Quantcast
Channel: ደላላው
Viewing all 213 articles
Browse latest View live

የዓለም ባንክ የኢትዮጵያን ብር የማርከስ እሰጥ አገባና የአሥራ አንደኛው ሰዓት ንሰሐ

$
0
0

በጌታቸው አስፋው

የዓለም ባንክና የዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) የብሔራዊ ኢኮኖሚ አባት በሆነው ጆን ሜናርድ ኬንስ አነሳሽነትና ተሳትፎ በብሬተንውድስ ማሳቹሰትስ አሜሪካ እ.ኤ.አ. በ1944 ሲቋቋሙ ዋናው ዓላማቸው የአገሮችን ገንዘብ ለማገበያየት፣ የምንዛሪን ዋጋ ለማመጣጠን፣ ምንዛሪ ለቸገራቸው አገሮች በቀላል የወለድ መጣኝ ለማበደር፣ መጠባበቂያ ለመያዝ፣ የገንዘዘብ ዕዳ ለማወራረድና በማዕከላዊነት ለመምራት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ይህነንኑ አገልግሎታቸውን ከመስጠታቸውም በተጨማሪ ለአገሮች ብድር ለማግኘትና የውጭ ኢንቨስተሮች ወደ አገሮች ሄደው መዋዕለ ንዋይ ለማፍሰስ የእነርሱ ምስክርነት አስፈልጓል፡፡

ከእነዚህ ተቋማት ጋር ጥቅምና ጉዳትን መዝኖ ምንዛሪን በማርከስ አለመስማማት የሚቻል ቢሆንም፣ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ህልውናቸው በብድርና በውጭ ቀጥታ መዋዕለ ንዋይ ላይ ለተመሠረተ አገሮች ምስክርነታቸውን ላለማጣትም መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡

ኢኮኖሚስቶች ሀብትን አመጣጥኖ በማደላደል በግል ኢኮኖሚው የገበያ ውጤታማነት (Microeconomic Market Efficiency) አምነው የሚሟገቱና ለብሔራዊ ኢኮኖሚ ፖሊሲ (Microeconomic Policy) የቆሙ ተብለው ለሁለት ጎራ ሲከፈሉ፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ሁለቱን የግል ኢኮኖሚውን የገበያ ሕግጋትና የብሔራዊ ኢኮኖሚውን ፖሊሲ ማጣመር ይገባል የሚሉ የግል ኢኮኖሚው መሠረታውያን ለብሔራዊ ኢኮኖሚው (Microeconomic Foundations of the Microeconomic) የሚሉ ሦስተኛ ጎራ የየራሳቸውን አመለካከት የሚተነትኑበት ዘመን ላይ ነን፡፡

የእነዚህን የኢኮኖሚ አስተሳሰብና አመለካከት ጎራዎች አንድነትና ልዩነት የየአንዳንዳቸውን ጥቅምና ጉዳት ጠንቅቆ ማወቅ፣ የአገርን ኢኮኖሚ ለሚያስተዳድሩ መንግሥታት የኢኮኖሚ አማካሪ ባለሙያዎች ጉዳዩ የሕዝብ ጉሮሮ ስለሆነ ግዴታ እንጂ ውዴታ አይደለም፡፡

በተለይም በብሔራዊ ኢኮኖሚ ፖሊሲ እናምናለን የሚሉ የመንግሥት ኢኮኖሚ ፖሊሲ አማካሪዎችና የብሔራዊ እቅድ ባለሙያዎች፣ ፖሊሲያቸውና ዕቅዳቸው ሀብትን በማደላደልና በምርታማነት ከግል ኢኮኖሚ የገበያ ሕግጋት ውጤታማነት መሻሉን በተግባር ማስመስከር አለባቸው፡፡ የብሔራዊ ኢኮኖሚ ፖሊሲዎች የሚያጠነጥኑት በሁለት ዓይነት የፖሊሲ መሣሪያዎች በመንግሥት ገቢና ወጪ የበጀት ፖሊሲና በጥሬ ገንዘብ አቅርቦት ፖሊሲ ላይ ነው፡፡

ለጊዜው በዚህ ጽሑፍ የምዳስሰው የጥሬገንዘብ ፖሊሲውን ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም የዓለም ባንክ ኃላፊዎች ከገንዘብ ሚኒስትሩና ከብሔራዊ ባንክ ኃላፊዎች ጋር በውጭ ምንዛሪ መጣኝ የብርን ዋጋ በማርከስ ሐሳብ ላይ ተከራከሩ የሚል ዘገባ በሪፖርተር ጋዜጣ ኅዳር 27 ቀን 2009 ዓ.ም. ዕትም ስላነበብኩ፣ ይህ ክርክር እንደ መነሻ ስለሆነኝ ነው፡፡

የጥሬ ገንዘብ  ፖሊሲ

ባለፉት ሃያ ወራት ውስጥ በሪፖርተር ዕትሞች ባቀረብኩዋቸው አሥራ ሰባት ጽሑፎች በሁሉም ላይ ስለምርት ኢኮኖሚና ስለጥሬ ገንዘብ ኢኮኖሚ ተዛምዶ በቂ ትኩረት አለመስጠት፣ የማታ ማታ እንደሚጎዳን ጠንከር ያሉ አስተያየቶች ስሰጥ ቆይቼአለሁ፡፡

ሐሳቡ የእኔ ሳይሆን የታላላቅ ኢኮኖሚስቶች ምክር ነው፡፡ አስፋፊ የጥሬ ገንዘብ ፖሊሲ (Expansionary Monetary Policy) በሕግ ገደብ (By the rule of the law) ካልተገደበ፣ በልክ ካልተመጠነና በዘፈቀደ (By Discreation) ካደገ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርትን ቢያሳድግም፣ በረጅም ጊዜ ግን ውጤቱ ዋጋን ማናርና ጥሬ ገንዘቡን ዋጋ በማሳጣት የብራችንን  የምንዛሪ መጣኝ ማርከስ ነው፡፡

በተለይም መስከረም 1 ቀን 2009 ዓ.ም. በወጣው ሪፖርተር ዕትም የአደጋ ጠርዝ ላይ የጣሉን የኢኮኖሚ ጉዳዮች በሚል ርዕስ የውጭ ኢኮኖሚ ግንኙነት ክፍያ ሚዛን ሠንጠረዥን (Balance of Payment Table) በመተንተን ያለንበትን አስደንጋጭ ሁኔታ አሳይቼአለሁ፡፡ የውጭ ምንዛሪ እጥረቱ የጥሬገንዘብ መሠረት ሆነው ተፅዕኖ በሚያሳድሩት በባንክ ሁለት የሀብት ዓይነቶች የውጭ ምንዛሪ ሀብትና የአገር ውስጥ ብድር ሀብት ንፅፅር ላይም ከድጡ ወደ ማጡ አካሄድ እያሳየ መሆኑን በአጭሩ ጠቅሼአለሁ፡፡ ከዚህ ቀጥዬም በመረጃዎቹ አማካይነት በተጨባጭ አመለክታለሁ፡፡

የጥሬገንዘብ አካል የባንክ ሀብቶች ንፅፅር

የበጀት ዓመት

የውጭ ምንዛሪ ሀብት በቢሊዮን ብር

የአገር ውስጥ ብድር ሀብት በቢሊዮን ብር

የውጭ ምንዛሪ ሀብት ከአገር ውስጥ ብድር ሀብት ንፅፅር

2003

55.5

135.5

41%

2004

39.8

189.1

21%

2005

45.6

233.4

19.5%

2006

56.1

299.7

18.7%

2007

37.5

393.5

9.5%

 

 

ከ2003 እስከ 2007 ዓ.ም. የባንክ የውጭ ምንዛሪ ሀብት ከአገር ውስጥ ብድር ሀብት ጋር ሲነፃፀር፣ በ2003 ዓ.ም. ከነበረበት 41 በመቶ በየዓመቱ ቀንሶ በ2007 ዓ.ም. ዘጠኝ በመቶ ብቻ ሆኗል፡፡

የብሔራዊ ባንክ ዓመታዊ ሪፖርት ገና ባይወጣም ሦስት ቢሊዮን ዶላር ያልሞላው ኤክስፖርትና ሃያ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የሆነው የ2008 ዓ.ም. ኢምፖርት በሚያስከትለው የውጭ ንግድ ጉድለት የውጭ ምንዛሪ ሀብትን ስለሚቀንስ፣ በ2008 ዓ.ም. ንፅፅሩ ከድጡ ወደ ማጡ እንደሚሆን ምንም አያጠራጥርም፡፡ ይህ የውጭ ምንዛሪ ሀብትና የአገር ውስጥ ብድር ሀብት ንፅፅር ሁኔታ በብር የውጭ ምንዛሪ መጣኝ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ የአገሪቱ ቁልል የውጭ ዕዳ ክምችትም (Outstanding Debt Stock) ይጨምራል፡፡

የብር ሸቀጦችን የመግዛት አቅም ጠንካራ እንዲሆንና በውጭ ምንዛሪ መጣኝ እንዳይረክስ ማድረግ የብሔራዊ ባንክ ኃላፊነት ነው፡፡ ይህንን ለማድረግም ራሱ ለመንግስትና ለንግድ ባንኮች የሚሰጠውን ብድር ከመቆጣጠርም በላይ፣ በጥሬ ገንዘብ አቅርቦት ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱትን የንግድ ባንኮችን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ይገባዋል፡፡

ብዙ ሰዎች ስለ ጥሬ ገንዘብ ሲነገር በገበያ ውስጥ የሚዘዋወርን ጥሬ ብር ማለት ሊመስላቸው ይችላል ነገር ግን በንግድ ባንኮች ቆጣቢዎች የሚያስቀምጡት ተቀማጭ ወይም ንግድ ባንኮች በተቀማጩ ላይ ተመርኩዘው ተቀማጩን አርብተው በማበደር የሚፈጥሩት ብድርም ጥሬ ገንዘቦች ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ለጥሬ ገንዘብ አቅርቦት መጠን ከፍተኛውን አስተዋጽኦ ያደረገው በብሔራዊ ባንክ የቀረበው በገበያ ውስጥ የሚዘዋወረው ጥሬ ብር ይሁን፣ ወይም የንግድ ባንኮች ተቀማጭ በሚከተለው ሠንጠረዥ ተመልክቶ መረዳት ይቻላል፡፡

                  የጥሬ ገንዘብ ዓይነቶች በቢሊዮን ብር

የበጀት ዓመት

በብሔራዊ ባንክ አቅራቢነት በገበያ ውስጥ የሚዘዋወር ጥሬ ብር

የንግድ ባንኮች ቀቀማጭ (ተንቀሳቃሽ፣ የቁጠባና የጊዜ ተቀማጮች)

ጠቅላላ ለገበያ የቀረበ ጥሬ ገንዘብ

የጥሬ ብርና የተቀማጭ ንፅፅር

2003

32.6

112.8

145.4

29%

2004

38.5

151.0

189.5

26%

2005

45.7

189.6

235.3

24%

2006

53.2

244.5

297.7

22%

2007

60.5

310.7

371.2

20%

 

 

አምናና ከዚያ በፊት በጥቃቅን የተደራጁ ወጣቶች ነበሩ በተቋቋምኩ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ከሺሕ ተነስቼ ሚሊዮኖች ውስጥ ገባሁ ይሉ የነበሩት፡፡ ከአምና ጀምሮ ግን ንግድ ባንኮች ሆነዋል በተቋቋምኩ በጥቂት ዓመታት ሚልዮኖችንና ቢልዮኖችን አተረፍኩ የሚሉት፡፡ ለቆጣቢው ከዋጋ ንረት በታች በሆነ የኪሳራ ወለድ መጣኝ (Negative Real Interest Rate) እየከፈሉ እነርሱ የቆጣቢውን ሦስት እጥፍ ወለድ የሞኖፖል ትርፍ ዝቀው ከቢሊዮን አልፈው ትሪሊየን ውስጥስ ቢገቡ፣ ማን ተቆጣጣሪ አላቸውና ነው በጥሬ ገንዘቡ እየከሰረ የተነገደበት ቆጣቢው ለእግዜር ሰጥቶ ዝም ብሏል፡፡

ጆንያ ለመቁጠር ሎንዶን ሄዶ መማር

ብዙ የቅርብ ጊዜ ኢኮኖሚስቶች ከአሜሪካ በተለይም ከቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ቢበቅሉም፣ የእንግሊዝ ሎንዶን አዳም ስሚዝ፣ ዴቪድ ሪካርዶና ሌሎች ጥንታውያን ኢኮኖሚስቶችና የብሔራዊ ኢኮኖሚ አባት የሆነው ኬንስ የበቀሉባት ዘመናዊ ኢኮኖሚክስ የተወለደባት አገር ናት፡፡ ብዙ የእኛ ምሁራንም ሄደው ተምረውባታል፡፡ ከንጉሡ ዘመን ጀምሮ እንደ እኛው ዋሸራ የቤተ ክህነት ትምህርት ቤት ከየትኛውም አገር በላይ በርካታ ምሁራን ያቀኑትም ወደ ሎንዶን ነበር፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህም በአውሮፓ፣ በአሜሪካ፣ በእስያ፣ በአፍሪካ ሄደው ብዙ ሰዎች ተምረዋል፡፡ አንዳንዶቹ አገር ቤት ተመልሰውም የፖሊሲ አማካሪ ሆነው ይሠራሉ፡፡ እነዚህ በአገር ውስጥና ኢኮኖሚክስ በተፈጠረባቸው አገሮች በሕዝብ ገንዘብ ተልከው የተማሩ የኢኮኖሚ አማካሪዎች፣ ስለብሔራዊ ኢኮኖሚያችን ስኬት ምን ይላሉ? የፖሊሲ ለውጥ የሰዎችን የወደፊት ግምት ቀይሮ የምርት፣ የሠራተኛ፣ የካፒታል፣ የሁሉንም ገበያዎች ማጣሪያ አጠቃላይ እኩልነት የኢኮኖሚ ልኬት ሞዴልን ውጤታማነት (Markets Clearing General Equilibrium Econometric Model Effectivenes) ያከሽፋል የሚሉ የብሔራዊ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ተቃዋሚና የግል ነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ተሟጋች ታላላቅ ኢኮኖሚስቶች ሲናገሩ አንዳንድ ሰዎችን ሁሌም ማታለል ይቻላል፣ ሁሉንም ሰዎችም አንዳንድ ጊዜ ማታለል ይቻላል፣ ሁሉንም ሰዎች ሁሌም ማታለል ግን አይቻልም የሚል የአብረሃም ሊንከንን ንግግር ጠቅሰው፣ በሒሳብ ሥሌት ላይ በተመሠረተ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ላይ ያላቸውን ጥርጣሬ ይገልጻሉ፡፡

ዛሬ በኢትዮጵያ ውስጥ የምርት ገበያውም፣ የሠራተኛ ገበያውም፣ የካፒታል ገበያውም የመሬት ገበያውም ተዛብተዋል፡፡ መዛባታቸውንም የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉ አውቋል፡፡ የምርት ገበያው ዋጋ ሰው አስመርሯል፡፡ ወጣቱ ትውልድ ሥራ አጥቷል፡፡ የጥሬ ገንዘብ አቅርቦት የምንዛሪ መጣኙን አዛብቶታል፡፡ በዓለም ታላላቅ ከተሞች እንኳ ባልታየ ዓይነት በአዲስ አበባ የአንድ ካሬ ሜትር መሬት ዋጋ ሦስት መቶ ሃምሳ አምስት ሺሒ ብር ደርሷል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ በአንድ ድምፅ ሁላችንንም ሁሌም ማታለል አይቻልም ብሏል፡፡ 

 በጊነስ ቡክ ሊመዘገብና ሊቃውንትን ለምርምር ሊጋብዝ የሚችለው በጆንያ ተለክቶ በጥሬ ገንዘብ ስታቲስቲክስ መረጃ መልክ ተተምኖ የቀረበው በ1983 ዓ.ም. አሥር ቢሊዮን ብር ገደማ የነበረው ጥቅል የአገር ውስጥ ምርት፣ በ2008 ዓ.ም. አንድ መቶ ሃምሳ እጥፍ አድጎ አንድ ተኩል ትሪሊየን መድረሱ ከገበያው ፍላጎትና አቅርቦት መጣጣም መረጃ ጋር ሆድና ጀርባ ሆኖ የሕዝብ ዓመኔታን አጥቷል

የወጣቱ ሥራ አጥነት ለአገር ህልውና የሚያሠጋ ሁከት ከመቀስቀሱም በላይ፣ የከፍተኛ ባለሥልጣናትና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት መነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ ገና መቋጫ ብልኃትም  አልተገኘለትም፡፡ በውጭ ምንዛሪና በካፒታል እጥረት ምክንያት ብዙ የመንግሥትና የግል ፕሮጀክቶች ተጓትተዋል፡፡ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስም አስቸጋሪ  ሆኗል፡፡ የከተማና የገጠር መሬት ሽሚያው ሕዝብን ከሕዝብ ከማጋጨቱም በላይ ለፀጥታ አስከባሪዎችም ፈታኝ ጊዜ ሆኖ ከርሟል፡፡

እህል በጆንያ እየለኩ የደቡብ ምሥራቅ እስያ አገሮችም ነፍሶባቸዋል፡፡ ብሪክስ የተባሉትና በቅርቡ በፍጥነት ስለማደጋቸው የተመሰከረላቸው በብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይናና ደቡብ አፍሪካም አርጅተዋል፡፡ አሁን ዓለም እያወራ ያለው ስለእኛ ዕድገት ነው ብለው እስከ አሥራ አንደኛው ሰዓት ያወሩ የነበሩ የኢኮኖሚያችን ባለሙያዎች በአሥራ አንደኛው ሰዓት ላይ የዋጋ ንረቱን አምነው እንቀንሰዋለን አሉ፡፡ ሁከት የቀሰቀሰው የወጣቱ ሥራ አጥነት ነው አሉ ለዓለም ባንክ ባለሙያዎቹ ምላሽ ሲሰጡ፡፡ ከጆንያ ምርት ውጪ ምንም ለዓለም ገበያ የሚቀርብ ሸቀጥ ስለሌለን የብር ምንዛሪ አናረክስም አሉ፡፡   

የጆንያ ምርት ቆጠራ በደጉም ጊዜ በክፉም ጊዜ አይቀርም፡፡ የዓለም መገናኛ ብዙኃን በዕለት ተዕለት የቢዝነስ ዘገባቸው ኢኮኖሚያቸውን በገንዘብ ገበያ መጣኞች፣ በቦንድና በአክሲዮን ዋጋዎች መውጣትና መውረድና የወለድ መጣኞች መውደቅና መነሳት አመልካች (Index) ይለካሉ፡፡ የእኛ መገናኛ ብዙኃንም በመሳለሚያ ገበያ የኩንታል ጤፍ ዋጋ፣ በአትክልት ተራ የኩንታል ድንች ዋጋ የቢዝነስ ዘገባ ያቀርቡልናል፡፡ 

በዚህ የሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን በሌሎች አገሮች የገንዘብ ገበያ መጣኞች የምርት ኢኮኖሚ መለኪያዎቸ ነፀብራቆች ናቸው፡፡ በብሔራዊ ኢኮኖሚ ጥቅል መረጃ ደረጃ በጆንያና በካርቶን መለካት ቀርቷል፡፡ እኛ ኢኮኖሚያችን ማደጉን ለመናገርም ሆነ የቢዝነስ ዘገባ ለማቅረብ፣ በዓለም ገበያ ለመወዳደር አለመቻላችንን ለመግለጽም መለኪያችን ጆንያ ነው፡፡ ራሳችንን በጆንያ ቆጠራ ልክ ገድበን ካሳነስነው ሁሌም ጆንያ ቆጣሪ ነው የምንሆነው፡፡

የአሥራ አንደኛው ሰዓት ንሰሐ

በጆንያ ከሚለካ የግብርና ምርት በስተቀር ምንም ሌላ የኤክስፖርት ምርት የሌለን ሰዎች፣ ከውጭ የሚገባውን ሸቀጥም በአገር ውስጥ ምርት መተካት የማንችል ሰዎች፣ የብርን ዋጋ አርክሰን ምን እንጠቀማለን ማለታቸውን እኔም የምጋራው ነው፡፡ ቢሆንም በሌላ የጥሬ ገንዘብ ፖሊሲ የብራችን ምንዛሪ መጣኝ እንዲስተካከል ማድረግ የሚጠበቅ የቤት ሥራ ነው፡፡ ቀድሞውንም ለዚህ ያበቃን የብሔራዊ ባንክ የጥሬ ገንዘብ ፖሊሲ መሆኑም አይዘነጋም፡፡

ጥሬ ገንዘብ የተፈጠረው የምርት ኢኮኖሚውን ለማገበያየትና ለመለካት እስከሆነ ድረስ የምርት ዋጋ አመልካች ከመሆን አልፎ የራሱ ዋጋ የለውም፡፡ የጥሬ ገንዘብ ዋጋ የሚተመነው ሊገዛ በሚችለው ምርት መጠን ነው፡፡ ስለዚህም ምርቱ ሳይኖር ጥሬ ገንዘቡን ማብዛት የምርቱን ዋጋ መጣል ነው፡፡ ለዚህም ነው በብሔራዊ ኢኮኖሚ ደረጃ የውጭ ሸቀጥ ለመግዛት ከሚያስችለው የውጭ ምንዛሪ በቀር የአገር ውስጥ ጥሬ ገንዘብ ለአገር ሀብትን ይለካል እንጂ ሀብት አይደለም የሚባለው፡፡

የአገር ውስጥ ምንዛሪ (Currency) ከሌላ አገር ምንዛሪ ጋር በመገበያያ ዋጋ የሚለካው በእርግጠኛ መመነዛዘሪያ መጣኝ (Effective Real Exchange Rate) የአንድ አገር ምንዛሪ ሸቀጦችን በመግዛት አቅሙ ከሌላ ተገበያይ አገር ምንዛሪ ሸቀጦችን በመግዛት አቅም ጋር ሲወዳደር፣ ወይም ከጊዜ ወደ ጊዜ በተመናዛሪዎቹ አገሮች ውስጥ ያለውን የዋጋ ንረት ልዩነት ከግምት ባስገባ የመመነዛዘሪያ መጣኝ ነው፡፡

ስለዚህም ለዛሬው የምንዛሪያችሁን ዋጋ ቀንሱ ምክንያት የሆነው ባለፉት ዓመታት ብራችን በአገር ውስጥ ሸቀጥን የመግዛት አቅሙ በመዳከሙ ነው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ የጥሬ ገንዘብ አቅርቦት ከልኩ በማለፉ ነው፡፡

ያለፉት ዓመታት የጥሬ ገንዘብ አቅርቦት ዕድገት

 

የበጀት ዓመት

 

መጠን

 

የመጠን ልዩነት

 

ዕድገት

የአምስት ዓመት ዕድገት አማካይ

2002

104

 

 

 

 

 

 

 

29%

2003

145

41

39%

2004

189

44

30%

2005

235

46

24%

2006

298

63

27%

2007

371

73

25%

 

 

የጥሬ ገንዘብ አቅርቦቱ ዕድገት መጣኝ እየቀነሰ ቢመጣም በአካፋዩ መነሻ መተለቅ ምክንያት እንጂ፣ የአቅርቦቱ መጠን እየጨመረ እንደመጣ እናያለን፡፡ የእርግጠኛ ጥቅል የአገር ውስጥ ምርት ዕድገትን በየዓመቱ 11 በመቶ ይሁን ብለን ተቀብለን እንኳ፣ ከአምስቱ ዓመት አማካይ የጥሬ ገንዘብ አቅርቦት ዕድገት 29 በመቶ ውስጥ 11 በመቶው ለምርት ዕድገት ዋለ ብንል ቀሪው 18 በመቶ የዋለው ለዋጋ ንረት ነው፡፡

ከጥሬ ገንዘብ ትንታኔ ፈቀቅ ብለን በአጠቃላይ ስለምርት ኢኮኖሚና ስለገንዘብ ኢኮኖሚ ብናስብ፣ እኛና ሌሎች አገሮች ያሉበትን ሁኔታ ስናነፃፅር እኛ በአሞሌ ጨው ዘመን እንደምንገኝ እንገነዘባለን፡፡ ሃያን አሥራ አሥር፣ ሰላሳን ሃያ አስር፣ አርባን ሰላሳ አሥር፣ ወዘተ ብለው ይቆጥሩ የነበሩት አያት ቅድመ አያቶቻችን ከእነርሱ ያለፈ የገንዘብ ቋንቋ እንደሌለን ቢያውቁ፣ እዚያው ባስቀመጥናቸው ቦታ እንደተቀመጡ ናቸው ይሉን ነበር፡፡

በዚህ የ21ኛው ክፍለ ዘመን ምርትን በጆንያ እየቆጠሩና በአሞሌ ጨው ጥሬ ገንዘብ እየለኩ ኢኮኖሚን መምራት አልቻል ብሎ፣ በአሥራ አንደኛው ሰዓት ላይ በቀውሱ አናዛዥ የንሰሐ አባትነት ምሎ ተገዝቶ እውነቱን መናገሪያ ጊዜ ላይ አድርሶናል፡፡ የንሰሐ ጊዜ ሆኖ ብዙ አናዞናል፡፡

ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከሚናገሩት ንግግር ውስጥ አንድ አስገራሚ አባባል አለ፡፡ አሜሪካ ሌሎችን ከምትመክርበት የዓለም አንድ የገበያ መንደርነት የግሎባላይዜሽን ሥርዓት ቢያፈነግጥም፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲያቸው ‹‹የአሜሪካንን ምርት ግዙ፣ አሜሪካውያንን ቅጠሩ፣ አሜሪካውያንን መቅጠር ራስን መቅጠር ነው›› የሚል እንደሚሆን ደጋግመው ተናግረዋል፡፡ እንደሳቸው የአገርን ምርት መግዛት ማለት የአገርን ሰው መቅጠር ነው፡፡

በዓለም ገበያ ተወዳድራ የማሸነፍ ዕድል ላላት ታላቅ አገር የአገራችሁን ግዙ፣ የአገራችሁን ሰው ቅጠሩ፣ የአገርን ሰው መቅጠር ራስን መቅጠር ነው ሲሉ፣ በዓለም ገበያ ለመወዳደር ዕድሉ የሌላት ለማደግ የምትፈልግ አገር ምን ዓይነት የውጭ ኢኮኖሚ ግንኙነትና የውጭ ንግድ ፖሊሲ ሊኖራት ይገባል?

የእኛ አስፋፊ የጥሬ ገንዘብ ፖሊሲ ለእኛ የሆነው “የቻይናን ግዙ፣ ቻይናውያንን ቅጠሩ” ነው፡፡ ወርቅ ሽጦ ጥብቆ ከውጭ መግዛት፣ እህል ሽጦ የቤት ቁሳቁስ ከውጭ  መግዛት፣ የቁም እንስሳትን ሽጦ መጫወቻ አሻንጉሊት ከውጭ መግዛት ለራስ ሳይሆን ለሌላ አገር ዜጋ የሥራ ዕድል መፍጠር ነው፡፡ ሥራውንና የሠራተኛ ገበያውን ወደ ውጭ አውጥቶ ሽጦ፣ ወጣቶችን ሥራ ፍጠሩ እያሉ መጨቅጨቅስ ምን ፋይዳ አለው?

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው  getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡     

Standard (Image)

በኤርትራ ላይ የተጣለው የጦር መሣሪያ ማዕቀብ መራዘምና ለቀጣናው የሚኖረው የሰላም አንድምታ

$
0
0

በዮሐንስ ገበየሁ

እ.ኤ.አ. ሜይ 2009 የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) በኤርትራ የጣለውን የጦር መሣሪያ ማዕቀብ ተከትሎ፣ በተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በዚያው ዓመት ዲሴምበር 23 ቀን በውሳኔ ቁጥር 1907 አማካይነት የጦር መሣሪያ ማዕቀብ በኤርትራ ላይ ጣለ። ማዕቀቡ ወደ ኤርትራ የሚገቡና ከኤርትራ የሚወጡ የጦር መሣሪያዎችንና ከጦር መሣሪያ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ቁሳቁሶችን የሚያግድ ውሳኔ ነው። ውሳኔው በተመድ የሶማሊያ ጉዳይ ተቆጣጣሪ ቡድን ሪፖርት ግኝት መሠረት የኤርትር መንግሥት አልሸባብ ለተባለውና ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት እንዳለው ለሚነገርለት አክራሪ እስላማዊ ቡድን የፖለቲካ፣ የፋይናንስና የሎጂስቲክ ድጋፍ እያቀረበች መሆኑ በመረጋገጡ የተላለፈ ነው።

ከዚህ በተጨማሪ ኤርትራ ከጂቡቲ ጋር በነበራት የድንበር ግጭት አለመግባባት ምክንያት ድንበር አካባቢ ያሉ የጦር ሠራዊቷን ከድንበሩ አስወጥታ ለድርድር ዝግጁ አለመሆኗን ተከትሎ የተጣለም እንደሆነ ውሳኔው ያመላክታል። ማዕቀቡ እ.ኤ.አ. በ2009 ከተጣለ በኋላ እየታደሰ እስከ 2016 የቆየ ሲሆን፣ በ2016ም በተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ውሳኔ ቁጥር 2317(2016) አማካይነት ታድሷል።

የጦር መሣሪያ ማዕቀቡ አንድም ከኤርትራና ወደ ኤርትር የሚገባውንና የሚወጣውን የጦር መሣሪያና ከጦር መሣሪያ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ቁሳቁሶችን ለመግታት፣ እንዲሁም የኤርትራ መንግሥት የባህሪ ለውጥ እንዲያመጣ ለማድረግና የአካባቢውን ሰላምና መረጋጋት ለመመለስ ታልሞ የተደረገ ነው። ስለሆነም ማዕቀቡን ለመከለስ፣ ለማሻሻል ወይም ለማንሳት የታለመለትን ግብ በተለይም በኤርትራ ያለውን የባህሪ ለውጥ ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆን አለበት። በዚህ መሠረት የኤርትራ መንግሥት የባህሪ ለውጥ ባለማምጣቱ፣ የሶማሊያና የኤርትራ ተቆጣጣሪ ቡድን (ከዚህ በኋላ በጽሑፉ ውስጥ ተቆጣጣሪ ተብሎ ይጠቀሳል) ወደ ኤርትራ ገብቶ የኤርትራ መንግሥት አልሸባብንና ሌሎች ታጣቂ ቡድኖችን እየረዳ መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ እንዲችል አለመፍቀዱ የባህሪውን ግትርነት ማሳያ ነው፡፡ ተቆጣጣሪ ቡድኑ እንዲገባ ያልፈቀደው አሁንም ድረስ ለአሻባሪዎች ድጋፍ እያደረገ፣ ማዕቀቡን እየጣሰ፣ በኤርትራዊያን ላይ ብሔራዊ ባርነት ሊባል በሚችል ሁኔታ ጭቆናና ኢሰብዓዊ ዕርምጃ እየወሰደ በመሆኑ፣ የጂቡቲ የጦር ምርኮኞችን በምን ዓይነት ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ ለማረጋገጥ የሚያስችል መረጃን አልሰጥም በማለት ጠብ አጫሪነቱን እየቀጠለ በመሆኑ፣ ቀጣናውን የብጥብጥና የሽብር ማዕከል ለማድረግ  የአካባቢውን ታጣቂ ቡድኖች አሁንም ድረስ እየረዳ መሆኑ በመረጋገጡ ማዕቀቡ ተራዝሟል። 

ተቆጣጣሪ ቡድኑ በኤርትራ የተጣለው ማዕቀብ በትክክል መተግበሩ አለመተግበሩን ወደ አገሪቱ ከሚገባውና ከሚወጣው የጦር መሣሪያ፣ የኤርትራ መንግሥት አካባቢውን የማተራመስ አጀንዳውን መተው አለመተውን በማረጋገጥ፣ በኤርትራ ያሉ የማዕድንና ሌሎች የሀብት ምንጮች የሚሰበሰበው ገንዘብ ታጣቂ ቡድኖችን ለመደገፍ መዋሉን በማረጋገጥ፣ የሰብዓዊ መብት ረገጣ መቆሙንና መሻሻል አለማሳየቱን ከእነዚህ ጉዳዮች አንፃር ገምግሞ እንዲያቀርብ ነው የተዋቀረው። የቡድኑ አባላት አወቃቀርን ስንመለከት የጦር መሣሪያ ባለሙያ (Arms expert) ከኤርትራና ወደ ኤርትራ ያለውን የጦር መሣሪያ ፍሰትና ሁኔታ ለማወቅ፣ የቀጣናውና የታጣቂ ቡድኖች ባለሙያ (Regional Expert and Armed Groups Expert) ኤርትራ በቀጣናው የምታደርገውን የማተራመስ አጀንዳ ለመገምገም፣ የፋይናንስና የተፈጥሮ ሀብት ባለሙያ (Finance Expert and Natural Resources Expert) በቀጣናው የሚንቀሳቀሱ ታጠቂዎችን ለመደገፍና የጦር መሣሪያ ለመግዛት ያለውን የፋይናንስ ምንጭ ለመተንተንና ያሉ የተፈጥሮ ሀብቶች ማዕቀቡን ለመጣስ መጠቀም አለመጠቀሟን፣ የሰብዓዊነት ባለሙያ (humanitarian expert) የሰብዓዊ መብቶችን ሁኔታ ሪፖርት ለማጠናከር በሚያስችል ሁኔታ የተዋቀረ ነው።  

የማዕቀቡ መራዘም ለቀጣናው ያለው አንድምታ ምንድነው?

ማንኛውም ማዕቀብና በተለይም የጦር መሣሪያ ማዕቀብ ውጤታማነት የሚለካው፣ ማዕቀቡ የተጣለበት አገር የባህሪ ለውጥ ማምጣት ሲችልና የተጣለው ማዕቀብ እውነትም ወደ አገሪቱ የጦር መሣሪያ መግባትን መከልከል ሲቻል ነው። ማዕቀቡ የኤርትራ መንግሥት ለዓለም ዓቀፍ ሰላም ፀር መሆኑን የሚያሳይ፣ ወደ ኤርትራ ወይም ከኤርትራ መንግሥት ወደ ሌሎች አካባቢዎች ያለን የጦር መሣሪያ ሽያጭ፣ ወታደራዊ ሥልጠና፣ የሎጂስቲክ ድጋፍ፣ ወዘተ. የሚገታና አገሪቱ በተለይም በሥልጣን ላይ ያለው አስተዳደር ከዓለም ማኅበረሰብ መገለል እንዲደርስበት የሚያደርግ ከፍተኛ የሆነ ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ፣ ሥነ ልቦናዊና ኢኮኖሚያው ቀውስን በኢስያስ መንግሥት እንዲፈጥር የታለመና የፈጠረ መሆኑ በግልጽ ይታያል።

በኤርትራ ላይ የተጣለው ማዕቀብ የኤርትራ መንግሥት የባህሪ ለውጥ ባለማምጣቱ ምክንያት ተራዘመ መሆኑ ግልጽ ቢሆንም፣ የኤርትራ መንግሥት በማዕቀቡ ምክንያት የደረሰበትን ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲያዊና ወታደራዊ ቀውስ ግን ማየት ይቻላል። ኤርትራ ባልሞት ባይ ተጋዳይነት በራሷ ሕዝብ ላይ የምታደርሰው በደል፣ ኢትዮጵያንና ጂቡቲን ለማተራመስ የምታደርገው ጥረት፣ የዓለም ማኅበረሰብን ከልክ ባለፈ ጥርጣሬ እየተመለከተች መምጣቷ የዚሁ ሥነ ልቦናዊ፣ ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ማሳያ ነው።

ይሁን እንጂ የማዕቀቡን ጥንካሬ ሊያዳክሙ የሚችሉ አንዳንድ ክስተቶችን ሁሉም አገሮች በንቃት መከታተል እንደሚገባቸው ማዕቀቡን የጣለው የፀጥታው ምክር ቤት በውሳኔው አመላክቷል። በዚህ ረገድ ከኤርትራ ወደ ጣሊያን በከፍተኛ የአገሪቱ የመከላከያ ሠራዊት ኃላፊዎች የተደረጉ ጉብኝቶች፣ በተለያዩ ሚዲያዎችና ለተመድ ተቆጣጣሪ ቡድን የደረሱት መረጃዎች ኤርትራ በእጅ አዙር ከዩክሬን የጦር መሣሪያ እየገዛች ስለመሆኑ የተገኙ መረጃዎች፣ ሳዑዲ ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ የየመን አማፂያንን ለመውጋት በሚል ሰበብ በኤርትራ የመሠረቱት የጦር ሠፈር፣ ኳታር ጂቡቲና ኤርትራን ለማስታረቅ በሚል ሰበብ የምታደርገው መውጣትና መግባት ማዕቀቡ በኤርትራ ላይ ያለው ተፅዕኖ እንዲቀጥል አድርጓል፡፡ ይህ ጤና የኤርትራን መንግሥት ባህሪን ከማሻሻል ይልቅ በእብሪት ልቡ እስኪፈነዳ ድረስ እንዲያብጥ የሚያደርግ ብቻ ሳይሆን፣ የጉዳዩን አሳሳቢነት የሚያመላክት መሆኑ በጥንቃቄ መታየት እንዳለበት ብዙዎች የሚስማሙበት ነው።

ማዕቀቡ በኤርትራ ለውጥ አለመኖሩን በደንብ ያሳየ ነው። በውሳኔው ወቅት አስተያየታቸውን የሰጡት የታላቋ ብሪታኒያና የአሜሪካ አምባሳደሮች ይህንኑ በደንብ አስቀምጠውታል፡፡ የእንግሊዝ አምባሳደር ማቲው ራይክሮፍት ስለኤርትራ ሲናገሩ፣ “We don’t welcome the progress because nothing has changed,” ብለዋል፡፡ የአሜሪካ አምባሳደር ኢዞቤል ኮልማን በበኩላቸው የተናገሩት የእንግሊዝ አምባሳደር ያሉትን ያጠናከረ ነበረ። ከላይ የተጠቀሱት የሁለቱ ኃያላን መንግሥታት እንዳስቀመጡት እውነተኛ ለውጥ በኤርትራ መጣ የሚባለው የኤርትራ መንግሥት ሽብርተኞችንና ታጣቂ ቡድኖችን ማገዝ ሲያቆም፣ በዚህም ለዓለም አቀፍ ሰላምና መረጋጋት አደጋ መሆኑ ሲያበቃ ነው።   

በዚህ ረገድ ያለው ዋና ጉዳይ በኤርትራ ያለው አስተዳደር ባህሪ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይቀየራል ወይ የሚለውና የእውነተኛ ለውጥ ጥያቄ ከአስተዳደሩ መሪዎች ጋር በጥብቅ የተሳሰረ መሆኑ ነው። ኤርትራ የመሪዋ የኢሳያስ አፈወርቂና በዙሪያቸው ያሉ ባለሥልጣናት ርስት በመሆኗና አገሪቱን የሚያስተዳድራት ቡድን በከፍተኛ የተማከለ የውሳኔ ዘዴ የታሰረ ከመሆኑ አንፃር፣ አመራሮች ካልተለወጡ አስተዳደሩ ይለወጣል ማለት ዘበት ነው። የውጭ ጉዳይ ፖሊሲው የኢሳያስ ፍላጎትና ምኞት የሚገለጽበት ሲሆን፣ የኢሳያስ ምኞት ደግሞ ከኢትዮጵያ ጋር በነበረው ‹‹የነፃነት ጦርነት›› ቂም በቀል የተቀረፀና የአፍሪካ ቀንድን የማተራመስ ፍላጎትን እየገታች ያለችውን ኢትዮጵያን ማተራመስ ቅድሚያ ሰጥቶ የሚንቀሳቀሰ የሥነ ልቦና ቀውስ ያለበት ነው።

የውጭ ጉዳይ ፖሊሲው ነገሮችን ሁሉ በመሣሪያና በጦርነት እልባት ለመስጠት የሚፈልግ ነው። የፖሊሲው ዕይታም አመራሮች ለተቀረው ዓለም ባላቸው ቂም በቀል፣ የአፍሪካ ቀንድ ባለው አለመረጋጋትና በኤርትራ ውስጥ ጠንካራ መንግሥት ለመመሥረት ባሉት ተግዳሮቶች ፍራቻ የተከበበ ነው። በመከበብ ስሜት ውስጥ ያለ ፖሊሲ ደግሞ የከበበውን ዓለም ሁሉ በጠላትነት የሚፈርጅ ብቻ ሳይሆን፣ በአዕምሮው ውስጥ የፈጠረውን የመከበብ ስሜት ለማርገብ መሣሪያን የሚያነሳ፣ ጦርነትን የሚያውጅ፣ ጠብ አጫሪነትን ቋንቋውና መግባቢያው የሚያደርግ ይሆናል ማለት ነው። የኤርትራ መንግሥት ፖሊሲ መግለጫም እነዚህ ናቸው።

