሕገወጡንም ሆነ ሕጋዊውን ሥራ እያፈራረቁ ለመተግበር አስገዳጅ ማነቆ ውስጥ ተዘፍቀዋል፡፡

ትልልቅ የሚባሉትም ባንኮች ቢሆኑ የነፃ ገበያ ሥርዓቱ በሚፈጥረው ዕድልና ውድድሩ በሚጠይቀው የአገልግሎት ጥራት ላይ ተመሥርተው በሕጋዊው የገበያ አቅም ላይ ከመወዳደር ይልቅ፣ በሕገወጥ መንገድ የሚካሄድ የውጭ ምንዛሪ ዝውውር ውስጥ እጃቸውን ሙሉ በሙሉ ዘፍቀው በባንኩ ባለቤቶች እጅ የዘንዶ ጉድጓድ እየለኩ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ይህንን ሕገወጥ ተግባር ሕጋዊ በማድረግም ከአንዱ ባንክ ወደ ሌላው በደላላ እየታገዙ ደንበኛን በማስኮብለል ተግባር ላይ በስፋት መሰማራታቸው አገር ያወቀው ፀሐይ የሞቀው እውነታ ነው፡፡ ይህንን ስል የትኞቹን ባንኮች እያነሳሁ እንደሆነ የእያንዳንዱ ባንክ ከፍተኛ አመራር ልቦናው እንደሚያውቀው እርግጠኛ ነኝ፡፡

እስካሁን እነዚህ ከላይ ያነሳኋቸው ችግሮች የየባንኮቹን ፕሬዚዳንቶች ወይም ከፍተኛ ኃላፊዎች ከሥራ እንዲሰናበቱ ከማድረግ ያለፈ ለጥፋታቸው ተመጣጣኝ ቅጣት የሚጥል አካሄድ ባለመኖሩ፣ ከፍተኛ ኃላፊዎቹ በሕገወጥ እንቅስቃሴው አማካይነት በአማላጅነትና በጥቅም ተጋሪነት በመሳተፍ የሚያግበሰብሱት ሀብት ከተሰጣቸው፣ የባንኩ ባለቤቶች የኃላፊነት አደራም ሆነ የአገሪቱ ኢኮኖሚ ሊፈጠርበት ከሚችለው አደጋ በላይ የሚያጓጓ በመሆኑ ከቀደመው ስህተት ለመማርም ሆነ ቢያንስ ከባንኩ ባለቤቶች የተሰጣቸው አደራ ቢቀር እንኳን ለአገር ከመቆርቆር የሞራል የበላይነት ተራ ለመሠለፍ እንኳን ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል› የባንክ አንዱስትሪው ባህል ሆኗል፡፡

ከባንኮች ጋር የቀረበ ግንኙነት ስላለኝ በብዙ ገዳዮች ላይ ማስረጃው ባይኖረኝም፣ መረጃ ግን በተፈለገው መጠን አለኝ፡፡ በተለያዩ ባንኮች ውስጥ ዓመታዊ ስብሰባም ሆነ ዝግጅት ላይ ስለምገኝ አጋጣሚውንም ተጠቅሜ  ከተሰብሳቢውም ሆነ ከደንበኛው መረጃ መቃረም የተለመደ ተግባሬ ነው፡፡ በዚህ ሒደት ውስጥ ከላይ እንደጠቀስኩት በመረጃ ለማስደገፍም ሆነ ስም ለመጥራት የሚያበቃኝ ተጨባጭ ነገር ባለመኖሩ (ሕገወጥ ሥራው በአብዛኛው የሚሠራው በከፍተኛ ሚስጥር በመሆኑ) ዝምታን መርጬ ነበር፡፡ በቅርቡ ግን ወደ ቶጎ ውጫሌ በግል ጉዳዬ በመሄዴ በወሬ ደረጃ የሰማሁት በተግባር እውነት መሆኑን ለማረጋገጥ ችያለሁ፡፡

ቶጎ ውጫሌ በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት ውስጥ የምትገኝ ትንሽ መንደር ነች፡፡ ቶጎ ውጫሌ በታሪክ ፊት ስትወሳ ግን እንደ ትንሽ መንደርነቷ ጠባብ አይደለችም፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የዜጎቻችን በርካታ መስዋዕትነት ያስተናገደች፣ እጅግ ስመጥር ጀግኖችን ያፈራች፣ የኢትዮጵያውያን አልገዛም ባይነት መገለጫ ነች፡፡

ዛሬ ግን ታሪኳ ሌላ ሆኗል፡፡ ይህች ትንሽ መንደር ከአቅሟ በላይ የባንኮች መናኸሪያ ሆኖለች፡፡ ቅርንጫፍ የሌለው ባንክ የለም፡፡ የባንክ ሠራተኛን ጥመርታ ከነዋሪዎቻ ጋር ብናሰላው እያንንዳነዱ ነዋሪ ሁለት ሁለት የባንክ ባለሙያ የሚደርሰው ይመስላል፡፡  የንግድ እንቅሰቃሴዋም በአብዛኛው በኮንትሮባንድ ዕቃ፣ በሕገወጥ የውጭ ምንዛሪና በሕገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ ተመሥርቶ የሚከናወን ነው፡፡ ታዲያ ለምን ይህንን ያህል የባንኮችን ትኩረት አገኘች የሚል ጥያቄ ለሚያነሳ መልሱ ከባድ ሊመስል ይችላል፡፡ እውነታው ግን ወዲህ ነው::

ቶጎ ውጫሌ ላይ የከተመው ወፈ ሰማይ ደላላ ዓላማው እንደየልምዱ የተለያየ ቢመስልም የኮንትሮባንድ ዕቃ፣ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና የዕፅ ማቀባባል ሥራ ማዕከል ያደረገው የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት፣ ሽያጭና ዝውውር ላይ ነው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ደላላ "በሙያው"የዚህ ወይም የዚያ ሥራ ደላላ ቢባልም ቀዳሚ ተግባሩ ግን በዚሁ ሕገወጥ እንቅስቃሴ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሪ ሕጋዊ እንዲሆን ወይም እንዲታጠብ (Money Laundering) ለማድረግ የውጭ ምንዛሪ ባለቤቶቹን ከባንኮቹ ጋር ማገናኘት ነው፡፡ ባንኮቹ በሕገወጥ መንገድ የተገኘውን የውጭ ምንዛሪ በሕጋዊ መንገድ እንደተገኘ በማስመሰል ወደ ባንክ ሥርዓት ውስጥ ያገቡታል፣ ወይም ያጥቡታል፡፡

ይህ እንግዲህ በወዳጅነት ቀርቤ መረጃ ከሰጡኝ ደላሎች የተገኘ መረጃ ነው፡፡ ይህንን እንድቀበል ጠቋሚ መነሻ የሆነኝ ደግሞ አንዳንድ ትንንሽ ባንኮች ያስመዘገቡት ትርፍ እመርታ ያሳየው ከተለመደው እንቅስቃሴ ይልቅ፣ በአንድ ዓመት ውስጥ ከተሰበሰበ ከፍተኛ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ላይ በመመሥረት መሆኑ ነው፡፡ የባንክ ኢንዱስትሪው ለእያንዳንዱ ባንክ ያለው የመቶኛ ድርሻ ይታወቃል፡፡ ሥሌቱ መሠረት የሚያደርገውም ባንኮቹ ባላቸው ቅርንጫፍ ብዛት፣ በኢንዱስትሪው ውስጥ በነበራቸው ቆይታ፣ ባላቸው ካፒታል፣ ተቀማጭ ሒሳብና በመሳሰሉት ነው፡፡ በዚህ ሥሌት መሠረት ትልልቆቹ ባንኮች ማሰባሰብ ከቻሉት በላይ ትንንሾቹ ባንኮች የውጭ ምንዛሪ ማሰባሰባቸው ሕጋዊ መሠረቱ ሊመረመር ይገባዋል የሚል አቋም አለኝ፡፡

ብሔራዊ ባንክ የሕዝብ ሀብትና የደንበኞችን ቁጠባ የመጠበቅ ግዴታ አለበት፡፡ በተጓዳኝም የባለቤቶቹ ሀብትም ሲጠበቅ ማየቱ ለባንኮቹ ጤናማ እንቅስቃሴ ወሳኝ መሆኑን የሚገነዘብ ይመስለኛል፡፡ ይህ ያልተለመደና የተገኘውን ከመሰልቀጥ የመጣ ትርፍ መንስዔ መመርመር ያለበት ለዚህ ነው፡፡ ከውድቀት በኋላ በድጋሚ ለመማር ታሪክ ዕድል የማይሰጥ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሌላው ቢቀር በሕገወጥ መንገድ የተፈራው የውጭ ምንዛሪ ዜጎቻችንን በሕገወጥ መንገድ በማዛወር የተገኘ ሊሆን እንደሚችልና ይህ ደግሞ ችግሩን ከሥሩ ለመፍታት መወሰድ ከሚገባው ዕርምጃ ቀዳሚው እንደሆነ በዜግነት የምከራከርለት ጉዳይ ነው፡፡ ቀጥሎም ይህ ገንዘብ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄዱ የሽብር ፈጠራ ድርጊቶችን ለማገዝ እንደማይውል ማን ዘብ ሆኖ ሊከራከር ይችላል ብዬ እጠይቃለሁ፡፡

የባንክ ኢንዱስትሪው ዕድገት በአቅሙ የሚጎርሰውን ያህል እየጎረሰ መሆን አለበት፡፡ የግል ባንኮችም ያገኙትን እየሰለቀጡ ትርፍ ብቻ ማዕከል አድርገው የሚራመዱ ከሆነ፣ አደጋው ከባንክ ለባንክ ግብግብ (Turf War) ወደ አገራዊና ሕዝባዊ ኪሳራ ላለመሸጋገሩ መከላከያ ማቅረብ አይቻልም፡፡ ብሔራዊ ባንክም ‹በዕንቁላሉ ጊዜ በቀጣሽኝ› ውሎ አድሮ ከመከሰቱ በፊት የቁጥጥር አድማሱን አስፍቶ መንቀሳቀስ ይጠበቅበታል፡፡ አሥጊና የተዛቡ የውጭ ምንዛሪ እንቅስቃሴዎችም (Suspicious Transaction) በጥልቀት ይመርመሩ፡፡ ሕገወጥ እንቅስቃሴዎችን በመጠቀም የተገኙ የውጭ ምንዛሪዎችን ተጠቅሞ የብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሪ አደላደል መመርያ ከሚፈቅደው ውጪ ደንበኞችን በማስተናገድ የሚከናወኑ የደንበኛን ተራ የማዛባት ተግባሮች መንስዔያቸው ሊመረመር ይገባዋል፡፡ እንደ ዜጋ ከሕገወጥ የሰውና የዕፅ ዝውውር በተገኘ የውጭ ምንዛሪ አቀባባይነት ከአቅማቸው በላይ የሚያብጡ ባንኮች ጉዳይ ትኩረት አለማግኝቱ ያሠጋኛል፡፡ መንግሥትንም ለሽብርተኝነት ሊውሉ የሚችሉ የገንዘብ ዝውውሮች ለዜጎች ደኅንነት ሲባል ሊያሳስቡት ይገባል፡፡ ኮንትሮባንድን፣ ሕገወጥ የሰውና የዕፅ ዝውውርን አልፎ ተርፎም ለሽብር ሊውሉ የሚችሉ ሕገወጥ የውጭ ምንዛሪ እንቅስቃሴዎችን በመግታት፣ የሕዝብን በሰላም የመኖር መብት ለማስከበር እንዲቻል የባንኮችን ጓዳ ጎድጓዳ መንግሥትና ብሔራዊ ባንክ መፈተሽ  ይገባቸዋል፡፡ በቅርቡ በዚህ ጉዳይ ላይ በተብራራ ትንተና እመለሳለሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

    

   

Standard (Image)

በተሃድሶው የተንቆረቆሩ ‹‹ሒሶች›› ማረፊያቸው የት ነው?