ኤርትራ የአፍሪካ ቀንድን ለማተራመስ ለሚሹ ታጣቂ ቡድኖች የምታደርገው ድጋፍ፣ የጂቡቲን የጦር ምርኮኞች ሁኔታ መረጃ አልሰጥም ማለቷ፣ ከማዕድን የምታገኘውን ገንዘብ ለጦር መሣሪያ ግዥ በማዋል ማዕቀቡን ለመተላለፍ የምታደርገው ጥረት፣ የተመድ ተቆጣጣሪ ቡድን በኤርትራ ገብቶ ኃላፊነቱን እንዲወጣ አለመፈለጓ፣ የኤርትራ መንግሥት ባህሪውን ለመለወጥ አለመፈለጉን በደንብ ሊያሳዩ ከሚችሉ ጉዳዮች በጥቂቱ የሚጠቀሱ ናቸው። የኤርትራ መንግሥት አልሸባብን ከኳታር በሚለቀቅ ገንዘብ፣ የኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ)፣ የትግራይ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ትሕዴን)፣ የአርበኞች ግንቦት 7፣ የሕዝቦች ትብብር ለነፃነትና ለዴሞክራሲ ለሚባሉ ኢትዮጵያን ለማተራመስ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ቡድኖችንና በጂቡቲ የሚንቀሳቀሰውን ‹‹Pour la Restauration de L’unité et de la Démocratie›› (አንድነትና ዴሞክራሲ አስመላሽ ግንባር) በመደገፍ ቀጣናውን ለማተራመስ የሚያደርገውን እንቅስቃሴና አጀንዳ እየቀጠለ መሆኑን ሪፖርቶች በግልጽ ያሳያሉ።

ከላይ የተጠቀሱትን ታጣቂ ቡድኖችን በፋይናንስ፣ በፖለቲካና በሎጂስቲክስ በመደገፍ ኢትዮጵያን ለማፈራረስ እየሠራ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ። በቅርቡ እንኳ 113 የሚሆኑ የግንቦት 7 አባላት በምዕራብ ትግራይ በኩል ሲገቡ መያዘቸውና 15 የሚሆኑት መገደላቸው፣ 73 የሚሆኑት መማረካቸው የኤርትራ መንግሥት ቀጣናውን የማተራመስ አጀንዳውን አለመተውን ብቻ ሳይሆን፣ ይልቁንም በብርቱ እንደገፋበት የሚሳይ ይፋ ማስረጃ ነው። የኤርትራ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ማዕከል ቀጣናውን ማተራመስ እንደሆነ ማሳያ ነው።

በዘርፉ ጥናት ያደረጉ አካላት ኤርትራ ከተባበሩት ዓረብ ኢምሬትስ፣ ሳዑዲ ዓረቢያ፣ ኳታርና መሰል አገሮች ጋር ያላትን ግንኙነት በጥርጣሬ ነው የሚመለከቱት። ኤርትራ ውስጥ የጦር ሠፈር የገነቡት አገሮችና ከኤርትራ ጋር ጥብቅ ግንኙነት ያላቸው አገሮች በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ኢትዮጵያን ‹‹የክርስቲያን ደሴት›› እንደሆነች የሚፈርጁ፣ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ቀንድን ለማስለምና ቀይ ባህርን የዓረብ እንዲሆን ለማድረግ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ የምትገታ ደንቃራ አገር አድርገው የሚያምኑ መሆናቸው፣ ጉዳዩን ‹‹በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ›› የሚያደርግ ነው።

በኤርትራ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ ተሳትፎ ያላቸውና በኤርትራ የጦር ሠፈር የመሠረቱ አገሮች ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ያለውን አልሸባብንና አይኤስ የተባሉ የሽብር ቡድኖችን መደገፍ ብቻ ሳይሆን፣ ቡድኖቹ በአምሳላቸው የተቀረፁ መሆኑ የታወቀ ሀቅ ነው። እነዚህ አካላት ኳታር የምታደርገውን እስላማዊ አክራሪነትን የማስፋፋት ዓላማ የሚያራምዱና የሙስሊም ወንድማማቾችን ርዕዮተ ዓለም የሚወክሉ መሆናቸውን በዘርፉ ጥናት ያደረጉ ምሁራን ይገልጻሉ። በዚህ ረገድ ጥናትና ትንታኔ ያደረጉት ሩሲያዊው የፖለቲካ ተንታኝና ታዋቂው ጋዜጠኛ አንድሪው ኮሪብኮ፣ የባህረ ሰላጤው አገሮች በኤርትራ ያላቸው የጦር ሠፈር በየመን አማፅያንን ለመዋጋት ካላቸው ፍላጎት እኩል የኢትዮጵያን ተፅዕኖ ለመቀነስ፣ ብሎም አገሪቱን ለማዳከም ነው ማለት ማጋነን እንዳልሆነ አስተያየታቸውን ይሰጣሉ።

እንደ አንድሪው ኮሪብኮ በኤርትራ ያለው የጦር ሠፈር ኢትዮጵያን ለማዳከምና በየመን አማፅያንን ለመዋጋት ያለመና በሁለቱም ወገን የተሳለ ጎራዴ ነው ይላሉ። ስለኳታር ሲተነትኑ የኳታር በኤርትራ መኖር በኢትዮጵያ ላይ የተቀነባበረና ሆን ተብሎ የታለመ (Orchestrated, Managed and Ideologically Induced Chaos) አመፅ በመቀስቀስ፣ የአፍሪካ ቀንድ የመጨረሻ የሰላም ዕድልን (Bastion of Peace, Security and Stability) የሆነችውን ኢትዮጵያ ለማተራመስ ያቀደ ነው ይላሉ።    

ይህን ሁኔታ የኢትዮጵያ መንግሥት በጥበብ፣ በዕውቀትና በትንታኔ ላይ በተመሠረተ የብሔራዊ ጥቅም፣ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲና ዲፕሎማሲ እየመራው ስለመሆኑ የተለያዩ አመልካቾች አሉ። ኢትዮጵያ ለተመድ ተቆጣጣሪ ቡድን የምትሰጣቸው መረጃዎች፣ ከኃያላኑ አገሮች ጋር የምታደርገው የሠለጠነ ትብብር፣ የምሥራቅ አፍሪካን ሰላም ለማስጠበቅ የምታደርገው ያላሰለሰ ጥረት፣ የኢትዮጵያ መንግሥት ኤርትራን አስመልክቶ ያለውን ግንኙነት ለማሻሻል ያለው የምንጊዜም ዝግጁነት፣ በኤርትራ የጦር ሠፈር ካላቸው አገሮች ጋር ኢትዮጵያ ያላት ጥበብ የተሞላበት እንቅስቃሴና ዲፕሎማሲ ለዚህ ማሳያ ነው።    

ኢትዮጵያ በኤርትራ እየሆነ ያለው ወሳኝ ብሔራዊ ጥቅሟን (Vital National Interest) የሚነካ መሆኑን በግልጽ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ፣ በኤርትራ ውስጥና ከኤርትራ ጋር ትብብር ላላቸው አገሮች ማሳሰብ እንደ ቀጠለች ነው። ድምፅን በድምፅ መሻር የሚችሉ የፀጥታው ምክር ቤት አባል አገሮች ኢትዮጵያ ስታነጥስ፣ ታላቁ የአፍሪካ ቀንድ ጉንፋን እንደሚይዘውና ለኢትዮጵያ አለመረጋጋት ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ሁሉ ለዓለም አቀፍ ሰላም፣ መረጋጋትና ደኅንነት ያለውን አንድምታ መመልከት እንዳለበት የሚያሳይ ነው በኤርትራ ምድር ላይ ያለው ተጨባጭ ሁኔታና የኤርትራው መንግሥት ባህሪ፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት በሚያደርገው ዲፕሎማሲም ይህንኑ ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለማሳየት ከቀን ተሌት እየሠራ መሆኑ ይታወቃል።

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው yohannes.mofa@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የጋምቤላ የእርሻ ኢንቨስትመንት የገጠሙት ፈተናዎች ምን ያስተምሩናል?

$
0
0

በያሲን ባህሩ

በምዕራብ የአገሪቱ ጫፍ የሚገኘው የጋምቤላ ሁሌም ክልል በዓለም አቀፍና በአገር ውስጥ ትኩረት እንደሳበ ነው፡፡ ቀደም ባሉት ዓመታት በእርስ በርስ ግጭት፣ በጎርፍ መጥለቅለቅና በመቶ ሺዎች የደቡብ ሱዳን ስደተኞችን በማስተናገዱ ስሙ ይጠቀሳል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ ከግብርና ኢንቨስትመንት ጋር በተያያዘ በሚሊዮን ሔክታር የሚገመት መሬት በሊዝ ሽያጭ የተዘጋጀበት መሆኑ በትልልቆቹ መገናኛ ብዙኃን ሳይቀር ተዘግቧል፡፡

ለዚህ አባባል ጥሩ ማሳያ የሚሆነው ከሦስት ዓመታት በፊት አልጄዚራ የተባለው የቴሌቪዥን ጣቢያ ‹‹ኢትዮጵያ ለሽያጭ የቀረበች መሬት›› (Ethiopia Land for Sale) በሚል ርዕስ ያስተላለፈው ዶክመንተሪ አንዱ ነው፡፡ ሲኤንኤንም ‹‹ህንድ 1.2 ቢሊዮን ሕዝቦቿን እንድትመግብ እየረዳት ያለች አፍሪካዊት አገር›› (The African Country Helping India feed 1.2 Billion People) የሚል ተቀራራቢ ዘገባ አስተናግዷል፡፡ የእንግሊዙ ዘ ጋርዲያንና ሌሎችም የጋምቤላን የመሬት ጉዳይ በስፋት ዘግበውታል፡፡

በኢትዮጵያ መንግሥት አገላለጽ ‹‹ኒዮ ሊብራል›› የሚባሉት ተፅዕኖ ፈጣሪ መገናኛ ብዙኃንና ርዕዮተ ዓለም ተኮር ተቋማት (ሒውማን ራይትስዎች፣ አክላንድ ኢንስቲትዩት) ተጨማሪ መግለጫዎች አውጥተዋል፡፡ እነዚህ ከሰብዓዊ መብትና ከአካባቢ ጥበቃ ‹‹ተቆርቋሪነት› የሚመነጩ ሒሶች የተለያዩ ፍላጎቶቸን መሠረት አድርገው ቢሰነዝሩም፣ የአገር ውስጥ ተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎችና የግሉ ሚዲያም ሐሳቡን በስፋት ተቀባብለውታል፡፡ መንግሥትም ‹‹በሀብታችን መጠቀም ስንጀምር በድህነት ታስረን እንድንኖር የሚመኙ ኃይሎች ይጮኻሉ፤›› ሲል ሲያጣጥለው ቆይቷል፡፡

አሁን ደግሞ የጋምቤላ መጠሪያ ሌላ ሆኗል፡፡ ከሰባትና ከስድስት ዓመታት በኋላ ብዙ የተወራላት የግብርና ኢንቨስትመንት ፍሬው ያልታየ፣ የተነገረለትን ያህል ያላመረቃ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ በቢሊዮን የሚገመት የአገር ሀብት የሚመዘበርበትና የሀብት ውድመት መፈንጫ ሆኗል፡፡

ለአባባሉ ማሳያ የሚሆነው ከቀናት በፊት ሪፖርተር ጋዜጣ ‹‹ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የቀረበ ጥናት›› ማለት ያቀረበው መረጃ ነው፡፡ ይኼ 14 ገለልተኛ ባለሙያዎች እንደተሳተፉበት የተነገረለት ጥናት እንደሚያስረዳው፣ በክልሉ ከ2001 ዓ.ም. ጀምሮ ለ623 ባለሀብቶች ከ630 ሺሕ ሔክታር በላይ መሬት ተላልፏል፡፡ ከዚህ ውስጥ 409 ሺሕ ሔክታር የሚደርሰው በጋምቤላ ክልል፣ ቀሪው 220 ሺሕ ሔክታር ደግሞ በፌዴራል የግብርና ኢንቨስትመንትና መሬት አስተዳደር ኤጀንሲ በውክልና ከወሰደው መሬት የተላለፈ ነው፡፡

ከተላለፈው መሬት ግን እስከ 2008 ዓ.ም. ድረስ በድምሩ ከ76.8 ሺሕ ሔክታር ያልበለጠ መሬት ብቻ መልማቱን ነው ጥናቱ ያሳየው፡፡ ለዚህ ምክንያቱም ባለሀብቶች ለልማቱ ትኩረት አለመስጠታቸው፣ አብዛኛው ባለሀብት መሬት እየወሰደ ያለው አልምቶ ራሱንና አገርን ለመጥቀም ሳይሆን በአቋራጭ የባንክ ብድር ለማግኘትና በታክስ ነፃ ለመጠቀም ነው፡፡ ይኼ በአቋራጭ የመበልፀግና የመበዝበዝ ዝንባሌ 29 ባለሀብቶች ከወሰዱ መሬትና ከተበደሩት የሕዝብ ሀብት ውጪ ‹‹የት እንዳሉም አይታወቁም›› በሚል ተወስቷል፡፡

‹‹አልሚ›› ተብዬዎች ከልማት ባንክና ሌሎች ባንኮች ከ4.96 ቢሊዮን ብር በላይ ተበድረዋል፡፡ ይሁንና ከ200 ዋነኛ ተበዳሪዎች ከሚጠበቀው በስድስት እጥፍ ያነሰ ልማት ከመታየቱ ባሻገር፣ ሙስናን መደራደር ጎልቶ የታየበት ሁኔታ አጋጥሟል፡፡ በቅርቡ ገዢው ፓርቲ ባካሄደው የ‹‹ተሃድሶ ግምገማም›› ለሥርዓቱ ቅርበት ያላቸው ነባር ታጋዮች፣ ጡረተኛ የመከላከያ መኮንኖችና የተሻረኩ ኪራይ ሰብሳቢዎች የዘረፋው ዋነኛ ተዋናይ መሆናቸውን በግልጽ አሳይቷል፡፡  

‹‹በታዳጊው ጋምቤላ ክልል›› ብዙ ያነታረከው የግብርና ኢንቨስትመንት ለአካባቢው ነዋሪዎችም ሆነ ለአገሪቱ የሚታይ ጥቅም አላስገኘም፡፡ እንዲያውም ‹ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል› እንዲሉ ቀማኞች መሬት መውሰዳቸው ሳያንስ በገፍ እየተበደሩ በሌላ አካባቢ ሕንፃና ቤት እየሠሩ አከራዩ፡፡ የማሽነሪ ኪራይ፣ የኮንትሮባንድ ንግድና መሰል አመቺ የአቋራጭ መንገዶች ላይ ተረባረቡ፡፡ በነገራችን ላይ ከወራት በፊት በሪፖርተር ጋዜጣ ላይ በመቶ ሺሕ ሔክታር መሬት ይዞ ለመከነው የካሩቱሪ (የህንድ ኩባንያ) እርሻ ልማት ውድቀትም ሰፊ ዘገባ መቅረቡን እናስታውሳለን፡፡

ይኼ ሁሉ መቀራመትና የሕዝብ ሀብት ብክነት ዘግይቶም ቢሆን መንግሥትን አሁን አባኖታል፡፡ ሁሉንም አልሚዎች በጅምላ መፈረጅ ባያዳግትም፣ አብዛኛው ‹‹ኢንቨስተር›› በኪራይ ሰብሳቢነት እየነጎደ መሆኑ ሲታይም ወዴት እየተሄደ ነው? የሚል ከፍ ያለ ጥያቄን የሚያጭር ነው፡፡ ግን ምን ይደረግ?

ጋምቤላ የእምቅ ሀብት ምድር

     3.2 ሚሊዮን ሔክታር ስፋት ያለው የጋምቤላ ምድር ከአውሮፓዊቷ ሥልጡን አገር ቤልጅየም እኩል የሚባል የቆዳ ሽፋን አለው፡፡ በዚህ ክልል ከ337 ሺሕ ያልበለጠ ሕዝብ ብቻ ሲኖር፣ ቤልጀየም ግን 12 ሚሊዮን ሕዝብ (36 እጥፍ በልጣ) እንደሚኖርባት ልብ ይሏል፡፡ ስለሆነም ጋምቤላ ከስፋቱ ጋር ሲሰላ በአማካይ በአሥር ሔክታር አንድ ሰው ብቻ የሚኖርበት ነው፡፡ ይኼም ገና ሊለማ የሚችል ሰፊና ዕምቅ መሬት ባለቤት የሆነ ክልል መሆኑን ያስገነዝባል፡፡

ከክልሉ ኢንቨስትመንት ቢሮ በተገኘ የቅርብ መረጃ መሠረት ጋምቤላ ካለው 3.2 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ውስጥ 2.6 ሚሊዮን የሚሆነው ለእርሻ አመቺነት አለው፡፡ ከዚህ ውስጥ 1.2 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ለኢንቨስትመንት ዝግጁ የተደረገ ሲሆን፣ እስካሁን ከግማሽ ያነሰው ነው ለአገር ውስጥና ለውጭ ባለሀብቶች በሊዝ የተሰጠው፡፡

የጋምቤላ ክልል የመሬት ሀብት ብቻ አይደለም ያለው፡፡ ይልቁንም ሌሎች የተፈጥሮ ፀጋዎቹም ለእርሻ ኢንቨስትመንት አመቺ ያደርጉታል፡፡ የጋምቤላ የዝናብ መጠን ከ800 እስከ 1,200 ሚሊ ሜትር መሆኑ አንዱ ተጠቃሽ ፀጋ ነው፡፡ ክልሉ 1.9 ቢሊዮን ሜትር ኩብ የከርሰ ምድር ውኃ ሀብት ያለው ሲሆን እንደ ባሮ፣ አኮቦ፣ ጊሌና አልዌሮ የመሳሰሉ ትልልቅ ወንዞች ባለቤትም ነው፡፡ በክልሉ ውስጥ በርካታ ጅረቶችና አነስተኛ ሐይቆች (ሙሉ፣ ታታ፣ ቡሬና አልዌሮ) ሰው ሰራሽ ሐይቆች ይገኛሉ፡፡፡ የክልሉ የውኃ ሀብት ክምችት ከእርሻም ባሻገር ለዓሳ ሀብት ልማትና ለውኃ ትራንስፖርትም ጠቀሜታ ይሰጣል፡፡

የጋምቤላ ወንዞች የዓሳ ሀብት ልማት ከፍተኛ መሆኑ በጥናት ተረጋግጧል፡፡ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት እስከ 107 ዓይነት የዓሳ ዝርዎች በአካባቢው የሚገኙ ሲሆን፣ ዘርፉም ገና ያልተነካና ዕምቅ ነው፡፡ ለነገሩ የክልሉ የዓሳ ሀብት ገና ጥቅም ላይ ያልዋለ ነው፡፡ በዋነኛነት በአርብቶ አደርነት የሚተዳደረው የኑዌር ዞን ተዝቆ የማያልቅ የእንስሳት ሀብትን ይዟል፡፡

የጋምቤላ ክልል በማዕድን መስክም ትኩረት የመሳብ ዕድል ያለው ነው፡፡ ምንም እንኳን በተፈጥሮ ነዳጅና ድፍድፍ ዘይት ረገድ ያለው ይዞታ በጠራ መረጃ ታውቆ ይፋ ባይደረግም፣ ከፍተኛ የወርቅ ማዕድን የተከማቸበት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በባህላዊ መንገድ ከሚወጣ ጥቂት ወርቅ በስተቀርም እምብዛም ጥቅም ላይ ያልዋለ መሆኑም ይታወቃል፡፡

ዘመናዊ ሆቴሎች፣ ሎጆችና የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች አለመጠናከራቸው ነው እንጂ የቱሪዝም ሀብቱም የጋምቤላ ክልል ተስፋ ነው፡፡ በተለይ በዱር እንስሳት ሀብቱ በአፍሪካ በሁለተኛ ደረጃነት የሚቀመጠው የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክና ዋና ከተማዋን ለሁለት ከፍሎ የሚያልፈው የባሮ ወንዝ ብዙ ትኩረት የሚስቡ ናቸው፡፡ ለዚህም ጋምቤላ የኤሌክትሪክ፣ የቴሌኮሙኒኬሽን፣ የአየር መንገድና ዋና ዋና መንገዶች ማግኘትና ሰላሟን አጠናክራ ማስጠበቅ ከቻለች ተስፋ ይኖራታል፡፡

ጋምቤላ ወጥመድ የማያጣት ቆቅ

የጋምቤላ ብሔራዊ ክልል የአችዋ፣ የኑዌር፣ የሚንጃንግ፣ የኮምፕሮኦፓ ነባር ብሔረሰቦችን ጨምሮ በርካታ የአማራ፣ የትግራይ፣ የኦሮሞ፣ የጉራጌ፣ ወዘተ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች የሚኖሩበት ነው፡፡ ከዚያም አልፎ በየጊዜው ቁጥር ቢቀያየርም በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ሠፍረውበታል፡፡

ይሁንና በክልሉ በተደጋጋሚ እንደታየው ብሔር ተኮር ግጭቶች ሲቀሰቀሱ በዚህ መዘዝ የሰው ሕይወት ይጠፋል፣ ንብረት ይወድማል፡፡ እዚህ ላይ የፌዴራሉ መንግሥትም ሆነ የክልሉ መንግሥት የተለያዩ ጥረቶችን ቢያደርጉም ቦታው ሰፊና ድንበር ላይ የሚገኝ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ ከደቡብ ሱዳን በመጎራበቱ ‹‹ከአጋም የተጠጋ ቁልቋል›› መሆኑ አልቀረም፡፡

አሁን በተጨባጭ እንደታየው የውጭውም ሆነ የአገር ውስጡ ጥገኛ ታዲያ ጋምቤላን ያጠመዳት ለሥውር ጥቅሙ ብቻ እንዲሆን ያደረገው አንዱ ‹‹የሰላም ዋስትና የለም›› የሚል አጉል ጨዋታ ነው፡፡ በነገራችን ላይ በቅርቡ በአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ ጣቢያ የጋምቤላ እርሻ አልሚዎች ማኅበር መሪ የተባሉ ቅሬታ አቅራቢ ብዙዎቹ እርሻ የወሰዱ የትግራይ ባለሀብቶች ያልተገባ መገፋት አጋጥሟቸዋል ሲሉ የመንግሥትን የቅርብ ጊዜ የእርምት ዕርምጃ ተችተዋል፡፡

መረጃዎች እንደሚሳዩት በክልሉ የትግራይ ባለሀብቶች በርከት ብለው የገቡበት አንዱ ምክንያት ያለውን የፀጥታ ሥጋት ተጋፍጠው ለመሥራት በመድፈራቸው ነው፡፡ በተለይ ቀደም ሲል በትግሉ የተሠለፉና ከመከላከያ የተሰናበቱ ዜጎች ይኼን ፈተና (Challenge) ደፍሮ ለመቋቋም ወደኋላ እንደማይሉ ይታመናል፡፡ ይሁንና አሁን በታየው የኪራይ ሰብሳቢነት መንገድ በአቋራጭ ለመገልፀግ የሚደረግ ጥድፊያ በጊዜው ካልታረመ፣ በሶማሊያ በየመንደሩ ታንክና መድፍ ያጠመዱ የጎሳ መሪዎች ዓይነት አስቸጋሪ ጥገኞች ላለመቀፍቀፋቸው ዋስትና የለም፡፡

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ነባሩ የጋምቤላ ክልል ማኅበረሰብ በአንፃራዊነት ሕይወቱ በመቀየር ላይ ነው፡፡ በመንደር እየተሰባሰቡ ከተበታተነ ሕይወት መውጣት ከመጀመሩም ባሻገር፣ የትምህርትና የጤና ልማት ተቋዳሽ መሆን ችሏል፡፡ ለዚህም ከአንደኛ ደረጃ ትምህርት እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ ክልሉ ያለው ሲሆን 34 ጤና ጣቢያዎች፣ 126 ጤና ኬላዎችና አንድ ሆስፒታል መኖሩም አብነት ናቸው፡፡ የመጠጥ ውኃ አቅርቦትን ጨምሮ የመሠረተ ልማቱ መስፋፋቱም ተስፋ ሰጪ መሆኑ ሊካድ አይችልም፡፡

በግልጽ የሚታየው ጉድለት ግን አሁንም ነባሩ ማኅበረሰብ የፖለቲካው እንጂ የኢኮኖሚው ተዋናይ አልሆነም፡፡ በጋምቤላ ከተማ ከአነስተኛ ሱቅ አንስቶ ሆቴል ቤቶች፣ የአልባሳት መሸጫና ልዩ ልዩ አገልግሎቶች መስጫ ቢዝነሶች በደገኞች ነው የተያዘው፡፡ የመሬት ቅርምቱ የፈጠረው አዲስ የድለላና የኪራይ ሰብሳቢነት ትስስሩ እየፋፋ የመጣውም ከነባሩ ይልቅ በሌላኛው ማኅበረሰብ አንዳንድ ተዋናዮች መሆኑን ለመገንዘብ አያዳግትም፡፡

ይኼ ሁኔታም የመንግሥት መዋቅሩን፣ የባንክ የሌብነት ተዋንያንን፣ የግብርናና የመሬት ሰጪ ሴክተሩን በጥገኛ መረብ እያስተሳሰረ ለመሆኑ የሰሞኑ ጥናት አረጋግጧል፡፡ ይኼ የተዛባ አካሄድ ደግሞ መንግሥት ያለውን ውስን ሀብት ለግብርናው መስክ መጠናከር ለማዋል ካለው ፍላጎት አንፃር ይበልጥ ለብልሽት ተጋልጧል፡፡ ልማታዊ አካሄድ እንዲቀጭጭ ከማድረጉ አንፃር ሲመዘንም፣ በአሁኑ ወቅት ጋምቤላን ወጥመድ የሆነባት ኪራይ ሰብሳቢነት መሆኑን በግልጽ ያሳያል፡፡

ጋምቤላ ሆይ ትኩረት ይገባሻል!

     ‹‹የጥቁሩ ወርቅ ምድር›› የምትባለው ጋምቤላ ቤልጂየምን የሚያክል መሬትና ሀብት ይዛ እንኳን በዓለም በአገራችንም ሳትታወቅ ኖራለች፡፡ ባለፉት 25 ዓመታት በደግም በክፉም ከመጠቀሷ ባሻገር ያላት ዕምቅ አገራዊ ሀብትም ተለይቷል፡፡ ይኼን ሀብት ያለብልሽትና ውንብድና በጤነኛ መንገድ ለክልሉ ሕዝብም ሆነ ለአገሪቱ እንዲጠቅም ማድረግ የዚህ ትውልድ ድርሻ ነው፡፡ በተለይ ክልሉን ኪራይ ሰብሳቢነትና ኢፍትሐዊነት አጥለቅልቆት ያልተፈለገ ትርምስና ቀውስም እንዳይከሰት፣ ከ‹‹ብሔር ፖለቲካ››ና ከሙስና አጓጉል ጨዋታ ወጥቶ አሠራሮችን ግልጽነትና ተጠያቂነት ማላበስ፣ በመርህ ላይ የተመሠረተ ልማታዊ አካሄድን መከተል ያስፈልጋል፡፡

እንደ መፍትሔ

  • መንግሥት አሁን በጀመረው መንገድ የጋምቤላን ዕምቅ ሀብቶችና ተግዳሮቶችን በጥናት ይለይ፣ የታሰበውን አካሄድ በቁርጠኝነት ያርም፣ ያስተካክል፣
  • ያላለሙ የመሬት ባለይዞታዎች ይነጠቁ፣ የተበደሩት የሕዝብ ሀብትም በአፋጣኝ ይመለስ፣ እንዲያውም የቀረጥ ነፃና የግብር እፎይታም በሕዝብ ጥቅም ላይ ያላአግባብ የተፈጸመ ደባ ለሁሉም ማስተማሪያ በሚሆን መንገድ ይጋለጥ፣ እርምትም ይወሰድ፣
  • በልማታዊ መንገድ ተስፋ ሰጪ እንቅስቀሴ ውስጥ የገቡ ባለሀብቶችና ኩባንያዎች ይበረታቱ፣ ሁለንተናዊ ዋስትና የሚያገኙበት ሥርዓትም ይዘርጋላቸው፣ በተለይ በትንሽ በትልቁ ባለሀብቱን ለማማረርና ለመዝረፍ ያሰፈሰፈው ‹‹የመንግሥት ሌባ›› የሚጋለጥበት መንገድ ይበጅ፣
  • ጋምቤላ የሁሉም ብሔር ብሔረሰቦች ምድር ብቻ ሳትሆን የነባሩ ማኅበረሰብም መጠቀሚያና በእኩልነት መኖሪያ እንድትሆን በትኩረት ይሠራ፣  
  • በተለይ ከመሬት ልማት ጋር በተያያዘ በክልሉ ያለው ሀብት በመሬት ባንክ ሥርዓት ተይዞ ውጤታማ የውጭ ባለሀብቶችና ከአገር ውስጥም የተደራጁ ወጣቶችን እንዲያሳትፍ ይደረግ፣ እስካሁን የተሄደበት የተዝረከረከና የኢፍትሐዊነት አካሄድም በአስቸኳይ ይገታ፣ ይገታ፣ ይገታ፣

በመጨረሻ ሌሎች ታዳጊ ክልሎች ከጋምቤላ ሊማሩት የሚገባው የኪራይ ሰብሳቢነት መፈልፈያ ከሚሆን አደጋ ራሳቸውን ሊጠብቁ ይገባል፡፡ አፋር፣ ቤንሻንጉልና ሶማሌ ክልሎች በባለሀብትና በመንግሥት ኃላፊነት ስም የሚዘረጋን የሕዝብ ሀብትን የመበዝበዝ ዝንባሌ ሊፋለሙ ይገባል፡፡ በዚህ ረገድም የፌዴራሉ መንግሥት የተጣለበት ኃላፊነት ከፍ ያለ መሆኑን ማጤን ይገባል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው yasenbb@yahoo.com.  ማግኘት ይቻላል፡፡       

 

Standard (Image)

በባብኤል መንደብ አካባቢ ያለው የወቅቱ ሁኔታ ኢትዮጵያ በጂቡቲ የጦር ሠፈር እንደሚያስፈልጋት አመልካች ነው

$
0
0

በተስፋዬ ታደሰ (ኮማንደር)

      የባብኤል መንደብ ስትራቴጂካዊ ምንነትና የወቅቱ የመካከለኛው የምሥራቅ የደኅንነት ሁኔታ ሲቃኝ፣ ጂቡቲ ቁልፍ ስትራቴጂካዊ ሥፍራ ሆና በመገኘትዋ በዓለም ኃያላን መንግሥታትና ሌሎቹም የአካባቢው ጉዳይ ያሳስበናል ያሉ አገሮች ሁሉ፣ በዚህ ሥፍራ የጦር ሠፈር በመገንባት ላይ ይገኛሉ፡፡

ጂቡቲም ለሁሉም ባይሆንም ለጠየቁ አገሮች ለአብዛኛዎቹ ማለትም ለፈረንሣይ፣ ለአሜሪካ፣ ለጃፓን፣ ለሳውዲ ዓረብያና ለሌሎችም አወንታዊ መልስ እየሰጠች በማስተናገድ ላይ ትገኛለች፡፡

በአሁኑ ወቅት የጂቡቲ ወደብ ለኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ ወጪና ገቢ ንግድ ማስተናገጃ ብቸኛ ወደብ በመሆን እያገለገለ ይገኛል፡፡ የዚህ ወደብ የልብ ትርታ በኢትዮጵያ ኢኮኖሚና ብሔራዊ ደኅንነት ላይ ትልቅ አንድምታ አለው፡፡

የባብኤል መንደብ ጂኦፖለቲካል ምንነት

ባብኤል መንደብ የአፍሪካ ቀንድና በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኝ የባህር ላይ አጣብቂኝ የሆነ (Check Point) መተላለፍያ መንገድ ነው፡፡ ባብኤል መንደብ ለአፍሪካ ቀንድና ለመካከለኛው ምሥራቅ፣ ለሜድትራኒያን ባህርና ለህንድ ውቅያኖስ አገናኝ ድልድይ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ይህ ሥፍራ የመን፣ ጂቡቲና ኤርትራ ድንበር አካባቢ ይገኛል፡፡ የቀይ ባህርን ከኤደን ባህረ ሰላጤና ከዓረብ ባህር ያገናኛል፡፡ ከአፍሪቃ ቀንድ ከፔርሺያ ባህረ ሰላጤ በስዊዝ ካናል የሚያልፉ ገቢና ወጪ ንግዶችን በባብኤል መንደብ በኩል ያልፋሉ፡፡ 2.3 ሚሊዮን በርሜል ያልተጣራና የተጣራ ነዳጅ በዚህ የባህር መንገድ በኩል ወደ አውሮፓ፣ ዩናይትድ ስቴትስ፣ እስያና አፍሪካ ቀንድ ይጓጓዛል፡፡

ባብኤል መንደብ 18 ማይልስ ስፋት ያለው ጠባብ ሥፍራ አለው፡፡ ይኼ የነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በሁለት ማይልስ ስፋት ብቻ ያስተናግዳል፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው የባህር ጥልቀት ብዙም ባለመሆኑ በዚህ ውስን ሥፍራ ብቻ መርከቦች ለመንቀሳቀስ ይገደዳሉ፡፡

የባብኤል መንደብ ቢዘጋ ከፔርሺያ ሰላጤ የሚመጡ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ደቡብ አፍሪካ ጫፍ ዞረው ለመሄድ ይገደዳሉ፡፡ ይኼ ግን ነዳጅ ወደተፈለገበት ሥፍራ ለመጓጓዝ ረጅም ጊዜ ስለሚወስድ ለከፍተኛ ወጪ ይዳርጋል፡፡

በቀድሞው ዘመን የቀደሙት መንግሥታት ቀይ ባህርን ለአፍሪቃ፣ ለእስያና ለአውሮፓ ንግድ ሥራ ይገለገሉበት ነበር፡፡ ሆኖም በነዳጅ ኃይል የሚንቀሳቀሱ መርከቦች ተሠርተው ሥራ ላይ ከዋሉ በኋላ፣ አውሮፓውያን ወደ ህንድና ቻይና የሚያደርጉትን ጉዞ በኬፕ ኦፍ ጉድ ሆፕ በኩል ሲያደርጉ፣ ቀይ ባህርና ባብኤል መንደብ ስትራቴጂካዊ ጥቅማቸው ዋጋ ቢስ ሆኖ ነበር፡፡

በኋላ የስዊዝ ካናል በመከፈቱ ወደ ነበሩበት ሁኔታ ሊመለሱ ችለዋል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1967 በእስራኤልና በዓረቦች መካከል በተከሰተው ‹‹የስድስት ቀን ውጊያ›› እስራኤል ስዊዝ ካናልን በመዝጋትዋ ምክንያት፣ ቀይ ባህርና ባብኤል መንደብ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታቸው እምብዛም ሆነ፡፡ ሆኖም እ.ኤ.አ. በ1973 በእስራኤልና በዓረብ አገሮች መካከል ሰላም ሲፈጠር፣ ይኼ የባህር መንገድ እንደገና ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታው ሊመለስ ችሏል፡፡ ይኼ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታው በቋሚነት ዛሬም እንደቀጠለ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ 40 በመቶ የሚሆነው ነዳጅ ወደ አውሮፓና አሜሪካ በዚህ የባህር መንገድ ይጓጓዛል፡፡ በገንዘብ ሲመነዘር ወደ 700 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ ነዳጅ በዓመት በዚህ የባህር መንገድ ላይ ይስተናገዳል፡፡

ጂቡቲ በዚህ እጅግ ጠቃሚ በሆነ መንገድ ዳርቻ የምትገኝ አገር በመሆንዋ ወታደራዊ ጠቀሜታዋ ከምንጊዜውም በላይ እየጎላ በመምጣቱ፣ ታላላቅ የዓለም መንግሥታትና ሌሎችም የሚመለከታቸው አገሮች በዚህ ሥፍራ በመገኘት ብሔራዊ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ እየሞከሩ ነው፡፡

የባብኤል መንደብ የባህር ትራፊክ እንቅስቃሴን ቀጥሎ በተዘረዘሩት ሁኔታዎች በቀላሉ ማወክ ይቻላል፡፡

  1. የባህር ላይ ፈንጂ (Sea Mine) በመበተን
  2. በታጠቁ እጅግ ፈጣን አጥቂ ጀልባዎች በመርከቦች ላይ ሁከት በመፍጠር
  3. በአየር ጥቃት
  4. ከምድር በሚወነጨፉ ሮኬቶች
  5. በሌሎችም መሣሪያዎች

እ.ኤ.አ. በ1980 በኢራንና በኢራቅ መካከል በተከሰተው ግጭት የዚህ ዓይነት ሁከት በሆርሙዝ ስትሬት አካባቢ ተፈጥሮ፣ በፔርሺያ የባህረ ሰላጤ ለዓለም አቀፍ ንግድና ለነፃ የባህር ጉዞ መታወክ ምክንያት ሆኖ ነበር፡፡ በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች በተመረጡ የንግድ መርከቦች ላይ ጥቃት በማድረስ ነፃ የመርከቦችን ጉዞ ያውኩ ነበር፡፡

አሁንም የወቅቱ የአካባቢው ሁኔታ በዚህ ከቀጠለ በተመሳሳይ በባብኤል መንደብ የመርከቦች መተላለፍያ ላይ ይኼ ችግር የማይከሰትበት ምክንያት የለም፡፡

በየመን ወቅታዊ ሁኔታ ላይ የተደረገ ጥልቅ ትንተና እንደሚያመለክተው፣ የየመን ሁቲዎችና ደጋፊዎቻቸው በአካባቢው አገሮች ላይ የሚያደርጉት ትንኮሳ ብሎም ጥቃት ጦሱ ከአካባቢው አገሮች ያለፈና ሌሎችንም የሚያውክ ነው፡፡

በአካባቢ ያሉ የሁቲ ደጋፊዎች በየመን የጦር አውሮፕላኖችንና የጦር መርከቦችን በማሠለፍ ባልተጠበቀና ባልታሰበ ሁኔታ የባህረ ሰላጤውንና አካባቢውን ከበባ በማድረግ ሊቆጣጠሩት ይችላሉ፡፡ ይኼ ጉዳይ ደግሞ መዘዙ ብዙ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ላይ ያንዣበበ አደጋ

ከላይ የጠቃቀስኳቸው መንደርደሪያዎቼ ወደ ዋናው ቁም ነገሬ ወደ ኢትዮጵያ ጉዳይ ለመግባት እንዲረዱኝ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በባብኤል መንደብ አካባቢ እየሆነ ስላለው ጉዳይና ብሔራዊ ጥቅሟን በማስጠበቅ እያደረገች ያለችውን እንቅስቃሴ የትም ቦታ ያየሁት ወይም የሰማሁት ነገር በግሌ የለም፡፡ ሆኖም አይኖርም ብዬ ድምዳሜ ላይም አልደረስኩም፡፡ ነገር ግን ጭብጡን ባለማወቄ ብቻ ነው የለም እያልኩ ያለሁት፡፡ ሆኖም ጂቡቲ ይኼን አስመልክቶ ከአቅም በላይ የሆነ ችግር ቢገጥማት ጉዳዩ ኢትዮጵያን እጅግ በጣም የሚያሰጋ ይሆናል፡፡

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ከጂቡቲ ጋር የሚያገናኛትን ትራንስፖርት ማለትም የባቡር መስመርና ሌሎችም ለኢኮኖሚ ዕድገት እጅግ ጠቃሚ የሆኑ ፕሮጀክቶችን እያጣደፈች በመገንባት ላይ ትገኛለች፡፡ እነዚህ እጅግ በጣም ጠቃሚ የሆኑ የትራንስፖርት ግንባታዎች፣ ለኢትዮጵያም ሆነ ለሌሎች አገሮች በሁለት አንገብጋቢ ጉዳዮች በጣም ወሳኝ ናቸው፡፡ እነርሱም ለንግድና ለወታደራዊ ተግባራት፡፡

ስለወታደራዊ ተግባር ካነሳን አይቀሬውን ሥጋት አስመልክቶ ዛሬ ሌሎች አገሮች እያደረጉ እንዳሉት፣ ኢትዮጵያ በሥፍራው ምንም ዓይነት የባህር ኃይልም ሆነ ወታደራዊ ጠቀሜታ ያለው ተቋምና ዘላቂ ጥቅሟን ሊያስጠብቅ የሚችል በሥፍራው ያስቀመጠችው ነገር የለም፡፡ ጠንከር ያለ ችግር በሥፍራው ቢከሰት ኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ተጠቂ አገር ትሆናለች፡፡ ኢትዮጵያ ለጂቡቲም ሆነ ለባብኤል መንደብ በጣም ቅርብ አገር እንደመሆንዋ መጠን በአካባቢው ችግር ሲፈጠር ብሔራዊ ጥቅሟን በከፍተኛ ደረጃ ለመጠበቅ ጠንከር ያለ ወታደራዊ ኃይል በሥፍራው ሊኖራት ይገባል፡፡

ይኼ ማለት ግን ኃያላን አገሮች ዛሬ በሥፍራው ስላሉ ከእነሱ ጋር ለመወዳደር ሳይሆን፣ የእነሱን ቀድሞ መገኘት ሐሳብ በመደገፍና ለጥረታቸውም ተጨማሪ ኃይል ለማሠለፍ ነው፡፡ ዓላማው ዓላማችንን  የደገፈ ሆኖ በመገኘቱ፡፡

የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በአካባቢው ማውለብለብና የኢትዮጵያ ተዋጊ መርከብም በሥፍራው መታየት፣ በአካባቢው ለሚከሰተው ወታደራዊ ሁኔታ ኢትዮጵያ ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል፡፡ በቀይ ባህርና በባህረ ሰላጤው ለተከሰተው ችግር ዘላቂ ጥቅሟን ለማስጠበቅ ምን ያህል የቆረጠች መሆንዋን ያመላክታል፡፡

በተጨማሪ ደግሞ 100 ሚሊዮን ሕዝብ ያላት ኢትዮጵያ ከቀይ ባህር ጥቂት ኪሎ ሜትሮች ርቃ የምትገኝ አገር በመሆንዋ የባህሩ ጉዳይ ከማንም በላይ ያሳስባታል፡፡ እንዲሁም ቀድሞ ካለው ልምድ በመነሳት በአካባቢው የሚከሰት ማንኛውም ሥጋት ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚና ብሔራዊ ደኅንነት ፀር ነው፡፡

በእርግጥም ወደ መቶ የሚጠጉ ወታደሮችና አንድ ሁለት የጦር ጀልባዎች ጂቡቲ ስናስቀምጥ የውጭ ምንዛሪ ማስወጣቱ አይቀሬ ነው፡፡ ይኼም ብቻ አይደለም በአጠቃላይ በመከላከያ በጀትም ላይ ትንሸ ጫና ሊፈጥር ይቻላል፡፡ ሆኖም የጂኦፖለቲካል ምንነቱ ሲገመገም ጥቂት ገንዘብ ለዚህ ወሳኝ ጉዳይ መመደብ ጥቅሙ እጅግ የላቀ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

በእርግጥ ኢትዮጵያ በምድርም ሆነ በባህር ሥጋት አላት፡፡ ለምሳሌ ኢትዮጵያ በርከት ያሉ የንግድ መርከቦች በባህር ላይ አሰማርታ ገቢና ወጪን ንግዷን እያጧጧፈች ትገኛለች፡፡ በአካባቢው ውጥረት በሚከሰትበት ወቅት እነዚህ መርከቦች በባብኤል መንደብና በባህረ ሰላጤው ሲደርሱ በኢትዮጵያ የጦር መርከቦች ታጅበው ወደ ጂቡቲ ወደብ መድረስ አለባቸው፡፡ ሌሎች አገሮች እያደረጉ እንዳሉት ሁሉ እኛም የጦር መርከቦች አሠማርተን ጥቅማችንን ማስጠበቅ አለብን፡፡ ጥቂት ኪሎ ሜትሮች ብቻ ከባህር ርቀን እያለን ነገር ግን በምድር ዙሪያችን የተከበብን ብቸኛ የዓለም አገር እኛ ብንሆንም፣ የወደፊት ሥጋታችንን ከአሁኑ በመገንዘብ ከማያስፈልግ ‹‹ሠርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ›› አባባል ርቀን ብሔራዊ ችግራችንን በአግባቡ ለመፍታት ዛሬ ብቁ ሆነን ቀድመን መገኘት አለብን፡፡

በአሁኑ ጊዜ በመካከለኛው ምሥራቅ እየሆነ ላለው ሁኔታ ቀደም ብለን ባንዘጋጅም፣ የዓለም ኅብረተሰብ እኛ ወደንና ፈቅደን ከተቀላቀልነው በኮሌክቲቭ ሴኪዩሪቲ ጉዳይ ኢትዮጵያ በማንኛቸውም መሥፈርቶች ቀደም ብላ የታወቀች ናት፡፡ ለዚህም ምስክራችን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተልዕኮ በኮሪያ፣ በኮንጎ አሁን ደግሞ በአፍሪካ ችግሮች ሁሉ ቀደም ብሎ በመገኘት ችግር ፈቺ አገር መሆናችን ይታወቃል፡፡ ይኼ ጉዳይ ብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር ቢሆንም፣ ሁሉም አገሮች በሥፍራው የተገኙት ለተመሳሳይ ዓላማ በመሆኑ የኢትዮጵያ ቡድኑን መቀላቀል እጅግ በጎ ተግባር ነው ብለው ያምናሉ፡፡ ለጥረታችንም በጎ ምላሽ እንደሚያደርጉ አያጠራጥርም፡፡ በዚህ ጥረት ላይ የኢትዮጵያ መሳተፍ በኮሌክቲቭ ሴኩሪቲው ላይ ኢትዮጵያ ያላትን ፍላጎት ዳግም በግልጽ ያረጋግጣል፡፡

እዚህ ላይ እንግዲህ የበጀት ጉዳይ ቀደም ሲል ማንሳቴ ያለምክንያት አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው በተለይም የባህር ኃይል ተልዕኮ (Operation) በወጪ በኩል ከሌሎች ኃይሎች ጋር ሲወዳደር ትንሽ ከፍ ያለ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ልዩ አጽንኦት ሰጥቼ ዘርዘር አድርጌ ለመግለጽ እገደዳለሁ፡፡ ይኼን ጉዳይ ወታደራዊ ዕቅድ አውጪዎችና ስትራቴጂስቶች በይበልጥ ይገነዘቡታል፡፡ አንድ ጊዜ በዚህ ጉዳይ ላይ ወስነን መርከበኞችና መርከቦችን በሥፍራው ካሠማራን፣ በተመሳሳይ ዓላማ በሥፍራው የሚገኙ ኃያላን አገሮች የመርከብ ሥምሪት የሚያስከትለውን የበጀት ጫና ይገነዘባሉ፡፡ ተልዕኮአችን ከተልዕኮአቸው ተመጋጋቢ መሆኑን በመገንዘብ፣ ከዚያ በላይ ደግሞ ከአካባቢው የወጣን ኃይል በመሆናችን በወጪ መጋራትና በሌላም ሁኔታ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ቀደም ካለው ልምድ በመነሳት ቅን ዕምነቴን እገልጻለሁ፡፡

ይኼ ብቻ አይደለም፡፡ ቀደም ሲል የኢትዮጵያ ባህር ኃይል በወርቃማ ዘመኑ በቀይ ባህር ላይ ለተሠማሩ መርከቦች አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በሥፍራው በመድረስ ለተቸገሩበት ጉዳይ መፍትሔ ይሰጥ ነበር፡፡ ማለትም በአካል መሰርጎድ ምክንያት መርከብ በውኃ ሲጥለቀለቅ፣ የእሳት አደጋ ሲያጋጥማቸው፣ በናቪጌሽን ስህተት መሬት ላይ ሲወጡ፣ የቴክኒክ ችግር ሲከሰት፣ ወዘተ የኢትዮጵያ የባህር ኃይል በተለይ በደቡብ ቀይ ባህር ቀድሞ በመገኘት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ በማድረግ ዓለም አቀፍ ግዴታውን በብቃት ይወጣ ነበር፡፡

ከዚህም በተጨማሪ እንደ ፕሬዚዳንት ጋዳፊ ያሉ አስገራሚ መሪዎች አንድ ሌሊት ቀይ ባህር ላይ ተንሳፋፊ አደገኛ ፈንጂ  በዘሩበት ወቅት፣ የኢትዮጵያ ባህር ኃይል በቀይ ባህር ላይ የነበሩ መርከቦችን ከአደጋው እንዲርቁ በሬዲዮ በመምከርና ፈንጂውም ሲታይ አቅጣጫውን በሬዲዮ በማሳወቅ፣ መርከቦች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የበኩሉን የዓለም አቀፍ ግዴታ ሁሉ ሲወጣ የነበረ ኃይል ነው፡፡

ለዓለም ሰላምና በጎ ተግባር በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የታወቁት የምድር ጦርና የአየር ኃይላችን ብቻ ሳይሆኑ፣ የኢትዮጵያ የባህር ኃይልም የተቀረፀው ከወታደራዊ ግዳጁ ባሻገር ለበጎ ተግባርም እንደነበር በጥረቱ ይታወቅ ነበር፡፡

በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ የአካባቢውን ጂኦፖለቲክስ ጠንቅቆ መረዳት እጅግ ብልህነት መሆኑን መገንዘብ አለባት፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትም ሆነ ኃያላን አገሮች ለጉዳዩ አጽንኦት በመስጠት በአካባቢው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ ከዚህ በላይ ደግሞ አካባቢው እጅግ በሚያስገርም ሁኔታ እየተለዋወጠ ነው፡፡ የመንም ሉዓላዊነትዋን ብዙዎች እንደሚገምቱት ቶሎ አስከብራና አስጠብቃ እንደ ነፃ አገር የምትኖርበት ጊዜ ብዙም ቅርብ አይመስልም፡፡

በተጨማሪ ከየመን ዳርቻ በባብኤል መንደብ ከአካባቢ የሚያልፉ መርከቦች ላይ ከምድር በተተኮሰ ሮኬት መርከቦችን ለማሸማቀቅ ጥረት ተደርጎ ነበር፡፡ ሆኖም እንደ አጋጣሚ የተተኮሰው ሮኬት በዩናይትድ ስቴትስ የጦር መርከብ ላይ በመሆኑ ወዲያው አፀፋ መልስ መስጠት ብቻ ሳይሆን የተተኮሰበትን ሥፍራ በግልጽ በአካባቢው ለሚገኙ የአሜሪካ ኃይሎች በማሳወቅ ወንጀለኞቹ በማያዳግም ሁኔታ ተደምስሰዋል፡፡ በዚህ ንቁና ፈጣን መልስ የተነሳ አካባቢው ከወንበዴዎች ከመፅዳቱ በተጨማሪ ለጊዜው ሥጋቱ ለመቀነስ ችሏል፡፡

ይኼን ሥጋት ለጊዜው ያቆመው የዩናይትድ ስቴትስ ባህር ኃይል ነው፡፡ ይኼ አጋጣሚ በቀይ ባህር ላይ የንግድ መርከቦች ተሸማቀው እንዳይንቀሳቀሱ ሥጋት ሊፈጥር ይችል ነበር፡፡ ሆኖም ቅፅበታዊ ዕርምጃ በመወሰዱ ለጊዜው ሥጋቱ ሊገታ ተችሏል፡፡

ጽሑፉን ከመደምደሜ በፊት ሳልጠቅስ የማላልፈው የኢትየጵያ ንግድ መርከብ ድርጅት በባህረ ሰላጤው የባህር ወንበዴዎች ጥቃት ወቅት የወሰደውን ቆፍጣና ዕርምጃ ሳላደንቅ አላልፍም፡፡ የዚህ ግዳጅ አፈጻጸም ዝርዝር መረጃ ባይኖረኝም፣ በጉዳዩ ታስቦና ታቅዶ በችግሩ ወቅት አንድም የኢትዮጵያ የንግድ መርከብ በወንበዴዎች ታግቶ ባለመወሰዱ፣ ይኼም አስቀድሞ የተደረገ ጥንቃቄና የብዙ ዝግጅት ውጤት ስለሆነ መልካም ጅምሩን ደግሞ አደንቃለሁ፡፡ አሁንም ችግሩ ለጊዜው ተዳፈነ እንጂ ጨርሶ ባለመወገዱ ቀደም ያለው ጥረት ግለቱ ሳይቀዘቅዝ ቢቀጥል እላለሁ፡፡

ዳግም በአጽንኦት ልገልጽ የምፈልገው ስለዓለም አቀፍ ማሪታይም ውዝግብና ድንገት በአገር ኢኮኖሚና ደኅንነት ላይ ስለሚያስከትለው አደጋ ነው፡፡

ኢትዮጵያ ይኼን ቅስም ሰባሪ ሁኔታ እንድትቋቋም አስቀድሞ መደረግ ስላለበት ቅድመ ዝግጀት ነው የማሳስበው፡፡ ኢትዮጵያ ይኼን አይቀሬ ሥጋት በመቋቋም የግዴታ የታጠቀና በብቃት የተደራጀ ተወርዋሪ ኃይል ጂቡቲ ላይ ሊኖራት ይገባል፡፡ ይኼን ካደረግን ስትራቴጂካዊ የሆኑ ሸቀጦቻችን (Strategic Commodities) ወደ አገራችን በሰላም ይገባሉ፡፡ የአገራችንም ደኅንነት በይበልጥ የተጠበቀ ይሆናል ብዬ በአጽንኦት አምናለሁ፡፡

በአሁኑ ወቅት የዓለማችን ኃያል አገሮችና ሌሎችም የሚመለከታቸው አገሮች በጂቡቲ መሰባሰብ፣ ኢትዮጵያ በቀይ ባህርና በባህረ ሰላጤው ያላት የፀጥታና የደኅንነት አመለካከት በሚገባ መመርመር አለባት እላለሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የቀድሞ ባህር ኃይል አባል፣ የቀይ ባህርና የባህረ ሰላጤው አካባቢ ወታደራዊ ጉዳዮች ተመራማሪ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው tadessetm28@gmail.com. ማግኘት ይቻላል፡፡

          

 

 

Standard (Image)

አገሪቱን ለቀውስ የዳረጋት መሠረታዊ ምክንያት የዴሞክራሲ ግንባታው ሒደት ወደ ኋላ መጓተት ነው

$
0
0

በበርሄ መኮንን (ዶ/ር)

   ኢሕአዴግ የደርግን መንግሥት በጉልበት ጥሎ ሥልጣን ከያዘ 25 ዓመታት አልፈዋል፡፡ በእነዚህ 25 ዓመታት አገሪቱና ገዢው ፓርቲ ከገጠሟቸው ፈተናዎችም ባለፈው ዓመት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተደረጉትን ተቃዋሚዎች ተከትሎ የተፈጠረው ቀውስ በግንባር ቀደም የሚጠቀስ ነው፡፡ ቀውሱ የብዙ ሰዎች ሕይወት ከጠፋና ከፍተኛ ዋጋ ያለው ንብረት ከወደመ በኋላም ሊቆም ስላልቻለ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እስከማወጅ ደርሷል፡፡ ሁኔታዎች ለጊዜው የተረጋ ቢመስሉም ችግሩ ከመሠረቱ ተፈቷል ማለት እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ በተከሰተው ቀውስ ምክንያትና መፍትሔ ዙርያ የተለያዩ ኢትዮጵያዊያን ሐሳባቸውን በመስጠት ላይ ይገኛሉ፡፡ እኔም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ በጉዳዩ ላይ ያለኝን ሐሳብ በዚህ ጽሑፍ አቀርባለሁ፡፡ በተቻለኝ መጠንም ካሁን በፊት በሌሎች ሰዎች ባልተነሱ ወይም በሚገባ ባልተነሱ ነጥቦች ላይ ለማተኮር እሞክራለሁ፡፡

   በእኔ እምነት አሁን ላለንበት ሁኔታ የዳረጉን ብዙ ተዛማጅ ምክንያቶች ቢኖሩም ዋናው ምክንያት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታው በበቂ ፍጥነት ባለመጓዙ፣ ይልቁንም በብዙ መልኩ ወደ ኋላ መጎተቱ ነው፡፡ የሙስናና ኪራይ ሰብሳቢነት መስፋፋት፣ የመልካም አስተዳደር ችግር፣ የኢኮኖሚ ዕድገቱ ተጠቃሚ አለመሆንና የመሳሰሉ ችግሮች እንደ ምክንያት ሲጠቀሱ ይሰማል፡፡ እነዚህን ችግሮች እንደ የቅርብ ጊዜ መነሻዎች (Immediate Causes) እንጂ እንደ መሠረታዊ ምክንያት አላያቸውም፡፡ ይህን የምለው በሁለት ምክንያቶች ነው፡፡ አንደኛ፣ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው የኋልዮሽ ባይሄድ (በሌላ አባባል የፖለቲካ ምኅዳሩ አሁን ባለበት ደረጃ ባይጠብ) ኖሮ ከፍ ብለው የተጠቀሱት ችግሮች ወይም አይፈጠሩም፣ ቢፈጠሩም ደግሞ አሁን ካሉበት ደረጃ አይደርሱም ነበር፡፡ በአንድ በኩል እነዚህ ችግሮቹ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን የፖለቲካ ምኅዳሩ በመጥበቡ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ ማለትም የፖለቲካ ምኅዳሩ መጥበብ አካል ተደርገው ሊታዩ ይችላሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የፖለቲካ ምኅዳሩ እየሰፋ ቢሄድ ኖሮ የዴሞክራሲ ሒደቱ ራሱ ችግሮች አሁን ካሉበት ደረጃ እንዳይደርሱ ያደርግ ነበር፡፡ ሁለተኛ፣ አንዳንዶቹ ችግሮች የፖለቲካ ምኅዳሩ እየሰፋ ቢሄድም ሊኖሩ እንደሚችሉ መገመት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ እንደ ድህነትና ሥራ አጥነት ያሉ የኢኮኖሚ ችግሮች በቅርብ ጊዜ ሙሉ በሙሉ የሚፈቱ አይደሉም፡፡ ሆኖም በእነዚህ ዓይነት ችግሮች ሳይቀር ሕዝብ ቅሬታ ቢኖረው የፖለቲካው ምህዳሩ አሁን ባለበት ደረጃ ባይጠብና እየሰፋ ቢሄድ ኖሮ ቅሬታው በዴሞክራሲያዊ መንገድ ይገለጽ ነበር፡፡ በሌላ አባባል ምንም እንኳን እነዚህ ችግሮች ቢኖሩም፣ ሕዝቡ ችግሩን የሚገልጽበትና የመፍትሔ አካል የሚሆንበት የተወሰነች ክፍተት አለች ብሎ ቢያምን ያቺኑ ክፍተት ለመጠቀም ይሞክር ነበር፡፡ ችግሩም ከቁጥጥር ሥርዓት ውጪ አይሆንም ነበር፡፡

    የሕዝብ ብሶት በተባባሰበትና ብሶቱንም በዴሞክራሲያዊ መንገድ ለመግለፅ በቂ ክፍተት በሌለበት ሁኔታ ደግሞ፣ የሚቀሰቅስ ነገር በተገኘ ጊዜ የሚፈነዳና በቀላሉ ከቁጥጥር ውጪ ሊሆን የሚችል የሕዝብ ተቃውሞ ይፈጠራል፡፡ የተፈጠረውም ይኸው ነው፡፡ በመንግሥት ሚዲያዎች በተደጋጋሚ ሲገለጽ እንደነበረው የሕዝቡን ቅሬታ ለራሳቸው የፖለቲካ ጥቅም ለማዋል ሲሉ አመፅ እንዲቀሰቀስ የሚሠሩ የውስጥም የውጭም ኃይሎች ሊኖሩ እንደሚችሉ ይታወቃል፡፡ ሆኖም እነዚህ ኃይሎች ኖሩም አልኖሩም መሠረታዊ ችግሩ እስካልተፈታ ድረስ አመፅ መፈጠሩ እንደማይቀር መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ መፍትሔውም በጣም እየጠበበ የመጣውን የፖለቲካ ምኅዳር ማስፋትና የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታውን በበቂ ፍጥነት ማስኬድ ነው፡፡ ለዚህም ገዢው ፓርቲ የአንበሳውን ድርሻ መውሰድ ቢኖርበትም፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎችም የራሳቸውን ሚና መጫወት ይጠበቅባቸዋል፡፡

     ቀሪው የጽሑፍ ክፍል በአራት ክፍሎች ይቀርባል፡፡ በመጀመሪያ ስለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሒደትና ጥቅሞቹ ለሚቀጥሉት ክፍሎች መንደርደሪያ በሚሆን መልኩ አጠር ያለ ገለጻ እሰጣለሁ፡፡ በመቀጠልም የ25 ዓመቱን የዴሞክራሲ ግንባታ ጉዞና አሁን ላለንበት ደረጃ እንዴት እንደደረስን በአጭሩ ለማስረዳት እሞክራለሁ፡፡ ከዚያም የጽሑፉ ዋና ክፍል ወደ ሆነውና የመፍትሔ ሐሳቦች ወደሚቀርብበት ክፍል እንገባለን፡፡ በዚህ ክፍል በገዢው ፓርቲናና በተቃዋሚ ፓርቲዎች ሊወሰዱ ስለሚገቡ ዕርምጃዎች አብራራና ከዚያም ባለፈው ዓመት ከተካሄዱት ተቃውሞዎችና አመፆች መወሰድ ስለሚገባቸው ትምህርቶች አንዳንድ ሐሳቦችን አቀርባለሁ፡፡ በመጨረሻም ማጠቃለያ ሐሳብ ይኖራል፡፡

   

ዴሞክራሲ እንዴት ይገነባል? ጥቅሞቹስ ምንድን ናቸው?

    ዴሞክራሲ በብዙ መልኩ ሊተረጎም ቢችልም በመሠረታዊ ደረጃ በሕዝብ የተመረጠ አካል ለተወሰነ ጊዜ የመንግሥት ሥልጣን የማይዝበትና የሥልጣን ጊዜው ሲያልቅ ደግሞ ለተረኛ ተመራጭ የሚያስረክብበት ሒደት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ከኢዴሞክራሲያዊ (አምባገነን) መንግሥት የሚለይበት ዋናው ምክንያት እንደ ኋለኛው የሥልጣን መሠረቱ ጉልበት ሳይሆን የሕዝብ ይሁንታ መሆኑ ነው፡፡ ዴሞክራሲን ትንሽ ሰፋ አድርገን እንየው ካልን ደግሞ በሕዝብ የተመረጠ መንግሥት ከመኖሩ በተጨማሪ መሠረታዊ የሚባሉ ሰብዓዊ መብቶች የተከበሩበት የአስተዳደር ሥርዓት ልንለው እንችላለን፡፡

የዘርፉ ምሁራን እንደሚያስረዱት አንዲት አገር ከኢዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የምትሸጋገረው በመሪዎች (ሊህቃን) በጎ ፈቃድ ሳይሆን፣ በመሪዎችና በተራው ሕዝብ (ተመሪዎች) መካከል በሚኖረው የፍላጎት ተቃርኖ (Conflict of Interest) የተነሳ ተራው ሕዝብ በመሪዎች ላይ በሚያደርገው ግፊት ነው፡፡ ከሰዎች ተፈጥሯዊ ራስ ወዳድነት የተነሳ መሪዎች ሥልጣናቸውን በዋናነት ለራሳቸው ጥቅም ማዋል ይፈልጋሉ፡፡ ኢዴሞክራሲያዊ በሆነ ሥርዓት ደግሞ ተራውን ሕዝብ በመጨቆን የራሳቸውን ጥቅም ከማስጠበቅ የሚከለክላቸው ነገር አይኖርም፡፡ ተራው ሕዝብ በዚህ ደስተኛ ስለማይሆን ሁኔታዎች ሲመቹለት ተቃውሞ ያነሳል፡፡ የሕዝቡ ተቃውሞ የማንሳት ዕድልና የተቃውሞው ጥንካሬ በውስጡ ባለው የትብብርና የመደራጀት አቅም ይወሰናል፡፡ ለዚህ ነው የከተሞችና የትምህርት መስፋፋት ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ እንደ መልካም ነገር የሚታዩት፡፡ መሪዎች ደግሞ የሕዝቡን ተቃውሞ በጉልበት ወይም መለስተኛ ለውጥ በማድረግ ለመቀልበስ ይሞክራሉ፡፡ ተቃውሞው እየጠነከረ የሄደ እንደሆነና መሪዎችም በጉልበት ወይም መለስተኛ ለውጥ በማድረግ እንደማይመለስና ይልቁንም በቂ መልስ ካልሰጡ ወደ አብዮት ተቀይሮ ከሥልጣናቸው ሊያወርዳቸው  (ከዚያ የባሰም ሊገጥማቸው ይችላል) እንደሚችል ከተረዱ ሕዝቡ የጠየቃቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ቃል ይገባሉ፡፡ለቃላቸው ማረጋገጫም የእነሱን ሥልጣን የሚቀንሱ (የሕዝቡን ሥልጣን የሚጨምሩ) እና የሕዝቡን ጥቅም የሚያስጠብቁ ሕጎችንና አሠራሮችን ያወጣሉ፡፡ ይህንን የሚተገብሩና የሚከታተሉ ተቋማትን መገንባትም ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም በቀረቡት ማሻሻያዎችና በተቋቋሙት ተቋማት ጥንካሬ በተማመነ መጠንም የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታው እየተጠናከረ ይሄዳል፡፡ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሒደቱ ባጭሩ ይህን ቢመስልም በተግባር የተወሳሰበና ብዙ ውጣ ውረዶች የበዛበት ነው፡፡ ወደ ኋላ የመመለስ አደጋውም ሰፊ ነው፡፡ የዴሞክራሲ ተቋማቱ በጣም ካልዳበሩና የሕዝቡ ተቃውሞ ከተቀዛቀዘ መሪዎች ተቋማቱን በማጥፋት ወይም በመቆጣጠር የተጀመረውን የዴሞክራሲ ሒደት ሊቀለብሱት ይችላሉ፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ መሪዎች ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መገንባት ከምር ቢጀምሩም ሕዝቡ በግንባታው ፍጥነት ካልረካ አመፅ ቀስቅሶ ሊጥላቸውና የተጀመረው የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታም ወደ ኋላ ሊመለስ ይችላል፡፡

   በማንኛውም አገር ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚገነባበት ሒደት በመሠረታዊ ደረጃ ከላይ እንደተገለጸው ቢሆንም ዝርዝር ሒደቱ አገሮች ባሉበት ነባራዊ ሁኔታ የሚለያይና የሚወሰን ነው፡፡ በዚህ ረገድ ቀድመው ዴሞክራሲን በገነቡ አገሮች (በተለይ ምዕራባዊያን አገሮች) እና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ በቅርቡ በጀመሩ ወይም ገና ባልጀመሩ አገሮች መካከል አንድ ትልቅ ልዩነት አለ፡፡ ይኸውም በቀደሙት አገሮች የነበረው ሒደት ምንም እንኳን የራሱ ውጣ ውረዶችና መስዋዕትነቶች የነበሩት ቢሆንም፣ በአመዛኙ በአገሮች ነባራዊ ሁኔታ የተነሳሳና ተፈጥሯዊ ሊባል የሚችል አካሄድ የነበረው ነው፡፡ በኋለኞቹ ላይ ግን ከውስጣቸው ነባራዊ ሁኔታ በተጨማሪ የውጪ ተፅዕኖውም ቀላል አይደለም፡፡ የውጭ ተፅዕኖው በሁለት ዋና ዋና መንገዶች ሊገለጽ ይችላል፡፡ የመጀመሪያው በቀጥታ ከምዕራባዊያን መንግሥታት የሚመጣ ነው፡፡ ይኼ ተፅዕኖ በተለይ ከቀዝቃዛው ጦርነት ማብቃት በኋላ እየጨመረ መጥቷል (ምንም እንኳን አሁን ደግሞ በዓለም አቀፍ የፀረ-ሽብር ትግሉ ምክንያት እየቀነሰ ነው ቢባልም)፡፡ ከምዕራባዊያን የሚመጣው ግፊት ከጊዜ ወደ ጊዜና ከአገር ወደ አገር ቢለያይም ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ሁሉም አገር ሊከተለው የሚገባ ሥርዓት ስለመሆኑ ከመንግሥታቱ አልፎ በዋናነት በእነሱና በሕዝባቸው ድጋፍ የሚንቀሳቀሱ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች በተደጋሚ ስለሚሰበክ ገና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባልገነቡ አገሮች ላይ ያለው ተፅዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ ለዚያም ይመስላል በአሁኑ ጊዜ ወቅቱን እየጠበቀ የሚመጣ ምርጫ የማያካሂዱና በግልፅ ዴሞክራሲያዊ አይደለም የሚሉ መንግሥታት በጣት የሚቆጠሩ ብቻ የሆኑት ፡፡

   ሁለተኛው ተፅዕኖ ዓለም ከቀድሞው በበለጠ በመተሳሰሯ ገና ዴሞክራሲ ባልዳበረባቸው አገሮች ያሉ ዜጎች በተለይ ደግሞ የተማሩትና ከተሜዎች ዴሞክራሲ በዳበረባቸው አገሮች ያለውን ነፃነትና መብት እነሱ አገርም እንዲኖር በመፈለግ ከሚያደርጉት ግፊት የሚመጣ ነው፡፡ የዳያስፖራው ተፅዕኖም ከዚህ ጋር ይያያዛል፡፡ ይህ ከማኅበራዊ ሚዲያ መስፋፋት ጋር ተያይዞ ከፍተኛ ተፅዕኖ ሊፈጥር ይችላል፡፡ እየፈጠረም ነው፡፡ እነዚህ ተፅዕኖዎች የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታው በፍጥነት እንዲጀመር የማድረግ አስተዋፅኦ ሊኖራቸው ቢችልም፣ ከአገር ውስጥ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር ካልተቀናጁ ለወትሮው አስቸጋሪ የሆነውን ሒደት የበለጠ ውስብስብና ውጣ ውረዶች የበዙበት ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ በተለይ ከምዕራባውያን የሚመጡ ቀጥተኛ ተፅዕኖዎች መንግሥታት ከእነዚሁ አገሮች የሚያገኙትን ዕርዳታ እንዳይቀርባቸው ሲሉ ብቻ የውሸት ዴሞክራሲ እንዲጀምሩ ስለሚያደርጉ፣ ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው እንደሚያመዝን ይታመናል፡፡ ከላይ እንደተገለጸው የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ በጣም ከባድና ብዙ ውጣ ውረዶች ያሉበት ቢሆንም፣ ጥቅሞቹም የዚያን ያህል ብዙ ናቸው፡፡ ዜጎች የሚያስተዳድሯቸውን መሪዎች መምረጥ መቻላቸው በራሱ ጥሩ ነገር ቢሆንም፣ ከዚ ያለፈ ተግባራዊ (Practical) ጥቅሞችም አሉት፡፡

   ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ከኢዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ጋር ሲነፃፀር ለሕዝብ ጥቅም የቆመ፣ሰብዓዊ መብቶችን የሚያከብርና በአጠቃላይም የተሻለ የማኅበራዊ ፍትሕ እንዲኖር የሚጥር ጥሩ መንግሥት እንዲኖር የማድረግ ዕድሉ በእጅጉ የሰፋ ነው፡፡ ይህ የሚሆነውም በሁለቱ ምክንያቶች ነው፡፡ አንደኛ ፓርቲዎች የሕዝቡን ይሁንታ አግኝተው ሥልጣን ላይ ለመውጣት (እንዲሁም ወጥቶ ለመቆየት) ሲሉ ሕዝብ የሚወደውን ፖሊሲ ለመቅረፅና ለመተግበር ይታትራሉ፡፡ ሁለተኛ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚኖሩ እንደ ነፃ ፍርድ ቤት፣ ገለልተኛ ሚዲያ፣ ጠንካራ ሲቪክ ማኅበራት፣ ወዘተ ያሉ ተቋማት ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱ እንደ ምሰሶ ከማገልገል በተጨማሪ፣ መንግሥት በዜጎች ላይ የመብት ጥሰት እንዳይፈጽምና ቃል የገባቸውን ፖሊሲዎች እንዲተገብር ጫና ያደርጉበታል፡፡ እነዚህ ጥቅሞች ታድያ ዴሞክራሲ የሚፈጥራቸው ዕድሎች (Permissive Advantages) እንጂ ዴሞክራሲ ስላለ ብቻ በእርግጠኝነት የሚከሰቱ አይደሉም፡፡ አንዲት ዴሞክራሲያዊት አገር ምን ያህል በእነዚህ ዕድሎች ተጠቃሚ እንደምትሆን በአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታዎችና ዴሞክራሲው ራሱ በተገነባበት መንገድ ሊወሰን ይችላል፡፡ ለምሳሌ በዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ እንደ ግንባር ቀደም አርዓያ ተደርጋ የምትጠቀሰውና ራሷን ነፃው ዓለም (The Free World) እያለች የምትጠራው አሜሪካ፣ ከማኅበራዊ ፍትሕ አንፃር በጥሩ እንደማትነሳና እጅግ ብዙ የሚቀሯት ሥራዎች እንዳሏት ብዙዎች ይስማማሉ፡፡

    የዴሞክራሲያዊው ሥርዓት ሌላኛውና እርግጠኛ ጥቅሙ የተረጋ (Stable) ሥርዓት መሆኑ ነው፡፡ የዳበረ ዴሞክራሲ ባለበት አገር የተገነባ ሥርዓት ብዙ ያልተጠበቁ ፈተናዎች (ለምሳሌ ድርቅ፣ የኢኮኖሚ ቀውስ፣ ጦርነት፣ ወዘተ) ቢገጥሙትም የመበታተን ዕድሉ ወደ ዜሮ የተጠጋ ነው፡፡ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ቢወርድ እንኳን (የተመረጠበት ጊዜ ሳያልቅም ቢሆን) ሥርዓቱ እንደ ሥርዓት የመቀጠል ዕድሉ በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ ደግሞ አገሪቱ አንድነቷንና ሰላሟን ጠብቃ እንድትቀጥል በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ በአንፃሩ ኢዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባለበት አገር ከባድ ፈተና በገጠመ ጊዜ መንግሥት ቢፈርስ ሥርዓቱም አብሮ ስለሚፈርስ፣ አገሪቱ የመበታተን አደጋን ጨምሮ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ የመግባት ዕድሏ እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ ጥቅም በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ላለች ከፍተኛ ብዝኋነትና ገና ያልሻሩ ብዙ ብሶቶችና ቁርሾዎች ላላት ትልቅ አገር የበለጠ ነው፡፡ ለዚህ ይመስለኛል የኢሕአዴግ ባለሥልጣናት ዴሞክራሲ ለኢትዮጵያ የአማራጭ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው ሲሉ በተደጋጋሚ የሚሰሙት፡፡ ይህን ታዲያ በተግባር ማሳየት ያስፈልጋል፡፡

 ያለፉት 25 ዓመታት በዴሞክራሲ ግንባታ ዓይን

    ኢሕአዴግ የደርግን መንግሥት ጥሎ ሥልጣን ሲይዝ ዴሞክራሲያዊ ባህሪ ያለው ሥርዓት እንዲመሠርት የሚገፋፋ ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶች ነበሩ፡፡ አንደኛ በወቅቱ የቀዝቃዛው ጦርነት ማለቅና ከምዕራባውያን አሸናፊ ሆኖ መውጣት ጋር ተያይዞ ዴሞክራሲ እንደ መልካምና ሁሉም ሊተገብረው እንደሚገባ ነገር ይታይ ነበር፡፡ እንዲሁም ኢሕአዴግን በረሃ እያለ ይደግፉ የነበሩ (መንግሥት ከመሠረተም በኋላም ድጋፋቸውን የቀጠሉ) ምዕራባውያን አገሮች ኢትዮጵያዊ ውስጥ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲመሠረት ግፊት ያደርጉ ነበር፡፡ ሁለተኛ እንደ ኢትዮጵያ ባለች የብሔር፣ የሃይማኖትና ሌሎችም ብዝኋነቶች ባሏት አገር ለዚያውም ከረዥም የእርስ በእርስ ጦርነት በወጣች ማግሥትና ብዙ ሽምቅ ተዋጊዎች በተለያዩ የአገሪቱ ማዕዘናት በነበሩበት ወቅት አምባገነናዊ ሥርዓት መመሥረት ከባድ ነበር፡፡ ሦስተኛ ኢሕአዴግ ከስልሳዎቹ የተማሪዎች እንቅስቃሴ እንደተወለደ ማርክሲስት ድርጅት (ከነችግሮቹ) በሽምቅ ተዋግተው ሥልጣን ከያዙ ብዙ ኃይሎች አንፃር የተሻለ ዴሞክራሲዊ ሥርዓት የመጀመር ዕድል ነበረው፡፡ ከሕዝባዊ ወገንተኝነትና ከዴሞክራሲ እሴቶች ጋር የሚስማሙ አመለካቶች ነበሩት (ለምሳሌ የራስን ዕድል በራስ መወሰንና የብሔር፣ የሃይማኖት፣ ወዘተ እኩልነትን መጥቀስ ይቻላል)፡፡ ይህም ዴሞክራሲን (ሙሉ በሙሉ ባያምንበትም) እንደ አማራጭ እንዲያየው ሳያደርገው አልቀረም፡፡ ሌላው ኢሕአዴግ ይከተለው የነበረው (አሁንም እንደሚከተለው የሚናገርለት) የጋራ አመራር መርህ ነው፡፡ በዚህ መርህ መሠረት የኢሕአዴግ የበላይ መሪዎች ውሳኔዎችን በጋራ ስለሚያሳልፉና ስለሚያስፈጽሙ እያንዳንዳቸው (ሊቀመንበራቸውን ጨምሮ) ውስን ሥልጣን ነው የነበራቸው፡፡ ከዚህ የተነሳ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመጀመር በአንድ መሪ ከሚመራ ሽምቅ ተዋጊ አንፃር ለኢሕአዴግ የቀለለ እንደነበር መገመት ይቻላል፡፡ ከላይ የተጠቀሱቶች ምክንያት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እንዲጀመር አስተዋፅኦ ቢያደርጉም፣ የግንባታው ሒደት የሰመረ በማድረጉ በኩልም አዎንታዊ ሚና ነበራቸው ማለት አይደለም፡፡ በአንፃሩ ሒደቱን ከባድ የሚያደርጉ ምክንያቶችም ነበሩ፡፡

   በአጠቃላይ ኢትዮጵያ ለረዥም ጊዜ በድህነት፣ በጦርነትና በኋላ ቀርነት የኖረች አገር ስለሆነች ለዴሞክራሲ የተመቻቹ ሁኔታዎች አልነበሩም፡፡ በንጉሡ ጊዜ የነበሩ ለዴሞክራሲ ግንባታ እንደ ግብዓት ሊያገለግሉ የሚችሉ አንዳንድ ባህሎችና አሠራሮች በአብዮቱ ጊዜ ጠፍተዋል፡፡ በስፋት ይታዩ የነበሩ ባህላዊና አክራሪ (Conservative) አመለካከቶችን በመገዳደር ለዴሞክራሲ ግንባታ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ሊያደርጉ ይችሉ የነበሩ በተማሪዎች እንቅስቃሴ ጊዜ የታዩ ተራማጅ (Progressive) አመለካከቶችም፣ የደርግን ወደ ሥልጣን መውጣት ተከትሎ በነበረው መተላለቅ እንዳልነበሩ ሆነዋል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በደርግ የማያባራ ፕሮፓጋንዳ ምክንያት ቀላል የማይባል ከተሜ (በተለይ የተማረው ክፍል) ኢሕአዴግ ኢትዮጵያን ሊያጠፋ እንደመጣ ከፋፋይና ዘረኛ ኃይል ያይ ነበር፡፡ ኢሕአዴግ ያቀነቅናቸው የነበሩ ተራማጅ አመለካከቶችም በመሠረታዊ ደረጃ በተማሪዎች እንቅስቃሴ ይራመዱ ከነበሩ አመለካከቶች ጋር አንድ ዓይነት ቢሆኑም (ምንም እንኳን በአንዳንዶቹ ላይ ኢሕአዴግ ወደ ጫፍ የወጣ አመለካከት ቢኖረውም) እሱ እንደፈጠራቸውና ምንም መልካም ነገር እንደሌላቸው ተደርገው ይታዩ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳም ቁጥሩ ቀላል የማይባል ከተሜ የደርግን ውድቀት እንደ ራሱ ውድቀት አድርጎ የማየት አዝማሚያ ነበረው፡፡ የዚህ አስተሳሰብ ተፅዕኖ እስካሁን ቀጥሎ በተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ በጋዜጠኞች፣ በምሁራን፣ እንዲሁም ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ በተወለዱ ወጣቶች ሳይቀር ማየት የተለመደ ነው፡፡ በአንፃሩ ኢሕአዴግ ማርክሲስት አስተሳሰቡ ደርግን የሚያህል ግዙፍ ኃይል በጉልበት ከማሸነፉ ጋር ተደምሮ ከእሱ የተለየ ሐሳብ ያራመዱትን ሁሉ የመናቅና የማጣጣል አዝማሚያ ነበረው፡፡ የተቃወሙትን ሁሉ የተለያዩ ስሞችን በመስጠት (ለምሳሌ ትምክህተኞች፣ የድሮ ሥርዓት ናፋቂዎች፣ ወዘተ) ከመምጣቱ ጠላት ማፍራቱን ተያይዞት ነበር፡፡ አሁን ከዚህ በሽታው የተላቀቀ አይመስለኝም፡፡ ይህ አመለካከቱ በራሱ ለዴሞክራሲ ግንባታ የማይመች ሆኖ ሳለ፣ በተለይ በተቃራኒው ደግሞ የዴሞክራሲን ባህል ያላዳበረና በቀላሉ የሚገፋ ከተሜ ብዙ ከመሆኑ ጋር ተደምሮ ለዴሞክራሲ ግንባታ ጠንቅ ነበር ማለት ይቻላል፡፡