$
0
0

(ክፍል ሁለት)

በልዑል ዘሩ

በዚሁ ዓምድ ላይ ባለፈው ሳምንት በተስተናገደው ምልከታዬ በአገሪቱ በገዢው ፓርቲና በመንግሥት ውስጥ ሁለተኛው ፈጣን ተሃድሶ አለመደረጉን አንስቻለሁ፡፡ በተለይ ከስድስትና ከሰባት ዓመታት በፊት ሥር ነቀል ማሻሻያ ማድረግ ሲገባ፣ ለተፈጠረው መጓተት ምክንያት የሚባሉ ትንታኔዎችንም ለጋዜጣ አንባቢያን በሚመች መንገድ ብቻ ሰንዝሬአለሁ፡፡ ያ ባለመሆኑና አገሪቱ በከፍተኛ ብድር ጭምር ያሳየችውን የኢኮኖሚ ዕድገት መጋረጃ በማድረግ ‹‹በተሳክቶልናል›› ስም የተፈጠረው የሥርዓት ብልሽት የጋበዘውን ሕዝባዊ እምቢተኝነትና ጥፋትም በስፋት አንስቻለሁ፡፡ እስከ የአሁኑ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ድረስ በመተንተን ማለት ነው፡፡

በሕዝቡ ቁጣና ፍላጎት ጭምር ተገፍተው ወደ ተሃድሶ የገቡት ገዢው ፓርቲና መንግሥት የጀመሩትን ተሃድሶ (Reform) የሚጠራጠሩ ሰዎችን መከራከሪያም ጠቃቅሻለሁ፡፡ በግሌ ይኼ የሥርዓት መታደስና ወቅቱንና የሕዝቡን የግንዛቤ ደረጃ ከግምት ያስገባ የማሻሻያ ዕርምጃ ጠንካራ አይደለም የምልበትን ምክንያት ለማንሳት እወዳለሁ፡፡ ይኼ በየብሔራዊ ድርጅቱ ደረጃ የማነሳው ክፍተት ‹‹እነማንን ተጠያቂ አደረገ?›› ስል ለመሞገትም እወዳለሁ፡፡

የአማራ ክልልና ብአዴን

ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) የ36 ዓመት ዕድሜ ያለው ከሕወሓት ቀጥሎ የዕድሜ ባለፀጋ ድርጅት ነው፡፡ በትጥቅ ትግሉ የ11 ዓመታት፣ አገር በመምራት 25 ዓመታት ዕድሜ ያለው ነው፡፡ ይኼ ድርጅት በአገሪቱ የጋራ አመራር ውስጥ ካለው ድርሻ ባሻገር፣ የአማራ ክልልንም በማስተዳደር ለተገኘው የመሠረተ ልማት የማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትም ሆነ ለሰላሙ (በተለይ በአማራ ክልል ሽፍታ ለሚያስተዳድራቸው አካባቢዎች ነፃ መውጣት ድርሻው የጎላ ነበር) አስተዋጽኦው ነበረው፡፡

አሁን የክልሉ ሕዝብም ሆነ ከክልሉ ውጪ ያሉ የአማራ ተወላጆች በድርጅቱ ላይ የሚያነሱበት ጥያቄ ግን በርትቷል፡፡ ተለጣፊና የወከለውን ሕዝብ ጥቅም የማያስከብር አድርገው ይቆጥሩትም ይዘዋል፡፡ ለዚህ አገላለጽ የሚያነሱት መገለጫም አለ፡፡

አንደኛው በተለያዩ ክልሎች የሚኖሩ የአማራ ብሔር ተወላጆች ‹‹በነፍጠኛ ሥርዓት›› ወይም በገዥ መደቦች ስም የሚደርስባቸውን ዱላ አለመመከቱ ነው፡፡ ሌላው ቢቀር ድርጊቱ ፍትሐዊ እንዳልሆነ በይፋ አለማውገዙ ዋነኛው ድክመቱ እንደነበር በራሱ አባላትና አመራሮች በተሃድሶው መድረክ እየተነሳ ነው፡፡

ለምሳሌ ከ1984 ዓ.ም. ኦነግ የተባለው ጽንፈኛ የፖለቲካ ቡድን በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በአርሲና በምሥራቅ ወለጋ የፈጸመው በደል ይጠቀሳል፡፡ በመቀጠልም በተከታታይ ኦሕዴድ በተባለው የገዢው ፓርቲ አባል ድርጅት ካድሬዎችና ጠባብ ብሔርተኞች በምዕራብ ደቡብ ሸዋ፣ በአርሲ፣ በምዕራብ ወለጋ የተፈናቀሉ ሀብታቸው የወደመ የክልሉ ተወላጆች ትንሽ አልነበሩም፡፡ በቅርቡም በደቡብ ክልል ጉራፈርዳ፣ በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል የንፁኃን ሕይወት ሳይቀር የጠፋባት ክስተት ትልቅ የታሪክ ጠባሳ ጥሎ አልፏል፡፡ በዚህ ክስተት የተጎዱ ዜጎችን እያሰባሰበ ለማገዝ ይሞክር የነበረው እንኳን መኢአድ የተባለው ተቃዋሚ ድርጅት መሆኑ የብአዴንን ቅቡልነት ጥያቄ ውስጥ ጥሎት እንደነበር በሒስ ተገልጿል፡፡ እንደ አገር ይኼ አካሄድ እንደ ጥፋት የተነሳውም ዘንድሮ ከአማራ ክልል ሌሎች ሲፈናቀሉ ነው፡፡

የብአዴን ግምገማ ላይ ሌላው ተደጋግሞ የተነሳው የመሪዎቹ አስመሳይነትና አድርባይነት ነበር፡፡ በአገሪቱ የሥልጣን እርከን እስከ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ የደረሱ የድርጅቱ መሪዎች ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› የተባውን የሥርዓቱ አደጋ ለመመከት ያደረጉት ጥረት ደካማ ነበር፡፡ ዛሬ ‹‹እነ እገሌ ተጠቀሙ፣ በለፀጉ …››  የሚለው ካድሬ ሁሉ ትናንት ድርጊቱ ሲፈጸም እያወቀ የድርሻውን እየወሰደ አልያም በአድርባይነት ዘርፍ ሲፈጸም በዝምታ እያለፈ እንደነበር ጥርጥር የለውም፡፡

ለእዚህ አንድ ማሳይ የሚሆነው ሁሉም የትምህርት ሚኒስትሮች (ወ/ሮ ገነት ዘውዴ፣ ዶ/ር ስንታየሁ ገብረ ሚካኤልና አቶ ደመቀ መኮንን) የመሩት መሥሪያ ቤት የክልሉን ሕዝብ የሚያስቆጣና ለውዥንብር የሚያጋልጥ መጽሐፍ ሲያሳትም በዝምታ አልፈዋል፡፡ በቅርቡም ‹‹ድክመታችን ነው›› ሲሉ ግለ ሒስ አድርገዋል፡፡ ግን ምን ቅጣት ደረሰባቸው? ለሚለው ጥያቄ መልስ የሚሰጥ የለም፡፡

በቅርቡ በሰሜን ጎንደር ለተነሳው ቀውስ ብአዴን ተጠያቂ ነው፡፡ የቅማንትን የማንነት ጥያቄ በአግባቡ ባለማስተናገድም ሆነ የወልቃይትን (የግጨውን ወሰን ጉዳይ) በወቅቱ መልስ እንዲሰጥ ባለማድረጉ ይወቀሳል፡፡ ከጉዳይም አልፎ ጉዳዩ የሞት ሽረት አጀንዳ ሆኖ በሕዝቡ ውስጥ እንዲብሰከሰክ ከተቃዋሚዎች በላይ ራሳቸው የብአዴን ካድሬዎች መሥራታቸውን ራሱ ኢሕአዴግ በተሃድሶው ማረጋገጡ በቅርቡ ተገልጿል፡፡ ግን ምን ዓይነት ዕርምጃ በእነማን ላይ ተወሰደ? ሌላውስ ምን ተማረ?

በመሠረቱ ብአዴን የተባለው የአማራ ክልል ገዢ ፓርቲ አሁንም ከአንድ አካባቢ ልጆች እጅ ወጥቶ ክልላዊ ገጽታን አልተላበሰም፡፡ በአብዛኛው የሰሜን ወሎና የዋግምራ ‹‹ታጋዮች›› ድርጅቱን ከላይ እስከ ታች መምራታቸው ብቻ ሳይሆን የጎንደር፣ የጎጃምና የሸዋ ፖለቲከኞችን አለማፍራቱ ‹‹ውስጠ ወይራ›› አስመስሎታል፡፡ ድርጅቱ በእነዚህ ዓይነቶቹ ውትፍትፍ አሠራሮቹ ቢተችም ግን የጎላ ሌብነት ውስጥ የተሰማሩ መሪዎች እንደሌሉት ተወሰቷል፡፡ ይኼንን ወደፊትም አስጠብቆ መሄድ አለበት፡፡

በግምገማው እንደተረጋገጠውም ‹‹እገሌ ውስኪ ስላመጣልህ አሾምከው፣ ያቺ ተሿሚ የሚስትህ እህት ወይም ውሽማህ አይደለችም ወይ? ከድርጅት ጽሕፈት ቤቱ እስከ ላይ ያለ ቡድነኝነት….›› ከመነሳት የዘለለ የዘርፍ ጉዳይ አልነበረም፡፡ ‹‹ማሽነሪ ገዝተው ያከራያሉ፣ ሁለትና ሦስት ቦታ ይዘዋል፣ ሕንፃ ሠርተዋል፣ ከፍ ያለ ሀብት አከማችተዋል....›› የተባሉትም ጥቂትና በአዲስ አበባና በፌዴራል መዋቅር ያሉት ባለሥልጣናት ብቻ ናቸው፡፡

ይኼ ሁሉ ድክመት ለቀናት በዘለቀ ተሃድሶ የተነገረበት ድርጅት ግን በሚያስቅና በሚያሳዝን ሁኔታ መሪዎቹን እንኳን አልቀየረም፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን አስተዳዳሪና የጎንደር ከተማ ከንቲባ ከመነሳታቸው በስተቀር ‹‹በመጨረሻ ማስጠንቀቂያ› የታለፉት ሊቀመንበሩና ምክትል ሊቀመንበሩ እንኳን ባሉበት መቀጠላቸው እየተወራ ነው፡፡ ዕውን ይኼ ተሃድሶ ነውን?!

የትግራይ ክልልና ሕወሓት

ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ (ሕወሓት) የኢሕአዴግ እርሾ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ከትጥቅ ትግሉ ጀምሮ ተፅዕኖ ፈጣሪ ድርጅት ነው፡፡ ጠንካራ የክልሉ ሕዝብ ድጋፍ ያለው መሆኑም ይታወቃል፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ግን አሁንም ከስያሜው ጀምሮ የነፃ አውጭ ባህሪን መላበሱ በሌላው ወገን ዘወትር ለሐሜትና ለትችት አጋልጦታል፡፡

በዘንድሮው ተሃድሶ በሕወሓት መሪዎችና ካድሬዎች ላይም ሆነ በራሳቸው የተነሱ በርካታ የብልሽት መሣሪያዎች እንዳሉ ውስጥ አዋቂ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ ቀዳሚው የፀረ ዴሞክራሲ ባህሪ መንገሡ ነው፡፡ ማሳያው ክልሉ የማዕከል ውሳኔን ገሸሽ ማድረጉ ብቻ አይደለም፡፡ በወልቃይት ጉዳይም ሆነ በሌሎች የወሰን ጉዳዮች ጫጫታ ሳያስነሱ ሕዝብ ያሳተፈ ውሳኔ ከመስጠት ይልቅ፣ የክልሉን ሕዝብ ሠልፍ ወደ ማስወጣትና ማስፈራራት መግባትም አገር የሚበትን እንደነበር ተሂሷል፡፡ አንዳንዶች ‹‹ነባር ታጋይ ነኝ›› ማለትን የበላይነት ስሜት መፍጠር እንደ ማድረግም ይቆጥሩታል፡፡

የትግራይ ሕዝብና ታጋዮች አገሪቱ ከፀረ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንድትላቀቅ ታሪክ እንዳልሠሩ አሁን አሁን ብቅ ብቅ እያለ ያለው ትምክህትም አደገኛ ነው፡፡ ‹‹እኛ ታግለን ቤተሰቦቻችን መስዋዕት ሆነው … ›› በሚል ትርፍና እላፊ የመፈለግ ዝንባሌ ያላቸው የተወሰኑ የክልሉ ተወላጆች በሕገወጥ መንገድ በልፅገዋል፡፡ በአዲስ አበባ አንድ አካባቢ በሙሉ ከመያዝና በሕንፃ ከመንቆጥቆጥ አንስቶ በእርሻ፣ በኢንዱስትሪና በንግድ ዘርፍ ለፍቶ ጥሮ ባገኘው ሀብት ከለማው ዜጋ በላይ በፍጥነት ‹‹ቱጃር›› የሆኑ እንዳሉ በስፋት ይነገራል፡፡

ይኼን አስመልክቶ በቅርቡ ለ17 ቀናት በትግራይ ክልል በተካሄደው የከፍተኛ አመራሮች ተሃድሶ ላይ ዝርዝርና አሳዛኝ ጉዳዮች ተነስተዋል፡፡ በተለይ በክልሉ ያለው ነባር ካድሬ በአዲስ አበባና በፌዴራል መዋቅሩ ላይ ያነሳው ሒስ እውነተኛና መፍትሔ አመላካች ነው፡፡ ‹‹… ከድርጅታችን መርህ ውጪ በግል መጠቃቀምና በመንደር ልጅነት እየተሳሳቡ መሿሿም አለ፡፡ በአዲስ አበባ መዋቅር በዚህ ደረጃ ሕወሓት ተፅዕኖ መፍጠሩ ለብልሽትም ዳርጓል፡፡ ከመከላከያ፣ ከደኅንነትም ሆነ ከቢሮክራሲው እየወጡ የበለፀጉ ሙሰኞች ሕወሓትንም ሆነ የትግራይ ሕዝብን ሊወክሉ አይችሉም፡፡ እንዲያውም የአንዳንዶች ስግብግብነት ለዘመናት አብሮን ከኖረው ሕዝብ ጋር እያጋጨን ለፍተው ያገኙ የክልላችን ተወላጆችን ለአደጋ እያጋለጠ ነው፡፡ ስለዚህ ይኼ ሊወገዝና ሊታረም ይገባል፡፡ መጠየቅ ያለበትም በአብዮታዊነት ተወስኖ መጠየቅ አለበት፤›› ማለታቸው የትልቅነት ማሳያ ነው፡፡