   በመጀመሪያዎቹ አሥር ዓመታት የነበረው የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሒደት እዚህም እዚያም ችግር ቢኖሩትም፣ ከላይ የተዘረዘሩትን ነባራዊ ሁኔታዎች ግምት ውስጥ አስገብተው ካዩት በአመዛኙ መልካም የሚባል ነበር፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአንፃራዊ ነፃነት ይንቀሳቀሱ ነበር፡፡ አብዛኞቹ የምክር ቤት አባላት ኢሕአዴጎችና አጋሮቹ ቢሆኑም የተወሰኑ ተቃዋሚዎችም የሚመረጡበት ዕድል ነበር፡፡ ብዙ የግል ጋዜጦች ነበሩ፣ፍርድ ቤቶች ቀላል የማይባል ነፃነት ነበራቸው፡፡ የመንግሥትና የገዢው ፓርቲ ግንኙነትም እንደ አሁኑ ሙሉ በሙሉ አልተደበላለቀም ነበር፡፡ ወዘተ፡፡

  በ1993 ዓ.ም. የኤርትራ ጦርነት ካለቀ በኋላ በሕወሓት ውስጥ ጀምሮ ከዚያ በሁሉም የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች የተሰራጨው የመከፋፈል ችግርና የተፈታበት መንገድ ገና በማደግ ላይ በነበሩ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ላይ ቀላል የማይባል ተፅዕኖ ፈጥሯል፡፡ ምክር ቤቶች የራሳቸውን አባላት መብት እንኳን ማስከበር የማይችሉ ጥርስ አልባ አንበሶች መሆናቸው በግልጽ ታየ፡፡ በማደግ ላይ የነበረው የፍርድ ቤቶች ነፃነትም ጥያቄ ውስጥ ገባ፡፡ ቢሆንም በመጀመሪያዎቹ አሥር ዓመታት የተመዘገቡት ድሎች ሙሉ በሙሉ አልተቀለበሱም ነበር፡፡ ይልቁንም ኢሕአዴግ የልማትና የዴሞክራሲ ግንባታ ሒደቴን ወደ ኋላ ይጎትቱ የነበሩ አባሎቼን በማስወገድ “ተሃድሶ አድርጌያለሁ” አለ፡፡ ብዙዎችም ከተሃድሶው መልካም ነገር ይወጣል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡ ከተሃድሶው ቀጥሎ በነበሩት ጥቂት ዓመታት የተወሰኑ የሚታዩ ለውጦችን ለማምጣት ይጥር የነበረው ኢሕአዴግ፣ በ1997 ምርጫ ዋዜማ ተሃድሶውን ከፍ ወዳለ ደረጃ ለማድረስ የቆረጠ በሚመስል መልኩ ነፃና ፉክክር የሞላበት ምርጫ ለማሄድ ቁርጠኝነቱን አሳየ፡፡ ኢትዮጵያም ያልጠበቀችውንና የማታውቀውን ሰላማዊ የሥልጣን ትንቅንቅ ለማየት በቃች፡፡ ዳሩ ምርጫው በጠንካራ ገለልተኛ ተቋማት ያልታጀበና በገዢው ፓርቲ ሕዝብ ይወደኛል ስለዚህ በምርጫም ማሸነፍ እችላለሁ ከሚል ግብዝነት የመነጨ “በጎ” ፈቃድ የተደረገ ስለነበረ የኋለ ኋላ መጨረሻው ሳያምር ቀርቷል፡፡ በ1997 ዓ.ም. ብዙዎች ተስፋ እንዳደረጉት ዴሞክራሲ የዳበረበት ዓመት መሆኑ ቀርቶ፣ ከዚያ በፊት የነበሩትም መልካም ለውጦች ወደ ኋላ መሄድ የጀመሩበት ዓመት ሆነ፡፡

  የዴሞክራሲ ተቋማት ባልጠነከሩበትና ትንሽም ብትሆን ሥልጣን ለተቃዋሚዎች ማካፈል ፈቃደኛና ዝግጁ ባልሆነበት ሁኔታ እንደዚያ ዓይነት ምርጫ እንዲካሄድ ማድረጉ በኢሕአዴግ በኩል ታሪካዊ ስህተት ነበር፡፡ ተቃዋሚዎች (በተለይ ቅንጅት) ሥልጣን “ወይ ዘንድሮ ወይ መቼም (Now or Never)” የሚል የከረረ አቋም መያዛቸውና በውስጣቸው የነበረው ኢዴሞክራሲያዊነት ለችግሩ መባባስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ በኢሕአዴግና በተቃዋሚዎች መካከል የነበረው ጥላቻና መናናቅም እንዲሁ፡፡ ከዚያ በኋላ ኢሕአዴግ ለዘለቄታው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት በማምጣት ለጊዜው ደግሞ ፖለቲካውን በመቆጣጠር ሥልጣን ላይ ለመቆየት መወሰኑን በግልጽ በሚያሳይ ሁኔታ ዕርምጃዎችን መውሰድ ጀመረ፡፡ ገና በማደግ ላይ የነበሩትን ዴሞክራሲያዊ ተቋማት አዳዲስ ሕጎችን በማውጣት ጭምር ማዳከሙን ተያያዘው፡፡ አብዛኞቹ የግል ጋዜጦች ተዘጉ፡፡ ፍርድ ቤቶች ገለልተኝነታቸው እጅግ ቀነሰ፣ ገና ያልዳበሩ የነበሩ የሲቪክ ተቋማት ይበልጥኑ ተዳከሙ፣ ወዘተ፡፡ መንግሥትና ገዢው ፓርቲም ከልክ በላይ ተደበላልቀው የመንግሥት ሥራና ጥቅማ ጥቅም የፖለቲካ ድጋፍ ማግኛ መሣሪያ ሆኑ፡፡ በዚህ ሁኔታ የተካሄደው የ2002 ምርጫ የፌደራል ምክር ቤቱን ከሁለት ወንበሮች ውጪ በኢሕአዴግ ቁጥጥር እንዲሆን አደረገ፡፡ ኢሕአዴግም የምርጫውን ውጤት ያልጠበቀው ይመስል (ምናልባትም አልጠበቀው ይሆናል) ኢትዮጵያ ለጊዜው የሚያስፈልጋት አንድ አውራ ፓርቲ ነው የሚል መላምታዊ ክርክር መደጋገም ጀመረ፡፡ ምክር ቤቱን ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ሁኔታ መቆጣጠሩ ለእሱም ለአገሪቱም መልካም እንዳልሆነ ተረድቶ በ2007 ዓ.ም. በሚካሄደው ምርጫ የፖለቲካ ምኅዳሩን በተወሰነ ደረጃ ከፈት ያደርዋል ተብሎ ቢጠበቅም ያ ሳይሆን ቀረ፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ የባሰ እየጠበበ ሄደ፡፡ የመንግሥትና የገዢው ፓርቲ ግንኙነትም የባሰውን ቅጥ አጣ፣ ሙስናና የአስተዳደር በደሎችም ተባባሱ፡፡ በምርጫውም ኢሕአዴግ 100% አሸናፊ ሆነ፡፡ አሁንም ውጤቱን ያልጠበቀው ወይም ያልተቀበለው ይመስል በ100% ያሸነፈው ተቃዋሚ ፓርቲዎች ስለደከሙና ስለበዙ ነው የሚሉ ምክንያችን መደርደር ጀመረ፡፡ ዳሩ ውጤቱ በመጠኑም ቢሆን ነፃና ፍትሐዊ ፉክክር ተደርጎበት ሕዝቡም በነፃነት መርጦ ቢሆን ኖሮ፣ ይህ ሁሉ ማስተባበያ አያስፈልግም ነበር፡፡

    ፖለቲካውን ለመቆጣጠር ብሎ የወሰዳቸው ፀረ-ዴሞክራሲያዊ ዕርምጃዎች የኋላ ኋላ እሱ ራሱ መቆጣጠር ወደማይችለው ባሕልና መረብ እየተቀየሩ ሙስና፣ ብልሹ አሠራርና የመልካም አስተዳደር ችግር ሥር እየሰደዱ ሄደው ሕዝቡን ክፉኛ ወደ ማማረር ብሎም የኢኮኖሚው ዕድገት ላይም ጥላቻውን ወደ ማጥላት ደረሱ፡፡ በመጨረሻም ለብዙ ሰዎች ሕይወት ማለፍና ከፍተኛ ዋጋ ያለው ንብረት መውደም ምክንያት ወደ ሆነውና የአገሪቱንም ህልውና ወደ ተፈታተነው ቀውስ አስገቡን፡፡

የመፍትሔ ሐሳቦች

በኢሕአዴግ መወሰድ ያለባቸው ዕርምጃዎች

   ኢሕአዴግ አስቀድሞ ማድረግ ያለበት ነገር የችግሩ መሠረታዊ መንስዔ የፖለቲካ ምኅዳሩ ከሚገባ በላይ መጥበቡ መሆኑን መቀበል ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ መጥበብ ችግር መሆኑን በተወሰነ ደረጃ የተቀበለ ቢመስልም እስካሁን ዋናው ትኩረቱ የመልም አስተዳደር ችግሮቸን መቅረፍ፣ ሙስናን መዋጋት፣ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ማሻሻልና የመሳሰሉ ተጓዳኝ ጉዳዮች ላይ ነው፡፡ እነዚህን የመልካም አስተዳደርና የኢኮኖሚ ችግሮችን መፍታት ጥሩ ቢሆንም በበሳል የዴሞክራሲያዊ ተቋማት ግንባታ ዕቅድና ተግባር ካልታገዙ መሠረታዊ ችግሩን ይፈታሉ ብዬ አላምንም፡፡ እነሱ ራሳቸው የመፈታት ዕድላቸው ጠባብ ነው የሚሆነው፡፡ ለሁሉም ችግር እንደ መንስዔ እየተጠቀሰ ያለው ሥልጣንን ለግል ጥቅም የማዋል ባህልም እንዲሁ የመጣ ሳይሆን፣ ከፍ ብሎ እንደተገለጸው እሱ ራሱ ፖለቲካውን ለመቆጣጠር ሲል በወሰዳቸው ኢዴሞክራሲያዊ ዕርምጃዎች የመጣ መሆኑን መቀበል አለበት፡፡

   ይህን ተቀብሎ ለዴሞክራሲ ግንባታ የራሱን ተራ መወጣት አለበት፡፡ እንዲያውም በሁለት ምክንያቶች የአንበሳውን ድርሻ መውሰድ ይጠበቅበታል፡፡ አንደኛ ገዢ ፓርቲ በመሆኑና የመንግሥትን ሥልጣን በመቆጣጠሩ በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ ተወዳዳሪ የሌለው አቅም ስላለው ነው፡፡ ሁለተኛ ዴሞክራሲ ቢዳብር እሱ ራሱ ተጠቃሚ ስለሚሆን ነው፡፡ እሱ በማይቆጣጠረውና ሊተነብየው በማይችል  የሕዝብ አመፅ ከሥልጣኑ ከሚወርድ፣ እሱ በመራው የዴሞክራሲ ሒደት ሥልጣኑን ቢያስረክብ ይሻለዋል፡፡ በዴሞክራሲያዊ መንገድ ከሥልጣን ቢወርድ ተመልሶ ወደ ሥልጣን የመመለስ ዕድል ይኖረዋል፡፡ በጉልበት ከወረደ ግን እንኳን እሱ አገሪቱ ራሷ ምን እንደሚገጥማት አይታወቅም፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ባለፉት 25 ዓመታት ያስመዘገበችው የፖለቲካና የኢኮኖሚ ድሎችም የበለጠ እንዲዳብሩ እንጂ እንዲቀለበሱ አይፈለግም ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህ ታዲያ አሁን ባለበት ሁኔታ ቀላል ይሆናል ማለት አይደለም፡፡ በመጀመሪያ የውስጥ ትግል አድርጎ የምር “በጥልቀት” መታደስና የዴሞክራሲ ባህሉንም ማዳበር አለበት፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችንም እንደ ጠላትና አፍራሽ ኃይሎች ማየቱን አቁሞ በዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው ሒደት ወሳኝ ሚና እንዳላቸው አካላት ማየት አለበት፡፡ ከእሱ የተለየ አመለካከት ላላቸው ወገኖች የተለያዩ ስሞችን በመስጠት የሐሳብ የበላይነት እንደማይገኝ አውቆ ሐሳብን በሐሳብና በሰለጠነ መንገድ የመሞገት ልምድም ማዳበር አለበት፡፡

   የችግሩ ዘለቄታዊ መፍትሔ ዴሞክራሲ ግንባታውን ማፋጠን መሆኑንና ለዚህም የመሪውን ሚና መጫወት እንዳለበት ከተቀበለ የሚቀጥለው ዕርምጃ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጨምሮ ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመነጋገርና በመመካከር፣ የፖለቲካ ምኅዳሩ የሚሰፋበትን መንገድ መፈላለግ ይሆናል፡፡ ለዚህ ታድያ የተለመደውን ሁሉን አውቃለሁ ዓይነት አስተሳሰቡን መተው አለበት፡፡ ለዴሞክራሲ ግንባታ ምሰሶ የሆኑት ተቋማት ላይም የሚታይ በቂ ለውጥ መምጣት አለበት፡፡ ለምሳሌ የሚኒስትሮች ምክር ቤቱን እንደ አዲስ እንዳዋቀረው ሁሉ የምርጫ ቦርዱንም ተዓማኒነቱንና ገለልተኝነቱን በሚያሻሽል ደረጃ እንደገና ቢያዋቅር፣ የፍርድ ቤቶችን ገለልተኝነትና አቅም የሚጨምሩ ዕርምጃዎችን ቢወስድ፣ የመንግሥት ሚዲያ ከተራ ፕሮፓጋንዳ ተቋምነት ተላቆ የተለያዩ ሐሳቦች የሚቀርቡበትና የተሻለ ተአማኒ እንዲሆን የሚያደርጉ ዕርምጃዎችን ቢወስድ፣ ወዘተ ጥሩ ነው፡፡ በዴሞክራሲ ተቋማት ላይ በቂ ለውጥ ማምጣት አለበት ሲባልም በአንዴ የዳበረ ዴሞክራሲ ባላቸው አገሮች ያሉት ተቋማት የደረሱበት ደረጃ ላይ ይድረሱ ማለት ሳይሆን፣ አሁን ካሉበት በጣም መሻልና ሕዝቡ መንግሥት የዴሞክራሲ ግንባታውን ሒደት ከምር ወደ ፊት ለማስኬድ እንደወሰነ የሚያሳምኑ መሆን አለባቸው ለማለት ነው፡፡ ኢሕአዴግ የዴሞክራሲ ተቋማቱ ላይ በበቂ መሥራት ከጀመረ የተራዘመ የተረጋ ሁኔታ የመፍጠር ዕድሉ ከፍተኛ ይሆንና የመልካም አስተዳደርና የኢኮኖሚ ችግሮቹን ለመፍታት የተመቻቸ ሁኔታ ይኖራል፡፡ የመልካም አስተዳደርና የኢኮኖሚ ችግሮቹ እየተቃለሉ በሄዱ ቁጥር ደግሞ ለረጅም ጊዜ በፍትሕ ዕጦት እየተሰቃየ የኖረው ሕዝብ ትዕግሥት ማጣቱ ይቀንስና የዴሞክራሲ ግንባታው ላይ የበለጠ ለመሥራት ጊዜ ይኖራል፡፡

በተቃዋሚ ፓርቲዎች መውሰድ ያለባቸው ዕርምጃዎች

    ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለዴሞክራሲ ግንባታ ያላቸው ሚና በጣም ከፍተኛ ነው፡፡ በአገሪቱ ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ እንዲሰፍንና ሕዝቡን በማስተባበር መንግሥት ላይ ጫና በመፍጠር የዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲጠናከሩ ማድረግ ይችላሉ፡፡ ለዚህም ይህንኑ ሚናቸውን መቀበልና ለዚያ በሚመጥን ደረጃ ራሳቸውን መቀየርና ማዘጋጀት አለባቸው፡፡ በዴሞክራሲ ግንባታው አዎንታዊ አስተዋፅኦ ለማድረግ በመጀመሪያ እነሱ ራሳቸው ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብና ባህል በውስጣቸው ማዳበር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ዴሞክራሲም በገዢው ፓርቲ በጎ ፈቃድ ወይም በኃያላን መንግሥታት ጫና ሳይሆን፣ በተቀናጀ የሕዝብ ትግል ብቻ እንደሚገነባም ከምር መቀበል አለባቸው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በውጭ አገር የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን (ዳያስፖራ) ጋር ያላቸው ግንኙነት ጥንቃቄ የተሞላበት መሆን ይኖርበታል፡፡ በተለይ ለዴሞክራሲ ግድ የሌላቸውና ኢሕአዴግ እንዲወርድላቸው ካላቸው ፅኑ ፍላጎት ብቻ ድጋፍ ለማድረግ ፈቃደኛ ከሆኑ ፅንፈኛ የዳያስፖራ አካላት በተቻለ መጠን ራሳቸውን ማግለል አለባቸው፡፡ ሁኔታዎች በፈቀዱት መንገድ በምርጫ ተወዳድሮ ሥልጣን ለመያዝ መሞከር ለዴሞክራሲ ግንባታው አስፈላጊና ተገቢ ነገር ቢሆንም፣ የእነሱ ዓላማ ግን ከዚያ የላቀና የዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱን በማጎልበት ረገድ አዎንታዊ ሚና መጫወት መሆን አለበት፡፡ ለዚህም በየአምስት ዓመቱ ለሚካሄደው ምርጫ ከሚያደርጉት የበለጠ የረዥም ጊዜ ዕቅድና ቁርጠኝነት ያስፈልጋቸዋል፡፡ በምርጫ ተወዳድረው ሥልጣን መያዝ ባይችሉ እንደ ሽንፈት ማየት የለባቸውም፡፡ ለወደፊት ፓርቲዎች በነፃነትና በእኩልነት ተወዳድረው ሥልጣን የሚይዙበት የዳበረ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ማድረግ ከቻሉ ተሳካላቸው ማለት ነው፡፡ በሌላ አባባል ለሚቀጥሉት ትውልድ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ለአገሪቱ በአጠቃላይ መስዋዕት ለመሆን ዝግጁ መሆን አለባቸው፡፡ አለበለዚያ በዴሞክራሲ ግንባታው ሒደት የሚኖራቸው አስተዋፅኦ አዎንታዊ መሆኑ ቀርቶ አፍራሽ የመሆን ዕድሉ ከፍ ያለ ይሆናል፡፡ አንዳንድ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ይህን እንደሚቀበሉና ወደ ፖለቲካው የገቡበት ምክንያትም የፖለቲካ ምኅዳሩ እንዲሰፋ የራሳቸውን አስተዋፅኦ ለማበርከት መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ይህ ታዲያ በተግባር መታየት አለበት፡፡

   ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግን ደግሞ በባህሪው መጥሮ እንደሆነና አፍራሽ ዓላማ ይዞ እንደሚንቀሳቀስ ኃይል አድርጎ ማየቱን ማቆም አለባቸው፡፡ ጥንካሬውና ስኬቶቹን ደግሞ ከቻሉ ዕውቅና መስጠት ካልቻሉ ደግሞ አለማጣጣል መልመድ አለባቸው፡፡ በአጠቃላይ ኢሕአዴግን ለዴሞክራሲ ግንባታ ትልቅ ተራ ሊኖረው እንደሚችል አካል ቆጥረው በቅንነት ከእሱ ጋር ለመሥራት መዘጋጀት አለባቸው፡፡ ብዙ ተቃዋሚ ፖለቲከኞችና ደጋፊዎቻቸው (ምሁራንን ጨምሮ) ኢሕአዴግ የዴሞክራሲ ግንባታው ሒደት አካል ሊሆን እንደማይችልና የዴሞክራሲ ግንባታውን ለመጀመር መጀመሪያ እሱ ከሥልጣን መውረድ እንዳለበት በእርግጠኝነት ሲናገሩ መስማት የተለመደ ነው፡፡ ይህን የተሳሳተ አመለካከት የሚያራምዱት በሁለት ምክንያቶች ይመስለኛል፡፡ አንድም ዴሞክራሲ የሚገነባው በመሪዎች በጎ ፈቃድ ሳይሆን በሕዝብ ትግል መሆኑን ከልብ ካለማመን የተነሳ ነው፡፡ አልያም ኢሕአዴግ ላይ ካላቸው ጥልቅ ጥላቻ የተነሳ በምንም ምክንያት ሥልጣን ላይ እንዲቆይ ስለማይፈልጉ ነው፡፡ አንድ ትግል ዴሞክራሲን በመገንባት ረገድ ስኬታማ ለመሆን ዋና ዓላማው የሕዝቡን መብትና ጥቅም ማስከበርና ለዚያም ዋስትና የሚሆኑትን ዴሞክራሲያዊ ተቋማት መገንባት መሆን አለበት፡፡ ይህን መርህ መሠረት ያደረገ ትግል ደግሞ በቂ የሕዝብ ድጋፍና ብቃት ያለው አመራር እስካገኘ ድረስ ስኬታማ መሆኑ አይቀርም፡፡ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚገነባው ኢሕአዴግ ሥልጣን ላይ እያለ ነው ወይስ ከወረደ በኋላ ነው የሚለው ጥያቄ፣ በሁኔታዎች የሚወሰንና በሁለተኛ ደረጃ የሚታይ ጉዳይ ነው፡፡ እርግጥ ነው ኢሕአዴግ የለውጡ አካል ቢሆን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱ ባጠረ ጊዜና ባነሰ ኪሳራ ሊመሠረት ይችላል፡፡ ከወዲሁ ኢሕአዴግ የለውጡ ሒደት አካል ሊሆን ስለማይችል፣ የትግሉ የመጀመሪያ ዓላማ ኢሕአዴግን ከሥልጣን ማውረድ መሆን አለበት ከተባለ ግን ትግሉ ኢሕአዴግን ከሥልጣን በማውረዱ በኩል ስኬታማ ቢሆን እንኳን ዴሞክራሲ ሊገነባ አይችልም፡፡ እንደገና ሌላ ትግል መጀመር ሊኖርብን ነው ማለት ነው፡፡ አንድን ቡድን ከሥልጣን ለማውረድ (ወይም ወደ ሥልጣን ለማውጣት) የሚደረግ ትግል ከበጎ ፍላጎት ቢነሳ እንኳን በባህሪው ኢዴሞክራሲያዊ ስለሚሆን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ሊገነባ አይችልም፡፡

ባለፈው ዓመት ከተካሄዱት ተቃውሞዎች መወሰድ ያለባቸው ትምህርቶች

   ባለፈው ዓመት በተለያዩ አካባቢዎች የተነሱት ተቃውሞዎች የተለያዩ መነሻዎች ቢኖሯቸውም በመሠረታዊ ደረጃ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ ሁሉም ተቃውሞዎች የተከሰቱት በሕዝቡ መሀል ሥር የሰደዱ ቅሬታዎች በመኖራቸውና ቅሬታዎቹንም በመደበኛ መንገድ ለማቅረብ በሩ በጣም ስለጠበበ ነው፡፡ ተቃውሞዎቹ ለዴሞክራሲ ግንባታ መሠረት የመሆን ዕድል የነበራቸው ቢሆኑም፣ የኋላ ኋላ ወደ ብጥብጥና ሥርዓት አልበኝነት እያመዘኑ ሄደው ለብዙ ሰዎች ሕይወት መጥፋትና ለብዙ ንብረት መውደም ምክንያት ከመሆን አልፈው፣ የአገሪቱን ህልውና ወደ መፈታተን ደርሰው ነበር፡፡ ተቃውሞዎቹ ሙሉ በሙሉ ከሽፈዋል ባይባልም በዴሞክራሲ ግንባታ ዙሪያ ሊያመጡ ይችሉ ከነበሩት ውጤትና ካስከተሉት ኪሳራ አንፃር ስኬታማ ነበሩ ለማለት ያስቸግራል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ተቃውሞዎች እንዴትና መቼ እንደሚነሱ መገመት አስቸጋሪ የሆነውን ያህል፣ እንዴት እንደሚያልቁም ማወቅ ወይም መቆጣጠር ከባድ ነው፡፡ ቢሆንም የነበሩ ስህተቶችን ለይቶ አውጥቶ መነጋገርና ትምህርት መውሰድ ተገቢ ነው፡፡ ተቃውሞዎቹ በጥንቃቄና በጥበብ የሚመራቸው የተደራጀ አካል ስላልነበረና ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ቶሎ ብለው ዕርምጃ መውሰድ ስላልቻሉ ፅንፈኛና ነውጠኛ የሆኑት የዳያስፖራ ኃይሎች ሰለባ ለመሆን በቅተዋል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከዚህ ትልቅ ትምህርት መውሰድ ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ ተቃውሞዎቹ ጥሩ መሪ በማጣታቸውና በአገሪቱ የዳበረ ዴሞክራሲያዊ ባህል ባለመኖሩ መጨረሻቸው እንዳያምር ያደረጉ ኢዴሞክራሲያዊ የሆኑ አካሄዶች ታይቶባቸው ነበር፡፡ የተወሰኑትን እንይ፡፡

  1. በተለያዩ አካባቢዎች ከታዩት የተቃውሞ መንገዶች መካከል የቤት ውስጥ መቀመጥና የንግድ ቤቶችን መዝጋት አድማዎች ይገኙበታል፡፡ እነዚህ የተቃውሞ መንገዶች በራሳቸው ችግር ባይኖራቸውም የተቃውሞውን ጥሪ ባልተቀበሉ (ማለትም ቤት ባለመቀመጡ ወይም የንግድ ቤታቸውን ባልዘጉ) ሰዎች ላይ ይወስድ የነበረው የማሸማቀቅና የድብደባ ድርጊት ተገቢ አይደለም፡፡ ለዴሞክራሲ ቁልፍ የሆነውን የግለሰብ ነፃነት የሚፃረር አደገኛ አካሄድ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት የተቃውሞ ጥሪ ሲደረግ በተለያዩ ምክንያቶች የማይሳተፉ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ የተቃውሞው አስተባባሪዎች ወይም ተሳታፊዎች በቂ ሰው በአድማው አልተሳተፈም ብለው ካመኑ ደግሞ ያልተሳተፉ ሰዎችን በሐሳብ አሳምነው የአድማው አካል እንዲሆኑ መጣር እንጂ፣ ጉልበት መጠቀም ትክክል አይደለም ለስኬትም አያበቃም፡፡ እንዲያውም የተቃውሞውን ትክክለኝነት ጥያቄ ውስጥ በማስገባት ሊያዳክመው ይችላል፡፡
  2. ተቃውሞ በተካሄደባቸው አካባቢዎች በተለይ በኦሮሚያ ክልል ፋብሪካዎችና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችን ጨምሮ ከፍተኛ ዋጋ ያለው ንብረት ወድሟል፡፡ እንደዚህ ባለ ተቃውሞ አልፎ አልፎ የንብረት መውደም ማጋጠሙ የተጠበቀ ቢሆንም፣ የውድመቱ መጠንና አኳኋን ባጋጣሚ የተከሰተ ሳይሆን እንደ ተቃውሞ ስትራቴጂ የተወሰደ ነበር ለማለት ያስደፍራል፡፡ ንብረት የማውደሙ ተግባርም ተቃውሞውን ስኬታማ በማድረግ በኩል በሁለት መንገድ አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ በማኅበራዊ ሚዲያ በሰፊው ይነገር ነበር፡፡ አንደኛ የልማት ተቋማት ሲቃጠሉ ሥራ አጥነት ይጨምራል፣አጠቃላይ ኢኮኖሚውም ይዳከማል፣ ከዚህ የተነሳም ሕዝቡ የባሰ ይማረርና ተቃውሞውን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ሁለተኛ ኢንቨስትመንትና ኢኮኖሚው ይዳከማል፣ መንግሥት ከመሬት ሽያጭና ከቀረጥ የሚያገኘውም ገቢም ይቀንሳል፡፡ ስለዚህ መንግሥት የሕዝቡን ተቃውሞ የመቀልበስ አቅሙ ይዳከማል፡፡ ሁለቱም መላ ምቶች የተሳሳቱ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ የዳበረ ዴሞክራሲ እስከሌለ ድረስ ለሕዝብ ተቃውሞ የሚሆን ምክንያት እንኳን እንደ ኢትዮጵያ ባለች ሥር የሰደደ ድህነት ባለባት አገርና በተሻለ የኢኮኖሚ ዕድገት ደረጃ በሚገኙ አገሮችም ይኖራል፡፡ የተቃውሞው ጥንካሬ የሚለካውም በዋናነት በሕዝቡ የመደራጀት አቅምና በመሪዎቹ ብቃት ነው፡፡ በአንፃሩ ከልክ ያለፈ ድህነት ለዴሞክራሲ ግንባታ እንደማይጠቅም ይታመናል፡፡ መንግሥት ገቢው ሲቀንስ ተቃውሞዎቹን የመቀልበስ አቅሙም አብሮ ይቀንሳል የሚለውም ብዙ ውኃ የሚቋጥር አይደለም፡፡ ሀብታም መንግሥት ሳይሆኑ ጨቋኝ ሆነው ለረዥም ጊዜ መቆየት እንደሚቻል ለመረዳት ሩቅ ሳንሄድ የአገራችንን ቅርብ ጊዜ ታሪክ ማየቱ በቂ ይመስለኛል፡፡ ይልቁንም እንደዚህ ዓይነት ተግባር ተቃውሞውን ወደ ለየለት ሥርዓተ አልበኝነትና የእርስ በእርስ ግጭት በመቀየር የአገሪቱን ህልውና ሊፈታተን እንደሚችል በተግባር ታይቷል፡፡ የአደጋው ጊዜ አዋጁን ተከትሎ አገሪቱ ላይ ተደቅኖ የነበረው የህልውና አደጋ (ለጊዜውም ቢሆን) ቢወገድም ተቃውሞዎቹ በዴሞክራሲ ግንባታ ረገድ ሊኖራቸው ይችል የነበረው አስተዋፅኦ እንደቀነሰ ግልጽ ነው፡፡ ለወደፊት በሚደረጉ የዴሞክራሲ ግንባታ ትግሎች ላይም መጥፎ ጠባሳ ማሳረፉ አይቀርም፡፡
  3. በአንዳንድ አካባቢዎች የተደረጉ ተቃውሞዎች የዘረኝነት አዝማሚያ ነበራቸው፡፡ ይህ ችግር በተለይ በአማራ ክልል በተደረጉ ተቃውሞዎች የታየ ሲሆን፣ ዘረኝነቱ ያነጣጠረውም በትግራይ ሕዝብ ላይ ነበር፡፡ በትግሬዎች ላይ ያለው ጥላቻ በተቃውሞው ጊዜ ጎልቶ ይውጣ እንጂ ከዚያ በፊትም በስፋት ይንፀባረቅ ነበር፡፡ ጥላቻውም የተፈጠረው በሁለት ተያያዥ ምክንያቶች ነው (የለየለት ዘረኝነትን ትተን ማለት ነው)፡፡ አንደኛው ትግሬዎች የመንግሥትን ሥልጣን ተቆጣጥረዋል የሚል ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ በዚህ መንግሥት ትግሬዎች ከሌሎች ብሔሮች አባላት የበለጠ ተጠቃሚ ናቸው የሚለው ነው፡፡ እነዚህ አመለካከቶች በተወሰነ ደረጃም ቢሆን እውነተኛ መሠረት አላቸው ቢባል እንኳን፣ አንድን ሕዝብ ለመጥላትና ዒላማ ለማድረግ በቂ ምክንያት ሊሆኑ አይችሉም፡፡ መታገል ያለብንም ኢፍትሕዊነቱን እንጂ ግለሰቦቹን ወይም ሕዝቡን አይደለም፡፡ እነዚህ ሁለት ምክንያቶች ከመጠን በላይ ተጋነው የአመፅ መቀስቀሻ መሣሪያ ሆነው ነበር፡፡ በዚህም ሥልጣኑም ጥቅሙም ላይ የሌሉበት ብዙ ትግሬዎች ሰለባ ሆነዋል፡፡

    አገሪቱ በፌደራልም በክልልም ደረጃ ሙሉ በሙሉ በትግሬዎች የምትተዳደር ለማስመሰል ብዙ ፕሮፓጋንዳ ተካሂዷል፡፡ መንግሥት ተቃውሞዎቹን ለመቆጣጠር ያሰማራቸው የፀጥታ ኃይሎችም ሁሉም ትግሬዎች እንደሆኑ ለማሳመን ብዙ ተጥሯል፡፡ የፀጥታ ኃይሎች ተቃዋሚዎች ላይ ላደረሱት ጉዳትም በብዛት ተጠያቂ ሲደረግ የነበረው በትግሬዎቹ ብቻ እንደተዋቀረ የሚነገርለት መከረኛው የአግአዚ ክፍለ ጦር ነው፡፡ የትግሬዎች በሥርዓቱ ተጠቃሚ መሆንም ከምንም ጊዜ በላይ ተራግቧል፡፡ ለወትሮው በደፈናው ይወራ የነበረው በ “መረጃ"ተደግፎ መቅረበ ጀመረ፣ ትግሬ በመሆናቸው ብቻ “የከበሩ” ስም ዝርዝር ወጣ፣ የመንግሥት ንብረትም ወደ ትግራይ እየተወሰደ እንደሆነ ተነገረ፡፡ የዚህ ሁሉ ፕሮፓጋንዳ ዓላማ በመንግሥት ስም ሌሎች ብሔሮች ላይ በደል እየፈጸሙ ያሉት ትግሬዎች ሲሆኑ፣ ምክንያቱም በዚህ መንግሥት ያላቸውን የበላይነትና ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ ነው የሚለውን መልዕክት ማስረፅ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ማንነትን መሠረት ያደረገ ቅስቀሳ ስኬታማ የመሆን ዕድሉ በአደገኛ ሁኔታ ከፍተኛ ነው፡፡ ምክንያቱም ተበድያለሁ ብሎ ያሰበው አካል ለጊዜውም ቢሆን ለቅስቀሳው በተመረጠው ማንነቱ (ማለትም ብሔር) ብቻ እንዲያስብና ሌሎች ማንነቶችን (ኢትዮጵያዊነት፣ ሰብዓዊነት፣ ሃይማኖት፣ የአገር ልጅነት፣ ጓደኝነት፣ ወዘተ) እንዲረሳ ስለሚያደርግ ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ብዙ በመንግሥት አካላት በደል የደረሰበት ኢትዮጵያዊ በደል የደረሰብኝ በብሔሬ (አማራ በመሆኔ፣ ኦሮሞ በመሆኔ፣ ወዘተ) ነው፡፡ በደል ያደረሰብኝም ትግሬ ነው ብሎ ሊያስብና ለበቀልም ሊነሳሳ ይችላል፡፡ እንደዚህ ዓይነት ቅስቀሳ አገሪቱን ወደ ለየለት የእርስ በእርስ ግጭትና ደም መፋሰስ ሊከት የሚችል አደገኛ አካሄድ ነው፡፡ ከዚያ በመለስም ለዴሞክራሲ ግንባታ ያለው አሉታዊ ተፅዕኖ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ማንኛውም አገር ወዳድና በዴሞክራሲ አምናለሁ የሚል ወገን ሊቃወመው ይገባል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በዚህ ጉዳይ በአመዛኙ ዝምታን መምረጣቸው እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡

     ከዚህ ጋር በተያያዘ ድርጊቱን ወደ ማስተባበል የተጠጉ አንዳንድ ንግግሮች ይሰሙ ነበር፡፡ ለምሳሌ ይህ ችግር የተከሰተው ኢሕአዴግ ለ25 ዓመታት ሲከተለው በነበረው ከፋይ ፖሊሲ ምክንያት መሆኑ በስፋት ይነገር ነበር፡፡ ብዙ ፖለቲከኞችና ተንታኞችም “ኢሕአዴግ የዘራውን ማጨድ ጀመረ” ሲሉ ተሰምተዋል፡፡ ይህ በጣም ስህተት ነው፡፡ እርግጥ ነው የኢሕአዴግ ፖሊሲ ለችግሩ አስተዋፅኦ አድርጎ ሊሆን ይችላል፡፡ ሆኖም እንደዚህ ዓይነት ነገር ሲከሰት መጀመሪያ መደረግ ያለበት ነገር ድርጊቱን ማውገዝ ነው፡፡ ነገሩ እንዴት ሊከሰት ቻለ የሚለው ጉዳይ ሁኔታዎች ከተረጋጉ በኋላ የሚነሳ ይሆናል፡፡ አንዳንድ ወገኖች በተቃውሞዎቹ የታዩትን መጥፎ አዝማሚያዎች መኮነን ኢሕአዴግን እንደ መደገፍ ስለሚቆጥሩት ወይም የኢሕአዴግ ደጋፊዎች እንዳያስመስላቸው በመፍራት ዝምታን ይመርጣሉ፡፡ ድርጊቱን ባይደግፉትም አመፁ እንዲጠናከር አድርጎ የሥርዓት ለውጥ ሊያመጣ እስከቻለ ድረስ ምን ቸገረኝ ብለው ዝም ያሉም አይጠፉም፡፡ ሌላው በስፋት ይነገር የነበረው ዒላማ የተደረጉት ግለሰቦች ትግሬዎች በመሆናቸው ሳይሆን፣ ከመንግሥት ጋር ንክኪ ስላላቸው ነው የሚለው ነው፡፡ ይህ አባባል በመርህ ደረጃ ትክክል ነው ቢባል እንኳን ሊተገበር እንደማይችልና ዞሮ ዞሮ ማንኛውንም ትግሬ ዒላማ ከማድረግ ብዙም እንደማይለይ ግልጽ ነው፡፡ ዳሩ በመርህ ደረጃም ትክክል አይደለም፡፡ በማንኛውም ግለሰብ በምንም ምክንያት የሚወሰድ የጥቃት ዕርምጃ የዴሞክራሲ ትግሉን ይጎዳል እንጂ አይጠቅምም፡፡    

   ማጠቃለያ

    ባለፈው ዓመት በተለያዩ የአገራችን ክፍሎች የሕዝብ ተቃውሞዎች ተቀስቅሰው ነበር፡፡ ተቃውሞዎቹ የተነሱት በቂ ምክንያት ስለ ነበራቸው ነው፡፡ በመጀመሪያም ሰላማዊ ነበሩ፡፡ የኋላ ኋላ ግን ወደ አመፅና ሥርዓት አልበኝነት እየተቀየሩ ሄዱ፡፡ የብዙ ሰዎች ሕይወት ጠፍቷል፡፡ ከፍተኛ ዋጋ ያለው ንብረትም ወድሟል፡፡ በመጨረሻም የአገሪቱ ህልውና አደጋ ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ መንግሥት ያወጀውን ጊዜያዊ አስቸኳይ አዋጅ ተከትሎ ነገሮች የተረጋጉ ቢመስሉም ችግሩ ከመሠረቱ ተፈቷል ማለት አይደለም፡፡ አገሪቱን ለዚህ ቀውስ የዳረጋት ዋናው ምክንያት የዴሞክራሲ ግንባታው ወደ ፊት በመሄድ ፈንታ የኋልዮሽ መሄዱ ነው፡፡ መንግሥት ይህን በተወሰነ ደረጃ የተረዳ ቢመስልም፣ ዋናው የመፍትሔ ትኩረቱ ግን የመልካም አስተዳደርና የኢኮኖሚ ችግሮች ላይ ይመስላል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለመፍታት መሞከር መጥፎ ባይሆንም ችግሩ ከመሠረቱ እንዲፈታ ከፈለገ ግን መፍትሔው የዴሞክራሲ ግንባታውን በበቂ ፍጥነት ማስኬድ መሆኑን መቀበልና የበኩሉን መወጣት አለበት፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ከእነሱ የሚጠበቀውን ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከተደረጉት ተቃውሞዎች እንደ ሕዝብ ብዙ ትምህርት መውሰድ አለብን፡፡ በተለይ የታዩት አንዳንድ ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አዝማሚያዎች ዳግም እንዳይታዩ ሁሉም የበኩሉን ማበርከት ይኖርበታል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው  berhemek@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡      

 

Standard (Image)

ስብሰባዎች የሥራ መቀስቀሻና ማበልፀጊያ እንጂ በራሳቸው ሥራ አይደሉም

$
0
0

በደረጀ ተክሌ ወልደማርያም

መቼ እንደተጀመረ ወቅቱ በትክክል ባይታወቅም የሰው ልጅ በማንኛውም የሕይወት እርከን ላይ ተሰባስቦ የመመካከር ጥቅሙን ከመገንዘቡ የተነሳ፣ ለዘመናት በውይይት አማካይነት በሚወሰኑ ውሳኔዎች ላይ በመመርኮዝ የጋራ ተግባራትን ሲያቀላጥፍ ቆይቷል፡፡ ሥልጣኔ ሲስፋፋም ሁለንተናዊ ጉዳዮችን በስብሰባ ተወያይቶ መወሰን የዘመናዊነት መገለጫ እየሆነ በመምጣቱ የቤተሰብ፣ የማኅበረሰብ፣ የድርጅት (መሥሪያ ቤቶች) የአኅጉርና የዓለም አቀፍ ድርጅቶች የወደፊት አቅጣጫዎች ሁሉ በስብሰባ ውሳኔ ሲያገኙ ይታያሉ፡፡

በአገራችንም ከጥንት ጀምሮ በሸንጎ የሚወሰኑ ጉዳዮች እያደር ዘመናዊ ሥርዓት ተቀርፆላቸው፣ ሕግ ተደንግጎላቸው አብዛኛዎቹ የአገርና የመንግሥት ጉዳዮች በጉባዔ ሲወሰኑ ረዥም ዘመናት አስቆጥረዋል፡፡ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ ያደረግኳቸው አገልግሎት ሰጪ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችም አብዛኛው ተግባራቸው ከተገልጋዩ ማኅበረሰብ ጋር የተቆራኘ በመሆኑ ስብሰባዎች እንደሚበዙባቸው መገመት ይቻላል፡፡ ይሁን እንጂ ስብሰባዎች ሰዓትና ቀን ተገድቦላቸው ተገልጋዩን ማኅበረሰብ ሊጎዱ በማይችሉበት ደረጃ ታቅደው በሕግና በሥርዓት ሊመሩ ውጤታማነታቸውም እንዲሁ ሊረጋገጥ ይገባል፡፡

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን አገልግሎት ሰጪ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ካለ ምንም ቅድመ ማስጠንቀቂያ ለቀናት ቢሮዋቸውን እየዘጉ ሠራተኞቻቸውን ሰብስበው ለጉዳይ የመጣውን ተገልጋይ ስብሰባ ላይ ናቸው እያሉ መመለስ እየተለመደ መጥቷል፡፡ ይሁን እንጂ ስብሰባዎቹ በከፊል ዓላማቸውን ሲያሳኩ ካለመታየታቸውም በላይ፣ እንዲያውም የሥራ ሰዓትን የሚሻሙ ባለ ጉዳይን የሚያጉላሉ ሆነው ተገኝተዋል፡፡ ስብሰባዎቹ ውጤት ላለማምጣታቸው ማረጋገጫው ደግሞ መደጋገማቸው ብቻም ሳይሆን፣ ርዕሳቸው ያው በጎ ምላሽ ያላገኘው መልካም አስተዳደር መሆኑ ነው፡፡ በመሆኑም ስብሰባዎች ውጤት የማያስገኙ ከሆነ ምክንያታቸውን መመዘኑና መፍትሔውን ማመላከቱ የማንኛውም ዜጋ ድርሻ በመሆኑ፣ በቅድሚያ ቢሮዎቻችንን ያጨናነቁትን የስብሰባ ዓይነቶች መለየት ያስፈልጋል ብዬ አስባለሁ፡፡

ለስብሰባ ዓይነቶች የሚሰጡት ምላሾች እንደየሰው አመለካከት የሚለያዩ ቢሆኑም፣ በልምድ ካየሁት በየትኛውም የመንግሥት መሥሪያ ቤት የሚካሄድ ስብሰባ ከዚህ በታች ከተዘረዘሩት ዓይነቶች ውጪ አይሆንም ማለት እችላለሁ፡፡

የመጀመርያውመሥሪያ ቤቱ በሕግ በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት የረዥም ጊዜ ዓላማውንም ሆነ የየዕለት ተግባሩን በጋራ በመመካከር፣ የተለያዩ ሐሳቦችን በየእርከኑ ከተቀመጡ የመሥሪያ ቤቱ አባላት በማሰባሰብ፣ የባለ ድርሻ አካላትን በበለጠ የሚጠቅመውን፣ ለቀልጣፋ አፈጻጸም የተመቸውንና ዘላቂነት ያለውን በመምረጥ የጋራ ውሳኔ ላይ ለመድረስና በታሪክም ሆነ በሕግ የመሥሪያ ቤቱን ገጽታ የሚያስጠብቅ፣ ምንጊዜም እየዳበረ የሚሄድ ተግባርን ለማከናወን የሚደረግ የመመካከሪያ መድረክ ነው፡፡

ሁለተኛውደግሞ የየመሥሪያ ቤቱ ኃላፊዎች በሕግም ሆነ በመዋቅር በተሰጣቸው ኃላፊነት በራሳቸው ሥልጣን መወሰን የሚገባቸውን ጉዳዮች ወደ ጎን በመተው፣ ውሳኔዎቻቸው በተናጠል ከተሰጡ ሊያስከትሉ የሚችሉትን ውጤቶች በመፍራት፣ እንዲሁም በሥርዓቱም ሆነ በበላይ አለቆቻቸው ላይ እምነት ሲያጡ ‹‹ጎመን በጤና›› በሚል የፍርኃት ዋሻ በመጠለል ከሥጋት በመነጨ ለትልቁም ለትንሹም፣ ለሚያስፈልገውም ሆነ ለማያስፈልገው የሚጠሩት የመጠለያ የምክክር ሥርዓት ነው፡፡

ሦስተኛውአለቃነት የሚገለጸው በሰብሳቢነት ብቻ የሚመስላቸው፣ በሰበሰቡና በአነጋገሩ መጠን ከተግባራቸው ዋና ዋናውን የተወጡ የሚመስላቸው፣ በየዋህነት የሠራተኛውን የየዕለት የልብ ትርታ ቀርበው የሚያዳምጡ የሚመስላቸውና በተንኮልም የሠራተኛውን የየዕለት እንቅስቃሴ የመቆጣጠርያ መስመር የዘረጉ የሚመስላቸው ኃላፊዎች የሚጠሩት የማስመሰያ የስብሰባ ዓይነት ነው፡፡

በአገራችን ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ የትኞቹ የስብሰባ ዓይነቶች አመዝነው ይታያሉ የሚለውን ጥያቄ ለአንባቢያን በመተው፣ ዛሬ በየመሥሪያ ቤቱ ያለውን የስብሰባ ሁኔታ በዝርዝር እንመልከት፡፡

ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ‹ስብሰባ ላይ ናቸው› የሚለው ዓረፍተ ነገር ከተራ መልዕክትነት አልፎ የሥራ መለኪያና ሠራተኝነትን ማረጋገጫ፣ በሌላ በኩል ደግሞ የሥራ መሸሺያና የአለቃ መደበቂያ በመሆን እየተፈረጀ ነው፡፡ ትርጉሙ ላይ የትኛው እውነት እንደሆነ ለማወቅ ቢያከራክርም ግን፣ አብዛኛው የኅብረተሰብ አካል በአንድ ዓብይ ጉዳይ ይስማማል ብዬ አምናለሁ፡፡ ይኼም እያደገ የመጣውን አሰልቺ የስብሰባ ባህርይ፡፡ የስብሰባን አሰልቺነት በምሬት የሚገልጸው ጉዳዩን ለመፈጸም መጥቶ ቢሮ ለቢሮ ሲዞር ውሎ፣ ተፈላጊው የቢሮ ሠራተኛ ስብሰባ ላይ መሆኑ በተደጋጋሚ ቀናት የተነገረውና መልካም አስተዳደር የተነፈገው ባለ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ስብሰባውን የተካፈለው የቢሮ ሠራተኛም ጭምር ነው፡፡

የቢሮው ሠራተኛ ባለ ጉዳዩን ሊያገለግል በሚገባው የመልካም አስተዳደር ይዞታ ላይ ባለመገኘቱ ተገልጋይ እየተጎዳ ነው በሚባልበት በአሁኑ ጊዜ፣ የቢሮው ሠራተኛ ዘመኑን በማይመጥን የስብሰባ ሥርዓት እየተጎሳቆለ መሆኑም የአደባባይ ሚስጥር ሆኗል፡፡ ዛሬ ዛሬ ሠራተኞች እዚያው በግቢያቸው ውስጥ ለስብሰባ ሲጠሩ ፊታቸውን ‹‹ቅጭም›› አድርገው ሲሄዱ የሚስተዋሉ ሲሆን፣ ሲመለሱ ደግሞ የመታከት ምልክት ያሳያሉ፡፡ አንዳንዶቹም በስብሰባው ወቅት የተንጠለጠለ የግል ሐሳባቸውን በማሰላሰል ወይም እንደ ዝንባሌያቸው የዶሮም ሆነ የኮንዶሚኒየም ሥዕል በመሣል ጊዜውን ይጠቀሙበታል፡፡

ስብሰባዎች ለምን አሰልቺ ይሆናሉ?

1ኛ. የስብሰባው አጀንዳ ግልጽ አለመሆን፣ለስብሰባው የታደሙት ሠራተኞች የስብሰባውን አጀንዳ ከስብሰባው በፊት ቀድመው እንዲያውቁትና እንዲዘጋጁበት ስለማይደረግ፣ ውይይቱ በዚያው ስብሰባ ላይ በድንገት በሚፈነጠቁ ሐሳቦችና በአለቆች አጀንዳዎች ላይ ብቻ የሚወሰን ይሆናል፡፡ ይኼም ስብሰባውን ጥልቀት እንዳይኖረው ያደርግና ተደጋጋሚ ሐሳቦች ብቻ እንዲዘዋወሩ ስለሚያደርግ፣ ውይይቱ ቀድሞውኑም ‹በተግባቡበት ጉዳይ ላይ እንዲግባቡ› ከማድረግ በስተቀር አንዳችም አዲስ ነገር ሲያስጨብጥ አይስተዋልም፡፡

2ኛ. የስብሰባው ሰዓትና አጀንዳው አለመጣጣም፣ለስብሰባው የተያዘው እያንዳንዱ አጀንዳ ምን ያህል ሰዓት ሊወስድ እንደሚችል በቅድሚያ ስለማይተመን፣ በአንዱ አጀንዳ ላይ ያለቀውን ሰዓት ለማካካስ ሌሎችን አጀንዳዎች በመጫን ወይም በማዋከብ ያልተገቡ ውሳኔዎች እንዲያልፉ ስለሚደረግ፣ የስብሰባን አስፈላጊነት በአሉታዊ ጎኑ ይገልጸዋል፡፡

3ኛ. በስብሰባው ላይ የስብሰባው አጀንዳ በቀጥታ የማይመለከታቸው ሠራተኞች መገኘት፣በስብሰባ ላይ እንዲገኙ በመደረጋቸው ምክንያት ብቻ ተፈላጊነታቸው የተረጋገጠ የሚመስላቸው አንዳንድ ታዳሚዎች፣ በማይመለከታቸውና በማያውቁት ጉዳይ ላይ ብዙም የማይገናኝ ረጅም ጊዜን በመወሰድ ሐሳብ ሲሰጡ ይታያሉ፡፡ ይኼ ደግሞ የስብሰባውን ጊዜ ከማራዘሙም በላይ በጉዳዩ ላይ እውቀትም ልምድም ያላቸውን ሰዎች ጊዜ በመሻማት፣ የአዋቂ ሰሚ ከማድረግም በላይ የአጀንዳውን ውሳኔም ሲያዛባ ይታያል፡፡

4ኛ. የስብሰባ ሰዓት አለመከበር፣አብዛኛው ስብሰባ በታቀደለት ሰዓት አይጀመርም፡፡ አብዛኛው ሠራተኛ በሰዓቱ ተገኝቶ ሌሎችን ከመጠበቅ ይልቅ ሌሎች ጨርሰው አዳራሽ ገብተው ከተጠናቀቁ በኋላ መድረሱን ይመርጣል፡፡ ይኼ ደግሞ ቀድመው የደረሱትን በጊዜ መቅጣት ብቻ ሳይሆን፣ ለሌላ ጊዜ በሰዓቱ እንዳይገኙ ይገፋፋል፡፡ የስብሰባውን መጨረሻ ሰዓትም አዝጋሚ ያደርገዋል፡፡

5ኛ. ሐሳብን በአጭሩ የመግለጽ አቅም ማጣት፣በእያንዳንዱ አጀንዳ ላይ ካልተናገሩ ማለፍ የማይችሉ ታዳሚዎች እንዳሉ ሁሉ፣ ለእያንዳንዱ አጀንዳ የአገሪቱን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ይዞታ አስደግፈው ካልተናገሩ ሰው የገባው የማይመስላቸው ወይም ደግሞ የቡድንም ሆነ የሥርዓት ጠላት ፈጥረው በስፋት ካልኮነኑ በስተቀር፣ ሐሳባቸውን በሚገባ የገለጹ የማይመስላቸው ታዳሚዎች መኖራቸው ስብሰባውን እጅግ አሰልቺ ያደርገዋል፡፡

6ኛ. ሰብሳቢዎች በስብሰባዎች ላይ የሚፈጥሩትን አሉታዊ ጫና በተመለከተ፣

ሀ. በስብሰባ መክፈቻና መዝጊያ ላይ ንግግር ማራዘም፣ በማንኛውም ስብሰባ በመክፈቻ ንግግር ይከፈታል፡፡ ይሁን እንጂ ንግግሩ አጀንዳውን ከማስተዋወቅ ያለፈ መሆን የለበትም፡፡ ሰብሳቢው የመግቢያ ንግግሩን በማራዘሙ ምክንያት በአንዳንድ አጀንዳዎች የውሳኔ ሐሳብ ላይ ተፅዕኖ ማድረግ ከመቻሉም በላይ፣ ታዳሚዎች በሚያስቡት አቅጣጫ እንዳይሄዱ ገደብ ሊያደርግባቸው ይችላል፡፡ የመዝጊያው ንግግር ሲራዘም ደግሞ በአብዛኛው የተነገሩትን በመድገም ነገሩን መልሶ ጥሬ ያደርገውና ‹ያልጣመው› ውሳኔም ካለ በተራዘመው ንግግሩ ስለሚተች ውሳኔውን ያሳለፉትን ታዳሚዎች ስሜት ይጎዳል፡፡

ለ. በእያንዳንዱ ታዳሚ ንግግር ላይ ማጠቃለያ መስጠት፣ሰብሳቢው ሌሎች የተናገሩትን በመድገም ብዙ በተናገረ ቁጥር ከሌሎች ይበልጥ የተረዳ ወይም ለሌሎች ግልጽ ያደረገ እየመሰለው፣ ከራሱም በመጨመር ከመጀመሪያው ተናጋሪ በላይ ረጅም ጊዜ የፈጀ አላስፈላጊ መግለጫ መስጠቱ ለእያንዳንዱ ሐሳብ ሁለት ሁለት ተናጋሪ የመመደብ ያህል ከመሆኑም በላይ፣ የመጀመሪያዎቹ ተናጋሪዎች ንግግሮች ሊዛቡ የሚችሉበትን ሁኔታ ሲፈጥር የቀደምት ተናጋሪዎችንም የመናገር ብቃት ይጎዳል፡፡

ሐ. ውሳኔዎች ወደ ሰብሳቢው ፍላጎትና አቅጣጫ እንዲያመሩ የማድረግ፣ አንዳንድ ስብሰባዎች በእጅጉ የሚራዘሙት አጀንዳዎቹ ከባድ ሆነው ሳይሆን ሰብሳቢዎች በሚፈልጉት አቅጣጫ ባለመሄዳቸው ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ሰብሳቢዎች አጀንዳዎችን ቀርፀው ሲገቡ ውሳኔዎችንም በልባቸው ይዘው ነው፡፡ ታዳሚው የተጠራውም እነሱ የፈለጉትን ውሳኔ እንዲያፀድቅላቸው ለማድረግ እንጂ ነፃ ሐሳቡን ፈልገው አይደለም፡፡ እንዲያውም ስብሰባው በፈለጉት አቅጣጫ ካልሄደ ውሎ ማደሩን የተገላቢጦሽ የዴሞክራሲ መገለጫ አድርገው የሚገልጹም አሉ፡፡ ይኼ የታዳሚውን ቁርጠኝነት ይሸረሽረዋል፡፡ ጥላቻም ስለሚያሳድርበት ለስብሰባ ያለው አመለካከት አሉታዊ ይሆናል፡፡

መ. እርከንን ያልጠበቀ ስሜታዊ ስብሰባ ማካሄድ፣አለቆች በውክልና የሰጡትን ሥልጣን በስብሰባ ወቅት መልሰው ሲነጥቁ ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ ግቢው ፅዳት ከራቀው፣ ወይም የተሸከርካሪ አጠቃቀም ሥርዓት ከሌለው፣ ወይም የሥራ መግቢያ ሰዓት የማይከበር ከሆነ እነዚህ ሁሉ ስህተቶች የሚታረሙበት አግባብ ያለው ሥርዓትና ለዚሁ ጉዳይ የተመደቡ ኃላፊዎች እያሉ ቢሮ ዘግቶ ጠቅላላ የመሥሪያ ቤቱን ሠራተኞች በመጥራት፣ ስሜታዊነት የተሞላበት ስብሰባ ለግማሽ ቀን ሲካሄድ ይውላል፡፡ ይህ ዓይነቱ የንትርክ ስብሰባ የኃላፊውን ደረጃ ዝቅ ከማድረግም አልፎ የበታች ኃላፊዎች ተግባራቸውን በሚገባ እንዳይወጡ ያደርጋል፡፡

ሰ. ምዘናና ግምገማን አግባብ ባልሆነ መንገድ መተርጎም፣ሥራዎች የሚመዘኑበትና የሚገመገሙበት ሳይንሳዊ  አግባብ አለ፡፡ ይህም ምዘናው በየዕለቱና በየሰዓቱ የሚከናወን ሲሆን ግምገማው ደግሞ የሥራው አካሄድ በሚጠይቀው ቀደም ሲል በዕቅድ በተያዘ አግባብ ይሆናል፡፡ የምዘናውም ሆነ ግምገማው ዓላማ ለሥራው የተቀረፁ ሥርዓቶችን በሥራው ላይ በተከሰቱ ችግሮች አማካይነት እንደገና እንዲመረመሩ የሚያደርግና ሌሎች አስፈላጊ መሆናቸው የታመነባቸው የሌሉ የሥራ ሒደቶች እንዲፈጠሩ የሚያደርግ ሲሆን፣ ይኼም በተመደቡ ሠራተኞችና በመዋቅር ይመራል፡፡ አሁን ግን በየመሥሪያ ቤቱ የሚታየው ምዘና ሥራንና ሥርዓትን ሳይሆን ሰብዕናን ያማከለ፣ አንዱ አንዱን ለማዋረድና በጥቃት ለመፈላለግ ብቻ የቆመ፣ በዚህ ዘመን መሥራት ሳይሆን መታሰብ የሌለበት ያልሠለጠነ አካሄድ ይመስላል፡፡ ይኼም ተደርጎ ምንም የረባ ውጤት አለመገኘቱና ችግሮቹ እየተባባሱ መሄዳቸው የምንከተለው የግምገማ ሥርዓት ረብ እንደሌለው ያሳያል፡፡ የእርስ በርስ መተራረብንና መወራረፍን አቁመን፣ ሥርዓቶችንና ዘመናዊ የአሠራር ሥልቶችን በመንደፍ ብቻ መልካም አስተዳደርን መገንባት ይቻላል፡፡    

ረ. የስብሰባውን  ውጤት በተግባር ላይ አለማዋል፣ ማንኛውም ስብሰባ ሲጠናቀቅ የአፈጻጸም መርሐ ግብር ሊወጣለት ይገባል፡፡ በመርሐ ግብሩም የማን ክፍል ኃላፊነቱን ይወስዳል መቼና እንዴት ይሠራዋል የሚለው ይነደፋል፡፡ አብዛኛው ስብሰባ ይኼንን ዓብይ ጉዳይ አያስከትለውም፡፡ ይህ ስብሰባ ወደ ውጤት ሳይሸጋገር ሌላ አስቸኳይ የተባለ ስብሰባ ይጠራል፡፡ በዚሁ የቀደመው ስብሰባ ይዘነጋል፡፡ በዚህ ምክንያት ያለፈውን ስብሰባ ረብ የለሽነት ያወቁ ታዳሚዎች ለሚቀጥለው ስብሰባ በሙሉ ልባቸው አይመጡም፡፡ ለስብሰባውም ሆነ ለሰብሳቢው መልካም አመለካከትም አይኖራቸውም፡፡ የመሥሪያ ቤቱንም መሪዎች የአመራር ደረጃ ዝቅ ያደርገዋል፡፡   

በመሆኑምየስብሰባን ዓላማና ይዘቱን እንዲሁም ተግባራዊ አፈጻጸሙን በማዘመንና ወቅቱ የሚጠይቀውን ሥርዓት በመከተል በየቀኑ የሚደረጉትን ‹‹ጉንጭ አልፋ›› ስብሰባዎች በመቀነስ፣ የተገልጋዩን ጊዜ ሳይሻማ በሚገባ መስተንግዶ መስጠት ይቻላል፡፡ ሁሉም የመንግሥት ሠራተኛ በቢሮው ቢያገለግልም በሌላው ቢሮ ግን ተገልጋይ መሆኑን ማወቅ ይገባዋል፡፡ የመልካም አስተዳደር መሠረቶች በጎ አመለካከት ተገቢ የመሥሪያ ቤት መዋቅሮችና ሁነኛ የሥራ ሥልቶች ናቸው፡፡ እነዚህ እርስ በርሳቸው ሊደጋገፉ የሚችሉ የመልካም አስተዳደር መሠረቶች በሚገባ መስመር ከያዙ መልካም አስተዳደር በራሱ ይገነባል፡፡ በመሆኑም ተገቢ የሥራ ሥልቶችን፣ መዋቅሮችንና አመለካከቶችን ከመሥሪያ ቤቱ ዓላማና ተግባር ጋር በማዋሀድ መልካም አስተዳደርን ለማስፈን እንትጋ፡፡

ሰላም ሁኑ

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው dereje460@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡ 

Standard (Image)

ለውጥ አደናቃፊው የመንግሥት የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ

$
0
0

በልዑል ዘሩ

የሕዝብ ግንኙነት ሥራ በዓለም ላይ ከፍ ያለ ቦታ እየተሰጠው የመጣ ቢዝነስ፣ የፖለቲካና የሥራ አመራር ቀዳሚ መስክ ነው፡፡ በአገራችንም ቢሆን በተለይ ካለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት ወዲህ እየታወቀ ከመምጣቱ ባሻገር፣ ስሙ እየተቀያየረ (አንድ ጊዜ ፕሬስ፣ ሌላ ጊዜ ኮሙዩኒንኬሽን ወይም ቃለ አቀባይ እየተባለ በድብልቅልቅ አጠራር) እዚህ የደረሰ ሙያ ነው፡፡

ለሕዝብ ግንኙነት ሙያ አሁንም በርካታ መጠሪያ ስያሜዎች መኖራቸው ብቻ ሳይሆን፣ ተግባራቱም ያንኑ ያህል የተምታቱ ናቸው፡፡ ዘርፉ አንድ የማኅበራዊ ዘርፍ መሆኑን ጠቅሰው አሁን እኛና መሰል አገሮች ከምንጠቀምበት አንፃር ከሚገልጹት ምሁራን መካከል ሞርና ካሉፕ አንዱ ናቸው፡፡

‹‹የሕዝብ ግንኙነት ሥራ ለየት ያለ አገልግሎት ያለው ሆኖ የሕዝብን አስተያየት የሚሰበስብና አመለካከት በማይጤን የተቋማትን ዓላማ፣ ፍላጎት፣ የአሠራር ሒደትና ፖሊሲ የሚያብራራ ዝርዝር የሥራ ፕሮግራሞችንና ተግባራትን እንዲሁም ክንውኖችን ኅብረተሰቡ እንዲያውቃቸውና እንዲረዳቸው የሚያደርግ ነው፡፡ በተቃራኒው የሕዝቡ (የደንበኞች) ፍላጎትና ጥያቄንም እያጠናና እየቀመረ ወደ ድርጅቱ የማቅረብ ሚና አለው፤›› ሲሉ ይገልጹታል፡፡

ከዚህ ሳይንሳዊ ብያኔ በመነሳት የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ በኩባንያ (መንግሥት) እና በደንበኛ (ሕዝብ) መካከል መስተጋብር የሚፈጥር ድልድይ ነው፡፡ ዋናው ትኩረታችን ወደ ሆነው የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሕዝብ ግንኙነት (Public Relation) ተግባር ሳናተኮርም ከዚሁ የተለየ ተግባር ሊቀመጥለት አይችልም፡፡ እውነታው ይኼ ነው፡፡ ቢሆንም በየትም አገር የሚገኙ ሕዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች የሚዘነጉት ከሕዝቡ በኩል ያለውን ፍላጎትና ጥያቄ ነው፡፡ አንድም ፍላጎታቸው ወደ መንግሥት በማድላቱ፣ በሌላ በኩል በአቅምና ቁርጠኝነት ውስንነት ተግዳሮት ሲፈጠር ይታያል፡፡ በእኛ አገርም ቢሆን ከእነዚህ ፈተናዎች ባሻገር የሕዝብ ግንኙነት ሁለንተናዊ ተሳትፎ ለመፍጠር የሚያስችል አቅም ላይ አይገኝም፡፡ ዘርፉ በአዋጅ የተሰጠውን ተግባር ወደ ጎን ማለትና ከሚጠበቀው ተግባር ባነሰ የአጫፋሪነት ሚና ላይ የመጠመዱ አደናቃፊነት፣ አገሪቱ ለጀመረችው የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ እንቅፋት ሆኖበት ይገኛል፡፡ አንድ በአንድ እንመልከት፡፡

ሙያዊ ብቃትና ፍላጎት የለሽ የሕዝብ ግንኙነት ክፍሎች

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ (በ2004) የተዘጋጀ አንድ መድበል ላይ ‹‹የሕዝብ ግንኙነትና በዘርፉ ያሉ አመለካከቶች›› በሚል ርዕስ የቀረበ ጥናት ይዟል፡፡ በጥናቱ መሠረት መጠይቅ ከቀረበላቸው ከ60 በላይ የዘርፉ ሙያተኞች 68 በመቶ ያህሉ የሕዝብ ግንኙነት ሙያና ተዛማጅ ሥልጠና የላቸውም፡፡ በሥራ መደቡ ላይ የተቀመጡትም በፖለቲካ ታማኝነት፣ በብሔር ተዋፅኦ ወይም ከሌላ ክፍል በተደረገ የሽግሽግ ምደባ ነው፡፡ በየጊዜው በሚደረጉ የቢፒአርና ሌሎች ሽግሽጎች መሠረት ተፈናጥረው ክፍሉን የሚሞሉትም ቁጥራቸው ትንሽ አይደለም፡፡

በአንዳንድ መሥሪያ ቤቶች የሥነ ጽሑፍ ወይም የንግግር ችሎታ፣ አንዳንዴም ፎቶግራፍ ማንሳትና ‹‹ቅልጥፍና›› በማሳየት ብቻ እስከ ዳይሬክተርነት የደረሱ ሙያተኞችም አሉ፡፡ ጉዳቱ ይኼ ብቻ ሳይሆን መረጃ ከሰጡት መሀል 40 በመቶው ለሥራው ሙሉ ፍላጎት እንደሌላቸው ሲናገሩ፣ 40 በመቶው ደግሞ በመጠኑ ደስተኛ ነኝ ያሉ ናቸው፡፡

በዚህ ጥናት ግኝትም ሆነ መሬት ላይ ባለው ሀቅ መሠረት አብዛኛው የሕዝብ ግንኙነት ሙያተኛ የዕውቀትና የፍላጎት ክፍተት ብቻ አይደለም ያለበት፡፡ ከዚያም በላይ ለሙያው ሥነ ምግባር የማይገዛ፣ እውነትም ይሁን ውሸት የአንድ ወገንን መረጃ የሚያንበለብል (ያውም መረጃውን አሟልቶ ከያዘ)፣ የሕዝቡን ጉዳይ የረሳ ሆኖ ይታያል፡፡

በቅርቡ የፌደራል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጽሕፈት ቤት በጠራው አንድ የምክክር መድረክ ላይ ሚኒስትሩ ዶ/ር ነገሪ ሌንጮም ይህንኑ ሐሳብ ተጋርተውታል፡፡ ‹‹በፌደራልም ሆነ በክልሎች ደረጃ ያለው የሕዝብ ግንኙነት ዘርፉ የሙያ ክፍተት ብቻ ሳይሆን ያለበት፣ ከተሰጠው ኃላፊነትም አንፃር ተግባሩን አሟልቶ የማይወጣ ሆኖ ይታያል፡፡ ይህንን ኃይል ሳያስተካክሉና ሳያራግፉ የተጀመረውን የመልካም አስተዳደር ማስፈንና  የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ከዳር ማድረስ ስለማይቻል ፈጣን የዕርምት ዕርምጃ ይወሰዳል፤›› ነው ያሉት፡፡

መንግሥት በተለይ ከምርጫ 97 ወዲህ የፌደራል የሕዝብ ግንኙነት መስኩን በክልል ካድሬዎች ሞልቶታል፡፡ እነዚህ ሙያተኞች አንዳንዶች በትምህርት ብቃት ራሳቸውን ያሳደጉና ያሻሻሉ ሲሆን፣ ብዙዎቹ እንደቆሙ የቀሩ ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት መረጃ መከልከል፣ ማጓተት፣ አንዳንዶቹም ስለራሳቸው (የፕሮቶኮል ሥራ፣ የድግስና የስብሰባ ማስጀመር አልባሌ ጉዳይ ላይ) ተጠምደዋል፡፡

ለዚህ ጽሑፍ ዝግጅት ሲባል የሕዝብ ግንኙነት ሚናን አስመልክቶ ጥያቄ የቀረበላቸው መረጃ ፈላጊዎች (የሚዲያ ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች) በየደረጃው በሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት ተገቢውን መረጃ ማግኘት ተስኖአቸዋል፡፡ በተለይ የፈለጉትን ሚዛናዊ መረጃ በፍጥነትና በጥልቀት የሚያገኙባቸው ተቋማት እጅግ ውስን እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ አብዛኛዎቹ የሕዝብ ግንኙነት ክፍሎችም ተመሳሳይ በሆነ የፕሮፓጋንዳ ተግባር የተጠመዱ ናቸው፡፡

ከዚህ አንፃር የአሁኑ ተሃድሶም ይባል የመንግሥት የእርምት ዕርምጃ አንዱ ሊፈትሸው የሚገባው ዘርፍ ይህንኑ መሆኑን መገንዘብ አያዳግትም፡፡ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤትና የሕዝብ ግንኙነቶችን በድርጅታዊ አሠራር ጠፍሮ በመገምገም፣ ወይም በዓመት አንድ ጊዜ በሚካሄድ የቀናት ሥልጠና ብቻ ዘርፉን ማሻሻል አዳጋች ነው፡፡ ይልቁንም የሕዝብ ግንኙነት ዘርፉን በሰው ኃይል (በተለይ በሠለጠነና ብቃት ባለው)፣ በግብዓትና በሥልጠና ወደላቀ ምዕራፍ መውሰድ፣ ከጓዳ ተልኮስኳሽነት ማውጣት ይገባል፡፡ በሕዝብ የማይጠረጠር እንዲሆን ማድረግም ግድ ይላል፡፡

የመረጃ ነፃነትና የመገናኛ ብዙኀን አዋጁ ይፈጸም

በአገሪቱ ፓርላማ የፀደቀው አዋጅ 590/2000 የሚባለው ሕግ በፅኑ እየተተገበረ ያለው በጋዜጠኛው ወገን ብቻ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ በግልም ይሁን በመንግሥት መገናኛ ብዙኀን ላይ የሚሠሩ ጋዜጠኞች በሚያሳትሙት (ብሮድካስት በሚደያደርጉት) ዘገባ ልክ ይመሰገናሉ፣ ይጠየቃሉም፡፡ በዘገባ ሥራቸው ‹‹አጥፍተው›› የተከሰሱና የተጠየቁ (በተለይ የታሰሩ) ጋዜጠኞችም ለአባባሉ ምስክር ናቸው፡፡

በአዋጁ ክፍል ሦስት መሠረት ከመረጃ ሰጪው (ሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ) በኩል ያለው አፈጻጸም ግን ዋጋ አልባ የሚባል ነው፡፡ የመንግሥት አካላት መረጃ የሕዝብ ሀብት መሆኑን ተገንዝበው በአግባቡና በጊዜው እንዲሰጡ ቢገደዱም፣ አዋጁን በመተግበር በኩል የተጠየቀ (የታረመ) የመስኩ ሰው እንደሌላ ግልጽ ነው፡፡ አንዳንዱ መረጃን የግሉ (የተቋሙ) ንብረት እያሰመሰለ ሲሸሸግ፣ ሲቀሽብ ወይም ሲያዛባ ቀጪ አላገኘም፡፡ አዋጁን እንዲያስፈጽሙ ሕግ አደራ የጣለባቸው የእንባ ጠባቂ ተቋምና የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤትን የመሰሉ ሕዝባዊ ተቋማትም እስካአሁን ከ‹‹ግንዛቤ ማስጨበጥ›› ምክክር ተላቀው፣ የማስፈጸሚያ መመርያና ደንቦችን እንኳን ሳይወጡ ከስድስት ዓመታት በላይ ተንከባልለዋል፡፡ መረጃ የመስጫ ጊዜና መጠን፣ የመረጃ አያያዝና አጠባበቅ ጉዳይ፣ የሚስጥራዊ መረጃ አያያዝ ጉዳይ ከአዋጁ ወርዶ ለትግበራ አስገዳጅነት እንኳን አለመብቃቱ የሚያስተዛዝብ ክስተት ሆኗል፡፡

ይህ በመሆኑም አሁን በተግባር እየታየ እንዳለው አብዛኛው የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ለግልጽነትና ለተጠያቂነት የሚያግዝ መረጃ ሰጪ ሳይሆን፣ መካችና ከልካይ ሆኖ ተጎልቷል፡፡ በየዓመቱ በየመሥሪያ ቤቱ በመቶ ሺሕዎች ብር ለኅትመት እያወጣ የመሥሪያ ቤት ዕቅድና ሪፖርትን ማተም ወይም በኃላፊዎች ፎቶ ያሸበረቀ መጽሔት ‹‹ማዘጋጀት›› የሥራ ሁሉ አልፋና ኦሜጋ መስሎም ቀርቷል፡፡ ይህ በንጉሡ ዘመን (በ1950ዎቹ) ከነበረው የሕዝብ ግንኙነት አሠራር ያልተነጠለ ጉዞ ሁለት ትውልድ ተሻግሮ፣ ዛሬ ላይ ያለውን ዜጋ ነባራዊ ሁኔታ ሊመጥን አይችልም፡፡ እጅ እጅ  የማለቱ ሚስጥርም ይኼው ነው፡፡

አሁን ባለንበት ዓለም በመረጃ አንድ መንደር ሆኖ ምንም ዓይነት ኢንፎርሜሽን ከአጽናፍ አጽናፍ እየተዘናፈለ ስለክልከላ ማሰብ ኋላቀርነት ነው፡፡ እዚህ ግባ የማይባል ድረ ገጽና ማኅበራዊ ሚዲያ ያውም በግል ከፍቶ የሕዝብ የመረጃ ፍላጎትን ማርካት አይቻልም፡፡ በአንድ ወገን የፕሮፓጋንዳ ቀውስ ብቻ ሕዝብ የሚያውቀውን ሀቅ ለማዳፈን መሞከርም ከንቱ ድካም ነው፡፡ ይህ አካሄድ ከየተቋማቱ ሕዝብ ግንኙነትም አልፎ በብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያዎችና ውድ የጋዜጣ ዓምዶች ‹‹በስፖንሰርሺፕ›› እየታጀበ ሲለቀቅ ደግሞ ብክነት መሆኑ አያጠራጥርም፡፡

የመገናኛ ብዙኀንና የመረጃ ነፃነት አዋጅ በፅናት እንዳይተገበር እንቅፋት የሆኑ የመንግሥት አካላትና ራሱ የሕዝብ ግንኙነት መዋቅሩ ብቻ አይደለም የሚወቅሱት፡፡ ይልቁንም በሕገ መንግሥቱ መሠረት ትልቁን ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣን የያዘው ሕግ አውጭው አካል (ፓርላማውም) ከታሪክ ተወቃሽነት ሊያመልጥ አይችልም፡፡ ከአስመሳይ ‹‹ዴሞክራሲያዊነት›› ወጥቶ ሕዝብ የሚገለገልበትን ባህል ወደ መፍጠር ካልሄደ፣ ለሥርዓቱ ውድቀት ጠጠር እንዳቀበለ  የሚቆጠር ነው፡፡

በዘርፉ የሕዝብና የባለሥልጣናት ተቃራኒ አተያይ

ቀደም ሲል በተካሄደው ጥናት መሠረት በአገራችን ስላለው የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ሕዝብ ያለው አተያይ ያልጠራ ነው፡፡ ከ63 በመቶ በላይ የሚሆነው የሕዝብ ግንኙነት ሙያተኛ መልስ ሰጭዎች ለሙያው የሚሰጠው ክብርና ያለው እምነት በጣም ዝቅተኛ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ከቀሪዎቹም 18 በመቶ ያሉ መካከለኛ ነው ማለታቸው፣ ዘርፉ እንዴት ከሕዝቡ የተነጠለ መሆኑን ያመለክታል፡፡ በእርግጥ ይኸው ጥያቄ በሕዝቡ በኩልም ቢጠየቅ የተለየ መልስ አይኖረውም፡፡

   ለዚህ አተያይ የሚጠቀሱ ምክንያችም አሉ፡፡ አንደኛው መንግሥትና የመንግሥት ኃላፊዎች ለዘርፉ የሰጡት የተላላኪነትና የፕሮፓጋንዲስት አተያይ ነው፡፡ ሁለተኛው ራሱ ባለሙያና ዘርፉ ሕዝቡ የሰጠውን አደራ ወደጎን ብሎ ያልበላውን እያከከ ለዓመታት በመኖሩ ነው፡፡

ከዚህ ሁሉ በላይ በሕዝብ ግንኙነት ስም የገዥው ፓርቲ የፕሮፓጋንዳ ክንፉ ሆኖ መጠራቱ፣ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን የሚባለው ‹‹የወሬ ምንጭ›› ከላይ እስከ ታች በመዘርጋቱና ካለፉት ሥርዓቶችም ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የፕሮፓጋንዳ ዘርፉ (ዋሽቶ ማሳመን ገጽታ) ተቀባይነት ማጣት ያደረ ጥላሸት በመሆኑ ነው፡፡ ይህንን በሚዛናዊና በትክክለኛ ትግበራ መቀየር ያስፈልጋል፣ ይገባልም፡፡

ለዚህ ዓይነቱ ብልሽት የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች (ከሚኒስቴር እስከ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ድረስ) ሕዝብ ግንኙነትን ቃለ ጉባዔ ያዥና የፕሮቶኮል ተጠሪ አድርገው ማየታቸውም ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ይህ በመሆኑም አመራሩ ሊፈጥርበት የሚችለውን ጉዳይ (የግልጽነትና የተጠያቂነት መርህ) ለሕዝብ ግንኙነቱ እየተወ ገራገሩን መድረክ ከመምረጡ ባሻገር፣ እንደ አስፈላጊነቱ የመስኩን ባለሙያ ‹‹ገመና ሸሽግ›› ሲያርገው ታይቷል፡፡ ይህ መረገም ያለበት ነውር እንደሆነ በተለይ እንደ አሁኑ ባለው የተሃድሶ ወቅት ግልጽ ነው፡፡

በነገራችን ላይ በቀደመው ጥናትም ሆነ ከዚያ በኋላ በተደረጉ ዳሰሳዎች የመንግሥት ሠራተኞች ራሳቸው የሕዝብ ግንኙነት ዘርፉን ወሬ አቀባይ (ጆሮ ጠቢ) አድርገው የመሰሉበት ጊዜም ጥቂት አይደለም፡፡ ሥራው ካለው ተፅዕኖ ፈጣሪነትና ሕዝባዊ ተቀባይነት አንፃር እየተመዘነ እንደ ገለባ በመቅለሉ የዘርፉን ባለሙያም ሆነ አመራር ዝቅ ያለ ቦታ እንዲሰጠው አድርጎታል፡፡ ሕዝብ ግንኙነት የአመራር ዓብይ ተግባርነቱም ተዳፍኗል፡፡ ከዚህ አንፃር የተንሸዋረረውን ዕይታ የፈጠረው ልፍስፍሱ ተግባር ነው ለማለት ይቻላል፡፡

ሲጠቃለል ምን ማለት ይቻላል?

የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ለአምስት ዓመታት በመንግሥት የፌዴራል ተቋም ውስጥ በሕዝብ ግንኙነት ባለሙያነት ሠርቷል፡፡ ለጽሑፉ መንደርደሪያ የሆነው ከላይ የተጠቀሰው ቆየት ያለ የጥናት ሰነድ ማግኘቱ ቢሆንም፣ ዘርፉ አሁንም ከችግር ከመውጣት ይልቅ ሲንደፋደፍ ማየቱ ቢያንስ በተወዳጁ ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ የግል እምነቱን ጠቅሶ ሁሉንም እንዲወያይበት ማድረግን መርጧል፡፡

አሁን አገሪቱ ከደረሰችበት የማኅበረ ኢኮኖሚ ዕድገትም ሆነ ከሕዝቡ የንቃተ ኅሊና ደረጃ አንፃር፣ የሕዝብ ግንኙነት መንግሥታዊው መንገድ ውልክፍክፍ ነው፡፡ የስፖንጅ መዶሻ፣ የቄጤማ ምርኩዝ የሚሉት ዓይነት ለሕዝብ አይጠቅምም፡፡ ለመንግሥትም እንዲሁ፡፡ ስለዚህ ከዚህ ዓይነቱ የተዳከመ ሁኔታ ወጥቶ በእግሩ እንዲቆም የሚመለከታቸው አካላት በትኩረት ሊሠሩ ይገባል፡፡ ሕዝቡም የድርሻውን ቢወጣ መልካም ነው፡፡ ራሱ የዘርፉ ሙያተኛና አመራር ሚና ግን ተኪ የሌለው ነው ማለት እወዳለሁ፡፡ 

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው zliule@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡      

Standard (Image)

ከሥርዓት ወደ ሥርዓት ሽርሽር

$
0
0

በጌታቸው አስፋው

ከ16ኛው እስከ 18ኛው ክፍለ ዘመን ታላላቅ ነጋዴዎች ከአገራቸው ድንበር ተሻግረው ከሌላ አገር ሰዎች ጋር ወርቅ፣ የውጭ ገንዘብና ሸቀጦችን የሚነጋገዱበት በውጭ ንግድ አትራፊነት መርህ የባላባታዊ ከበርቴ አገራዊ ብሔርተኛ ዘመነ ንግድ (መርካንታሊዝም) የኢኮኖሚ ሥርዓት በአውሮፓ የነገሠበት ዘመን ነበር፡፡ መርካንታሊዝም መርቻንት ወይም ነጋዴ ከሚለው የእንግሊዝኛ ቃል የተወሰደ ነው፡፡

ግለ ነፃነት ወይም ሊበራሊዝም አዳም ስሚዝ በ18ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ ብሔርተኛ የዘመነ ንግድን ኢኮኖሚ ሥርዓት ተችቶና ነቅፎ በግለ ነፃነት ላይ የተመሠረተ ነፃ ገበያ ኢኮኖሚን የተነተነበት እስከ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ድረስ፣ ምዕራባውያን አገሮች የተመሩበትና ያቀነቅኑት የነበረ የካፒታሊዝም ኢኮኖሚ ሥርዓት ነው፡፡

እ.ኤ.አ. ከ1936 እስከ 1970ዎቹ ምዕራባውያኑ አገሮች በኬንስ ኢኮኖሚ አስተምሮ ከግለ ነፃነት ወይም ሊበራሊዝም ወደ መንግሥታዊ የብሔራዊ ኢኮኖሚ አስተዳደር ተሸጋገሩ፡፡ ከ1960ዎቹ ጀምሮ ጃፓንና ሌሎች በፍጥነት ያደጉ የደቡብና ምሥራቅ እስያ አገሮች፣ የቀድሞውን ዘመነ ንግድ በልማታዊ ብሔርተኛ የዳግም ዘመነ ንግድ ኢኮኖሚ ሥርዓት መልሰው አስቀጠሉ፡፡

ከ1970ዎቹ በኋላም ምዕራባውያኑ በመንግሥታዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር የተቋረጠውን የቀድሞ ግለ ነፃነት (ሊበራሊዝም) ኢኮኖሚ ሥርዓት በእንግሊዝ፣ በአሜሪካ፣ በጀርመንና በአንዳንድ አለም ዓቀፍ ድርጅቶች መሪነት እንደገና በዳግም ግለ ነፃነት (ኒዮ ሊበራሊዝም) ሥርዓት መልሰው አስቀጠሉ፡፡

ስለሆነም ዘመነ ንግድም (መርካንታሊዝም) ሆነ ግለ ነፃነት (ሊበራሊዝም) በሌሎች የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓቶች ከተቋረጡ በኋላ እንደገና በመምጣታቸው፣ ዳግም ዘመነ ንግድ ወይም ኒዮ መርካንታሊዝምና ዳግም ግለ ነፃነት ወይም ኒዮ ሊበራሊዝም ተብለው ይታወቃሉ፡፡

እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስም ልማታዊ ነን የሚሉት አገራዊ ብሔርተኛ ዳግም ዘመነ ንግድ አገሮች የራሳቸውን ሥርዓት ጥሩና ዓለም አቀፋዊ ዳግም ግለ ነፃነት ሥርዓትን መጥፎ አድርገው ይመለከቱ ነበር፡፡ በተቃራኒውም ዓለም አቀፋዊ ዳግም ግለ ነፃነት አገሮች ልማታዊ ዳግም ዘመነ ንግድ ሥርዓትን መጥፎና የራሳቸውን ሥርዓት ጥሩ አድርገው ይመለከቱ ነበር፡፡

ኢትዮጵያ እንኳ በውጭ ንግድ ገቢዋ ከወጪዋ በልጦ አትራፊ አገር ባትሆንም፣ እየከሰረችም ራሷን እንደ ሌሎቹ ልማታዊ አገራዊ ብሔርተኛ የዳግም ዘመነ ንግድ አገር  አድርጋ ቆጥራ የዳግም ግለ ነፃነት አገሮችን አክራሪ ነፃ ገበያውያን የሚል ስም ሰጥታ ታወግዝና ትኮንን ነበር፡፡

ከላይ እንደተመለከትነው የኢኮኖሚ አስተሳሰቦች ሁለት ጊዜ እንደታደሱ እንመለከታለን፡፡ በመጀመርያ ከግለ ነፃነት የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት በፊት የነበረው ብሔርተኛ ዘመነ ንግድ ሥርዓት፣ በልማታዊ መንግሥታት ከ1960ዎቹ ጀምሮ በብሔርተኛ ዳግም ዘመነ ንግድ ሥርዓተ ታደሰ፡፡ ሁለተኛ ከኬንስ መንግሥታዊ ኢኮኖሚ አስተዳደር በፊት የነበረው ግለ ነፃነት የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት ከ1980ዎቹ በኋላ ወደ ዳግም ግለ ነፃነት ሥርዓት ታደሰ፡፡

በዚህ ሰሞን ደግሞ በፍፁም ያልተጠበቀ ሦስተኛ የሽርሽር ለውጥ እየተመለከትን ነው፡፡ ታዳጊ አገሮች ልማታዊ ፍልስፍናቸውን እንደጨበጡ በምዕራባውያን አገሮች የዳግም ግለ ነፃነት ሥርዓት የግሎባላይዜሽን ፍልስፍና እምነት ጥለው የውጭ ቀጥታ መዋዕለ ንዋይን በማሳደድ ላይ እያሉ፣ የግሎባላይዜሽን ሰባኪዎች  ሜዳ ላይ ጥለዋቸው የዳግም ግለ ነፃነት ሥርዓትን ትተው ወደ ዳግም ብሔርተኛ ዘመነ ንግድ ሥርዓት ኮበለሉ፡፡   

‹የአሜሪካን ግዙ፣ አሜሪካውያንን ቅጠሩ› ብሎ ከመስበክም አልፈው ‹አሜሪካ ትቅደም በሚል መፈክር በውጭ መዋዕለንዋይ ያፈሰሳችሁ ወደ አገሮቹ ብትመለሱ የታክስ ዕረፍት ይሰጣችኋል፣ ከግሎባላይዜሽን ፍልስፍና ያፈነገጠ የተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አዲስ አገራዊ ብሔርተኝነት ስሜት ተንፀባረቀ፡፡ ነጩ ቤተ መንግሥታቸው እንደገቡም የተናገሩትን ሁሉ በተግባርም እያሳዩ ነው፡፡ ዓለም አቀፍ የትብብር ግንኙነቶችን እየሻሩ ነው፡፡

የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬዛ ሜየር ሰሞኑን በዳቮስ ስዊዘርላንድ ለዓለም የኢኮኖሚ መድረክ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ‹‹እንግሊዝ ከአውሮፓ ኅብረት መውጣቷ መጥበብና ከግሎባላይዜሽን ማፈንገጥ ሳይሆን ገበያችንን ከአንድ አኅጉር ወደ ዓለም አቀፋዊነት ማስፋት ነው፤›› ቢሉም፣ ሚስጥሩ ግን በዳግም ዘመነ ንግድ የአገራዊ ብሔርተኝነት ስሜት የእንግሊዝን ጥቅም የማስፋት እንጂ፣ ዓለም አቀፋዊነትን ወይም (ግሎባላይዜሽንን) የሚያንፀባርቅ አይደለም፡፡

በሌሎች የአውሮፓና አሜሪካ አገሮችም ብሔርተኛ መሪዎች ሥልጣን እየያዙ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በውጭ ቀጥታ መዋዕለ ንዋይ ማደግ ተስፋ ላደረጉና በግሎባላይዜሽን እምነት ለጣሉ፣ የኢንዱስትሪ ፓርክ ገንብተው ለሚጠባበቁ ታዳጊ አገሮች ተስፋ ሰጪ አይደለም፡፡ ተለምኖ የመጣው የሀብታም አገሮች መዋዕለ ንዋይ ጠግቦና ተንቀባሮ ሊሄድ ነው፡፡ አገርን ለማሳደግ እንደ ሌሎቹ አገራዊ ብሔርተኝነት ስሜት ሊያስፈልግ ነው፡፡

17 ዓመታት ኢትዮጵያን ያስተዳደሩት ሌተና ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ከሐራሬ ከላኩት መጽሐፋቸው በፊት ጎሳቸውን ከእርሳቸውና ከቤተሰባቸው በቀር የማያውቅ የኢትዮጵያ ሕዝብ በጠባብነት አቀንቃኞች መቶ ዓመታት ወደ ኋላ ሄዶ ስለ ምኒሊክ ዘመን ማንነቱ እያሰበ የአገራዊ አብሮ የማደግ ስሜቱ ተኮላሸ፡፡ ለራሱ ብቻ እንጂ ለአገር የማይቆረቆር ሀብታም ተፈጠረ፣ የወጣቶች ዕጣ ፈንታ የጀበና ቡና ፋብሪካ ሆነ፡፡

ግሎባላይዜሽን ዓለምን እንደ አንድ መንደር በማየት ሠርቶና ነግዶ ማደር በድንበር አይታጠርም፣ ሰውና ካፒታል በመረጡት አገር ተዘዋውረው ይሥሩ፣ ሰው ሁሉ ከአገራዊ ብሔርተኝነት ስስት ይላቀቅ የሚል ይመስል ነበር፡፡

አሁን ግን ግሎባላይዜሽንን መጀመርያ ያቀነቀኑት እንግሊዝና አሜሪካ አገራዊ ብሔርተኝነትን ለማቀንቀንም የመጀመርያዎቹ ሆኑ፡፡ በሰው አገር ሄዶ የሌሎችን የተፈጥሮ ሀብትና ማዕድናት ተጠቅሞ በጥቂት ዓመታት ውስጥ የዓለምን ኢኮኖሚ በእጥፍ ያሳደገው ካፒታላቸው ወደኛው ይመለስ አሉ፡፡

እንደ ካፒታሉ ሙሉ የመዘዋወር ነፃነት ባይሰጠውም ከመጣ እንቀበለው በሚል ላላ ተደርጎ ተይዞ የነበረው የስደተኞች ጉዳይ፣ ምንም እንኳ ከፊሎቹ መንገድ ጠርገው ፅዳት አፅድተው ዝቅተኛ ሥራዎችን በሠሩ ለምን እንዳይመጡ እንከለክላቸዋለን ቢሉም፣ ስደተኞች ወደ አገራችን እንዳይመጡ ግንብ እንገነባለን በሚል የመጥበብ ስሜት ተተካ፡፡

የዚህ ዘመን የአውሮፓና የአሜሪካ መንግሥታትና መሪዎች ምርጫ በስስት የታጀበ ሆነ፡፡ የዳግም ግለ ነፃነት ወይም ኒዮ ሊበራሊዝም አቀንቃኞች በምርጫ እየወደቁ የዳግም ዘመነ ንግድ ወይም ኒዮ መርካንታሊዝም አቀንቃኞች በምርጫ እያሸነፉ ነው፡፡

የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን የጥንቱን ኃያልና ገናናነት ናፋቂ ተብለው በሌሎች አገሮች መሪዎች ቢብጠለጠሉም፣ በአገራቸው ሰዎች ግን አገር ወዳድ ብሔርተኛ ተብለው ተወድሰዋል፡፡ አዲሱ የአሜሪካ ፕሬዚዳንትም ከዚህ አገር ወዳድ ብሔርተኛ ሰው ጋር እወዳጃለሁ ብለዋል፡፡

እንግሊዝ በአውሮፓ ኅብረት ውስጥ በመቆየት የግል ጥቅሜን ማስጠበቅ አልችልም ብላ በስስት ምክንያት ተገነጠለች፡፡ ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት አሜሪካንን ለአሜሪካውያን ብቻ አደርጋለሁ በማለታቸው ለመመረጥ በቁ፡፡ በሌሎች የምዕራብ አገሮችም ተመሳሳይ ሁኔታ ይታያል፡፡

ሰዎች ሠልጥነናል፣ ሥልጣኔም ስሜታዊነትንና ጠባብነትን ያስወግዳል ካሉ ከዓመታት በኋላ እንደገና ስሜታዊና ጠባብ ሲሆኑ፣ ገና ካለመሠልጠናቸው  ባሻገር ውስጣዊ ማንነታቸውንም መመርመር ያስፈልጋል፡፡

ወትሮውንም ዳግም ዘመነ ንግድ ዳግም ግለ ነፃነት በሚሉ ሥርዓቶች ሽፋን ድብቅ ዓላማቸው የደሃ አገሮችን የተፈጥሮ ሀብት መበዝበዝ ኖሮ፣ ግሎባላይዜሽኑም አገራዊ ብሔርተኝነቱም እነርሱን የሚጠቅሙ ብቻ ሆኑ፡፡

በግሎባላይዜሽኑ ሀብታሞቹ ይበልጥ ከከበሩና ድሆቹም ይባስ ከደኸዩ በኋላ፣ የእነሱ ስምንት ሰዎች ሀብት የዓለምን ግማሽ (ሦስት ተኩል ቢሊዮን ሕዝብ) ሀብት ካከለ በኋላ የከበሩት ወደ የአገሮቻችን እንሰባሰብ ተባባሉ፡፡

በግሎባላይዜሽኑ የተማመነው የደሃ አገር ሕዝብ በሕይወት ለመቆየት እየተጠላም ቢሆን፣ በባህርና በበረሃ ወደ ከበርቴዎቹ ለሎሌነት መሰደድ ብቻ ነው ያተረፈው፡፡ ‹ሰውን ማመን ቀብሮ ነው› አለች ቀበሮ?

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው getachewasfaw240@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

Standard (Image)

ከተገልጋይ ጋር ቀጥተኛ ግንኙት ያላቸው የመንግሥት ተቋማት በሚታደስ የኮንትራት ቅጥር ሠራተኞች አገልግሎት እንዲሰጡ ቢደረግስ?

$
0
0

በዓለሙ ሳሙኤል

መንግሥታችን የመልካም አስተዳደር ችግር ኅብረተሰቡን እያማረሩ እንደሆነና ለዚህ መንስዔው ደግሞ የመንግሥት አገልግሎት የሚሰጡ አመራርና ሠራተኞች በኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ ችግሮች እየተለከፉ፣ የመንግሥት አገልግሎት ሟጓተታቸው መሆኑን በግልጽ አስቀምጧል፡፡ ዕውን የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ ችግር ብቻውን ለመልካም አስተዳደር ችግር እያደረገ ነው ያለው? የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ ችግር የችግሮቹን ትልቅ ቦታ ቢይዝም፣ ሌሎች ቀላል የማይባሉ ችግሮችም በስፋት መንስዔ ናቸው፡፡ የችግሮቹ መንስዔ የመንግሥት አመራርና ሠራተኞችና የኅብረተሰብ አካል የሆኑ ሰዎች ናቸው፡፡

የአመራርና የሠራተኞች የሥራ ላይ ብቃትና ክህሎት ማነስ የመጀመሪያው  መንስዔ ነው፡፡ ለመንግሥት አገልግሎት ተሹመው አገልግሎት የሚሰጡትን አመራርና ሠራተኞችን በቅድሚያ እንያቸው፡፡ ከእነዚህ ሰዎች የድርጅት አባል የሆኑ በብዛት አሉ፡፡ አባል በመሆናቸው ለድርጅቱ ታማኝ ናቸው፣ የድርጅቱን መዋጮ በወቅቱ ይከፍላሉ፡፡ የድርጅቱን የተለያዩ ድርሳናት ገዝተው ያነባሉ፡፡ አያመልጣቸውም፡፡ በድርጅት ጉዳይ ላይ እየተሰበሰቡ ይወያየሉ፣ ይገምግማሉ፣ አስተያየት ይሰጣሉ፣ ይቀበላሉ፡፡

ከእነዚህ ሰዎች ውስጥ በዕውቀትና በክህሎት ላይ የተመሠረተ የሥራ እንቅስቃሴ የሚያደርጉና የዓላማ ፅናት ያለቸውና የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ ችግር የሌለባቸው ንፁህ ዜጋ የሆኑ አባላት ስላሉ፣ ይህ አስተያየት እነሱን አይመለከትም፡፡  ቁጥራቸው አነስተኛ ያልሆኑ ግን የለብ ለብ ዕውቀት ያላቸው፣ የጠለቀ ዕውቀት የሌለቸው፣ በተሰማሩበት የሥራ መስክ ምን ታቅዶ ምን እንደሚከናወን፣ የሥራ ውጤት ምን እንደሆነ በትክክል የማያውቁ  አባላት ናቸው፡፡ በድርጅት ውስጥ ጠብ የሚል ነገር ፍለጋ የገቡና የዓላማ ፅናት የሌላቸው ናቸው፡፡

እነዚህ ሰዎች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ዕውቀትና ክህሎት ስሌላቸው የወር ደመወዝ ከመጠበቅ ውጪ፣ ለዜጎች የተሰማሩበትን የመንግሥት አገልግሎት በተፈለገው ልክ መስጠት የማይችሉ ናቸው፡፡ በሰሙት ልክ ብቻ የማስተገባት አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ የመናገር አቅም ይኖራቸዋል፡፡ በዕውቀትና ክህሎት ላይ የመሠረተ አገልግሎት መስጠት ስለማይችሉ ኅብረተሰቡን በጣም ያጉላሉ፡፡ የለውጥ መሣሪዎችን አያውቁም፣ ለማወቅም ፍላጎት የሌላቸው ናቸው፡፡ ሥልጠና ተሰጥቶአቸው አይገባቸውም፡፡ በለውጥ ትግበራ ላይ አቃቂር ለማውጣት በጣም አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ ደመወዝ ስለሚከፈላቸው ብቻ መሥሪያ ቤት ውስጥ ይውላሉ፡፡ በዜጎች ቻርተር ላይ የሚያስቀምጡትን ስታንዳርድ እንዴት እንደሚላክ ዕውቀትና ክህሎት የላቸውም፡፡ እንዲኖራቸውም አይፈልጉም፡፡ በጉዳዮች ላይ ውሳኔ መስጠት ለመስጠት ይፈራሉ፡፡ ጊዜ ለመውሰድ ቀጠሮ በመስጠት ተገልጋዮች ያመላልሳሉ፡፡

ከእነዚህ ጋር ተመሳሳይ አቋም ያላቸው ነገር ግን የድርጅት አባል ያልሆኑ በብዛት በመንግሥት ተቋማት ውስጥ ይሠራሉ፡፡ በመንግሥት ተቋም ውስጥ ለምን እንደሚሠሩ፣ በተቋሙ ውስጥ የእነሱ ሚና መሆን እንዳለበት ዕውቀቱም ክህሎቱም የሌላቸው፣ ለሥራ ብለው ብቻ ከቤት የሚወጡ፣ በዕውቀትና በክህሎት ላይ ተመሥርተው ምንም ዓይነት ውጤታማ ሥራ የማያከናወኑ፣ በየወሩ ደመወዝ የሚጠብቁ፣ መንግሥትን በማማት ሲመሽ ቤታቸው የሚገቡ ቁጥራቸው ቀላል ያልሆነ  ሠራተኞች በብዛት አሉ፡፡

ዕውቀትና ክህሎት ካለቸው አመራርና ሠራተኞች ውስጥ የክፋት መንፈስ የተጠናወተቸውን በሌላ ረድፍ እንያቸው እስቲ፡፡ እነዚህ የመናገር፣ በውሸት የማሳመን፣ ለሥራ በቂ ዕውቀትና ክህሎት ያላቸው ናቸው፡፡ ከደመወዛቸው በተጨማሪ ገቢ እንዴትም ማግኘት ይፈልጋሉ፡፡ ለዚህም የግል የገቢ ማግኛ ዕቅድ አውጥተው ይንቀሰቀሳሉ፡፡ አቅም ስላለቸው የተሠማሩበትን የመንግሥት የሥራ መስክ ያወሳስቡታል፡፡ ለተገልጋይ የተዛባ መረጃ ይሰጣሉ፡፡ በተንኮልና በውሸት የተካኑ ናቸው፡፡ አገልግሎት ለማግኘት የሚመጡ ተገልጋዮች ጉቦ እንዲሰጥዋቸው የተመቻቸ ሁኔታ ይፈጥራሉ፡፡

 የገባው (አራዳው) ተገልጋይ ጉቦ ሰጥቶ አገልግሎት ሲያገኝ፣ ያልገባው ተገልጋይ ደግሞ በደላላ አማካይነት አዕምሮው ተዋክቦ ጉቦ ከፍሎ አገልግሎት ያገኛል፡፡ እነዚህ ሰዎች በሰጥቶ መቀበል መርህ ለሚንቀሳቀሱ ተገልጋዮች ንቁህ አዕምሮ ያላቸው ናቸው፡፡ የመንግሥት ሀብትና ንብረት በሕገወጥ መንገድ ይጠቀማሉ፣ ሌሎችም እንዲጠቀሙ ያደርጋሉ፡፡ ተጨማሪ ገቢ ስለሚፈልጉ ከመንግሥት በጀት ላይ የግል ድርሻቸውን ለማግኘት የተለያዩ ዘዴዎችን ይነድፋሉ፡፡ የማይሳካለቸውን ትተው የሚሳካውን ሥልት በመጠቀምና ግዥዎች በማወሳሰብ ጥቅም ያገኛሉ፡፡ ለዚሀ ማሳያ የዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታል የመድኃኒት ግዥና አስተዳደር ላይ የቀረበውን የኢብኮ ዘገባ ከዩቲዩብ ማየት በቂ ነው፡፡

ሀብታም ለመሆን የሚፈልጉ ተገልጋዮች እነዚህን ሰዎች በስፋት ይጠቀማሉ፡፡ በአቋራጭ ሀብታም የሆኑና የበለጠ ሀብት ለማግኘት ሲሉ የእነዚህን ሰዎች እጅ ጠምዝዘው ጭምር የሚፈልጉትን ጥቅም ያገኛሉ፡፡ በተለይም ልማታዊ ያልሆኑ ባለሀብቶች የመንግሥት አመራሮችና ሠራተኞችን በጥቅም በማንባርከክ የመንግሥትን ጠንካራ ሕግ ለመሻር ተግተው ይሠራሉ፡፡ ለእነሱ የማጭበርበር ፍላጎት የሚያመች ሕግ እንዲወጣ ከጀርባ ሆነው በትጋት ይሠራሉ፡፡ አሳሪ የሆኑ ሕጎችን ያስቀይራሉ፡፡ በጥልቀት የመታደስ ንቅናቄው ሰነድ ውስጥ ይህን የሚያመለክትና የሚያጠናክር ሐሳብ ያነበብኩ ይመስለኛል፡፡

ሌላው መልካም አስተዳደር ለማስፈን እንቅፋት የሚሆነው የአመራርና የሠራተኞች የኪራይ ሰብሳቢነት የአስተሳሰብ ችግር ነው፡፡ የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት ችግር ያለባቸው አመራሮችና ሠራተኞች ሥራ የሚሠሩት ለራሳቸው ገቢ ፍለጋ መሆኑን እያወቁ ሁሌም መንግሥትን ያማርራሉ፡፡ ጧት ሥራ ሲገቡ ተገደው እንዲገቡ እንደተደረጉ ያስባሉ፡፡ ሁሌም ይህ መንግሥት ለምን ደመወዝ አይጨምርም የሚል መፈክር ያሰማሉ፡፡ በእርግጥ ከፍተኛ የኑሮ ውድነት በተለይም በከተሞች ውስጥ መኖሩ ይታወቃል፡፡ የቤት ኪራይ ውድ ነው፣ አከራዮች በየጊዜ የኪራይ ዋጋ ይጨምራሉ፡፡

መንግሥት ሠራተኞች የትራንስፖርት አገልግሎት በነፃ እንዲያገኙ ቢያደርግም ጧት መነሳትን ስለማይፈልጉ ሥራ አርፍደው ሥራ ይገባሉ፡፡ በመሆኑም ለትራንስፖርት ወጪ ይጋለጣሉ፣ በራሳቸው ጥፋት መንግሥትን ያማርራሉ፡፡ ስህታተቸውን ስለማይረዱ ሁሌም ከአፋቸው የሚወጣው ይህ መንግሥት ለምን ደመወዝ አይጨምር የሚል ነው፡፡ የተሰጣቸውን ነፃ የትራንስፖርት አገልግሎት በመርሳት መንግሥት ለምን የትራንስፖርት ችግር አይፈታም እያሉ ያመርራሉ፡፡ የተሠማሩበትን ሥራ በቅልጥፍና ለመሥራትና ውጤታማ ለመሆን አያስቡም፡፡ ሁሌም እከሌ የሚባል መሥሪያ ቤት ብዙ ደመወዝ ይከፍላል፣ ለእኛ ግን አይጨመርም፣ መንግሥት የሀብት ክፍፍል ላይ ያዳላል ይላሉ፡፡ የቅልጥፍናና የፈጠራ አመለካከት ከእሱ በጣም የራቀ ነው፡፡

በእርግጥ የፈጠራና የኢንትርፕራነር ተሰጥኦ ያለቸው አመራሮችና ሠራተኞች ከፍተኛ ደመወዝ ወደሚከፈልበት ይሄዳሉ፡፡ ወይም የግል ሥራ የመፍጠር አቅም ስላለቸው በመንግሥት ተቋም ውስጥ እምብዛም ተቀጥረው አይሠሩም፡፡ እንግዲህ የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት መገለጫው የሚመጣው እዚህ ላይ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያሉት ግን ያልሠሩትን ማግኘት ይፈልጋሉ፣ ይመኛሉ፡፡ በተሰማሩበት የሥራ መስክ ምንም ተጨማሪ ነገር ሳይሠሩና ውጤት ሳያስመዘግቡ ተጨማሪ ጥቅም ብቻ ይፈልጋሉ፡፡ በመካከላቸው ጠንካራ ሠራተኛና አመራር ካለ የት ልትደርስ ነው ይላሉ፣ ያሸማቅቃሉ፣ ይፈታተናሉ፣ በሥራው ውጤታማነት ላይ አቃቂር ያወጣሉ፡፡

የትርፍ ሰዓት ሥራ በመሥራት እንኳን ገቢያቸውን ለማሳደግ ፍላጎት የላቸውም፡፡ ለተከፈላቸው በቂ አገልግሎት ሳይሰጡ መንግሥት የደመወዝ ጭማሪ እንዲፈቅድ ያልማሉ፡፡ ሥራ አርፍደው ስለሚመጡ ተገልጋይ ይጉላላል፡፡ ሁሌም የኑሮ ውድነትን እያሰቡ ስለሚሠሩ ወይም አገልግሎት ስለሚሰጡ ሥራን ከልባቸው አይሠሩም፡፡ ግማሽ ሐሰባቸው በቤት ኪራይ ውድነት፣ በልጅ ትምህርት ቤት ክፍያ መጠን ማደግ፣ በቤት ውስጥ ቀለብ ማነስ፣ በትራንስፖርት ችግር ላይ ስለሆነ ለተገልጋዩ ብዙ አያስቡም፣ ደንታም አይሰጡም፡፡ ለተገልጋዮች ተደጋጋሚ ቀጠሮ ይሰጣሉ፡፡ በስብሰባ ላይ መቀመጥንና ጊዜ አሳልፈው መሄድን ይመርጣሉ፣ ሻይ ባይጠጡ እንኳን ሻይ ቤት ወይም መዝናኛ ክበብ ውስጥ መቀመጥን ያዘውትራሉ፡፡ ላይብረሪ ጋዜጣ በማንበብ ጊዜ ያሳልፋሉ፡፡

ከላይ የተገለጹት የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰቦች እያደጉ ስለሚመጡ፣ ተመሳሰይ አስተሳሰብ ካለቸው የሥራ ባልደረቦች ጋር ሲገናኙ የመንግሥትን የልማት እንቅስቃሴ ያንቋሽሻሉ፣ መንግሥትን ያማሉ፡፡ ከሌሎች ሥርዓቶች ጋር እያነፃፀሩ የበፊቱ የተሻለ ነው ይላሉ፡፡ ለምሳሌ የደርግ ወይም የንጉሡ ዘመን እያሉ ያወራሉ፣ ያስወራሉ፡፡ የእከሌ መንግሥት በነበረበት ወቅት ጥሩ ጥቅም አገኝ ነበር አሁን አጣሁ ይላሉ፡፡ አንዱን ብሔር ከሌላው ያስበልጣሉ፡፡ መንግሥት የሚሠራቸው የልማት ሥራዎች ለእሱ አይዋጥላቸውም፡፡ ለእነሱ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ምናቸውም አይደለም፡፡ መንግሥት ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ስለመሆኑ ምን ማረጋገጫ አለው ይላሉ፡፡ በመንግሥት ተቋማት እየተተገበረ ያሉ የለውጥ መሣሪያዎች በአግባቡ አልተተገበረም ይላሉ፡፡ በተቋም ውስጥ ለውጥን የሚመሩ ሰዎች አቅም የሌላቸው ናቸው የሚል ወሬ ይነዛሉ፡፡ ግን አማራጭ የለውጥ ትግበራ ሐሳብ ለማቅረብ አቅም የላቸውም፡፡ በከተማ ውስጥ የሕንፃዎች መብዛት የእኔን ሕይወት አይቀይርም እያሉ ያማርራሉ፡፡ መንግሥት ቤታቸው ድረስ ደመወዝ እንዲልክላቸው ይፈልጋሉ፡፡

በተቀራኒ ደግሞ አቅም እያላቸው መንግሥትን የሚያሙት የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ የሚያራምዱ ሠራተኞችና አመራሮች ተጨማሪ ገቢ ሊያገኙ የሚችልበት መስክ ያስሳሉ፣ ዕቅድ ያወጣሉ፣ በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ተግባራዊ ያደርጋሉ፡፡ በዚህም የመንግሥት ንብረት ይዘርፋሉ፡፡ ጥቅም ለማግኘት ሲል አድሎአዊ ሥራዎችን ይሠራሉ፡፡ የማጭበርበር ሥራዎችን ያከናውናሉ፡፡ በተለይም የሚሰጠው አገልግሎት ከተገልጋይ መስተንግዶ ጋር የተያየዘ ከሆነ ጥቅም የሚያገኙባቸውን ሥራዎች አሳደው ይሠራሉ፡፡ እነዚህን በጥልቀት የመታደስ ንቅናቄ ሥራ አይለውጣቸውም፡፡ መንግሥትና ሕዝብን እያቃቀሩ ይኖራሉ፡፡ የመንግሥት መሥሪያ ቤትን በጡረታ ወይም በሞት ካልሆነ በስተቀር አይለቁም፡፡ በዲስፕሊን ተጣርቶ እንዳይበራሩ ሥራቸው በሥውር ነው፡፡ ካልተነቃባቸው ጥቃቅንና ከፍተኛ ሙስናዎችን ይሠራሉ፡፡ ሌቦች ስለሆኑ የመንግሥትን አገልግሎት ማጥላላት፣ ጥላሸት መቀበትና ውሸት ማስወራት ይወዳሉ፡፡ ሰው አቅሙን በማሳደግ ውጤታማ ሥራ ሲሠራ አይዋጥላቸውም፡፡

መንግሥት ይህን በመረዳት በተቋማት የጥልቅ ተሃድሶ እንዲካሄድ አቅጣጫ ሰጥቷል፡፡ የጥልቀት የመታደስ ንቅናቄ ፕሮግራም መኖሩ በጣም ጥሩ ጅማሮ ነው ሚል አስተያየት አለኝ፡፡ ቢያንስ በተለይም ከላይ የተጠቀሱት ችግሮች ያሉባቸው ሠራተኞች እንደተነቀባቸው እንዲያወቁት ያደርጋል፡፡ ሌሎች ታታሪና ሥነ ምግባር ያላቸው ሠራተኞች በሆዳቸው ይዞውት የነበረውን ችግርና ቂም በአደባባይ ለመጋለጥ ዕድል አግኝተዋል፡፡ ይህም ሆኖ ግን ችግር ያለባቸው አመራሮችና ሠራተኞች ከሌሎች የሚነሱ ችግሮችን ላለመቀበል በጣም ሲንፈረፈሩ ነበር፡፡

 እኔ ችግር አለብኝ ልታረም የሚል ሰው አለመኖር የሰዎች ባህሪ ቢሆንም፣ አንዳንድ የቀናነት ባህሪ የሚስተዋልባቸው በጣም ጥቂት ሰዎች ጥፋት ባይኖርብኝም ውስንነት አለብኝ ማለታቸው ለእኔ በቂ ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ችግሩን ውጫዊ ያደርጉታል፡፡ ወይም ወደ ሌላ አካል እጃቸውን ይቀስራሉ፡፡ ሆኖም ግን የተሃድሶ ፕሮግራም እንደ አሁኑ ለዓመታት ቆይቶ መምጣት የለበትም፡፡ የአንድ ጊዜ ሥራም ሊሆን አይገባም፡፡ በበጀት ዓመት በየስድስት ወራት ሊካሄድ ይገባል፡፡ የመንግሥት ተቋማት ተከታታይነት ያለው የአመለካከት ለውጥ የሚያመጡ ሥልጠናዎችን እንዲሰጡ፣ በመንግሥት በኩል ግልጽ አቅጣጫ ሊቀመጥና ሊተገበር ይገባል፡፡

በአሁኑ ተሃድሶ ቢያንስ ውስንነት አለብኝ ያሉት ቦታቸውን ለሌለ ኃላፊና ሠራተኛ በመልቀቅ ሌላ ሥራ እንዲሠሩ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ መንግሥትም ለዚህ ግልጽ አቅጣጫ ማስቀመጥ አለበት፡፡ አቅም ያላቸውና ታታሪ የሆኑ አመራርና ሠራተኞች ተለይተው እንደገና ምደባ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡ በተለይም ከተገልጋይ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ባለቸውና በተለይም በጣም ትኩረት የሚሰጥባቸው ቦታዎች በየጊዜው ዕድሳት በሚደረግ የኮንትራት ቅጥር ሠራተኞች መያዝ ይኖርባቸዋል፡፡ የኮንትራት ቅጥሩ የዓመት፣ የሁለት ዓመትና ከዚያ በላይ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለሆነም መንግሥት የመልካም አስተዳደር ችግሮች የሚስተዋልባቸው፣ በተለይም የዕለት ተዕለት አገልግሎት መስጫና ከፍተኛ የሀብት እንቅስቃሴ የሚደረግባቸው የሥራ ቦታዎች ላይ፣ በጊዜ ገደብ ዕድሳት በሚደረግበት የኮንትራት ቅጥር ሠራተኞችና ኃላፊዎች አገልግሎት እንዲሰጥ ቢደረግ አሁን እየታየ ያለው የመልካም አስተዳደር ችግር ሊቀረፍ ይችላል፡፡

ዳታኛ የሆነና ችግር ላለበት አመራርና ሠራተኛ የኮንትራት ቅጥር ዕድሳት ላለማድረግ በጣም ዕገዛ ያደርጋል፡፡ ስለሆነም የኮንትራት ቅጥር አመራርና ሠራተኛ ሥራውን ተጠንቅቆ እንዲሠራ፣ የመንግሥት አገልግሎትን በጥንቃቄ እንዲሰጥ አስገዳጅ ሁኔታ ይፈጥራል የሚል አስተያየት አለኝ፡፡ ከዕድሳት ጋር ሠራተኛው ራሱን እንዲያየው ሊያደርግ ስለሚችል፣ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ ቢያስብበት መልካም ነው የሚል አስተያየት አለኝ፡፡ አፍሪካን ጨምሮ በብዙ አገሮች ይህ ተግባራዊ እንደሚደረግ አውቃለሁ፡፡ መንግሥት በሚገባ ያስብበት፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው muluqene@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡      

Standard (Image)

ትውልድን የመታደግ አደራና የገባንበት አጣብቂኝ

$
0
0

በሒሩት ደበበ

ለዛሬ አሁን ያለውን ትውልድ ስኬት በማንሳት ላሰለቻችሁ አልሻም፡፡ ይልቁንም እንደ አገር በማኅበረሰቡ በተለይም በወጣቱ ትውልድ ላይ የተደቀኑ ፈተናዎችን መንቀሴን መርጫለሁ፡፡ ከዚያም አልፎ የወደፊቷ ኢትዮጵያ እንደ መርግ ሊጫናት ያረበበውን አስከፊ ሁኔታ ሁሉ በማንሳት የመነጋገሪያ አጀንዳ ለመሰንዘር እሞክራለሁ፡፡ ለዚህም ስል ‹‹እውነትን ሰቀሏት›› በሚለው የግጥም መድብሉ የሚታወቀውን ሰለሞን ሞገሥ (2001) አንድ ግጥም የጽሑፌ መግቢያ አድርጌዋለሁ፡፡

አክሱም አቃጥሉት

በሥውር - በሥውር ሳትወጡ ይፋ፣

አክሱምን አቃጥሉት ላሊበላም ይጥፋ!

ሁሉም ቢተባበር የሚያቅት አይደለም፣

ጢያና ጀጎልን ባንድ ላይ ለማውደም፤

መስጅድ ቅርሳ ቅርሱ፣ ፍልፍል ቤተ መቅደስ፣

በዘዴ በዘዴ በየተራ ይፍረስ፤

የጥበብ መጻሕፍት ጥንታዊ ብራና፣

በእሳት ይቃጠል ጋዝ ይርከፍከፍና!

የአያቶቹ ጥበብ ደብዛው የጠፋበት፣

ለምን ይኼ ትውልድ ወቀሳ ይብዛበት?

አክሱም ፋሲል ግምብን ማቃጠል ነው ጥሩ፣

በዘመናችን ላይ እንዳይመሰክሩ!!