ይኼ በራሱ በሕወሓት ካድሬዎች የተነሳ ‹‹የእንታረም›› ትግል በሌሎቹ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶችም መነሳቱ ይነገራል፡፡ በተለይ በመሬት፣ በኮንትሮባንድ፣ በወጪና ገቢ ምርት እንዲሁም በታዳጊ ክልሎች አካባቢ ባለ ቅርምት ጤነኛ የማይመስል ዝንባሌ አለ፡፡ ይኼ ደግሞ ‹‹ሥልጣንን መበልፀጊያ›› የሚያደርጉ ዝንባሌ አንዳንድ መሥሪያ ቤቶችን የብሔር ሥርዓት የሚያደርጉ የተሳሰተ አስተሳሰብ አስተዋፅኦ አድርጓል በሚል፣ በአሁኑ ተሃድሶ ለመቀየር ጥረት እየተደረገ ይመስላል፡፡ ግን ውጤቱ ምን ይሆናል? ዕርምጃውስ እስከ የት ይደርሳል? የሚለው ወደፊት የሚታይ ይሆናል፡፡ ከዚህኛው ድርጅት ጋር በተያያዘ ተደጋግሞ የሚነሳው የኢንዶውመንት ግዙፍ ሀብት ጉዳይም ዝብርቅርቅ ስሜት እንደፈጠረ ቀጥሏል፡፡

የኦሮሚያ ክልልና ኦሕዴድ

ሰፈውን የኦሮሞ ሕዝብ እየመራ ያለው የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ገና ከተቋቋሙበት ጊዜ አንስቶ ፈተና ያልተለየው ነበር፡፡ በተለይ በኦሮሞ ሕዝብ ውስጥ ከፍ ያለ ዕውቅና የነበረው አንጋፋው ኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ከነበረው ተገዳዳሪነት አንፃር ድርጅቱም ሰፊ ተቀባይነት አልነበረውም፡፡ በኋላ ላይ ወጣቶችን በማሳተፍ፣ የክልሉን ልማትና ሰላም በማፋጠን የተሻለ ተቀባይነት እያገኘ መምጣቱ ግን አይካድም፡፡ በዚያው ልክ በአገሪቱ በርከት ያሉ የኦሮሞ ተቃዋሚ ድርጅቶች የመሠረቱ ፖለቲከኞች ተፅዕኖ ቀላል አልነበረም፡፡

በተሃድሶው በየመድረኩ እንደተነሳው ይኼም ድርጅት የጎሉ ችግሮች የነገሡበት ሆኗል፡፡ ቀዳሚው ሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነት ነው፡፡ በተለይ ከመሬት ጋር በተያያዘ ክልሉ ያለውን ሰፊና ወሳኝ የከተማ መሬት የመቀራመትና የመቸብቸብ ጉዳይ የተፈቀደ በሚመስል ደረጃ ተፈጽሟል፡፡ አመራሩ ብቻ ሳይሆን ታች ያለው ካድሬ አራትና አምስት መሬት ይዞ በመሸጥ ሀብት ከማፍራቱም በላይ፣ የክልሉ ሕዝብ እንዲማረርም አድርጓል፡፡ አንዳንድ የድርጅቱ ባለሥልጣናትም ከትልልቅ ባለሀብቶች ጀርባ ስማቸው ከመነሳቱ ባሻገር ባለሕንፃና ፋብሪካም ሆነዋል የሚል ጉምጉምታም አለ፡፡ ይኼ ብቻ ሳይሆን የሥራ አስፈጻሚና የፖሊስ ኮሚሽነሮች ቤተሰቦችና ወንድም/እህቶች እንዴት ትልቅ ኮንትራክተርና ባለሀብት ሆኑ? ሲባል መልስ አይገኝም፡፡

ይኼ የከፋ ችግር ዋነኛ የጥቅም ማዕከል ከመሆኑ የተነሳም የአዲስ አበባና የዙሪያዋ የጋራ ማስተር ፕላንን ፉርሽ ያደረገውም ራሱ ኦሕዴድ እንደሆነ በግልጽ ታይቷል፡፡ ማስተር ፕላኑ በጥበብና በሥነ ምግባር ከተመራ ያለው አገራዊ ፋይዳ ተዘንግቶ፣ የኦሮሞን ሕዝብ መሬት የመንጠቅ ጉዳይ አስመስሎ የቀሰቀሰውም ካድሬው ራሱ ነው፡፡ ይኼ ደግሞ ቀደም ሲል አንስቶ በመሬት ካሳ አሻጥርና ቅሸባ የተማረረውን የክልሉ ሕዝብ ‹‹እሳት እንዲጎርስ እሳት እንዲለብስ›› አድርጎታል፡፡

በመሠረቱ በኦሮሚያ ክልል ለደረሰው የሰው ሕይወትና የአገር ሀብት ጥፋት የጽንፈኛው ጃዋር መሐመድና ቢጤዎቹ አሉታዊ ቅስቀሳ ድርሻው የጎላ ቢሆንም፣ የኦሕዴድ ድክመትም ትልቅ ድርሻ ነበረው፡፡ አሁን አገር አቀፍ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመደንገጉና የፌዴራሉ የፀጥታና የደኅንነት ኃይል ወደ ክልሉ በመግባቱ አንፃራዊ ሰላም ቢሰፍንም፣ ኦሮሚያ ግን ለአደጋ ተጋልጣ ነበር፡፡ ለዚህ ጥፋትም የድርጅቱ መሪዎችና የክልሉ አስተዳዳሪዎች ቁጥር አንድ ተጠያቂ እንደሆኑ መግባባት ላይ ተደርሶ ነበር፡፡

ኦሕዴድ ግን ሊቀ መናብርቱን ቢቀይርም ‹‹በፈቃዳቸው እንደለቀቁ›› ገልጾ ነበር፡፡ ምንም እንኳን አዲስ በመሠረተው ካቢኔ የተሻለ ብቃትና ያላቸውና  አዳዲስ ሰዎችን ቢያስገባም በሀብት ‹‹የተንበሸበሹ›› የሚባሉ ሰዎችን አሁንም በተለያዩ ድርጅትና በመንግሥት ኃላፊነቶች ላይ አስቀምጦ ያለምንም ተጠያቂነት ለመቀጠል መሻቱ ታይቷል፡፡ የቡድንና ሕገወጥ ኔትወርክ ትስስሩ ስለመበጠሱም ሆኖ አደርባይነቱ ስለመሸነፉም የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ ነገር ግን በአንፃራዊ ሁኔታ ለውጥ ማሳየቱ ደግሞ በተሻለ ደረጃ ላይ አስቀምጦታል፡፡

ደቡብ ክልልና ደኢሕአዴን

የደቡብ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢሕአዴን) በአንፃራዊነት አጭር ዕድሜ ያለው ነው፡፡ በትጥቅ ትግል እዚህ ግባ የሚባል ተግባር ባይጠቀስለትም፣ በአገር ግንባታው ሒደት ግን እስከ ጠቅላይ ሚነስትር የደረሱ መሪዎችን ያፈራ፣ በልማትም ሆነ በሰላምና መልካም አስተዳደር የበኩሉን ሚና የተጫወተም ነው፡፡   

በአሁኑ ተሃድሶ በደኢሕዴን ውስጥ የሚነሳ ችግርና ድክመት መኖሩ ተለይቷል፡፡ አንደኛው የፓርቲው ፈላጭ ቆራጭ የሚባሉ አንዳንድ ግለሰቦች በሙስና መጠርጠር ጉዳይ ነው፡፡ ምንም እንኳን በዚህ ክልል የሚነሳው የኪራይ ሰብሳቢነት ተግባር ከሌሎቹ አንፃር አነስተኛ ሊባል ቢችልም፣ በሥልጣን ላይ ተቀምጠውም ሆነ ከባለሥልጣናት ተወዳጅተው የበለፀጉ ሰዎች የሞሉበት ነው፡፡

ደኢሕዴን የጠባብነት አዙሪት የሞላበት እንደሆነም ተናግሯል፡፡ እርግጥ 56 ብሔረሰቦችና ማንነት ባለበት ክልል ይኼ መሆኑ የሚጠበቅ ቢሆንም በሌሎች ሕዝቦች ታሪክና ማንነት ላይ ጥላቻ ያሳደሩ ካድሬዎች አሉበት፡፡ በየመንደሩ እየተነሳ ያለው ‹‹የማንነት ጥያቄ›› ምንጩ ይኼው እንደሆነ ይገመታል፡፡

አሁንም የድርጅቱ መሪዎች በኢሕአዴግም ሆነ በአገሪቱ ውስጥ ሥልጣን እየያዙ ከመጡት ቁልፍ ድርሻ አንፃር ኪራይ ሰብሳቢነት፣ ጠባብነት፣ ትምክህትንም ሆነ የሃይማኖት አክራሪነትን ከማስወገድ አንፃር ድርሻቸው ትልቅ ነው፡፡ ይሁንና በአብዛኛው ከአደርባይነት ጋር በተያያዘ ደፍሮ ብልሹ አመለካከትና ተግባሮችን ያለማስተካከል ችግር ተነስቷል፡፡

በአጠቃላይ በገዢው ፓርቲና በመንግሥት ደረጃ ተሃድሶው መጀመሩ መልካም ነው፡፡ የተሿሚ መቀያየር ወይም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሕዝብን ‹‹ፀጥ›› ማድረግ ብቻ ግን ተሃድሶ ሊሆኑ አይችሉም፡፡ እስካሁን ለተፈጸሙ መልካም ተግባሮች የሚመሠገኑ፣ ለጥፋቱም የሚወቀሱና የሚጠየቁ ሰዎች መኖር አለባቸው፡፡ ዴሞክራሲውን ያቀጨጩና ወደ መግደል እያደረሱ ያሉ ግለሰቦች አሠራሮችና አደረጃጀቶች ይፈራርሱ፡፡ የሕዝባችንን አንድነት የሚጎዱና መነጣጠልን የሚያመጡ አስተሳሰቦች ይቀረፉ፡፡ ከሁሉ በላይ ኢፍትሐዊነትን የሚያሰፋት አንዱ ዘራፊ ሌላው ተዘራፊ የሚሆኑባት የአሻጥር በሮች ይዘጉ፡፡ ይኼ ሲሆን ነው ተሃድሶው ከልብ ሊሆን የሚችለው፡፡ የሕዝብንም ቀልብ የሚገዛው እላለሁ፡፡   

 ከአዘጋጁ፡-ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን ኢሜይል አድራሻቸው zerul@yahoo.com. ማግኘት ይቻላል፡፡  

Standard (Image)

ግርድፉ የአዲስ አበባ ተሃድሶና አሳዛኙ ውጤት

$
0
0

በሒሩት ደበበ

ለሁለት ተከታታይ ሳምንታት በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ አቶ ልዑል ዘሩ የተባሉ ጸሐፊ ‹‹በተሃድሶው የተንቆረቆሩ ሒሶች ማን ላይ አረፉ?›› ሲሉ የሞገቱትን ሐሳብ አንብቤያለሁ፡፡ በእውነቱ ውስጥ አወቅ በሚመስል ዕይታቸው በየክልሉም ሆነ በፌዴራሉ መንግሥት ደረጃ ‹‹አሉ›› ያሏቸውን ዝርዝር ችግሮች አንስተዋል፡፡ ነገር ግን አሁንም ደፈር ብለው እነገሌ ብለው በዚህኛው ጥፋት ሊወቀሱ ሲገባ ታልፈዋል ወደሚል አቅጣጫ ቢያመለክቱን ኖሮ፣ የእሳቸውም ጽሑፍ ጥልቀት ያገኝ ነበር የሚል እምነት አለኝ፡፡

ያም ሆኖ ጥረታቸውን እያደነቅሁ በእኔም በኩል በተለይ እርሳቸው ያልተመለከቷቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ‹‹የጥልቅ ተሃድሶ›› መድረኮች ለመቃኘት እሞክራለሁ፡፡ እንደሚታወቀው አዲስ አበባ ከተማ በአራቱ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች የሚመራ ሲሆን፣ የተናጠልና ጥምር ኮሚቴ የሚዋኝበት ነው፡፡ በመሆኑም ‹‹የተሃድሶ መድረኮች›› እየተካሄዱ ያሉትም በሁለቱም አደረጃጀቶች ነው ለማለት ይቻላል፡፡

በእኔ እምነት የከተማ አስተዳደሩ የተለያዩ የልማት ተግባራትን ቢያከናውንም፣ በአፈጻጸም ወደኋላ የቀረባቸው ጉዳዮች አሉ፡፡ (ለምሳሌ የሕዝብ የልማት ተሳትፎ፣ በመልሶ ማልማት ፈጥኖ መገንባት ላይ፣ በውስጥ ለውስጥ መንገዶች ግንባታ፣ የከተማ ፅዳት፣ ትራንስፖርት…) ከዚህም በላይ በሌሎች ክልሎች እንደታየው ሕዝቡ በቁጣ ገንፍሎ አይውጣ እንጂ ቀላል የማይባል ምሬትና የመልካም አስተዳደር ዕጦት አለ፡፡ በኢፍትሐዊነት፣ በሙስናና ብልሹ አሠራር፣ የግልጽነትና የተጠያቂነት ማጣት፣ ሥርዓት አልበኝነት… የሚገለጸው ይኸው ሕዝብ የማያረካ ክስተት ያለጥርጥር አሁን ያለው አመራር ውጤት ነው፡፡ ተሃድሶውስ ይህን እንዴት እያየው ይሆን?!