      በእርግጥ እነዚህ ስንኞች ‹‹ሁሉ ድሮ ቀረ›› የሚሉ ሊመስሉ ይችላሉ፡፡ የቀደመው ትውልድ የአክሱም ሐውልቶችን፣ የጎንደር ግንብን፣ የላሊበላን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ኪነ ሕንፃዎች የጀጎል ግንብ ወዘተ ሲያንፅ የአሁኑስ ምን ሠራ? በደምሳሳው የሚልም ይመስላል፡፡ ይሁንና ከግንብና ከግድብ በላይ በአስተሳሰብ አገራዊ ፍቅር፣ ሞራላዊና ሥነ ምግባር ያለው ትውልድ እየተገነባ ነው ወይ? የሚለው ነው አንገብጋቢው ጥያቄ፡፡ በዚህ ጸሐፊ ዕይታ ግን ትውልዳዊ ክፍተት የተፈጠረባቸው ተጨባጭ ምልክቶች እየተንፀባረቁ ነው፡፡

ብዙዎች እንደሚስማሙት በአሁኒቷ ኢትዮጵያ የብሔር ብሔረሰቦችን መብት፣ ቋንቋ፣ ታሪክና ማንነት. . . ብዙ የተባለላቸውን ያህል ስለ አገራዊ ክብር፣ የጋራ እሴትና አንድነት የተባለው ከበቂ በታች ነው፡፡ ለዚህም፣ ነው ብሔር ተኮሩ ፌዴራሊዝም ዴሞክራሲያዊ አንድነትን አልገነባም እየተባለ ያለው፡፡ አንዳንዶችም በሕዝቦች አንድነት ላይ ብሔራዊ መግባባት ባለመፈጠሩ፣ አንዱ ማኅበረሰብ ወደ ሌላው አካባቢ በነፃነት ተንቀሳቅሶ መኖርና መሥራት የሚቸገርበት ድክመት መፈጠሩን በፀፀት እየገለጹ የሚገኙት፡፡

የሥርዓቱ ነፀብራቅ የሆነው አዲሱ ትውልድ ‹‹ከኢትዮጵያ አገሬ፣ ወደ መርካቶ ሰፋሬ ወርዷል፤›› ሲል የመንደርተኝነቱን መባባስ ክፉኛ የተቸው መንግሥታዊው ዘመን መጽሔት በኅዳር 2009 ዕትሙ ነው፡፡ ትውልዱ የጋራ አገር፣ የወል ባንዲራ፣ መግባቢያ የጋራ ቋንቋ፣ የአብሮነት፣ የጋራ እሴት፣. . . የሌለው ይመስል በየቀበሌ አድባር ሥር እንደተወሸቀ ነው፡፡ ‹‹ትልቁ›› ምሁራን የፖለቲካ ልሂቃን የሚባለው እንኳን የብሔር ባርኔጣ የሚጎትተው ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን ለአገራች ሉዓላዊነት ቀናዒነት የነበራቸው፣ በሃይማት መቻቻልና አብሮነት የሚጠቀሱ፣ የመረዳዳትና እንግዳ የመቀበል. . . እሴት የነበራቸው ድንቅ ሕዝቦች ናቸው፡፡ አሁንስ እነኝህ እሴቶች አሉ ወይ? ነው ጥያቄው፡፡

ኢትዮጵያውያን በጭቆና ውስጥ እንኳ ሆነው የአገዛዞቹን ጥሪ የሚሰሙ፣ አገራዊ የእኔነት ስሜት ያላቸው፣ ከልዩነቱም ቢሆን የጋራ ታሪክ (በተለይ የነፃነት) ለመገንባት የሚጥሩም ነበሩ፡፡ ለዚህም ነው የሰሜኑ ከደቡብ፣ የምሥራቁ ከምዕራቡ ሕዝብ ታሪክ ጋር እየተጋመደ የሦስት ሺሕ ዓመታት ባለታሪክ ሲያስብለን የኖረው፡፡ አሁንስ ይኼ እውነታ አድጓል ወይስ ቀጭጯል? ነው ጥያቄው፡፡

አሁን አሁን ያለው የታሪክ መጎተት፣ ‹‹የእኛና የእነሱ›› ሙግት በአንድ አገር ውስጥ የምንኖር ሕዝቦች አላስመስል ብሎናል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር የአገሪቱ ሕዝብ በስደት ላይ ነው፡፡ አሁንም የያዘ ይዞት እንጂ ከአገር በመውጣት በየበረሃው የሚወድቀውና ውቅያኖስ የሚበላው ቁጥሩ ትንሽ አይደለም፡፡ በአገሩ ጥሮ ግሮ የሚቀየር የለም ባይባልም፣ ሒደቱ ብዙኃንን እያሳተፈ ለመሆኑ ያጠራጥራል፡፡ ምክንያቱም አሁንም ከ22 በመቶ የማያንስ ሕዝብ ከድህነት ወለል በታችና 17 በመቶ ሥራ አጥ መኖሩ አባባሉን የሚያሳይ ነው፡፡

ከዚህ አንፃር አዲሱ ትውልድ ከማኅበራዊ ድረ ገጽ የክፋት ወሬዎች፣ ከአልባሌ ሱሰኝነትና የጎጠኝነት ንትርክ ወጥቶ በድህነት ላይ ለመዝመትም ሆነ ዴሞክራሲያዊት አገር ለመገንባት በአንድነት ሊቆም ይገባዋል፡፡ የተፈጠሩ ዕድሎችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም ፍትሐዊነትና አሳታፊነትን በትግሉ ዕውን ማድረግም ይኖርበታል፡፡ ይህ ሲሆን ነው ከስሜት ወጥቶ በምክንያታዊነት ላይ የተመሠረተ ጥያቄ፣ ታቀውሞና ድጋፍ ሊያራምድ የሚችለው፡፡ አሁን በተጀመረው መንገድ እየተጓዘ ትውልዳዊ ኃላፊነትን መወጣት ግን በእጅጉ ከባድ ነው፡፡

በእርግጥ ትውልድን መውቀስ ቀላል ይመስላል፡፡ ምንም ተባለ ምን አሁን ያለው የእኛ ትውልድ ከቀደሙት ኢትዮጵያዊ ትውልዶች የሚያንስባቸው ጉዳዮች የሚበዙ ይመስለኛል፡፡ ለዚህ ደግሞ የዓለም ነባራዊ ሁኔታ፣ የተጠራቀመው ችግራችንና ሥርዓቱና አገራዊ ልማዱ የየራሳቸው አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚኖራቸው ጥርጥር የለውም፡፡ ቀጪና ተቆጪ የጠፋበት፣ መተፋፈርና ፈሪኃ እግዚአብሔር የተዳከመበት የጉድ ጊዜ እየመጣ እንዳይሆን ያሳስባል፡፡

ይህ አባባል ልቦለድ ሳይሆን እውነት መሆኑን የሚያረጋግጠው በእምነት ተቋማት ሳይቀር ውሸት፣ ማጭበርበር፣ የሥልጣን ሽኩቻና ምድራዊ ፉክክር አይሎ መታየቱ ነው፡፡ ከታችኛው የትምህርት ደረጃ አንስቶ መኮረጅ፣ ኮፒ አድርጎ ፈተና ማለፍ በርክቷል፡፡ በሐሰተኛ የትምህርት መረጃ ሥራ መያዝና ገንዘብ መሰብሰብ ብቻ ሳይሆን፣ አገር መምራትም ‹‹ኖርማል›› ሆኗል፡፡  ይህን ጽሑፍ በምጽፍበት አንድ ምሽት በብሔራዊው የአገራችን ቴሌቪዥን ጣቢያ ከጋምቤላ ክልል ካቢኔ አባላት ዘጠኝ ያህሉ በፎርጅድ (ሐሰተኛ) የትምህርት መረጃ ወንጀል ተጠርጥረው መባረራቸውን ሰማሁ፡፡

እውነት ለመናገር ምርመራው ተጠናክሮ ከቀጠለ ግን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና በአንዳንድ የፌዴራል መሥሪያ ቤቶችም የባሰ ውጤት ሊገኝ ይችላል፡፡ በተለይ በርቀት ትምህርትና በውጭ ሥልጠና ስም ተወዳድሮ ማሸነፍ የማይችለው ግብስብስ ሁሉ፣ የፓርቲና የመንግሥት ሥልጣን ካባ እየደረበ አገር እየበደለ ይገኛል፡፡ በንፋስ አመጣሽ መንገድ የደለበ አንዳንዱ ‹‹ባለሀብትም›› አዋቂ ለመባል ያህል የትምህርት ማዕረግ ሲያግበሰብስ ማየት፣ ሥልጣንና ገንዘብ ከዕውቀትም በላይ ናቸው የሚለው ድምዳሜ እንደ ጉም አገሩን እንዲጋርደው እያደረገ ነው፡፡

በዕውቀት፣ በብቃትና በተወዳዳሪነት ላይ ያልተመሠረተ የአገር ግንባታ ሥር እንዳይሰድም ሊደረግ ይገባል፡፡ ገና ከዩኒቨርሲቲ ጀምሮ ወደ ፓርቲ አባልነት ወይም ከምክንያታዊ አስተሳሰብ ይልቅ ወደ አድርባይነት የሚጣበቅ ትውልድ እየታየ ነው፡፡ በእንዲህ ያለ መርህ አልባ ጉዞ የሚነጉድ ኃይል ደግሞ ሄዶ ሄዶ ለመልካም አስተዳደር ብልሽት፣ ለኢፍትሕዊነትና ለሙስና የተጋለጠ መሆኑ የሚገርም አይሆንም፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየታየ እንዳለውና መንግሥትም እንዳረጋገጠው፣ በአገሪቱ  በአቋራጭ መበልፀግና ሥልጣንን ያላግባብ መጠቀም ጎልቶ ታይቷል፡፡ ትናንት ባዶ እጅ የነበሩ አንዳንድ አባላት በአገርና የሕዝብ ሀብት ላይ እያዘዙ መበልፀጋቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ በተለይ የከተማ መሬት፣ የቀረጥና ግብር ጉዳይ፣ ኮንትሮባንድ፣ የመንግሥት ግዥና ሽያጭ፣ እንዲሁም የኮንትራት ግዥ ላይ የሚታየው ጥፋት ከወዲሁ ወገቡን ካልተመታ አገር የሚያፈርስ ነው፡፡ ይህ የሥርዓት ብልሽት ደግሞ ያለ ጥርጥር ትውልዱን ሌብነት እንዲጫጫነው አድርጎታል ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡

እንግዲህ አሁን ያለውን ትውልድ ከኩረጃና ከሌብነት አውጥቶ ለተሻለ ውጤት ለማድረስና አገር ገንቢ እንዲሆን ለማስቻል ብዙ ሥራ ማከናወን ያስፈልጋል፡፡ ከሃይማኖት ተቋማት ጀምሮ፣ ትምህርት ቤቶች፣ መንግሥትና የሲቪክ ማኅበራትም ኃላፊነታቸው ከፍ ያለ ነው፡፡ የራሱ የትውልዱ ሚና ግን ተኪ ሊኖረው አይችልም፡፡

ይኼ አገር የታሪክ ችግር ያለበት አይደለም፡፡ የውጭ ወራሪን በሌለ አቅምና በኋላ ቀር መሣሪያ ቀጥቅጦና ደጋግሞ ካሳፈረው ቀደምቱ ትውልድ አንስቶ ‹‹ፋኖ ተሰማራ እንደ ቼጉ ቬራ. . .›› እያለ በረሃ ወርዶና ተፋልሞ አምባገነን ሥርዓቶችን እስካሽቀነጠረው የቅርቡ ትውልድ ድረስ ብዙ መስዋዕትነት፣ ገድልና ትርክት ሞልቶናል፡፡ እውነት ለመናገር ድሮም ሆነ ዛሬ በግል ጥረታቸውና በላባቸው ሠርተው የተቀየሩ (ነጋዴዎች፣ ሯጮች፣ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ ምሁራንና የፈጠራ ሙያተኞች. . .) ቁጥራቸው አይበርክት እንጂ ታሪክ ሠሪነታቸው ሊናቅና ሊንኳሰስ አይገባም፡፡

አሁን አሁን እየመጣ ያለው አዲስ ትውልድ ግን ይህን እውነት ምን ያህል ይገነዘባል? የራሱንስ የታሪክ አሻራ ለማሳረፍ ምን ያህል ይተጋል? ነው የጥርጣሬ ጥያቄው፡፡ በአንድ በኩል ትውልዱ በአወዛጋቢ እውነታዎችና በግል ፍላጎት በተጠመዘዙ መረጃዎች እየተደናገረ ይመስላል፡፡ በሌላ በኩል ‹‹ታሪክን አድንቆ ታሪክ ለመሥራት እንዳይተጋ›› ብዙ እንቅፋቶች እየተደነቀሩበት ያለ ባለአደራ መስሏል፡፡ መገናኛ ብዙኃኖቻችን፣ የፊልም፣ የቴአትርና የሥነ ጽሑፍ ለዛችን ሁሉ ‹‹እንትንሽ እንትንህ›› ውስጥ ገብቶ መስመጥ ዓላማው ይኼው መስሏል፡፡

እዚህ ላይ መንግሥታዊ ሥርዓቱም ቢሆን ከ25 ዓመታት ወዲህ ላለው ስኬት እንጂ፣ ከዚያ በፊት ለነበሩ ጭላንጭል በጎ ሥራዎች ዕድል አለመስጠቱ የራሱን ተፅዕኖ አላሳደረም ማለት ያዳግታል፡፡ ከቀደሙት ሥርዓቶችም ሆነ ሕዝብ ጥፋትና ጉድለት የመኖሩን ያህል በጎነት፣ ጀግንነት፣ አንድነትና ሃይማኖተኝነት የሌለ ይመስል ሲድፈነፈን መታየቱ ትውልዱ ለአዲስ ታሪክ እንዳይነሳም እያደረገው ነው ባይ ነኝ፡፡

ከዚያ ይልቅ የእኛ ትውልድ እንቅልፍ እያጣበት ያለው ጉዳይ ስደት፣ የሌላውን ዓለም ‹‹ሞዴል›› ማድነቅና ለራሱ ትውፊት ትኩረት ያለመስጠት ሆኗል፡፡ ጠዋት ማታ አገሩን ከሚያደነቁሩት ሬዲዮኖች ጀምሮ የአውሮፓን እግር ኳስ ከነቅንጥብጣቢው ማመንዥክ ተለምዷል፡፡ ለሽብርም ሆነ ለጥፋት ወሬ ቀልብን ሰጥቶ መመሰጥም አለ፡፡ ይህ የማይጠቅም አካሄድ ደግሞ ትውልድን ከታሪክ ሠሪነት ያናጥባል፡፡ የአገሩን ታሪክ አውቆ፣ በጋራ እሴት ላይ እንዲቆም የሚረዳውን ተመራማሪነት እንዳያጠናክርም ያውከዋል፡፡

የማይካደው እውነት በመንግሥታዊ ሥርዓት ደረጃ እየተሠራ ያለ ታሪክ መኖሩ ነው፡፡ እንደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ፣ የባቡር መስመር ዝርጋታ፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት፣ የማኅበረ-ኢኮኖሚያዊ ግንባታዎች . . . ያሉ አመርቂ የልማት ፍሬዎችን እያሳየ ነው፡፡ ይህ የፍጥነትና የጥራት ጥያቄ ብቻ ሊሳበት የሚችል የልማት መስክ፣ ‹‹ድህነትን ታሪክ ለማድረግ ለሚሠራ ትውልድ ራሱን የቻለ ታሪክ›› እንደሆነ ጥርጥር የለውም፡፡ ግን የብዙኃኑን አዲስ ትውልድ ቀልብ ሰቅዞ የሚይዝ አገራዊ ራዕይና ‹‹እኔነትን›› የሚፈጥር አስኳል መሆን አለበት፡፡

በአጠቃላይ አሁን ያለው ትውልድ ያለውን ዕድልና መልካም አጋጣሚ ያህል የገባበት ልክ ያልሆነ አካሄድም አለ፡፡ በተለይ ከታሪክ አዋቂነት፣ ከብሔራዊ መግባባት፣ ከዴሞክራሲያዊ አንድነትና ከታሪክ ሠሪነት ውጪ ሆኖ ረዥም ርቀት መሄድ አይቻልምና ሊታሰብበት ይገባል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

 

Standard (Image)

ለተጠናወቱን ችግሮች ዓይንና ልቦናን መክፈት ይበጃል

$
0
0

በደጊቱ ቱፋ

ኢትዮጵያ በብዙኃንነት ብቻ ሳይሆን በሕዝብ ቁጥርም ትልቅና ሰፊ የምትባል አገር ነች፡፡ ከ80 የማያንሱ የራሳቸው ባህል፣ ቋንቋና ማንነት ያላቸው ብሔር ብሔረሰቦችና በጥቂት ዓመታት ውስጥ 100 ሚሊዮን የሚደርስ ሕዝብ ያላት አገር መሆኗን ያስታውሷል፡፡ እስከ ቅርብ ዓመታት ድረስ የዓለም ጭራ ደሃ አገር፣ በጦርነትና በኋላ ቀርነት የኖረች ምሥራቅ አፍሪካዊት ቀደምት ምድር የሚል ስያሜ ተሰጥቷት ቢቆይም፣ አሁን አሁን በሌላ ገጽታ ስሟ እየተነሳ ይገኛል፡፡

አሁን ኢትዮጵያ የፈጣን ልማትና የተከታታይ ዕድገት ተምሳሌት (በተለይ ከምዕተ ዓመቱ ግብ አኳያ)፣ የሰላም አስከባሪ ሠራዊት ዋነኛ አሳታፊ፣ በአገር ውስጥም አንፃራዊ ሰላምና የተረጋጋ ሁኔታ ያለባት ተደርጋ እየተወሰደች ነው፡፡ በአትሌቲክሱ መስክ ስሟ ተደጋግሞ መጠራቱ፣ ቡናና አበባን የመሳሰሉ ልዩ የኤክስፖርት ምርቶች መጠናከርና የታሪክና የብዙኃንነት ገጽታዋ የቱሪስት መስህብ የመሆናቸው ዕድልም፣ ገጽታዋን በመቀየር ረገድ ዓይነተኛ ሚና በመጫወት ላይ ናቸው፡፡

ለእነዚህና ሌሎች ተስፋ ሰጪ ስኬቶች የዓለም ነባራዊ ሁኔታና የአጋር አካላት መብዛት ወይም ሉላዊነት (Globalization) የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ብቻ አመስግኖ ማለፍ አይቻልም፡፡ ይልቁንም ባለፉት 25 ዓመታት አገሪቷን የመራው ኢሕአዴግና በእርሱ የሚመራው መንግሥት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች እንዲሁም አሠራር፣ አደረጃጀትና አመራር ከፍተኛውን ሚና እንደተጫወቱ መጥቀስ ተገቢ ነው፡፡ ሕዝቡ ራሱም የተፈጠረለትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም እጁን አጣጥፎ ከመቀመጥና ተስፋ ከመቁረጥ በመውጣት ያደረገው ርብርብ በቀላሉ አይታይም፡፡

ይህ ሁሉ ሆኖ ሲያበቃ ግን የኢሕአዴግና የመንግሥቱ ዋነኛ ፈተናዎች እንደሆኑ የቀጠሉት የተሟላ ዴሞክራሲንና የጠነከረ መልካም አስተዳደርን የማስፈን ጉዳዮች ናቸው፡፡ ከእነዚህ ጋር የተያያዙት የግልጽነትና ተጠያቂነት መጥፋት፣ የሙስና ማቆጥቆጥ፣ የቡድንተኝነት ፈተናዎች፣ የትምክህትም ሆነ የጠባብነት ልክፍቶች ሥርዓቱን ወደ ብልሸት ይመሩታል የሚል ሥጋት አለ፡፡

ብዙ ጊዜ እንደሚባለው የኢሕአዴግ አብዛኛው ነባር አመራርና አባል ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የታገለና ከብሔር ጭቆና ነፃ ለመውጣት የተፋለመ ብቻ ሳይሆን፣ የገዥዎችን የተዛባ አገዛዝ ለማስወገድ ዋጋ የከፈለ ነው፡፡ ስለሆነም ለታገለባቸው ጉዳዮች መስተካከልና ለዴሞክራሲያዊ ባህል ግንባታ በዋናነት ዘብ መቆም ያለበት ይኼው አካል ነው፡፡ በእርግጥም ብዙዎቹ የከፍተኛ አመራሩ አካላት ይኼንን አስተሳሰብ ሊይዙ እንደሚችሉ መገመት ጤናማነት ነው፡፡ ግን ‹‹ምን ዓይነት ዴሞክራሲ?!›› የሚለው ጥያቄ በግልጽና በማያሻማ መንገድ ካልተመለሰ ሲያወዛግብ መቆየቱ አይቀርም፡፡

ገዥው ፓርቲ አብዮታዊ ዴሞክራሲ፣ ልማታዊ ዴሞክራሲ በኋላም የህዳሴው መስመር የሚለው ከኒዮ ሊብራሊዝም የተለየ ግራ ዘመም ፖለቲካን አዋጭ ነው ብሎ ከያዘ ሰነባብቷል፡፡ ይህንኑ የፖለቲካ ኢኮኖሚ አስተሳሰብ ‹አስመሳይ ዴሞክራሲ፣ ሶሻሊስታዊ ባህሪ የሚበዛበት፣ የተሞላ ዴሞክራሲን ለማስፈን የሚያስቸግር›› እንደሆነ የሚገልጹ አሉ፡፡ ሌላው ቀርቶ በራሱ በኢሕአዴግ ውስጥ ለረጅም ጊዜ የታገሉና አሁን የተነጠሉ ወገኖች ‹‹ኢሕአዴግ ዴሞክራት አልነበረም፣ አይደለም…›› ሲሉ፣ ‹‹ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት፣ የአንዳንዶች ፈላጭ ቆራጭነትን፣ እስካሁን ኅብረ ብሔራዊ ጠንካራ ድርጅት ሆኖ አለመውጣቱን…›› የጠላት ወዳጅ ፖለቲካዊ ጉዞውን በመምዘዝ ሲተቹ ይታያሉ፡፡ ገዥ መደብ ያፈረሰ ፓርቲ በየአካባቢው ሌሎች ‹‹ገዥ መደቦች››ን እየቀፈቀፈ መጥቷል የሚሉ መከራከሪያዎች ይደመጣሉ፡፡

በዚህ ጽሑፍ ላይ ማተኮር የተፈለገው ግን የኢሕአዴግን ዴሞክራሲያዊ ጥረትና የመልካም አስተዳደር መስፈን ትግል እያንሻፈፈው ያለውን የበታች መንግሥታዊ ድርጅታዊ አካል ችግሮች ማሳየት ነው፡፡ ከዚህ ተነስቶም ራሱ ግንባሩ አሊያም ሌሎች አገር ወዳድ አካላት ሕዝቡን ያሳተፈ መፍትሔ እንዲያቀጣጥሉ የውይይት መነሻን ማንፀባረቅም ነው፡፡ አንባቢያን የመሰላቸውን አቋም የመያዝ መብታቸውን ግን ለመጋፋት አልሻም፡፡

ተደጋጋሚወሬናንግግርተግባርንያዘገያል

ቭላድሚር ኢሊች ሌኒን ከሚጠቀሱለት ንግግሮች አንዱ እንዲህ ይላል፡፡ ‹‹እስካሁን ብዙ ንግግር፣ ውይይት፣ ቧልትና ወሬ አድርገናል፡፡ ከዚህ በኋላ ፈጥነን ወደ ተግባር እንግባ!›› ጠንካራው ኮሚኒስታዊ መሪ ይህን ያለው ወዶ አይደለም፡፡ ይልቁንም ልክ አሁን እንደ አገር እንደተደቀነብን ያለ ሁሉም የአጠቃላዩን ስኬት ብቻ እያደመቀ ማውራት፣ መለፍለፍ፣ የመድረክ አንደኛና ሀቀኛ መሆን ሲበዛና በተግባር መቆራረጥ ሞዴል መሆን የሚችል ሲጠፋበት ነው፡፡

‹‹በኢትዮጵያ ሁኔታ በተለይ በከተሞች መልካም አስተዳደርን ለማረጋገጥ ለምን አልተቻለም?›› ብሎ በድፍረት መጠይቅ ያስፈልጋል፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ በሚመራው ሲቪል ሰርቪስ አንስቶ እስከ ቀበሌ ባሉ የቅሬታ ሰሚና መልካም አስተዳደር ተቋማት ዕውን የአገልጋይነት ቁርጠኛ መንፈስ አለን? ሌላው ቀርቶ ሕዝብ መረጃም ሆነ አገልግሎት የመጠየቅ መብትና ሥልጣን እንዳለው ተረድቶ የሚተገብረው ስንቱ ነው?

ቀደም ባሉት ዓመታት በቢፒአር፣ በቢኤስሲ ወይም በሲቪል ሰርቪስና በፍትሕ ማሻሻያ ሥራዎች በከፍተኛ በጀትና ድካም ግንዛቤ እንዲያዝባቸው ተደርጓል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ መሻሻል የታየባቸው ተግባራትም ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በመረጃ አያያዝ፣ በሲቪል ሰርቪሱ ተደራሽነትና ማብቃት የመጡ መሻሻሎች አሉ፡፡ በብዙዎቹ መሥሪያ ቤቶች የሰው ኃይል፣ የግብዓትና የአሠራር ሥርዓትን ለማሳደግ የተደረገው ጥረትም ፍሬ አላፈራም ሊባል አይችልም፡፡

የተጻፉ መፈክሮች፣ የተደረጉ ስብሰባዎችና ንግግሮችን ያህል ውጤቱ የሚያኩራራ አይደለም፡፡ የፈሰሰውን በጀትም ሆነ የመንግሥት ትኩረትና ድካም የሚመጥን የሕዝብ እርካታም አልተገኘም፡፡ ይኼ ሲባል ከመሬት በመነሳትና በመላምት አይደለም፡፡ ተጨባጩ እውነት ስለሚናገር ነው፡፡

በዘርፉ የተለያዩ  ጥናትን በማድረግ የሚታወቁ አንድ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ የሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ መምህር እንደሚሉት፣ ‹‹የእኛ አገር የመልካም አስተዳደር ዋነኛ ችግር የአብዛኛው ሲቪል ሰርቫንትም ሆነ አመራር አባል ቁርጠኝነት ዝቅተኛ መሆን ነው፡፡ ከሁሉ በላይ በቅንነትና በታማኝነት ሕዝብ ማገልገል የሚሰጠውን ክብርና ሞራላዊ ልዕልና ለማጣጣም የሚመኘው ሰው ቁጥር ዝቅተኛ ነው፡፡››

ምሁሩ ለዚህ ደግሞ ዋነኛ መንስዔ ነው የሚሉት በማኅበረሰቡ ውስጥ ለዘመናት የበላይነት ይዞ የኖረው አመለካከት ‹‹ሲሾም ያልበላ…›› በመሆኑ ነው፡፡ ስለሆነም በታማኝነት ሠርቶና በቅንነት አገልግሎ ሕይወቱን ከሚቀይረው ይልቅ ተብለጥልጦና በአቋራጭ (በእጅ መንሻ) እየሠራ የሚበለፅግና የሚሾም በመብዛቱ ነው፡፡ በራሱ በድርጅቱም ውስጥ ቢሆን እያደር የአድርባይነት፣ የመሸካከምና እከክልኝ ልከክልህ እየበረታ እንደመጣ በየግምገማ መድረኩ ተደምጧል፡፡ ግን አመርቂ የእርምት ዕርምጃ ሊወሰድ አልቻለም፡፡

ተሿሚዎችም ሆኑ ተቀጣሪዎች የፖለቲካ እምነትና የጠራ አመለካከት መያዛቸው ተገቢ ቢሆንም፣ ዕውቀትና ክህሎት ሊኖራቸው ግድ መሆን አለበት፡፡ ዓለምም ሆነ አገሪቱ በፈጣን የለውጥ ምኅዳር ውስጥ መግባታቸው እየታወቀ፣ በትናንት በሬ ለማረስ መመኘት የሚሆን አይደለም፡፡ ስለዚህ ሌኒን እንዳለው እስካሁን በተሳካውም ባልተሳካውም ጉዳይ ብዙ ተወርቷል፣ ስንት ነገር ተነግሯል፡፡ ከአሁን በኋላ ግን ወደ ቁርጠኛ ተግባር መግባት ግድ ይላል፡፡

የታችኛውየኢሕአዴግአመራርዴሞክራሲያዊነትንአልዘነጋውም?

የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ከአንድም በላይ በሆነ ትውልድ ቅብብሎሽ ሊገነባ እንደሚችል ብዙ ነጋሪ አያሻውም፡፡ ይኼ በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በሌላውም ዓለም ቢሆን ያለና የሚኖር ነው፡፡ ይኼን ተጨባጭ ሀቅ በሚታሰበው ጊዜ ዕውን ለማድረግ ግን ከወዲሁ ሥራ መሥራት ግድ ይላል፡፡

በእኛ አገር ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አመቺ የሆነ ሕገ መንግሥት መውጣቱ አንድ ዕርምጃ ነው፡፡ አፈጻጸሙ ላይ ግን ከላይና ከታች የመንግሥት መዋቅር አንፃር ሲመዘን፣ የሁለት መንግሥታት ሕገ መንግሥት መምሰሉ በይፋ የሚናገሩ ብዙዎች ናቸው፡፡

ለዚህ እንደ አብነት የሚጠቀሰው በአገሪቱ የመደራጀትና ያመኑበትን የፖለቲካ እምነት የማራመድ መብት ጉዳይ ነው፡፡ በላይኛው የመንግሥት ኃላፊዎች ዘንድ የፖለቲካ ተፎካካሪነት ሰላማዊና ሕጋዊ መንገድን ይከተል እንጂ ኃጢያት አይደለም፡፡ በአንፃሩም ቢሆን ከኢሕአዴግ ኃላፊዎች ጋር የመነጋገር ዕድልም አለው፡፡ ወደ ታችኛው እርከን እየተወረደ ሲሄድ ግን ሁኔታው ይቀየራል፡፡ ‹‹በሌላ የፖለቲካ ፓርቲ (ተቃዋሚ) ሥር ተደራጅቶ ዴሞክራሲያዊ መብትን ለመተግበር መሞከር በጠላትነት ያስፈርጃል፤›› ይላሉ አንድ ታዛቢ፡፡ ገዥው ፓርቲ አገር እየመራ ያለ አካል በመሆኑ በንግድ፣ በግብርና በታክስ፣ በገጠር የማዳበሪያና የግብዓት አቅርቦት ጫናን በመሸሽ የፖለቲካ ፓርቲዎቹን ለመደገፍም ሆነ ለማረምና ለመተቸት ራሱን የሚያሳምን ሰው ቁጥር እጅግ ዝቅተኛ ነው፡፡

‹‹እንደ አገር የሕግ የበላይነት እያደገ መሄድ ሲገባው አሁንም የአስፈጻሚው ጫና የሕግ ተርጓሚው ላይ በመኖሩ የመደራጀትና ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ ጥቅምን በማስከበር ረገድ ተከራክሮ መርታት እየከበደ ነው፤›› ያሉኝ ደግሞ በመኢአድ ውስጥ በረጅም ጊዜ በአባልነትና በአመራርነት የቆዩ ፖለቲከኛ ናቸው፡፡ ይኼም በመሆኑ በሕጋዊ መንገድ የተቋቋሙ ፓርቲዎች በየክልሉ ጽሕፈት ቤት መክፈትም ሆነ መደራጀት አልቻሉም፡፡ ለመንቀሳቀስ ቢፈቀድላቸውም ለምርጫ ሰሞን ብቻ እየሆነ ነው፡፡

ሌላው የአገሪቱን የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ሸራፋ እንዲሆን እያደረገው ያለ እውነት በክልሎች በተለይ በወረዳዎች ያለው የፖለቲካ አመራር፣ ‹‹ኢሕአዴግ ወይም ሞት›› አስተሳሰብ ነው፡፡ ባለፈው ምርጫ ወቅት በአንዳንድ ቦታዎች እንደታየው ሕዝቡ ፈቀደም አልፈቀደም በወረዳችን ማሸነፍ ያለበት ኢሕአዴግ ብቻ ነው ብለው የተንቀሳቀሱ የሥራ ኃላፊዎች መታየታቸው ይወሳል፡፡ እዚህ ላይ መታወቅ ያለበት የአገሪቱ ሕገ መንግሥት ያጎናፀፈውን መብት ማንም መንጠቅ እንደማይችል ነው፡፡ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ችግር የሚፈጥሩ ሲያጋጥሙ የማረቅ ኃላፊነት የማን ነው? ይኼ በብርቱ ሊታሰብበት ይገባል፡፡

ዴሞክራሲያዊነትሲደበዝዝግልጽነትናተጠያቂነትይንበረከካል

ሰላማችን ያኮራናል፡፡ ልማታችን ያለጥርጥር እየተጠናከረ ነው፡፡ በዴሞክራሲና በመልካም አስተዳደር ጉዳይ ላይ ግን ሥራ ይቀረናል፡፡ መንግሥትና የላይኛው አመራር ‹‹ሮም በአንድ ጀንበር አልተገነባችም ዴሞክራሲም እንደዚያው ስለሆነ በሒደት እንጃ በአንድ ጊዜ አይመጣም፤›› ሲሉ ይደመጣል፡፡ ይኼ ማለት ግን በሕገ መንግሥቱ ላይ የተቀመጡ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች ሊጣሱ እንደማይገባ በማሳሰብ፡፡

ይሁንና ከላይ እስከ ታችኛው የመንግሥት መዋቅርም ሆነ ከፌዴራል እስከ ቀበሌ ባለው መንግሥታዊ እርከንና ማኅበረሰብ ውስጥ ጉድለቶችን መፈተሽ ይገባል፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች የዜጎች ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መያዝ፣ በፀጥታ ኃይሎች መደብደብና አለፍ ሲልም በምርመራ ወቅት ጫና መደረግ እንዳለ ይታወቃል፡፡ ይኼ ችግር በአንዳንድ ማረሚያ ቤቶች መፈጸሙንም ፍርድ ቤት በችሎት ላይ ተጠርጣሪዎች አቤቱታ ሲያሰሙ አዳምጠናል፡፡

በዳኝነት አካሉ፣ በፖሊስና በትራፊክ ፖሊስ የምርመራና ውሳኔ ሒደቶች ላይ ሙስና፣ መድልኦና የተዛባ ፍርድ ላለመሰጠቱ እንዴት እየተረጋገጠ ነው ብሎ መጠየቅም ተገቢ ነው፡፡ መንግሥት የፍትሕ ሴክተሩን ተደራሽነት ለማስፋት እሠራለሁ የሚለውን ያህል በሥነ ምግባርና ሞራል የተነሳ፣ ለሕግ የበላይነት ቁርጠኝነት እየተጋ ያለ ‹‹የፍትሕና የፀጥታ ሠራዊት›› (በኢሕአዴግ ቋንቋ) ገንብቷልን?

ይኼን ጥያቄ እንድናነሳ የሚያስገድደው የአንዳንድ ወገኖቻችን ደመወዝ እንደማናውቀው ሁሉ ባለሕንፃ፣ የሚከራዩ ሁለት ሦስት አራት ተሽከርካሪዎች ባለቤቶች፣ የቪላና የሆቴል ቤቶች ባለንብረቶች ያደረጋቸው ምንድነው ስንል ነው፡፡ በመንግሥት ሹመትና ‹‹ጥቅም›› የሚያስገኝ ሙያ ላይ ከአሥር ዓመታት ያነሰ አገልግሎት ያላቸው ባለሕንፃዎች፣ ባለግዙፍ ቪላ ባለቤቶች፣ የተሽከርካሪዎችና ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ባለቤቶች አልተፈጠሩምን? ሌላው ቀርቶ በዝምድና፣ በአገር ልጅነትና በቅርበት ስም ስንቶች ሕገወጥ ደላሎችና ‹‹ጉዳይ ገዳይ›› ሆነዋል? ይኼ ከሕዝቡ ያልተሰወረ ሀቅ ቢሆንም የግልጽነትና የተጠያቂነት ሥርዓቱ መዳከም ‹‹ተከድኖ ይብሰል›› የሚል እንዲበዛ አድርጎታል፡፡

በአንድ ወቅት የመንግሥት ልሳን የሆነው አዲስ ዘመን ጋዜጣ የፀረ ሙስና ኮሚሽንን ሀብት የማሳወቅና ይፋ የማድረግ ሕገ ደንብ ለምን አይተገበርም ሲል በአጽንኦት ጠይቋል፡፡ የጠቀሳቸው የመረጃ ምንጮች (ምሁራንና የሕግ አዋቂዎች) ብቻ ሳይሆኑ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ጉዳዩ ከንክኖት በቀናት ውስጥ መወያያ አጀንዳም አድርጎታል፡፡ ነገር ግን ኮሚሽኑ ወደኋላ የተመለሰ መስሎ ‹‹የተሿሚዎችን ሀብት መዝግበን ሲፈለግ ወይም የጠየቀ ሕጋዊ አካል ሲቀርብ መረጃ መስጠት እንጂ ለሕዝብ ይፋ የማድረግ ግዴታ የለብንም፤›› ሲል የግልጽነት መርሁን ጥያቄ ውስጥ ከቶታል፡፡

እንግዲህ የዴሞክራሲ ሥርዓት መደብዘዝን እንደ ጉዳት መቁጠር የሚያስፈልገው የመልካም አስተዳደር ግንባታውንም ስለሚሰነክለው ነው፡፡ በሠለጠነ ማኀበረሰብ ግንባታም ሆነ በዴሞክራሲ አስተሳሰብ ማነፅና የቀደመውን ኋላቀር አስተሳሰብ የመናድ ተግባር ውስጥ ግልጽነትና ተጠያቂነትን የሚያክሉ ጠንካራ መልሶች የሉም፡፡ ለእነዚህ ቁልፍ ጉዳዮች ዘብ የማይቆም መንግሥት ደግሞ ሄዶ ሄዶ የወደቁትን ዓይነት ቀን ነው የሚጠብቀው፡፡ ስለሆነም ለዴሞክራሲ ባህል ግንባታና ለዜጎች ነፃነት ደጋግመን ማሰብ ያስፈልጋል መባል አለበት፡፡

በአገራችን በቅርቡ ተከስቶ የነበረው ሕዝባዊ አመፅ ይኼ ሁሉ ብሶት የወለደው እንደነበር መርሳት ተላላነት ነው፡፡ ያ ሁሉ ሕዝብ ሞቶ፣ ቆስሎና የአገሪቱ አንጡራ ሀብት ወድሞ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጊዜያዊ እፎይታ ቢገኝም፣ እያመረቀዙ ያሉ ችግሮች ዘለቄታዊ መፍትሔ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ›› እንዲሉ፣ በአገሪቱ ውስጥ በተለያዩ ጊዜያት ያየናቸው ችግሮች አዙሪት ሆነው ሊቀጥሉ ይችላሉ፡፡ በተቻለ መጠን ዓይንንና ልቦናን መክፈት ተገቢ ነው፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

Standard (Image)

አንዱ የበላይ ሌላው የበታች የሚሆንበት ሥርዓት ሊታሰብ አይገባም

$
0
0

 

አሁን ባለው የኢትዮጵያ ሁኔታ አዲስ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ገጽታ ተፈጥሯል፡፡ በአንድ በኩል ስማቸውና ቋንቋቸው እንኳን በወጉ ያልታወቁ አናሳ (Minority) ሕዝቦች ሕገ መንግሥታዊ ዕውቅና ማግኘታቸው የፈጠረላችሁ መነቃቃት አለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቀደም ባሉት ጊዜያት በቋንቋ፣ በባህል፣ በሃይማኖትና በመሳሰሉት ሁሉንም ይጠቀልል የነበረው አሃዳዊ አስተሳሰብ ሁለንተናዊ ተፅዕኖ ቀንሷል፡፡ ቢያንስ ወደ እኩል ዕውቅና የሚያመጣ መንገድም ተጀምሯል ማለት ይቻላል፡፡

በዚህ መሀል ግን በየትኛውም ሥርዓት ሊገጥም እንደሚችለው የተለያዩ መደነቃቀፎችና እንቅፋቶች አጋጥመዋል፡፡ እነዚህ ችግሮች ሊከሰቱ የቻሉት ደግሞ፣ በመንግሥት የውስጥ ችግርና በማኅበረሰቡ ውስጥም ባሉ የተዛቡ አስተሳሰቦች ነው፡፡

መንግሥት መልካም አስተዳደርን ማስፈን ሲያቅተው፣ የግልጽነትና ተጠያቂነት አሠራሩ ሲዳከም፣ ዴሞክራሲያዊነት በገዢው ፓርቲ ውስጥ ሲኮሰምን፣ በተፃራሪው አድርባይነትና ‹‹ምን አገባኝ‹‹ ባይነት ሲንሰራፋ ለውድቀት መንደርደር ይጀመራል፡፡ በዚህ ላይ ከመጠን ያለፈ ራስ ወዳድነትና ሌብነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረከቱ መምጣታቸውም ታይቷል፡፡

በሕዝቡ ዘንድም ቢሆን ኋላቀር አስተሳሰቦችን የመሸከም ነገር እያገረሸ ይሄዳል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደታየው ጠባብነት፣ ትምክህተኝነት፣ አክራሪነትና ጽንፈኝነት በአገሪቱ ውስጥ ሥር እየሰደዱ ያሉ በሽታዎች ሆነዋል፡፡ ለነገሩ መንግሥታዊ አካሉም ቢሆን ከሕዝቡ ውጪ ያለ ግዑዝ ነገር ባለመሆኑ፣ የእነዚህ ዝንፈቶች ተሸካሚ መሆኑ አልቀረም፡፡ በተጨባጭም ሆኗል፡፡

ከዚህ አንፃር የትግራይ ሕዝብና ሕዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) የበለጠ ተጠቃሚ፣ በሥርዓቱም አድራጊ ፈጣሪ ሆነዋል የሚለውን እሳቤ ፖለቲካዊ አንድምታ ማየት ይጠቅማል፡፡፡ ይኼ አስተሳሰብ ዛሬ ዛሬ አደባባይ ወጥቶ ለውይይት  ቢበቃም ውስጥ ውስጡን የማኅበረሰቡ አጀንዳ ሆኖ የከረመ ነው፡፡ ይኼ ከጠባብነትም ይባል ከትምክህት አስተሳሰብ የመነጨ ጉዳይ ግን መነሻ መሠረት የለውም ለማለት ያዳግታል፡፡