ሙስናና ‹‹አስቂኙ ድራማ›› 

ከዚህ ቀደም ለትምህርት ጉዳይ በውጭ አገር አብሮኝ የቆየ አንድ ወዳጄ፣ ‹‹ከዚህ በኋላ ኢሕአዴግ ሙስናን ታግሎ ሊያሸንፍ አይችልም፤›› በማለት ደጋግሞ ይከራከረኝ ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ማን ማንን ሊጠይቅ ይችላል? የሙስና ጣራውስ እስከ የት ድረስ ተብሎ ይገደባል? መቶ ሺሕ፣ አንድ ሚሊዮን፣ ባዶ መሬት፣ የሚከራይ ማሽን ወይስ ሕንፃ ያለው? እነዚህ የሌሉት ‹‹ከፍተኛ አመራር›› የለም ባይባልም ቁጥሩ ግን እዚህ ግባ አይሆንም ሲል አስደምሞኛል፡፡ የአንዳንዶቹን ሀብትም በሚያውቀው መረጃ ላይ ተመሥርቶ እስከ መግለጽ ይደርስ ነበር፡፡

ለዚህ አባባሉ ጥሩ ማረጋገጫ የሆነኝ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የካቢኔ አባላት (ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች) ግምገማ ‹‹እየተጠናቀቀ ነው›› ተብሎ የተገኘውን ውጤት ስሰማ ነው፡፡ ውስጥ አዋቂ ምንጮች እንደሚያስረዱት እነኛ በኔትወርክና በቡድንተኝነት የተዘፈቁ፣ የሕዝብ መሬት ያዘረፉና የድርሻቸውን ቅንጥብጣቢ የወሰዱ፣ በኪራይ ሰብሳቢው ባለሀብት ኪስ ውስጥ እንደ መሀረብ ገብተው የሚዞሩ፣ በሐሰት የትምህርት መረጃ ‹‹የሚመሩን›› በማወናበድ የውጭ ጉዞን የውኃ መንገድ ያደረጉ፣ በአዲስ አበባና በኦሮሚያ ፊንፊኔ ዙሪያ ከአንድም ሁለት ሦስት ቤቶች እያሉዋቸው በመንግሥት ቤት የሚኖሩ፣ አንዳንዶቹ በድፍረት ጭምር በሚሠሩበት (በሚመሩት) መሥሪያ ቤት ሳይቀር ጨረታ የሚወዳደር ድርጅት (በሌላ ሰው ስም) ያላቸው ነጋዴዎች ሆነው ሳለ… ‹‹መዋቅሩ ከከፋ ሙስና ነፃ ነው›› ተብሎ ሲደመደም በዓይኔ ማየቴና በጆሮዬ መስማቴ የተሃድሶውን ፉርሽነትና ግድፈት አረጋግጦልኛል፡፡

በቅርቡ በስብሰባ ማዕከል አንድ የሕወሓት የተሃድሶ ጉባዔ ላይ ‹‹እንዴት ነው ማዕከላዊ ኮሚቴው ሙስና ውስጥ አልገባም የሚባለው? ለ25 ዓመታት ሁላችንም በበረሃ ታግለን ስንመጣ ከለበስነው ቁምጣ፣ ሸበጥና ክሹፍ በላይ ምን ነበረን? ዕውን ይኼ በደመወዝ ብቻ የተገኘ ነው?›› ያለች ነባር ታጋይ ነበረች፡፡

በእውነቱ የተሃድሶው እንዳይሆን፣ እንዳይሆን መሆን እንጂ አባባሏ ማንንም የሚያስቆጭ ነው፡፡ በየትኛውም ደረጃ ያለ የሥራ መሪ ኑሮ መርቶ፣ ልጅ አስተምሮ (አብልቶ፣ አልብሶ፣ አስጠልሎ)፣ እንደ አቅሙ ዘመድ ረድቶ በደመወዝና በአበል ብቻ ከኖረ በጣም ጠንካራ ነው፡፡ መሬት ላይ ያለው ግን ከዚያ በላይ ነው፡፡ ‹‹አመራሩ ነጋዴ ሆኗል›› እየተባለ ያለው በስሙ በተመዘገበ ንግድ ፈቃድ እንዳልሆነ ጥርጥር የለውም፡፡

በተለያዩ መረጃዎችና በሕዝብ ታዛቢዎች እንደሚደመጠው በእህት፣ በወንድም፣ በጋብቻ ትስስርና በዝምድና የሚፈጠር ሽርክና አለ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ‹‹እንዳይጠረጠር›› ከሌላ ብሔር ነጋዴ ሸሪኮች ጋር ሀብት የማካበት አደገኛ አካሄድም ተንሰራፍቷል፡፡ (አንድ የብአዴን አመራር በአርጎባ ማኅበረሰብ ውስጥ ከሚገኙ ባለሀብቶች ጋር ዱቄት ፋብሪካ እንደ ከፈተው ማለት ነው)፡፡ በአዲስ አበባ ደረጃ በተጨባጭ ወደ ውጭ ሀብት አሸሽቷል የሚባል ሰው ስለመኖሩ ማረጋገጫ የተገኘበት ባይኖርም፣ በሙስና የበለፀገ የለም ብሎ መደምደም ግን ተሃድሶ መቀመጫን ከመላጥና ወገብን ከመቁረጥ ያለፈ ተግባር እንደሌለው ያሳያል፡፡

ከአዲስ አበባ ከተማ አመራሮች መሀል የብረትና የግንባታ ቁሳቁስ አስመጪዎች፣ ኮንትራክተሮችና ተቋራጮች የሆኑ የሉም?! (በሪል ስቴት ሽርክና ጭምር የሚታሙ አሉ) የጤና ተቋማት፣ መድኃኒት ቤት፣ ትምህርት ቤት ከፍተው በዘርፉ የወጣን ሕግ እስከ ማዛባት የደረሰው ማን ነው?! ሌላው ይቅር ከገቢያቸው በላይ መኖሪያ፣ ተሽከርካሪ፣ የልጆች ትምህርት… ያላቸው ቡችላ ነጣቂዎች በምን ይወቀሱ!?

ተሃድሶውን ትዝብት ላይ የጣለው ሌላው ጉዳይ ፎቅና ቪላ ለግላቸው ሠርተው ከኃላፊነት የተነሱ ‹‹የወሰዱት የሕዝብ ሀብት የውለታቸው ካሳ ነው›› የተባሉ ይመስል ዝም መባላቸው ነው፡፡ በከተማዋ መሬት ሲቸበቸብ፣ የመንገድና መልሶ ማልማት ካሳ ሲጎርፍ፣ የመንግሥት ግዥ ላይ ‹‹በቴክኒክ ስም›› በመቶ ሚሊዮኖች ወጪ ሲደረግ እነማን ነበሩ? ምን ሠሩ? ማለት አልተቻለም፡፡ በሚያሳዝን ደረጃ ከግምገማዎቹ በፊት የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን፣ የደኅንነትና የፖሊስ መረጃ ሳይሰበሰብ፣ ጠንከር ያለ የሕዝብ አስተያየት ሳይቀመር እንደተለመደው በኔትወርክ ‹‹ተሃድሶ›› ተደርጓል፡፡ ውጤቱም ‹‹ነፃ›› የሚል ሆኗል፡፡

አብሮ የበላ፣ የጠጣ፣ በእንካ በንካ የጥቅም ተጋሪ የሆነ፣ በሥራው ሕገወጥ ቡድን የፈለገውን እያደከመና እየመዘበረ በብሔር፣ በመንደር ልጅነት፣ በሃይማኖት ግንኙነት፣ በትምህርት አብሮነት… የቀረበውን ሲሰበስብ የከረመው እየተሞጋገሰ አልፏል፡፡ ያለጥርጥር የአዲስ አበባ ሙስናና የመልካም አስተዳደር ዕጦትም ቅንጣት ያህል ሳትቀነስ ተባብሳ ትቀጥላለች፡፡

ብልሹ አሠራርና ኢፍትሐዊነት

አንድ ሌላ የአስተዳደሩ የቅርብ ሰው እንዳጫወተኝ አንድ ቱባ ባለሥልጣን ድምፁን አጥፍቶና ተደብቆ ከአምስት ዓመት በላይ በመማር የፒኤችዲ ዲግሪ ከውጭ ይዟል፡፡ ይህ ሰውና ባልደረቦቹ ባወጡት ቀጭን ትዕዛዝ ግን በግላቸው በርቀት ወይም በኤክስቴንሽን በአገር ውስጥ ትምህርት የጀመሩ ባለሙያዎችና መካከለኛ አመራሮች ‹‹ሥራ ትበድላለችሁ›› ተብለው ትምህርት አቋርጠዋል ወይም ከሥራ ተባረዋል፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት ብቻ ከ1,500 በላይ ዝቅትኛ አመራሮች እንዳይማሩ ሲከላከሉ ኖረው ብዙ ውለታ (ለሥርዓቱ) ቢሠሩም ከዲፕሎማ በታች ናቸው ተብሎ ተባርረዋል፡፡

በከተማዋ የተለያዩ መሥሪያ ቤቶች አይደለም ተገልጋይን ራሱን ሠራተኛውን የሚያማርሩ አሠራሮች ትንሽ አይደሉም፡፡ በቅጥር፣ በዝውውር፣ በምደባና በሹመት ላይ የሚታየው ደባ ኢሕአዴግን ሰው እንዲጠላ የሚያደርግ ነው፡፡ ቅሬታ ሰሚ፣ የዲሲፕሊን ኮሚቴ፣ የመልካም አስተዳደር ማስተባበሪያ… የሚሉ አወቃቀሮች የይስሙላ ናቸው፡፡ በብዙዎቹ ተቋማትም ከስም ባለፈ ሥራ ሲሠሩም አይታይም፡፡

ከዚህ በመነሳትም መርህና አሠራር ተሸርሽሯል፡፡ በብሔር መሰባሰብና መመዳደብ የተለመደ ተግባር ነው፡፡ ለዚህ ጥሩ ማሳያው በቅርቡ በአዲስ አበባ ከላይ እስከ ታች እየገቡ ላሉ የአንድ አካባቢ ተወላጅ አመራሮች እንኳን በኢሕአዴግ ደረጃ አባል ድርጅቱም በማዕከል አውቋቸውና እያረጋገጠ ያመጣቸው አልነበሩም መባሉ ነው፡፡ የግለሰብ መሳሳብ ማለት ይህንኑ ነው፡፡ ዘረፋና መጠቃቀሙም በዚያው እየበረታ ይሄዳል፡፡

በከተማው በሚያሳፍር ደረጃ የመንገድ፣ የቤቶችና ኮንስትራክሽን እንዲሁም የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክቶች ግንባታ በድርድር አልያም ‹‹በምርጫ›› ባለጨረታ አልተሰጠም!? ይህስ የኢፍትሐዊነት መገለጫ አይደለም? በሆስፒታሎች፣ በትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ፣ በክፍለ ከተማና በወረዳ ጽሕፈት ቤቶች ግንባታ በመቶ ሚሊዮኖች የአስተዳደሩን ሀብት የሚያንቀሳቅሱ ተቋራጮች እንዴትና በማን ተመረጡ?! ዕውን አሠራሩ ግልጽነትና ተጠያቂነት አለው? በግንባታ ወቅት ለተፈጠረ የጥራት መጓደልና ‹‹አሻጥር›› (ለምሳሌ ዘውዲቱ ሆስፒታል፣ ምኒሊክ ሆስፒታል) ማን ተጠየቀ? ምንስ ዕርምጃ ተወሰደ? እነዚህ ሁሉ የብልሹ አሠራር ውጥንቅጦች በአፍ ካራቲስቶች ታልፈዋል፡፡

በከተማ አስተዳደሩ የአገልግሎት አሰጣጥና ብልሹ አሠራር መንሰራፋት ምክንያት እያለቀሰ ያለ ሕዝብ አለ፡፡ ጉዳያቸው ከወራት አልፎ ለዓመታት እየተንከባለለ ተስፋ የቆረጡም ብዙዎች ናቸው፡፡ በመልሶ ማልማትና በተለይ ‹‹በሕገወጥ ግንባታ›› ስም ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው የጎዳና ተዳዳሪ እስከመሆን የደረሱም አሉ፡፡ ከዚህም በላይ በየጊዜው በሚደርስባቸው ጫናና ማስፈራሪያ ይዞታቸውን በወረደ ዋጋ እየሸጡ ወደ ዳር የወጡ (አንዳንዶቹም ደብዛቸው የጠፋ) አሉ፡፡ ይኼን ከብልሹ አሠራርና ኢፍትሐዊነት ውጪ ማን ያደርገዋል? እንዲያው ሌላው ይቅር በቅርቦቹ የሐና ማርያምና የቦሌ ወረገኑ 30 ሺሕ ሰዎች መፈናቀል የሚጠየቅ ሰው ጠፋ!? አሳፋሪ ነው፡፡

አቅም አልባ አመራሮችና አዲስ አበባ

በከተማ አስተዳደሩ ብቻ ሳይሆን በአገር ደረጃም ስም ከሌላቸው (አንዳንዶቹም ሕጋዊ ዕውቅና የላቸውም) የውጭ አገር ኮሌጆች ዲግሪ መግዛት ተለምዷል፡፡ የአገር ውስጥ የርቀት ትምህርት ቤቶች የከተፋ አካሄድም ጋዋን ለብሰው የተነሱትን ፎቶ በትልቅ ፍሬም ለመስቀል እየረዳ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ማወናበድ ግን ብቃትና ተወዳዳሪነትን አያመጣም፡፡ የሕዝብ አገልጋይነትና ቁርጠኛ አመራርንም አይፈጥርም፡፡

በአዲስ አበባ ደረጃ በርከት ያሉ የብቃት ችግር ያለባቸው ‹‹የሥራ መሪዎች›› እንዳሉ ተደጋግሞ ይታያል፡፡ የተነገረን ደግሞ በማነብነብ፣ ‹‹ሕዝብ ምን ይለኛል›› ሳይሉ ያለ ይሉኝታ በመዘላበድ ‹‹አዋቂ መሪ›› የሚመስሉት ሁሉ አቅማቸው ደካማ ነው፡፡ ይህንን በከንቲባ ጽሕፈት ቤት ደረጃ በጥልቀት መፈተሽ ተገቢ ይሆናል፡፡ ባልሠለጠኑበት ሙያና ባልጨበጡት ዕውቀት ውስጥ ገብተው ሴክተር ለመምራት (ኮንስትራክሽን፣ ትምህርት፣ ጤና፣ ዲዛይን) የሚንቦጫረቁም ትንሽ አይደሉም፡፡

ይህ እየታወቀ ግን በአሁኑ ‹‹መሬት አንቀጥቅጥ!›› ተሃድሶ አመራሩ የብቃት ችግር እንደሌለበት ተደምድሟል፡፡ ችግሩ የአመለካከትና የቁርጠኝነት እንጂ የሚያሠራ አቅም ማጣት አይደለም ተብሏል አሉ፡፡ የዚህ መደምደሚያ ዓላማ ደግሞ የፌዴራል መንግሥትና የኦሮሚያ ክልል የወሰዱትን የአመራር ሽግሽግ በጎ ዕርምጃ ያህል እንኳን ላለመነካካት ነው፡፡ እነዚያን የለውጥ ቀበኞች፣ አንዳንድ ቡድኖችና አቅመ ቢሶች በመድረኩ ላይ እግር እንዲዘረጉ ለማድረግም ነው፡፡

በመሠረቱ አዲስ አበባ የሸገር ልጆች ከተማ ብቻ አይደለችም፡፡ የመላው የአገሪቱ ሕዝቦች የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማዕከልም ነች፡፡ ከዚያም አልፎ የአፍሪካ መዲና፣ ከ120 በላይ ዲፕሎማቲክ ማኅበረሰቦች መገኛ፣ የዓለም አቀፍ ተቋማትም መሰብሰቢያ ነች፡፡ በዚህ ላይ ፈጣን ለውጥ የጀመረች እንደመሆኗ ወደ ሚትሮፖሊታን ደረጃ ለመድረስ ሰፊ ሥራ ይጠብቃታል፡፡ ይህን እውነታ ተገንዝቦ በላቀ ኃላፊነት የሚሸከም፣ ተወዳዳሪና ብቃት ያለው አመራር ሊኖራት ይገባል መባሉም ለዚሁ ነው፡፡

አሁን በተያዘው መንገድ በኢሕአዴግ ‹‹አባልነት›› ታፔላም ሆነ በብሔር ተዋጽኦ ስም (ነባሩን ከተሜ እየገፉ) የገጠር ካድሬ በመኮልኮል የከተማዋን ትራንስፎርሜሽን ማረጋገጥ አይደለም ችግሮቿንም መቅረፍ ያዳግታል፡፡ አዲስ አበባ እኮ አሁንም የሞቱ ወንዞች የሞሉባትና በቆሻሻ ክምሮች የተዋጠች ነች፡፡ ለሕፃናትና አረጋውያን መዝናኛ፣ ለወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያ ዕጦት ያደቀቃት፣ እየተሻሻለ ቢመጣም የአረንጓዴ ልማቷ ያልተሟላ ከተማ ነች፡፡ ነዋሪዎችን መላወሻ የሚያሳጣ የትራንስፖርት እጥረት፣ ኑሮን የሚያማርር የመኖሪያ ቤት እጥረት (የኪራይ ዋጋ ማሻቀብ)፣ የመጠጥ ውኃ አለመዳረስ፣ ያልተሟላ አገልግሎት አሰጣጥ ከፍተኛ ሥራ የሚፈልጉ ናቸው፡፡

መዲናዋ ያላትን ተስፋ ያህል የወጣቶች ሥራ አጥነት፣ በሱስና አልባሌ ምግባር መጠመድ ጭንቀቷ ሆኗል፡፡ ሴተኛ አዳሪነትና ልመና የዘወትር ገጽታዎች ናቸው፡፡ ከገጠር ወደ ከተማ የሚደረገው ፍልሰት ማስተናገጃ አዲስ አበባ ናት፡፡ እነዚህ ሁሉ የቤት ሥራዎች ከፊቷ በተደቀኑ ከተማ ላይ ነባሩን አመራር ሳይነካኩ ተዛዝሎ ለማሻገር ማሰብ ውድቀት ነው፡፡ ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› አድርገናል እያሉ ለቀናት በር ዘግቶ ተመሳሳይ ዲስኩር መደርደር ሕዝብን የሚያሳዝን፣ መንግሥትንም ትዝብት ላይ የሚጥልና አገርንም የሚጎዳ ተግባር ነው፡፡ ‹‹ጨው ለራስህ ስትል ጣፍጥ አለበለዚያ ድንጋይ ነው ብለው ይወረውሩሃል!!›› የሚባለው ተረት ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡  

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

            

Standard (Image)

የጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስትመንት ለምን ተዳከመ?

$
0
0

በጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስተሮች ኅብረት ሥራ ማኅበር

የጋምቤላ ሕዝብ ወኪል የሆነው የጋምቤላ ሕዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትና የፌዴራል መንግሥት ክልሉን በማልማት የክልሉ ሕዝብ የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል፣ ቆራጦች የሆኑና ራሳቸውንም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ልማታዊ ዜጎችና አጋሮች በክልሉ ልማት እንዲሳተፉ በይፋ ጋበዙ። ጋምቤላ ታዳጊ ክልሎች ተብለው ከሚጠሩ የአገራችን ክልሎች በጣም በዝቅተኛ ደረጃ የምትገኝ ክልል ናት። የተሻለ ምቾት፣ ብዙ ባለሀብት ከሰፈረባትና ብዙ ገንዘብ ከሚንሸራሸርባት ከመዲናችን አዲስ አበባ ጠረፍ አካባቢ ያለችው ጋምቤላ ከ780 ኪሎ ሜትር በላይ ርቃ ትገኛለች። የክልልና ፌዴራል መንግሥት ጋምቤላ ሰፊ ለም የመሬት ሀብት እንዳላት በማውሳት፣ ከመሬቷ ፍሬ አፍርተው ለገበያ በማቅረብ የሚያለሟትና የምታለማቸው ዜጎች ለማግኘት በሰፊውና በተደጋጋሚ ጥሪ አቅርቧል።

አቤት! የኛ አገር ምድር! የመንግሥታችን ፖሊሲና የልማት አቅጣጫ ሰንቀን በላብ በወዛችን ጥረን ግረን አብረንሽ እናድጋለን ብለን የሞቀ ጎጇችንና ቤተሰቦቻችን ተሰነባብተን ጥሪውን የተቀበልን ጥቂት ዜጎች፣ የእርሻ ኢንቨስተሮች ለመሆን የዛሬ ስምንት ዓመት ገደማ ጋምቤላ ደረስን። እርሻ ከባድ የኢንቨስትመንት ዘርፍ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ከተማ የለመደ ባለሀብት የማይመርጠው ዘርፍ መሆኑ ይታወቃል። ቢሆንም ከጋምቤላ ሕዝብና መንግሥት ጋር ተባብረን ለፍሬ እንበቃለን ብለን ተስፋ የሰነቅን ልማታዊ ዜጎች ከየአቅጣጫው መጥተን ጋምቤላ ተገናኘን። ጋምቤላም ቀድሞ ለደረሰ ቅድሚያ በሚል መርህ ‹‹እንኳን ደህና መጣቹሁ›› ብላ ታስተናግደን ጀመር።                                  

የጋምቤላ መሬቶች ለሜካናይዝድ እርሻ ልማት የተዘጋጁ አይደሉም። እኛ ወደ እርሻ ኢንቨስትመንት ስንገባ በከተማዋ ከሁለት ያልበለጡ ሆቴሎች፣ ከከተማዋ ወደ እርሻ ቦታ የሚወስድ መንገድ አልነበረም። ከሁሉም በላይ አስተማማኝ ያልሆነ ፀጥታ፣ የጉልበት ሠራተኛ ያለመኖር፣ ንፁህ ውኃ ያለማግኘት፣ መብራትና ሌሎች መሠረተ ልማቶች ባልነበሩበት ሁኔታ ነው። ታድያ ቀድም ባለ የሕይወት ጉዟችን በሌላ ቦታ ያፈራነውን ሀብትና ንብረት አፍስሰን ክልሉን ለማልማት የደፈርን ቆራጥ ኢትዮጵያዊያን በሞፈርና በቀንበር ሳይሆን በትራክተር፣ በበሬ ጉልበት ሳይሆን በነዳጅ ኃይል፣ ሜካናይዝድ ፋርም ለመፍጠር በጋምቤላ መሬቶች ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጀመርን። ይኼን ያደረግንበት ጊዜ ስለጋምቤላ መልካም ምሥል ባልነበረበት ጊዜ መሆኑ ማስታወስ ተገቢ ይመስለናል።                          

እንዲህ ባለው ሁኔታ ውስጥ ሆነን ተፈጥሮን ለእርሻ ምቹ ለማድረግ ከተፈጥሮ ጋር ልማታዊ ትግል አካሄድን። መሠረተ ልማት በሌለበት የመሬት ልማት ለማከናወን፣ ሕይወት፣ አካልና ንብረት ማጣት ለልማቱ የሚከፈል ዋጋ ነበር። የመሬት ልማት ሥራውን ስትታገል ከርመህ አንድ የአገሪቱ ልማት የማይፈልግ ‹ክፉ› ወይም ‹ነገሩ ያልገባው› ሰውም ሊጎዳህ ይችላል። በመሆኑም ብዙ ዓይነት ሰው ሠራሽ የደኅንነት ችግሮች ነበሩ ይኼም ታልፏል። ለእርሻ ዝግጁ ያልሆኑ ሰፋፊ ለም መሬቶች የእርሻ ማሳ እንዲሆኑ ለማልማት የሚከናወን ተግባር እንዲሁ በጥላ ሥር ሆነህ ዕቃን በመሸጥና በመለወጥ እንደሚገኝ ሀብት ተመኝተህ የምትገባበት አይደለም። አዲስ የአየር ፀባይ፣ አዲስ መንደር፣ ብዙ ያልተጠበቀ ነገር መጋፈጥ ግድ ይላል፡፡ ቆራጥነትንም ይጠይቃል።

ከዚህ በላይ ዘር መሬት ላይ በትነህ፣ በስብሶ፣ ተመልሶ በቅሎ፣ አረም ታርሞ፣ ከነፍሳት ታድገህ፣ ታጭዶ፣ ተወቅቶ፣ ለገበያ ቀርቦ ይኼ ሁሉ ረጅም መንገድ ተጉዞ ከቀናህ የበተንከውን ትሰበስባለህ፡፡ ለፍሬ ለአምሃ ትበቃለህ። ገበያና ኢንዱስትሪ ይንቀሳቀሳሉ። እርሻና የእርሻ ሰዎች ሕይወት እንዲህ መሆኑ የገባን ዜጎች፣ የአገራችንን ፀጋ አነቃቅተን ወሳኝ የኢኮኖሚ አውታር በሆነው የእርሻ ኢንቨስትመንት ተሠማራን።                  

የጋምቤላን የልማት ጥሪ ተቀብለን በልበ ሙሉነት የሄድን ኢንቨስተሮች ሀብትና ንብረታችንን ይዘን እንጂ፣ የመንግሥት ብድር አመቻችተን እንዳልነበረ መታወቅ አለበት። ይኼ እውነታ መረሳት የሌለበት ሀቅ ነው። በተጨማሪ ኢንቨስተሩ ወደ ተሰጠው የእርሻ ቦታ ይሁን ወደ አካባቢው የሚወስድ የተሰናዳ መንገድ አይታሰብም። መደበኛ ሆነ ተንቀሳቃሽ ስልክ አልነበረም። በሥራ ላይ ውለው አቅጣጫ ስተው በመከላከያ አብሪ ጥይት እየተፈለጉ የተገኙ ኢንቨስተሮች ብዙ ናቸው። ይኼም ለአገር ልማት የተከፈለ ዋጋ ነው።

ብዙ የመሠረተ ልማትና የአቅርቦት እጥረት ባለበት አካባቢ በዘመናዊ የእርሻ መሣሪያና በሰው ኃይል ለማልማት ዘመናዊ እርሻን ዕውን ለማድረግ የታገልን ዜጎች የከፈልነው መስዋዕትነት፣ አሁን ጋምቤላ የሞቀች ከተማ እንድትሆን ብዙ መንደሮችም ሰላም እንዲሆኑ ረድቷታል ቢባል ደፍሮ ‹ውሸት› የሚል አይኖርም። እኛ የጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስተሮች የክልሉን ኢንቨስትመንት ህያው ለማድረግ የከፈልነው ዋጋ በጣም ብዙ፣ እንዲሁም ዘርፈ ብዙ መሆኑ መዘንጋት የለበትም። መንግሥት እርሻን ለማሳደግ ባለው ቁርጠኝነት በዝናብ ለሚካሄድ እርሻ ከአራት ዓመታት በኋላ በ40/60 መዋጮ ብድር ፈቀደ ተባለ፡፡ ቀድመን በሥራ ለነበርን ኢንቨስተሮች እሰየው የሚያሰኝ ነበር። ይሁን እንጂ የሰማይ ዝናብና መሬት አቀናጅቶ ወደ ምርት ለመድረስ ለሚታገለው ኢንቨስተር ግን አሁንም ዘርፉ የዕለት ተዕለት ብዙ ውጣ ውረድ ስለሚሻ ሁሌም ጥንካሬውን፣ ፅናቱንና ውሳኔውን የሚፈትን ጭንቀት አይቀሬ ነው።

መንግሥት ባለፉት ዓመታት እርሻ መር ኢኮኖሚ መምረጡና አሁንም እርሻ ተቀዳሚ የትኩረት አቅጣጫ ማድረጉ ተገቢ እንደሆነ በማሳ ለዋለ ሰው ማብራርያ አያስፈልገውም። እርሻ ‹ሕይወት ያለው ነገር መንከባከብ ነው›፡፡ ነገር ግን ፈጣን የቢሮክራሲ ምላሽ ካላገኘና ምላሹ የዘገየ ከሆነ ከሞት በኋላ እንደመድረስ መሆኑ መታወቅ አለበት። የቢሮክራሲው ምላሽም የምታውቁት ነው። ቢሮክራሲው ከተፈጥሮ በላይ ለእርሻ ኢንቨስተሩ ሌላው በወረቀት ላይ ያለ ፈተና ነው። ተፈጥሮንም ቢሮክራሲንም በብቃትና በተደረጀ ስንታገል ቆይተናል። አሁንም በጋምቤላ ገጠሮች ትራክተሮች፣ የእርሻ ማሽነሪዎችና የግብርና ባለሙያዎች ላይ ታች ሲሉ ይውላሉ። የአካባቢው ነዋሪዎችም የቻሉትን፣ ያጠኑትን ያህል አብረውን ይንቀሳቀሳሉ። ኢንቨስተሩም የልጆቹን ናፍቆት፣ የካፌ ጨዋታ፣ የማኪያቶና ኬክ፣ ሳውናና ጃኩዚ፣ ጥላ ሥር ተቀምጦ መዝናናት፣ ይቆይልኝ ብሎ ከፀሐይ ንዳድና ከአቧራ ጋር ታግሎ ራሱንና አገሩን የሚለውጥ ፍሬ ለማፍራት ተስፋ ሰጪ በሆነ ደረጃ ይገኛል። ኢንቨስተሩ በቆሎ፣ ጥጥ፣ ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ ማሾ አምርቶ ለአገር ውስጥና ለውጭ አገሮች ገበያ ማቅረብ ጀምሯል። ዘግይቶ ከደረሰው የኢንቨስትመንት ብድሩንም መመለስ የጀመረ ብዙ ነው።                                  

‹ውሻው ይጮኻል ግመሉ ግን መንገዱን አላቋረጠም› እንዲሉ ስለኢንቨስተሩ ብዙ ተብሏል። የጋምቤላ መሬት ግን እትብታችን የተቀበረባት አገር መሬት ናት በሚሉ ቆራጥ ኢትዮጵያዊያን እየለማች ነው። ወሬን በወሬ ከመመለስ በተግባር የታየውን ለውጥ መናገር ይሻላል። የጋምቤላ ገጠሮች ባተሌ ወይም በእንግሊዝኛው “ቢዚ” ሆነዋል። እንደ ሌሎቹ የኢትዮጵያ ክልሎች የኢኮኖሚ መነቃቃት ተፈጥሯል። በክልሉ በተፈጠረው የኢኮኖሚ መነቃቃት በሳምንት አንድ ጊዜ የነበረው የአየር መንገድ በረራ በቀን ሁለት ጊዜ ሆኗል። ሌላው የኢንቨስትመንቱ ትሩፋት ከእያንዳንዱ የጋምቤላ ቤት በዚህ ኢንቨስትመንት ምክንያት ቢያንስ አንድ የቤተሰብ አባል የድርጅት ሠራተኛ ሆኖ ተጨማሪ ገቢ ለቤተሰቡ ይፈጥራል። ከአጎራባች ክልሎች የሚመጡ ሠራተኞችም ብዙ ናቸው።                             

ኢትዮጵያዊያን የእርሻ ኢንቨስተሮች ከጋምቤላ ሕዝብ ጋር አብረው ይውላሉ፣ አብረው ያድራሉ። በዚህም ኢንቨስተሮቹ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ብዙ ዓይነት ማኅበራዊ እገዛ ያደርጋሉ። ለተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ የሚያበረክቱ፣ ሰፋፊ መሬቶች አርሰው፣ ዘርተውና አፍሰው ምርቱን የሚያከፋፍሉ፣ ትምህርት ቤትና የጤና ተቋም የሚገነቡ ብዙዎች ናቸው። የጋምቤላን ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የተገነዘቡ የሆቴል ባለሀብቶችም አምና ባለአምስት ፎቅ ሆቴል ሠርተዋል። እኛ ግን ወደ እርሻ ስንሠማራ በጋምቤላ ሻይ ቤት ማግኘት ከባድ ነበር። አሁን ሁሉም ነገር ተለውጧል። በዚህም ደስተኞች ነን።  

ነገር ግን ክፉ ዘፈን የሚያቀነቅኑ አደገኛ ዘረኞችና የድል አጥቢያ አርበኛ የመሆን ልምድ ያላቸው ‹‹የበሬውን ምሥጋና ወሰደው ፈረሱ›› እንደሚባለው አስቸጋሪውን የልማት ሒደት ጥላሸት ቀብተው፣ ዛሬ በሌሎች መስዋዕትነት በተስተካከለው ጊዜ ብቅ ብለው ለመበልፀግ የተዘጋጁ የውስጥና የውጭ ሰዎች ከባድና አደገኛ ዘመቻ ሲያካሂዱ ሰንብተው መንግሥትንም ጭምር ለማደናገር ችለዋል። ሠራተኛ ወሬ እያወራ እያሳበቀ ሊውል አይችልም፡፡ ሥራውን ማን ይሠራለታል? ወሬኛው ግን ሥራው ወሬ ነው። የጠንካራውን ዜጋ ላብና ደም መምጠጥ ነው። ‹‹ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው›› የሚል እንጂ ‹ሥራ ችግር ያሸንፋል› የሚል መሪ ቃል የለውም። በመሆኑም የባተሌውን ፍሬ ለመንጠቅ ወሬ ሲፈበርክ፣ ሲያስተሳስር፣ ሲያዳርስ፣ ሲጋብዝና ሲነዘንዝ ይውላል። እንዲህ ያሉት ወሬኞችና ዘረኞች ያደረጉት የማደናገር ተግባርን መተረክም ሥራችን ባይሆንም፣ እየደረሰብን ያለውን ጥቃት ለመከላከል መናገር ግድ ስላለን እውነቱን እንነግራችኋለን።

የወሬ አሎሎው የተጀመረው ‹‹የጋምቤላ መሬት እየተወረረ ነው›› በሚል ሲሆን፣ ይኼም ወሬ ‹‹የባንክ ብድር ተፈቀደ›› ሲባል ተጀመረ። ከዚያ በፊት ያሳለፍናቸው የመሬት ልማት ትግሎች ዓመታት ላይ ወሬ አልነበረም። ምክንያቱም ቁርጠኝነትና ወገናዊነት የሚጠይቅ ውሳኔ የሚያስፈልግበት ጊዜ ስለነበር። የድል አጥቢያ አርበኞቹ አስቸጋሪው የመሬት ትግል እስኪያልቅና ሌላው ዜጋ መስዋዕት እስኪሆንላቸው መጠበቅ ነበረባቸው። በሌሎች መስዋዕትነት የጋምቤላ ኢኮኖሚ ተነቃቃ። ከዚህ በኋላ ወሬው መጠናከር ነበረበት። በመሆኑም በአገር ውስጥና በውጭ ያሉ ኃይሎች ሚዲያዎች በማስተባበር የመሬት ወረራ ወሬውን አጠናከሩት። እነዚህ ሰዎች ትኩረታቸው ኪሳቸው ነውና ከሁሉም ፀረ መንግሥትና ፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ጋር በመሆን ወሬውን አራገቡት። መንግሥትም በአጀንዳው ላይ ምላሽ እስኪሰጥ ድረስ ገፉበት። ተሳካላቸው። ወደ ሁለተኛውና ወደ ላቀው ደረጃ መሻገር ነበረባቸው። በመሆኑም ወራሪ የሚሏቸው ዜጎችን ማንነት መጥቀስ ጀመሩ።  

እንደተወራው የወሬ አሎሎ ብዛትና የቅስቀሳ ስፋት ብዙ ጥቃት በደረሰብን ነበር። የጋምቤላ ሕዝብ ምሥጋና ይድረሰውና ወሬኞቹ ወደፈለጉት አቅጣጫ አልሄደም እንጂ፣  የተደገሰው ድግስ በየማሳችን የምንቀርበት ነበር። ልባሙ የክልሉ ሕዝብ ይኼን ባለማድረጉ የተቆጩት የውስጥም የውጭም ኃይሎች የወራሪዎቹ ስም ዝርዝር በሚል በኢሳት ለወዳጅም ለጠላትም ይፋ አደረጉት። አሁንም ጨዋው የጋምቤላ ሕዝብ በኢትዮጵያዊያን ወገኖቹ ላይ እጁን አላነሳም፡፡ ይልቁንም ተባብሮ መሥራቱን ቀጠለ። በዚህ መንገድ ያልተሳካላቸው የአገርና የእኛ ጠላቶች ወደ ቢሮክራሲው በመዞር ሌላ አቅጣጫ ጀመሩ። እርግጥ ከመጀመርያውም ራሳቸው የቢሮክራሲው አባላትና ጓዶቻቸው ያሳበቁት ወሬ እንደነበረ ባይካድም፣ ጥቂት የትግራይ ሰዎች ጋምቤላን ተከፋፍለው እንደተቀራመቱት በማስመሰል አዲስና አደገኛ ወሬ አድርገው ቢሮክራሲውን አራገቡት። በተጨማሪም ‹‹የመንግሥት ፋይናንስ እየተዘረፈ ነው›› የሚል የማደናገሪያ ግብዓትም በመጨመር ማስፋፋታቸውን ቀጠሉ። በሥራ ላይ ያለ አርሶ አደር ለእነዚህ ሁሉ ወሬ ጊዜ የለውም። ወሬው ግን እግር አውጥቶ እየተከተለን ልማታዊ ሥራችንንና መልካም አገራዊ ራዕያችንን ተፈታተነ።  

በነገራችን ላይ የተጠቀሱት ወሬዎች የተፈበረኩት ‹‹በዝናብ ለሚካሄድ እርሻ መንግሥት ብድር ፈቀደ›› ከተባለ በኋላ መሆኑን እንዳትዘነጉ። ወሬው የታሰበለትን ‹ዒላማ› እንዲመታ የሚመስል ታሪክ እንዲኖረው ለማድረግ የወሬና የድል አጥቢያ አርበኞችና መሐንዲሶች የተዋቀረ መቸት ያለው የልብ ወለድ ድርሰት ተፈጥሮለታል።

‹‹ለጥቂት የትግራይ ተወላጆች የልማት ባንክ ያለ ኮላተራል ይሰጣቸዋል፣ ለግብርና ብለው የሚወስዱት ገንዘብ አዲስ አበባ ፎቅ ይሠሩበታል፣ ሃያ ሁለት ይዝናኑበታል . . . ›› ተባለ። ይኼ ወሬ ወዳጅንም ጠላትንም ለማደናገር እስኪችል ድረስ አቅም አግኝቷል። ማስቲካ፣ ክሬም፣ ቸኮሌት ለማምጣት ያልተገባ የፋይናንስ አሠራር ይኖር ይሆን? ብሎ የጠየቀ ብሎም ያወራ ቢሮክራት ግን አልሰማንም። በዚህ ዘርፍ ስንት የውጭ ፋይናንስ አገራችን አጥታ ይሆን? ብሎ ያዘነ ተቆርቋሪ ባለሥልጣን ግን አላየንም። ለእርሻ የተደረገው በጣም አናሳ የሆነ ብድር ግን ተዘረፈ ተባለ። የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ የሚጎዳው የትኛው ነው? ወይስ ነገሩ ዘርና ቀለም ይመርጣል? ይኼ የወሬ ደረጃ ዘመቻው የተሳካበት እርከን ነው። በመሆኑም ብድሩ ከአንድ ዓመት በላይ ቆመ። ኪሳራው በእኛ መሬት አልምተን፣ ተፈጥሮን ቀይረን፣ ልማት አይተን፣ አገር እንገነባለን ባልን ዜጎች ላይ ሆነ። አዲስ አበባን ሳይለቁ የሚንቀሳቀሱ ባለሀብቶች ግን ብድርም አልቀረባቸው፣ ነገርም አልደረሰባቸውም። የባንክ ብድር እንኳንስ ኢትዮጵያዊያን የሆነውን የትግራይ ተወላጆች ህንድ፣ ቻይና፣ ፓኪስታን . . . ይወስድ የለም? በዚህ የታሪክ አጋጣሚ መጪው ትውልድ ከእኛ ከአርሶ አደሮቹ ወይስ አየር በአየር ትርፍ ከሚገኝበት ሥራ ላይ ከሚሠሩ ዜጎች ይማር?

የልማት ባንክ ተበዳሪዎች ሁሉም ኢትዮጵያዊያንና የሌሎች አገር ዜጎች ሆነው እያለ፣ ወሬኞቹና የአገሪቷ መሠረታዊ ጠላቶች በትግራይ ተወላጆች ላይ ማነጣጠራቸው የሚያተርፉባቸው ነገሮች ስላሉዋቸው ነው። አንደኛ ለሃያ አምስት ዓመታት ሲያዜሙት የነበረ ዜማ ስለሆነ በቀላሉ የአድማጭ ህሊና ይቀበለናል በሚል እሳቤ ነው። ይኼ እሳቤ በጋምቤላ ሕዝብ ህሊና ውስጥ ሠርቶ ቢሆን ኖሮ ይደርስብን የነበረው የአካልና የሕይወት ጉዳት እጅግ ከፍተኛ ነው። ይኼ ተሳክቶላቸው ቢሆን ኖሮ የዜጎችን ተዘዋውረው የመሥራት መብታቸውን መገደብ ይችሉ ነበር፣ አልሆነም። የጋምቤላ ሕዝብ በየዕለቱ የምናደርገውን ጥረትና ድካም ስለሚያይ ወሬውን አልተቀበለውም። ይሁን እንጂ በሌላው ኢትዮጵያዊ ህሊና ግን የትግራይ ተወላጆች የተለየ ዕድል እየተሰጣቸው ይሆን? የሚል ጥያቄ አልፈጠረም ብለን አናስብም። ስለዚህ በቦታው በሌለ ሕዝብ ላይ የማደናገር ሥራ ተሳክቶላቸዋል የሚል ግምት አለን።  ሁለተኛው በራሱ ፈቃድ ልማቱን ለማደናቀፍ ዝግጁነት የነበረው ቢሮክራሲ ላይ የተካሄደ ዘመቻ ለወሬኞቹ ባለሙሉ ፍሬ ሆኖላቸዋል። በመሆኑም ግብርናውን ለአንድ ዓመት የሚጎዳ ብድርን የማቆም ውሳኔ ወስኖላቸዋል። በዚህም በኢንቨስተሮች ህሊናና ዝግጁነት ላይ ቀላል የማይባል ጉዳት አድርሷል። ሦስተኛው ሥርዓቱን ይደግፋሉ ብለው የሚያስብዋቸውን ሰዎች በሥርዓቱ ቢሮክራቶች ጉዳት እንደሚደርሳቸው በቂ መልዕክት አስተላልፏል። ይኼ ሁሉ ግን ምቾትና ድሎት ባለበት የንግድ ሥራ ስለተሰማራን ሳይሆን፣ የትግራይ ተወላጆች በመሆናችን ብቻ የደረሰብን የተቀነባበረ ግፍ ነው።   

የወሬው አሎሎ ስለፋይናንሻል ድህነታችንም አዚሟል። ዋናው ድህነት የአስተሳሰብ ድህነት ነው። እንኳንስ መሬት ላይ በግልጽ የሚታይ ትራክተርና ሌሎች የእርሻ መሣሪያዎች በግዢና በውሰት ይዘን ሄደን፣ ሥራ ጀምረን፣ ፍሬያማ ሆነን፣ ሐሳብ ብቻ ይዞ መሄድ በቂ ነው። ድሆች ናቸው ብለው የዘፈኑብን ግን በሆቴል ስም ካገኙት ብድር አተራርፈው ወይም  በኢምፖርት ሸቀጥ ገንዘብ ያካበቱ ወገኖቻችን ናቸው። እኛ ሀብት ከመሬት ይፈጠራል ማለታችን አዲስ ሀብት ለመፍጠር በማሰባችን ነው። ወሬኞቹ ግን በተመቻቸና በሌሎች ድካምና መስዋዕትነት መኖር የኑሮ ዘይቤያቸው ያደረጉ ስለሆኑ፣ በልማታዊ ባለሀብት ላይ ስም መለጠፍ ዋና ሥራቸው ሆኗል። እኛ ቀደም ብለን ያለንን ዕውቀት፣ ጉልበትና ሀብት  በጋምቤላ በማፍሰሳችን የሚታይ የኢኮኖሚ መነቃቃት ተፈጥሯል። ለዚህ እኛን አመስግነው ወደ ራሳቸው ሥራ መግባት ሲጠበቅባቸው፣ እኛን ለመጉዳት የሆነና ያልሆነ በማውራት ሥራችን መበደል ለምን አስፈለጋቸው? ሰው የግድ ከአንድ ዘር መፈጠር የለበትም። አስገራሚው ነገር በመንግሥት ቢሮክራሲ ውስጥ ያሉ ሰዎች ይኼንን ማራገባቸው ይገርማል። የሆነ ሆኖ እኛ ድሆች አይደለንም፡፡ ድሆቹ ጥገኞቹ ናቸው። እኛ ከመሬት ልማት ጋር በመታገል ላይ ያለን ዜጎች ነን። ለልማቱ ድፍረትና ፈቃደኝነት ይኑራቸው እንጂ ለሁላችንም ይበቃናል። በማንነታችን ላይ የሚያካሂዱት ዘመቻ ግን አገር የሚበትን ስለሆነ መንግሥትም ሆነ ልባም ዜጎች ሊያቆሙት የሚገባ ድርጊት ነው። ካልሆን ግን ጉዳቱ ለሁሉም ይደርሳል!፡፡    

በወሬኞች ምክንያት የደረሰብን ጉዳት

ሀብትና ንብረታችን በማሳ ላይ እያለ ለመሰብሰብ ሳንችል እንድንቀር ሆን ተብሎ ያለበቂ ሙያዊ ምክንያት ወሬ በማብዛት ብቻ የባንክ ብድር እንዲቆም ተደርጓል፡፡ በተወሰኑ የፌዴራል ሚኒስትር መሥሪያ ቤቶች ያሉ ለሥርዓቱ ወገንተኝነት የሌላቸው በወፍራም ወንበር ተቀምጠው ልማቱን ሳይሆን የአልሚው ማንነት የሚገዳቸው ባለሥልጣናት፣ በደስታ እያስተናገደን የነበረውን የጋምቤላ ክልል መንግሥት እየተጫኑ በሔክታር 30 ብር የነበረውን የመሬት ግብር በአንድ ጊዜ ወደ 111 ብር ከፍ እንዲልና አቅማችን ተዳክሞ እንድንወጣ አሲረውብናል። ከፍተኛ ድጋፍ የሚሻው የኢትዮጵያ የግብርና ኢንቨስትመንት ለዘርፉ የተቀመጠው የባንክ ብድር ወለድ 8.5 ብር የነበረ ሲሆን ወደ 12.5 ብር ከፍ እንዲል ተደርጓል። ይህም በጋምቤላ በእርሻ የተሠማራንን ለማክሰር ታስቦ የተደረገ ቢሆንም ጦሱ ግን ለሁሉም በዘርፉ ያሉ ኢነቨስተሮች ደርሷል። ሌላው ሆን ተብሎ የመሬት መደራረብ እንዲፈጠር ተደርጓል። በዚህም ኢንቨስተሩ እርስ በርሱ እንዲጋደል ለማድረግ የታቀደ ሴራ እንጂ ሥራው ከባድ ነገር ሆኖ አይደለም። ለመሬት ልማት በሔክታር የሚፈቀድ ብድር ከዘጠኝ ሺሕ ብር ጀምሮ በተካሄዱ ተከታታይ ጥናቶች 43 ሺሕ ብር ደርሶ የነበረ ሲሆን፣ ያለ ሙያዊ ጥናት ብድሩ በሔክታር በቀጥታ ወደ 11 ሺሕ ብር ድንገት እንዲወርድ ተደርጓል። ይኼም በኪሳራ እንድንወጣ ታስቦ የተደረገ እንጂ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጥናት እንኳን ለሔክታር 78 ሺሕ ብር ይፈቅዳል። በእርሻ ኢንቨስትመንት የሚሠማራ ዜጋ ከ7.5 ሚሊዮን ብር በላይ በካሽ ሊኖረው ይገባል የሚል ገዳቢና ከባድ ደንብ አስቀምጧል። ይኼም ድሆች ናቸው ከሚል እሳቤ የተነሳ የማጥቂያ ታክቲክ ነው እንጂ ለዘርፉ ዕድገት የሚጠቅም አይደለም። ለእርሻ ኢንቨስትመንት ተጨማሪ ኮላተራል እንዲቀርብ የሚደነግግ መመርያ ወጥቷል። በጣም አስገራሚው ነገር በከፍተኛ ዋጋ የለማው መሬት በመዋጮ እንዳይያዝ የሚያደርግ ደንብ ተቀርጿል። ይኼ አሠራር ከኢንቨስትመንት መሠረታዊ ባህርይ ጋር የማይገናኝ ሲሆን፣ እኛን ለማክሰር ያለሙት ወገኖች ግን ዒላማቸውን ለማሳካት ደንቡን ተግባራዊ ለማድረግ ወደ ኋላ አላሉም። ከመሬት መደራረብ እስከ ሌላኛው የቢሮክራሲ አሻጥር የፈጸሙት ሰዎች የጋምቤላ እርሻ ጉዳይ የአገር ችግር ለማስመሰል በመቻላቸው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ኮሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል። ይሁን እንጂ አጣሪ ኮሚቴው የወሬኞቹና የአሳባቂዎቹ ደጋፊዎች ስብስብ ሆኗል። ምክንያቱም የተጠቀመው የማጣራት ዘዴና ባለድርሻ አካላት የመፍትሔ አካል እንዲሆኑ ለማድረግ ፈቃደኛ ያለመሆን ማሳያዎቹ ናቸው። በተጨማሪ ኮሚቴው የታረሰ መሬት እንጂ የለማ መሬት በጥናቱ ለማካተት ፈቃደኛ ባለመሆኑ፣ መሬት ላይ ያለው ልማት አነስተኛ እንዲሆን የማድረግ ዘዴ ተጠቅሟል። ይኼም እውነተኛ የአካባቢው የልማት ሁኔታ ማሳየት አልቻለም።

በ2007 ዓ.ም የመሬት መደራረብ ችግር በሚል ሰንካላ ምክንያት የተደረበበትም ያልተደረበበትም ኢንቨስተር በጅምላ ብድሩ እንዲቆም ተደረገ። በ2008 ዓ.ም. ደግሞ ‹የባንኩ ገንዘብ እየተዘረፈ ነው› በሚል በድጋሚ ቆመ። በእነዚህ ሰንካላ ምክንያቶች የኢንቨስተሩን ልማት ሲጎዱ ከቆዩ በኋላ ጥናት እናካሂድ ብለው ተሠማሩ። ‹‹አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ›› የሚሉት ሆኗል። ተደጋጋሚ ጥቃት ካደረሱ በኋላ ዳኝነቱን ራሳቸው ይዘው ጠቅላይ ሚኒስትሩን የሚያሳስት ሪፖርት አቀረቡ። ይኼ ሁሉ ሴራ ግን ግብርናውን ወይስ ወሬኛውን ይጠቅማል?  ህሊና ያለውም ኃላፊነት የሚሰማውም ሰው ጉዳዩን ተመልክቶ ይፍረድ። መሬት ቆፍረን ተጨማሪ ሀብት ፈጥረን ለመኖር ያደረግነው ጥረት በማንነታችን ምክንያት ከተሰናከለ፣ በዘርፉም ላይ በአገር ሆነ ትርጉም ያለው ችግር ይፈጥራል ብለን እናምናለን። ከሁሉም በላይ ለዘረኞች የልብ ልብ ይሰጣል። ምክንያቱም በሙያተኞች እውነቱን መግለጥ እየተቻለ በጅምላ ችግር ውስጥ እንድንገባ ማድረግ የወሬኞቹና የአሳባቂዎቹ ችግር ብቻ ሳይሆን፣ የፈጻሚው አካልም ስህተት ስለሚሆን ነገሩ በጊዜው ይታረም እንላለን። ነገሩ ካልታረመ በበኩላችን እንደ ዜጎች ሠርተን የምንኖርበት ዕድል የጠበበ ሆኖ ሊሰማን ጀምሯል። ዛሬ በእኛ ላይ ነገ በሌሎች ላይ ሳይደገም ይታረም መፍትሔ ይሰጠን!!

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው yemanes@gmail.com.  ማግኘት ይቻላል፡፡     

 

 

 

 

 

Standard (Image)

ልዩነት ውበት የሚሆነው አበባ መሸጫ ሱቅ ውስጥ ነው

$
0
0

በመታሰቢያ መላከ ሕይወት ገብረ ክርስቶስ

ውበትን ለመግለጽ እጅግ በርካታ መንገዶችን መሄድ ይቻላል፡፡ በዚህ ጽሑፍ አርዕስት ላይ እንደተጠቀሰው የአበባ መሸጫ ሱቅ ውስጥ የተለያዩ አበቦችን አንድ ላይ በማዋሀድ ዕይታን የሚማርክ ውበት መፍጠር ይቻላል፡፡

ሠዓሊያን የተለያዩ ኅብረ ቀለማትን በማድመቅና በማደብዘዝ ዓይን የሚማርኩ ውብ ሥዕሎችን ይሥላሉ፡፡ መኪና አምራቾች የሚያመርቱት መኪና መስጠት የሚገባውን አገልግሎት ብቻ ሳይሆን፣ ውበቱን ጠብቆ ተወዳጅ እንዲሆንና በገበያ ውስጥ ተገቢውን ዋጋ እንዲያገኝ ከፍተኛ ጥረት ያደርጋሉ፡፡

በኅብረተሰብ ሳይንስ ውስጥ ግን ልዩነት መጥበብ እንጂ መሥፈርቱ ለዕድገትም ለልማትም የማይጠበቅ በመሆኑ፣ ‹‹ልዩነታችን ውበታችን›› እያልን የተሳሳተ ፍልስፍና ማራመድ የለብንም፡፡ ልዩነት በብሔር ብሔረሰቦች ባህል፣ ቋንቋ፣ አመጋገብ፣ አለባበስ ወዘተ ያለ ቢሆንም ይህ ሒደት ማንም ከሚጠብቀው ፍጥነት በላይ እየጠበበ እየሄደ ያለበት ዘመን በመሆኑ ‹‹ልዩነታችን ውበታችን›› እያልን ጊዜያችንን ማባከን የለብንም፡፡ ለዕድገትና ለልማት በሚደረጉ በርካታ ተግባራት ምክንያት ሕዝቦች እየተቀራረቡ የጋራ ማንነት እየፈጠሩ በመሄዳቸው ሒደት፣ ፍጥረቱ በእጅጉ እየጨመረ የመጣበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡

ኢትዮጵያን በአሁኑ ወቅት እየተዘዋወርን ብንመለከት የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች በአለባበስ፣ በአመጋገብና በሌሎችም በርካታ የዕለት ዕለት ተግባራችን ላይ በምናከናውናቸው ሥራዎች ተመሳሳይነት በእጅጉ የበላይነቱን እየያዘ ያመጣት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡

ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ደጋግሞ እያነጋገረን ያለው ልዩነትን ማስተናገድ የቻለ ሥርዓት የእኛ ብቻ ነው ይበለን እንጂ፣ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ማንነታቸው በእጅጉ በከፍተኛ አደጋ ውስጥ የገባው በኢሕአዴግ ዘመን ነው፡፡ ለምሳሌ ቋንቋን ብንወስድ በሦስት ከፍለን ልናየው እንችላለን፡፡

1ኛ ከፍተኛ ዕድገት ያስመዘገበ ቋንቋ

2ኛ ባለበት ሳያድግ ያለ ቋንቋ

3ኛ የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበት ቋንቋ

እነዚህን ሦስቱን ሁኔታዎች በአግባቡ ብናያቸው ኢሕአዴግ ለሥልጣኑ ሲል በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት የሚሠራበትን ቋንቋ ማለትም አማርኛን በሚያስገርም ሁኔታ እንዲያድግ አድርጎታል፡፡ አማርኛ ቋንቋ ባለፉት 25 ዓመታት ያሳየው ዕድገት ቋንቋው ከተፈጠረ ጀምሮ ካሳየው ዕድገት የሚበልጥ እንጂ የሚተናነስ አይደለም፡፡

በመቶኛ ደረጃ ዕድገቱን ለማየት ብንሞክር በወፍ በረር ግምት ከ1000 (አንድ ሺሕ) ፐርሰንት በላይ ዕድገት አስመዝግቧል፡፡

በሁለተኛ ደረጃ የሚገኙ ቋንቋዎች እንደ ኦሮሚኛ፣ ትግርኛና አፋርኛ የመሳሰሉት ቋንቋዎች ደግሞ ባሉበት ምንም ዓይነት ዕድገት ሳያስመዘግቡ የተጓዙበትን ሁኔታ በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡

እዚህ ላይ ዕድገት ሲባል በሁለት ከፍለን ብናየው መልካም ነው፡፡

 2.1 የተጠቃሚዎች ብዛት መጨመር

 2.2 ቋንቋው ራሱን ከሳይንስና ከዕድገት ጋር እያዛመደ የሚያደርገው ዕድገት

በሦስተኛ ደረጃ ልናያቸው የምንችለው ቋንቋዎች እጅግ በርካታ ሲሆኑ፣ እነዚህ ቋንቋዎች በከፍተኛ ደረጃ (በተለይ አዲሱ ትውልድ በፍላጎት ለመጠቀም ያለው ዝንባሌ እየቀነሰ በመሄዱ) የመጥፋት አደጋ ተጋርጦባቸዋል፡፡ እነዚህን ቋንቋዎች በተለያዩ መንገዶች ሌላ ቢቀር በቅርስነት እንኳን ጠብቆ ለማቆየት በቂ ሀብት መሰብሰብ ባለመቻሉ፣ የባህል ባለቤት የሆኑትን ሕዝቦችም የማዕከላዊም ሆነ የክልላዊ መስተዳድሮች በቂ እንክብካቤ ለማድረግ አቅም መፍጠር ባለመቻላቸው፣ ችግሮች በስፋት እየተስተዋሉ ነው፡፡

አለባበስ፣ አመጋገብና ባህልን በተመለከተ በብዙ ብሔር ብሔረሰቦች በእሴትነት የሚታዩ የዕለት ተዕለት መገልገያ መሆናቸው እያበቃ፣ በመጤ ቁሳቁሶችና አልባሳት እየተዋጡ መሄዳቸውን የበዓላት ቀን ብቻ ማድመቂያ መሆናቸው በስፋት ይስተዋላል፡፡

ኅዳር 29 በደረሰ ቁጥር ‹‹ልዩነታችን ውበታችን›› እያልን ልዩነት ግን እየተደመሰሰ የሚሄድበት ሁኔታ በስፋት የሚስተዋል በመሆኑ፣ ሌላው ቢቀር በቅርስነት ደረጃ ጠብቆ የማቆየት ሥራ ተገቢው ትኩረት ሊሰጠው ይገባል የሚል እምነት አለኝ፡፡

ከላይ እንደጠቀስኩት ውበት የከፍተኛ ችሎታና የከፍተኛ ትጋት ውጤት በመሆኑ፣ የሚሠራበትንና የሚጠቅምበትን ቦታ ለይቶ ማወቁ ተገቢ ነው፡፡ ለምሳሌ በአንድ አገር ውስጥ ያሉ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከልዩነታቸው ይልቅ አንድ ዓይነት አስተሳሰቦችን ወይም የተቀራረበ አስተሳሰብ ቢያራምዱ ለአገርም ለዕድገትም ጠቃሚ ነው፡፡ የተለያዩ አስተሳሰብ የሚያራምዱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወደ ግጭትም ሊያመሩ ይችላሉ፡፡ ብሔር ብሔረሰቦችም ልዩነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ አንድ ሰፊ አገር፣ የጋራ ጠንካራ ኢኮኖሚ፣ ጠንካራ ወታደራዊ ተቋም ቢኖራቸው በሁሉም መመዘኛ ተጠቃሚነታቸው ከፍተኛ ነው፡፡

‹‹ልዩነት ውበት ነው›› እያልን ለማጉላት መሞከር ሳይሆን፣ አንድነት የሚያስገኘውን ከፍተኛ ጥቅም ለወጣቱ ትውልድ  ማስተማር በእጅጉ የሚበጅ ተግባር ነው፡፡

ልዩነት በባህል፣ በአስተሳሰብ፣ በፖለቲካና በአኗኗር በሁሉም የሕይወት ዘርፍ ያለና ወደፊትም የሚኖር ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን ልዩነትን ለማስተዋወቅ ወይም ለማጉላት መሥራት በፍፁም የለብንም፡፡

በማንኛውም ተግባር ላይ አንድ አባባል ሁሌ የሚደጋገም ከሆነ፣ በተለይ ብሩህ አዕምሮ ያላቸው ወጣቶች አብሮአቸው ስለሚያድግ የማይጠቅምን ነገር አጉልቶና ደጋግሞ ማስተጋባት ጉዳቱ ከፍተኛ ነው፡፡

እኛ ኢትዮጵያውያን እንደ ሌሎች አገሮች ሁሉ ያለንን በጎ ነገር ነው ለማጉላት መሞከር ያለብን፡፡ ለምሳሌ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ፣ የጥንታዊ ሥልጣኔ ባለቤት፣ ለነፃነታችን የታገልን ሕዝቦች፣ አፍሪካን ከቅኝ ግዛት ለማላቀቅ የታገልን ሕዝቦች፣ ወዘተ እያልን በጎ በጎውን ብቻ እያየን መሄድ እንጂ፣ የማይጠቅም ነገር መናገሩ አስፈላጊ ስላልሆነ በዝምታ ማለፍ ተመራጭ ነው፡፡

እዚህ ላይ በኢሕአዴግ ፖለቲካ ውስጥ ስለብሔረሰብ ሲነሳ ‹‹ልዩነታችን ውበታችን›› ይልና ፓርላማ ውስጥ ደግሞ ልዩነት አስፈላጊ አይደለም ይለናል፡፡ ልዩነት ከላይ እንደተጠቀሰው ሁሌም ያለና የሚኖር ሲሆን፣ ልዩነትን ችሎ ለመኖር ብቃትን ማዳበር እንጂ ልዩነትን ለማጉላት ተግቶ መሥራት በፍፁም ተገቢ አይደለም፡፡

ሰሞኑን እያነበብነው ያለነው መጽሐፍ የሚያስገነዝበን በኢሕአዴግ መዋቅር ውስጥ በኃይል የተፈጠረ አንድ አስተሳሰብ መኖሩን እንጂ፣ በተግባር ግን ኢሕአዴግ ውስጥ ያሉ አባላት ሁሉ የራሳቸው አስተሳሰብ እንዳላቸውና ደብቀው ጊዜ እየጠበቁ እንደሆነ የሚያመለክት ነው፡፡ ፈረንጆች አንድ አባባል አላቸው ‹‹The best friend is the worst enemy›› ይላሉ፡፡ በፖለቲካ ሕይወት ውስጥ አንድ መንግሥት ተሳክቶለት አንድን አገር በአንድ አስተሳሰብ ብቻ ለመምራት ቢሞክርም፣ የሥርዓቱ አባላት በዚህ መልኩ የሥርዓቱ ገመናዎችን ማጋለጣቸው አይቀርም፡፡ ማንኛውም መንግሥት ነገሮችን ደብቆ ለማስኬድ የማይቻልበት ዘመን በመሆኑ፣ ግልጽነት በምንም ሁኔታ በግንባር ቀደምነት የሚጠበቀው ከፍተኛ ኃላፊነት ከተሸከመው መንግሥት ነው፡፡

ሰዎች መደበኛ መንገድ አጥተው በተለይ በሚዲያና በፓርላማ የተለያዩ ሐሳቦችን ማንፀባረቅ ካልቻሉ ውጭ አገር ሄደው የሚያቀርቡት የልዩነት ሐሳብ የሚያስከትለው አደጋ እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ ኢሕአዴግ ሥልጣን የያዘበት ጊዜና የሚያራምደው አስተሳሰብ በፍፁም አብረው የማይሄዱ መሆኑን ተገንዝቦ ጊዜ ሳይጠፋ፣ በራሱ ላይ ከፍተኛ ተሃድሶ ማድረግ አለመቻሉ ለአገርም ሆነ ለኢትዮጵያ ሕዝቦች  አደጋው የከፋ መሆኑን መገንዘብ አለበት፡፡

በአሁኑ ወቅት ከኢሕአዴግ ውስጥ እየወጡ ወደ ውጭ አገር በመሄድ ለኢትዮጵያ ሕዝቦች እጅግ የሚያስደነግጡ መረጃዎችን የሚቀርቡበት አጋጣሚ እየተፈጠረ በመሆኑ፣ መንግሥት ዝምታን መምረጡን ትቶ በሕዝብ ውስጥ እየተነሱ ያሉትን ጥያቄዎች አደጋ ከመፍጠራቸው በፊት አፋጣኝ ምላሽ መስጠት አለበት፡፡ መታረም ያለበት ጉዳይም በአስቸኳይ መታረም አለበት፡፡ የድሮ የኢትዮጵያ ነገሥታት እንኳን መጽሐፍ እስኪጻፍ ሳይጠብቁ ሕዝቦች ስለእኔ ምን ይላሉ እያሉ ሰዎችን በተለያዩ ቦታዎች በመላክ መረጃ ያሰባስቡ ነበር፡፡

አሁን በሠለጠነው 21ኛው ክፍለ ዘመን ይህንን አለማድረግ በእጅጉ በጣም አደገኛ ነው፡፡ በዓለማችን ላይ በአሳዛኝ ሁኔታ ራሳቸውንም ሆነ አገራቸውን ለከፍተኛ አደጋ የዳረጉ መንግሥታት በሕዝብ ዘንድ ስላለ አሳሳቢ ጉዳይ በቂ ትኩረት ወይም ምንም ትኩረት አለመስጠታቸው ነው፡፡ ኢሕአዴግ ይህንን ወሳኝ ወቅት በአግባቡ ሊገነዘበው ይገባል፡፡ ቀደምት የኢሕአዴግ አባላት ወይም ውስጥ አዋቂዎች የሚያቀርቡትን መረጃ መንግሥት በዝምታ ማለፉ የሚያስነሳው አቧራ አደገኛ በመሆኑ፣ በሕዝቦች ዘንድ የተለያዩ አረዳዶችን ሊፈጥር የሚችል በመሆኑ አፋጣኝና ትርጉም ያለው ዕርምጃ ከኢሕአዴግ ይጠበቃል፡፡ ወይም ስህተቱን ያለ ምንም ማቅማማት ማረም ወይ ደግሞ አጥጋቢ መልስ መስጠት፡፡

 ከአዘጋጁ፡ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

   

Standard (Image)
Viewing all 213 articles
Browse latest View live