አንደኛው ትግርኛ ተናጋሪው ወገን ከ25 ዓመታት በፊት በነበሩት ሥርዓቶች እንደ ሌሎች ሕዝቦች የተለያዩ ጭቆናዎች ደርሰውበታል፡፡ በአንድ በኩል እንደ ሌሎች የኢትዮጵያ ብሔሮች የብሔርም ሆነ የመደብ ጭቆና ደርሶበታል፡፡ በሌላ በኩል ከዚሁ ማኅበረሰብ በወጡ የትጥቅ ትግል አራማጆች ምክንያት ወደ ሁለት አሥርት ዓመታት ገደማ አካባቢው የጦርነት አውድማ ነበር፡፡ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ወገኖች ሞተዋል፡፡ ከዚህ በላይ አካል ጎድሏል፡፡ የተሰደደውም ቁጥሩ ከፍ ያለ ነው፡፡

እነዚህ ቀዳሚ የመከራ ገፈት ቀማሾች በአገሪቱ አዲስ ሥርዓት ከተመሠረተበት ከ1984 ዓ.ም. ወዲህ ከፍተኛ የተሳትፎና የእኔነት ስሜት ውስጥ ገብተዋል፡፡ በአንድ በኩል ለዓመታት የዘለቀው ጦርነት፣ ሞትና ስደት ሲቆም ከማንኛውም ኢትዮጵያዊ ጋር ፊታቸውን ወደ ተረጋጋ ሕይወትና ልማት ለማዞር ችለዋል፡፡ በሌላ በኩል አብዛኞቹ የትግራይ ተወላጆች በመስዋዕትነት የተገኘው ሥርዓት የሁሉም የአገሪቱ ሕዝቦች ሆኖ ፍሬ አፍርቶ ማየትን የሚሹ ለመሆናቸው ጥርጥር የለኝም፡፡ ነገር ግን ከሰው ሰው ሊለያይ ቢችልም የትግራይ ሕዝብና ሕወሓት አንድ የሆኑ ያህል ለሥርዓቱ የተሻለ ውግና ያላቸው ደግሞ አሉ፡፡ በአዲሱ ሥርዓት መገንባት ደስተኛ ያልሆኑና ከቀድሞዎች አገዛዞች ተጠቃሚ የነበሩ ኃይሎች ደግሞ እነዚህን ወገኖች ዒላማቸው አድርገው ለዓመታት እየዘመቱባቸው ነው፡፡

በመሠረቱ አሁን ያለው ሥርዓት አንዱ የበላይ ሌላው የበታች የሚሆንበት ሰፊ ዕድል ፈጥሯል ቢባልም፣ የትግራይ አብዛኛው ሕዝብ የተሻለ የመጠቀሙ ነገር ግን በጣም አሳሳች ነው፡፡ አንዳንድ ነጥቦችን ማንሳት ተገቢ ነው፡፡

አንደኛው በጥረትና በከፍተኛ የእኔነት ስሜት ለሥራ እየተረባረበ ያለ ወገን አለ፡፡ ለአብነት ያህል በትግራይ ክልል ያለውን አርሶ አደር መመልከት ጠቃሚ ነው፡፡ ይኼ ሰው ሠራሽ ብቻ ሳይሆን ተፈጥሮ ጭምር ጫና ያሳደረበት ማኅበረሰብ ያንጋጠጡ ተራሮችና ያልተመቹ መሬቶችን በደን እየሸፈነ፣ ጠንካራ የሚባል የመሬትና የውኃ ዕቀባ ሥራ እያከናወነ ከፍተኛ የሆነ ለውጥ እያየ ነው፡፡ ዛሬ ክልሉ በደን ሽፋን፣ በመስኖ ሥራ፣ በግብርና ምርታማነት ብሎም በገጠር ተጓዳኝ ሥራዎች (የንብ ማነብ፣ የእንስሳት እርባታ፣ የሳርና የመኖ ምርት፣ . . . ወዘተ) አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡ የዚህ ጥረት ውጤት ነው፡፡

ለዚህ ወሳኝ ተግባር የትግራይ ክልል አርሶ አደር የተበጀተለት የተለየ ገንዘብ ወይም ዝናብ ሊኖር አይችልም፡፡ ነገር ግን ቀድሞም በብዙ ፈተናዎች ያለፈው (እንደ ቻይናና መሰል ሕዝቦች) አርሶ አደር ቀን ከሌት የቤተሰቡን ጉልበት አሟጦ በመሥራቱና በጥብቅ ዲሲፕሊን በመንቀሳቀሱ ተራሮችን ምንጭ ማድረግ ጀምሯል፡፡ የተለያዩ ችግሮች ቢኖሩም የፖለቲካ አመራሩና የሙያተኛው ተነሳሽነትም ቢሆን በአንፃራዊነት የተሻለ እንደነበር ሊካድ አይቻልም፡፡  

በሌላ በኩል በአገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች ያለው ልማታዊ የሚባሉ የክልሉ ተወላጆች የሥራ ተነሳሽነትም ልምድ የሚወሰድበት ነው፡፡ ከትንሽ ጋራዥ ተነስቶ በጥረቱ መገጣጠሚያ የከፈተ፣ ከቆላማ አካባቢ ወርቅ ከማውጣት አልፎ ባለትልቅ ድርጅት የሆነ፣ ከትንሽ ግሮሰሪ ባለኮኮብ ሆቴል የገነባ፣ ወዘተ ማየት ይቻላል፡፡ ከዚህም በላይ በተለያየ አጋጣሚ ከአገር ተሰዶ በውጭው ዓለም ያጠራቀመውን ሀብት ይዞ ወደ አገር ተመልሶ በማፍሰስ ተጨማሪ ሀብት ያፈራው ተጋሩ (የትግራይ ተወላጅ) በርከት ያለ መሆኑን ማስተባበል አይቻልም፡፡

በእርግጥ ይኼ ተነሳሽነት ሥርዓቱ የፖለቲካ ዋስትና እንዲፈጠርለት ከመተማመንም ሊመነጭ እንደሚችል እርግጥ ነው፡፡ ምንም ተባለ ምን ግን በቀድሞዎቹ ሥርዓቶችም ጊዜ ቢሆን በጥረታቸው ተወዳድረው ሀብት እንዳፈሩት የአካባቢው ተወላጆች ሁሉ፣ ባለፉት 25 ዓመታትም ተበድረውም ይሁን ተጋግዘው ሕይወታቸውን የቀየሩ፣ ሀብት ያፈሩና ለአገር የሚጠቅም ልማታዊ ሥራ የጀመሩ የዚያ ማኅበረሰብ አባላት የሚበረታቱና ልምዳቸውም ትምህርት የሚቀሰምበት ነው፡፡ ዋናው ዋስትና ተገቢውን ግብርና ሕዝባዊ ኃላፊነት እየተወጡ እንዲሠሩ መደረጉ ብቻ ነው፡፡

አሁን ባለው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) መራሹ መንግሥት የሕዝብ ሥልጣንን ለግል ጥቅም ያዋሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ መካከለኛ መሪዎችና ልዩ ልዩ ባለሙያዎች ግን አካሄዳቸው መፈተሸ አለበት፡፡ በታሪክ አጋጣሚ የደርግ ሥርዓት ሲወድቅ በትግል ላይ የነበሩ ሰዎች እስከ ከፍተኛ ባለማዕረግ መኮንንነት ደረጃ ደርሰዋል፡፡ ተራ ካድሬ የነበረውም ከሚኒስትርነትም አልፎ በጡረታ እስከ መተካት ደርሷል፡፡

በእነዚህ 25 ዓመታት የሕዝብ አደራ የመወጣት ጊዜያት ግን በአገሪቱ ታሪክ ውስጥ አሻራቸውን ካሳረፉ ጀግኖች በተለየ ሁኔታ የግል ኪሳቸውን ያደለቡ፣ በኔትወርክና በቡድን አሠራር፣ እንዲሁም በወንዜ ልጅነት የተጠቃቀሙ የሉም ሊባል አይችልም፡፡ ከዚህ መሬት ላይ ያረበበ ሀቅ ሊወሰድ የሚችለው ትምህርት አካሄዱ አጥፊና አገር በታኝ እንደሆነ መገንዘቡ ላይ ነው፡፡ የሙሰኝነትና የሥልጣን ትስስርን መበጣጠስ እንደሚገባ ነው፡፡

በመሠረቱ አሁንም ድረስ ራሱ የሥርዓቱ አመራርና ካድሬ (በተለይ የሌላው ብሔር) ብሎም ሕዝቡ በስፋት የሚያነሳው ‹‹የብሔር ርስት የሚመስሉ አሿሿሞች ይፈተሹ›› ጥያቄ መነሻውም ይኼው ያላግባብ የመጠቃቀም አባዜ ነው፡፡ መንግሥት ራሱም እንደ አመነው የሥልጣን አተያዩ የተንሸዋረረ በሆነበት አገር ውስጥ እውቀት፣ ክህሎትና ሥነ ምግባር ብቻ ሳይሆን የብሔር ምጥጥን የሁሉም ነገር ማጣፈጫ መሆኑ አይቀርም፡፡ ለጊዜውም ቢሆን መተማመንን የሚያሰፍነውም ይኼው አሠራር ብቻ ነው፡፡

ከዚህ አንፃር በፌዴራሉ መንግሥት ደረጃ በተለያዩ ተቋማት የሚታየውን ገጽታ ማጤን ተገቢ ነው፡፡ እነዚህ የሥርዓቱ መጠበቂያ ምሰሶዎች ለአደጋ  በሚጋለጡበት ደረጃ ከክህሎትና ከቁርጠኝነት ውጪ ሁሉንም ብሔር ያሰባጠሩ ናቸው ባይባልም፣ መተማመንና አገራዊ ገጽታን በሚፈጥር ደረጃ መመጣጠን እንዳለባቸው ግን ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ይኼን አለማድረግ ደግሞ ግልጽነትና ተጠያቂነት እየደበዘዘ ለብልሽት እንደሚያጋልጣቸው፣ አሁንም ጥገኛ በሆኑ ኃላፊዎች በግልጽ ታይቷል፡፡

በሌላ በኩል በማወቅም ይሁን ቸል በማለት የክልሉ ተወላጆች በብቸኝነት በእጅጉ በዝተው የሚታዩባቸውን ተቋማት መፈተሽ ግድ ይላል፡፡ በአንዳንድ ተቋማት የሚታየው የስብጥር መዛነፍ ተቋማቱ ምን ቢሠሩና ውጤታማ ቢሆኑ እንኳ፣ የአንድ አካባቢ ሰዎች መሰባሰቢያ እየተባሉ እሮሮ ይሰማባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ሌላው ቢቀር ከጥልቅ ተሃድሶው አንፃር አሁንም ዋጋ የሚያስከፍል ነው፡፡

በእርግጥ እዚህ ላይ ለአገር ወሳኝ የሆኑ ሥራዎችን ሁሉ ለብሔር ስብጥር እየተጨነቅን እንመድብ የሚል ኋላቀርነት ተደጋግሞ ሊቀነቀን አይገባም፡፡ ዋናው ጉዳይ ሥራዎች በግልጽነት፣ በተጠያቂነት፣ በእርስ በርስ ቁጥጥርና ብሎም በማያወላዳ ዲሲፕሊን እንዲመሩ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ብቃትና ተወዳዳሪነት ዋነኞቹ የሥራው መሥፈርቶች እንዲሆኑ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን ለዜጎችም እኩል ዕድል ለመፍጠር ያስችላል፡፡

በመሠረቱ ከላይ በተጠቀሱ አንዳንድ መሥሪያ ቤቶችና ሜጋ ፕሮጀክቶች ላይ ጥሩ ውጤት ሲገኝ ምሥጋና የመኖሩን ያህል፣ ጥፋትም ሲታይ ወቀሳ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ከዚህ አንፃር በሚከሰቱ የአፈጻጸም ጉድለቶች፣ ብልሹነቶችና መንገዳገዶች ሁሉ ተጠያቂው አንድ ወገን ብቻ እንዳይሆንም ተሰባጥሮ  በአንድነት መንቀሳቀሱ አስፈላጊና ተገቢ ነው፡፡

በግሌ ከወራት በፊት በአገሪቱ ተከስቶ በነበረው አለመረጋጋትና ከዚያም ወዲህ በተከታታይ በተካሄደው መንግሥታዊ ማብራሪያና ስብሰባ ‹‹የትግራይ የበላይነት አለ/የለም›› የሚል ውዝግብ ሳዳምጥ ቆይቻለሁ፡፡ ጉዳዩ መነሳቱና አደባባይ መውጣቱም ይበጀናል እንጂ የሚጎዳን ነገር የለም፡፡

‹‹የበላይነቱ የለም!›› በማለት ሊያስረዱ የሚሞክሩት የመንግሥት ሰዎች አንዳንድ ማብራሪያ ‹‹ዶሮን ሲያታልሏት  . . . ›› እንዳይሆን በአግባቡ መታየት አለበት፡፡ ምክንያቱም ‹‹ሥርዓቱ አንዱ የበላይ ሌላው የበታች እንዲሆን አይፈቅድም፣ ለክልሎች የበጀት ድልድል የሚደረገው በፍትሐዊነት ነው፡፡ ክልሎች ባለመሥራታቸው ወደ ሌላ ጣት መቀሰር ነው . . . ›› የሚለው አገላለጽ በራሱ ሙሉ አይደለም ባይ ነኝ፡፡  

ይልቁንም ብዙኃኑ የትግራይ ሕዝብ የሕይወት ዋጋ ባስከፈለው የትጥቅ ትግል በቁርጠኝነት ተሠልፎ በፅናት እንዲታገለው ሁሉ፣ አሁንም በድህነት ላይ በትጋት መነሳቱን ማሳየት አንዱ ጉዳዩ መሆን አለበት፡፡ በተቃራኒው በጥገኝነትና በአቋራጭ ለብልፅግና እየተንደረደረ ያለ ጥገኛም ሥርዓቱን ለብልሽት እንዳያጋልጠው ሊነጠል ይገባል፡፡ ለአብነት ያህል በጋምቤላ እርሻ ላይ እንደታየው (ከባንክና መሬት ሰጪው ጋር የተሳሰረ ነጠቃ) በአዲስ አበባ ሕገወጥ መሬት ወረራ፣ በገቢዎችና ጉምሩክ የቀረጥና የግብር እፎይታ ‹‹ጨዋታ›› ላይ፣ እንደሁም የኮንትሮባንድና መሰል ዝንፈቶች ላይ በመንጠላጠል በስም የሚነግድ የለም ሊባል አይችልም፡፡

በእርግጥ ሙስናም ሆነ አጭበርባሪነት የብሔር ባርኔጣ ሊበጅለት አይችልም፡፡ አይገባምም፡፡ ሥርዓቱን ማስተካከል እንጂ ማንም ቢሆን ክፍት በር ካገኘ ዘው ማለቱ አይቀርም፡፡ የትግሪኛ ተናጋሪ ወገኖች ለእንዲህ ዓይነት ‹‹መጠርጠርና ሐሜት›› የሚጋለጡበት ሁኔታ ግን አለ፡፡ በተለይ በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች በማንነት ስም ለመጠቀም ዕድል ስለሚኖር ነው፡፡

ከዚህ ባለፈ ግን በቅርቡ በዚሁ ጋዜጣ ‹‹ተሟገት›› ዓምድ ላይ ‹‹የተሃድሶ መድረኮች የክርክር ከፍታዎች›› በሚል ርዕስ ሐሳባቸውን ያሰፈሩት አቶ መንግሥቱ መስፍንን ጽሑፍ መለስ ብዬ ልጠቅስ እወዳለሁ፡፡ በአንድ በኩል ‹‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል›› የሚለው ፅንፈኛ ፖለቲከኛ፣ በሌላ በኩል የአገራችንን አንድነት የማይሹ ወገኖች ‹‹የትግራይና ሕወሓት የበላይነት አለ፣ ዘረፋው ተባብሷል›› ሲሉ የሚነዙትን ልብ ወለድ በጭፍን መቀበል፣ በሰሜን ኢትዮጵያ ያለውን ለፍቶ አዳሪ ሕዝብ ኑሮና ሥነ ልቦና ያለመገንዘብ ውጤት ነው፡፡ ትርፉም መጠራጠርና ቅሬታ ከመፍጠር ውጪ አይሆንም፡፡

ይኼ ማለት ግን ተስፋዬ ገብረአብ የተባለው ጸሐፊ እውነቱን ይሁን ውሸቱን ‹‹የጋዜጠኛው ማስታወሻ›› (2001) በሚለው መጽሐፍ ገጽ 24 አካባቢ ሕወሓት በትጥቅ ትግሉ ወቅት የከፈለውን ዋጋ ያህል ልዩ ተጠቃሚ፣ ሰፊ የሥልጣን ቦታና ሌሎች ምቹ ሁኔታዎች የተፈጠሩለት የሚለው የሞኝ ብሒል ውስጥ መቀርቀር ትርጉም የለውም፡፡ ይህ ዓይነቱን አገር የሚበትን አካሄድ ከወዲሁ መገንዘብ ተገቢና አስፈላጊ ነው፡፡

በአጠቃላይ በተለያዩ መድረኮች እየተደመጠ እንዳለው የዘንድሮው ተሃድሶው አንዱ አንኳር ጉዳይ ይኼው ነው፡፡ ግን ኢትዮጵያውያን እውነታውን  በማጤን፣ ግድፈታችንን በመተራረም፣ የአባባሉን ፖለቲካዊ አንድምታ በማጤን ‹‹የትግራይ የበላይነት›› ቅላፄን በሚዛናዊነት ልንፈትሽ ይገባል፡፡ በውጤቱም ይበልጥ መተማመን የሚጥር ደረጃ ላይ መድረስ ይጠበቅብናል፡፡ ለዚህ ደግሞ መንግሥትና ገዢው ፓርቲ ያለባቸውን ትልቅ ኃላፊነት ያህል ማንም ሊኖርበት አይችልም፡፡ ምክንያቱም አንዱ የበላይ ሌላው የበታች የሚሆንበት ሥርዓት ሊታሰብ አይገባምና፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

    

 

 

Standard (Image)

ዕድገትን የሚታከከው ኢፍትሐዊነትና ሙስና የአገር ጠንቅ ነው

$
0
0

 

በተለያዩ የዓለም አገሮች ፈጣንም ይባል ዘገምተኛ፣ ወይም ተከታታይ ይሁን የሚቆራረጥ የኢኮኖሚ ዕድገት እየታየ ነው፡፡ በተለይ ካለፉት ሁለት አሥርት ዓመታት ወዲህ ግሎባላይዜሽንና የመረጃ ዘመን ዓለምን ወደ አንድ መንደርነት እየለወጠው በመምጣቱ፣ ተያይዞ ከመውደቅ በላይ ተደጋግፎ የመውጣት ምልክት እየታየ ነው፡፡ ለዚህም ዓለም ራሱ በዓመት እስከ ሁለት በመቶ፣ አፍሪካን የመሰሉ ደሃ አኅጉሮች ሳይቀሩም እስከ አምስት በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገባቸውን ለአብነት የሚጠቅሱ ትንታኔዎች አሉ፡፡

በሁለት አኃዝ ለሁለት አሥርትና ከዚያ በላይ እየተመነደጉ የመጡት እነ ቻይና፣ ታይዋን፣ ደቡብ ኮሪያ፣ ጃፓን ዓይነቶቹ ‹‹የእስያ ነብሮችም›› (Asian Tigers) መጠኑ ይለያይ እንጂ ዕድገታቸው አልቆመም፡፡ አሁንም ደግሞ ኢትዮጵያን፣ ኬንያን፣ ሩዋንዳን፣ ታንዛኒያን፣ ደቡብ አፍሪካን፣ ናይጄሪያን የመሳሰሉ የአፍሪካ ፈጣን አዳጊዎች በግስጋሴ ላይ ይገኛሉ፡፡ እንዲያውም ኢትዮጵያ ‹‹የአፍሪካዋ ነብር›› እየተባለች የፈጣን አዳጊ ስያሜ አግኝታ ተጠቅሳለች፡፡

ያም ሆነ በተለይ የፈጣን አዳጊ የሦስተኛው ዓለም አገሮች ዋነኛ ፈተና ከሆኑት ጉዳዮች አንዱ ሙስና ነው፡፡ በእርግጥ የዴሞክራሲያዊ ባህል አለመጎልበት፣ ተያያዥ የሆኑት የመልካም አስተዳደር ዕጦትና የሕግ የበላይነት አለመስፈን ፈተናዎችም ክፉኛ እየጎዱ ነው፡፡ የእነዚህ ጎታች አስተሳሰቦች መንሰራፋትም ያለጥርጥር በሚቆጠር ዕድገት ውስጥ ሙስናና የአቋራጭ ብልፅግና ፍላጎት ደርቶ ይታያል፡፡ ለዚህም ነው በአንዳንድ አገሮች ‹‹ሥልጣን ወይም ሞት›› የሚሉ ጥገኛ ኃይሎች ሥልጣን ላይ ለመቆናጠጥ የሚፋለሙት፡፡

ለዚህ አባባል ቀዳሚዋ ተጠቃሽ አገር ቻይና ነች፡፡ ከወራት በፊት በቻይና ንግሹ ከተማ በተካሄደው የቡድን 20 አገሮች ጉባዔ ላይ የቻይና መንግሥት ይፋ ያደረገው መረጃ ነበር፡፡ ይኼውም በአገሪቱ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ ሙስና ፈጽመው በ70 የተለያዩ አገሮች ተሸሽገው ከቆዩ ሁለት ሺሕ ያህል ሰዎች ተመዝብሮ የነበረ 1.12 ቢሊዮን ዶላር ወደ ቻይና እንዲመለስ የማድረጉ ሥራ ነው፡፡ ቻይና ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት ብቻ 300 ሰዎችን በሙስና ወንጀል መቅጣቷ ብቻ ሳይሆን፣ ሌሎች 100 ሺዎችን ከሳ በሒደት ላይ መሆኗ ሲታይም ‹‹ልማታዊ›› የሚባለው ሥርዓት ምንኛ ለዘረፋና ለአቋራጭ መንገድ ክፍት በር እንዳለው ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡ አንዳንዴ የሙስና ዝንባሌው ድንበር ተሻጋሪም ነው፡፡

ማጠንጠኛዬ ወደ ሆነው ኢትዮጵያ ሁኔታም ስንመለስ የተጀመረውን የዕድገት ጎዞ እየፈተነው ያለው ሙስናና ኢፍትሐዊነት መሆኑ ቁልጭ ብሎ ታይቷል፡፡ በተለይ መንግሥት ‹‹ጥልቅ ተሃድሶ›› ብሎ በጀመረው ችግርን የመለየትና መፍትሔ የማምጣት ትግል እንደተረጋገጠው በአቋራጭ የመበልፀግ፣ ሥልጣንን ያላግባብ የመጠቀም፣ የሕዝብን ጥቅም ወደጎን ብሎ ለዘመድ፣ ለወዳጅና ለሚቀርብ ሁሉ ‹‹መሯሯጥ›› መጠኑ ይለያይ እንጂ በዝቶ ታይቷል፡፡ አልፎ አልፎ ተቋማዊ አሠራርን በመሸራረፍ ለአንድ ወገን ጥቅም መሥራት የሚመስሉ ብልሹ ድርጊቶችም ሊወገዙ በሚገባበት አኳኋን ሲጠቀሱ ተደምጧል፡፡ አሁን ግን በአጭሩ መቀጨት አለባቸው፡፡

በአንዳንድ አካባቢዎች ሕዝብና መንግሥትን ለማገልገል በታማኝነት ስም የተቀጠሩ የፋይናንስ ኃላፊዎች፣ የሒሳብ ሙያተኞችና ሠራተኞች በማጭበርበር ተግባር ላይ ሲወድቁም ታይቷል፡፡ በተለይም የአገር ገንዘብን እንደ ራስ ቆጥሮ የመሠወር ድርጊት፣ ጉቦ ሲቀበሉ እጅ ከፍንጅ መያዝና የብዙዎችን ገንዘብ (በመኪና ልግዛላችሁ፣ ውጭ ልውሰዳችሁ፣ አክሲዮን ላደራጃችሁ፣ . . ስም) አጭበርብሮ መሠወር ተደጋግሞ ይታያል፡፡ ወደ ማኅበረሰቡ ወረድ ሲባል ያለው አጭበርባሪነትና በአቋራጭ የመበልፀግ ደረቅ ወንጀልም ብርቱና ሕጋዊ ትግል ካልተካሄደበት፣ ለዕድገቱ አደናቃፊ መሆኑ ብቻ ሳይሆን አገርን ለአደጋ የሚያጋልጥ ነው፡፡

የዕድገቱ ፍትሐዊነት ይታይ

በአገራችን የኢኮኖሚ ዕድገት ስለመምጣቱ የነፍስ ወከፍ ገቢን ወይም አጠቃላይ አገራዊ ምርትን (GDP) ማየት ብቻ በቂ አይደለም፡፡ ይልቁንም መጠኑ ይለያይ እንጂ በገጠርም ይሁን በከተማ ሕይታቸው የተቀየረ፣ አዳዲስ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው፣ ብሎም ሀብት እያፈሩ የመጡ አዳዲስ ባለሀብቶች መታየት መጀመራቸው ነው፡፡ በመጠኑም ቢሆን ሞዴል አርሶ አደሮች፣ የጥቃቅን አንቀሳቃሾችን ልብ ይሏል፡፡

አሁንም ቀላል የማይባል ድህነት (እስከ 22 በመቶ ከዚህ ውስጥም 17 በመቶ ሥራ አጥ) ቢኖርም፣ በገጠር የአብዛኛው ዜጋ አኗኗር ለውጥ እየታየበት ነው፡፡ አርሶ/አርብቶ አደሩ ለበጋና ለክረምት ያለው ቅርበት ከሁለት አሥርት ዓመታት በፊት ከነበረበት 200 ፐርሰንት አድጓል፡፡ የመጠጥ ውኃ የማግኘት ዕድሉም ከሁለት እጥፍ በላይ ማደጉን የዓለም ባንክ እ.ኤ.አ. የ2016 የልማት ሪፖርት አሳይቷል፡፡ የትምህርትና የጤና ተቋማት፣ የእህል ወፍጮ፣ የቀበሌ አስተዳደር ሥርዓትና ፍትሕ በማግኘት በኩልም ለለውጥ የሚያነሳሳ አዲስ አብዮት ተቀስቅሷል፡፡ ለዚህም ነው የገጠሩ ሕዝብ አኗኗር (አለባበስ፣ አመጋገብና መጠለያ አሠራር፣ . . . ) የሚፈለገውን ያህልም ባይሆን መሻሻል እያሳየ የመጣው፡፡ እንደ አገር የዜጎች የመኖር አማካይ ዕድሜም እስከ 20 ዓመት መጨመሩም ዓለም አቀፍ መረጃ ይፋ እየሆነ ያለው፡፡  

በከተሞች ያለው የተጠቃሚነት ተስፋም ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ በተለይ ለወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ (በመንግሥት፣ በግል ባለሀብቶችም፣ ሆነ በራሱ በዜጋው) ትንሽ የማይባል ውጤት እየመጣ ነው፡፡ አሁን አሁን በአገሪቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ሆቴሎች፣ ኢንዱስትሪዎችና የግል ኩባንያዎች ባለቤቶች ግለሰቦች ናቸው፡፡ ከውጭም ሠርተው ይሁን በአገር ውስጥ ባፈሩት ገንዘብ የመኖሪያ ቤት፣ ተሽከርካሪና ዘመናዊ አኗኗር እየጀመሩ ያሉትም ተበራክተዋል፡፡ በእርግጥ በከተሞች አሁንም ዋነኛ ፈተና የመኖሪያ ቤት ባለቤትነት ነው፡፡ መንግሥትና የግል ባለሀብቱ በመስኩ ቢሰማሩም ብዙኃኑን ደሃ እያረካ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ በማኅበር ቤት መሥራትን ማበረታታት የተጀመረውም (በትግራይና በኦሮሚያ) ገና ከሰሞኑ ነው፡፡

የከተሞች መሠረተ ልማት መሻሻል በተለይ በመንገድ፣ በባቡር መስመር፣ በቴሌኮም፣ በኤሌክትሪክ ኃይል ማጠናከር ኑሮን ይበልጥ አመቺ እያደረገ ነው፡፡ በማኅበራዊ ልማት መስክ (ትምህርትና ጤና) ረገድም ተስፋ ሰጪ ለውጦች እየታዩ ነው፡፡

አሁን በስፋት እየተሰማ ያለው ግን የፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል ጥያቄ ሆኗል፡፡ በተለይ በከተሞች ዓመት ሙሉ ካለሥራ ተቀምጠው እየዋሉ (በየጫት ቤቱ) በሀብት ላይ ሀብት የሚያጋበሱ አዳዲስ ቱጃሮች እየታዩ ነው፡፡ በደላላ፣ በጉዳይ ገዳይነትና ገቢና ወጪው በማይታወቅ የኮንትሮባንድና የኪራይ መሰብሰቢያ ሥልት ሕይወታቸውን የመሠረቱ አሉ፡፡ መንግሥት ይኼንን ድርጊት በፖሊሲና በሕግ ጭምር እንደሚያወግዘው ቢታወቅም፣ በተግባር ግን ለእንዲህ ዓይነቶቹ ፀረ ሥራ ኃይሎች መፈልፈል እያገዘ ያለው ሥርዓቱ ራሱ ነው ቢባል ማጋነን አይደለም፡፡

የሕዝብ አደራን እየበሉ ያሉ አንዳንድ ኃላፊነት የማይሰማቸው ባለሥልጣናት ራሳቸውንና የቀረባቸውን በአቋራጭ ለማበልፀግ የሄዱበት ርቀትም በግልጽ እየታየ ነው፡፡ በተለይ በአዲስ አበባ ከተማ ያለውን ሁኔታ ስንመለከት ትናንት ምንም ያልነበራቸው ባለሕንፃዎች፣ ባለቪላ ቤቶች፣ ከአንድም ሦትና አራት ቦታ የያዙ ዜጎች፣ . . . የሀብት ምንጫቸው ግልጽ አይደለም፡፡ የዚህ ነገር እየተባባሰ መምጣት ደግሞ በተቃራኒው በየጎዳናው ተደፍተው የሚያድሩ፣ በየቤቱ እምነቱና አድባራቱ የሚኮለኮሉ አረጋውያንና ሕፃናትን እየበረከቱ እንዲሄዱ እያደረገ ነው፡፡ በተለይ በመልሶ ማልማትና በሕገወጥ ግንባታ ስም ካለመጠለያ እየቀረ ያለው ነባሩ የከተማዋ ነዋሪን የመታደግ ጉዳይ ትኩረት ካላገኘ፣ ኢኮኖሚያዊ ‹አፓርታይድ› እንዲያቆጠቁጥ የሚያደርግ ነው፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሕዝቡ በይፋ እየገለጸ እንዳለውም (ምንም እንኳን የተጋነነ መረጃ እንደሚኖር ቢጠረጠርም) አንዱ አካባቢ ይበልጥ እየተጠቀመ ሌላው እየተጎዳ እንደሆነ የሚሰማ ስሜት ሕዝቡ ውስጥ ሰርጓል፡፡ ለምሳሌ በአማራ ክልል ሰሜን ጎንደር፣ ሰሜን ሸዋና ዋግ ህምራ ዞኖች በሕዝብ ልማት ጭምር ወደኋላ እንደቀሩ የክልሉ መንግሥት ሳይቀር ይቅርታ የጠየቀበት እውነት ነው፡፡ ከአገሪቱ ዋና ከተማ 200 ኪሎ ሜትር የማይርቁ የሰሜን ሸዋ ነባር ወረዳዎች የአስፋልት መንገድ፣ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ንፁህ የመጠጥ ውኃ ለማግኘት ፈጣሪን ሲማፀኑ ማየት በየትም ቦታ የሚኖረውን የየአካባቢዎቹ ተወላጅ ግፍ እንዲሰማው እያደረገ ነው፡፡

በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል በባሌና በአርሲ እንዲሁም በምዕራብ ሸዋና በወለጋ ሁሉም ዞኖች በሚገኙ አንዳንድ ወረዳዎች ያለው ሥራ አጥነት የገዘፈ ነው፡፡ አካባቢዎቹ በሕዝባዊ ልማት (መንገድ፣ ውኃና ኤሌክትሪክ) በተሻለ ተጠቃሚ ቢሆኑም፣ ብዙኃኑን የአዲሱ ትውልድ ዜጎች የሥራ ዕድል ድርቅ መትቷቸዋል፡፡ በተሃድሶው እንደሚታየውም እንዲያውም የመልካም አስተዳደር ዕጦቱና ሙስናው ተወላጁ እንደተበዘበዘ እንዲሰማው ከማድረግ አልፎ በቀላሉ በሥርዓቱ ላይ አስነስቶታል፡፡

መንግሥት በታዳጊ ክልሎችና በአናሳ ማኅበረሰቦች በኩል የሰጠውን ልማትና የሥራ ዕድል ፈጠራ ሰፊው ሕዝብ ባለባቸው አካባቢዎችም እየደገመው አይመስልም፡፡ ለዚህ አባባል አንዱ ማሳያ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ሕገወጥ ስደተኞች በየወሩ የሚፈልሱባቸው የሐዲያ፣ የከምባታ፣ የጋሞና የወላይታ ዞኖች ገጽታ ነው፡፡ እነዚህ ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ያላቸው ዞኖች ወጣቶቻቸውን በገፍ የሚሰዱት ወደ ባህር ማዶ ብቻ ሳይሆን፣ በመላው አገሪቱ ትልልቅ ከተማዎች (አዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ሐዋሳ፣ ደብረ ዘይትና ሻሸመኔ) ጭምር ነው፡፡

በድምሩ በሙስናም ይሁን በኢፍትሐዊነት ወይም ተደጋግሞ እንደሚባለው በአቅም ማነስ እየመጣ ያለው የፍትሐዊነት ጥያቄ መልስ የሚያሻው ነው፡፡ ብዙኃኑን ጥሎ ጥቂቱን አንጠልጥሎ የሚደረግ ‹‹ዕድገት›› መቋጫው አያምርም፡፡ ያውም የብሔር ፖለቲካው እንደ እሳተ ገሞራ በሚንተከተክበት በዚህ ጊዜ አካባቢያዊ የሚመስሉ የፍትሐዊነት ቅሬታዎችን አለመመለስ ዘላቂ ለውጥን ያደናቅፋልና ሊታሰብበት ይገባል፡፡

ሙስና በግልጽ ቢኖርም አልተፋለምነውም

ሙስና የኢትዮጵያ ብቻ ወረርሺኝ አይደለም፡፡ ብዙዎች ታዳጊና የሠለጠኑ አገሮችን አንቀጥቅጧል፡፡ ብርቱዎቹ አደጋውን ተገንዝበው በፅናት ተፋልመው ቢያንስ ከሕዝባቸው ታርቀው በሥርዓት እያረሙት ዘልቀዋል፡፡ ሙስና፣ ኢፍትሐዊነትና የሕግ የበላይነት ጥሰት ያሸነፋቸው የውድቀት ምሳሌዎች (ሶማሊያ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ናይጄሪያ፣ ማዕካላዊ አፍሪካ፣ . . . ) ግን ያሉበትን ደረጃ ማጤን ብቻ በቂ ነው፡፡

ከዚህ አንፃር የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ ሙስናን ሳያቅማሙ የመታገልን ጉዳይ ለነገ ሊሉት አይገባም፡፡ ዓለም አቀፎቹን ትራንስ ፖረንሲ ኢንተርናሽናልን በመሳሰሉ ድርጅቶች ከሚካሄዱት ጥናቶች በላይ፣ መንግሥት ራሱ በከፈተው ‹‹ተሃድሶው መድረክ›› ሕዝቡ በይፋ እያወጣው ያለው መረጃ ካልተድበሰበሰ አስተማሪና ጠንካራ እርምት ለመውሰድ ያስችላል፡፡ ግን በመንግሥት በኩል እዚህ ግባ የሚባል ዕርምጃ ባለመታየቱ፣ አንዳንዶች ‹‹ከሥርዓቱ ጋር ፖለቲካዊ ግጭት አትፍጠር እንጂ ሙስና በተናጠል አያስጠይቅህም፤›› እስከ ማለት አድርሷቸዋል፡፡

ለአብነት ያህል የመንግሥት ኃላፊነት ላይ ተቀምጠው ባለኮከብ ሆቴል የገነቡ፣ ሕንፃዎች የገነቡና ትልልቅ የንግድ ድርጅቶች የከፈቱ እንዳሉ ተረጋግጧል፡፡ እነዚህ ወገኖች ተበድረው ሠሩ፣ በባለቤታቸው ስም ፈቃድ አውጥተው ነገዱ ቢባል እንኳን በሥልጣናቸው መሬት፣ ብድርና የግብር ጣጣን አቀላጥፈዋል፡፡ በአንድ የሚዲያ ተቋም ኃላፊ የነበሩ አንድ ግለሰብ ደግሞ የካርጎና የመርከብ ጉዞ ላይ የግል የግንባታ ዕቃን በሚመሩት መሥሪያ ቤት ስም እስከ ማስገባት የመድረሳቸው ድፍረትም ተጋልጧል፡፡

አንዳንዱ ደፋር ‹‹ቱባ›› ባለሥልጣንም በቅርብ ወዳጁ ስም የቢስነዝ ግሩፕ ፈጥሮ ‹‹ሞኖፖል›› በሚመስል ደረጃ እየተወራ መገኘቱ ግልጽ ነው፡፡ የግል ኮሌጁን፣ ሆስፒታሉን፣ ሕንፃና የቢዝነስ ማዕከሉን፣ . . . ሁሉ እያግበሰበሱ ለመንጠቅ ጠንካራ መንግሥታዊ ጀርባ ማስፈለጉ አይቀርም፡፡ ይኼን ተጠቅሞ በግላጭ ሰማይ የነካን ሰው ተግባርና ሕገወጥ ኔትወርክ ለመደበቅ መሞከር፣ ግመል ሰርቆ እንደመሸሸግ የሚቆጠር ነው፡፡ ሕዝቡም በምንም ተዓምር ሊቀበለው አይችልም፡፡

እነዚህንና መሰል የሙስና ወንጀሎችና ንፋስ አመጣሽ ሀብት የማካበት ድርጊቶችን በይፋ ያወገዘው መንግሥት፣ በመረጃ ላይ ተመሥርቼ የሚጠየቀውን አከሳለሁ፣ የሚጠረጠረውንም የሕዝብ ኃላፈነቱን አስረክቦ ወደ ራሱ መንገድ እንዲሄድ አደርጋለሁ ብሏል፡፡ ይሁንና በሺዎች የሚቆጠሩ የበታች ሹማምንትን ሲከስ፣ አሁንም ድረስ በላይኛው ደረጃ መነካካት አልታየበትም፡፡ የሚከሰስ፣ የሚወረስም ሆነ ከወንጀል ነፃ የሚል መረጃም ‹‹ውሾን ያነሳ ውሾ . . . ›› መስሏል፡፡  

በመንግሥት በኩል ሥልጣንን ያላግባብ የመጠቀም ችግር (መኖሪያ ማድረግና የሀብት ማጋበሻ መሆን) እየከፋ መምጣቱ ተገልጿል፡፡ ይህን ችግር ለመቀነስም በፌዴራል መንግሥቱና በክልል ደረጃ ባሉ የካቢኔ አባላት ላይ ሹምሽር አድርጓል፡፡  አዳዲስ ምሁራንን ወደፊት መስመር የማምጣቱ ጅምር ግን በመካከለኛ ደረጃ (በኤጀንሲ፣ በኮርፖሬሽን፣ በድርጅቶችና በጽሕፈት ቤቶች) የሚገኙ ሥራ አስኪያጆችን አልዳሰሰም፡፡ በዚህም ምክንያት ‹‹ጥልቅ ተሃድሶውን›› እንደ መድረክ ራሳቸው መርተው፣ ያን ሁሉ በረዶም ወርዶባቸው፣ አሁንም ባለመዱት ኮርቻ ላይ ተፈናጠው ለመቀጠል ሸሚዛቸውን የቀየሩ ‹‹ሙሰኛ›› አመራሮች ቁጥራቸው ትንሽ አይደለም፡፡

የሚያሳዝነው የሕዝብ ሥልጣን ቢያንስ ‹‹የብዙዎች መኖሪያና መንደላቀቂያ ሆኗል›› ብሎ ያረጋገጠ መንግሥት ከአንድም ሁለት ሦስት ተሽከርካሪ የሚጠቀሙ አመራሮች፣ ከላይ እስከ ታች ራሳቸውን ሸፍነው በድብቅ ተሽከርካሪ የሚጓዙ ፀረ ዴሞክራቶችን ድርጊት አላስቆመም፡፡ በግላቸው ሁለትና ሦስት የመንግሥት ቤት ይዘው ‹‹የኪራይ ሰብሳቢነት ትግሉ ይፋፋማል!›› የሚል መፈክር የሚያስጮኹትም አሉ፣ እኛም አለን፡፡

ከሁሉ በላይ የብሔርና የዘመድ ኔትወርክን በመሳሳብ እያደራጁ የሥርዓቱን መልካም ገጽታ ያጎደፉ ሰዎች ጉዳይ አፋጣኝ እርምትን ይሻ ነበር፡፡ ምናልባት እንደ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴርና ኢቢሲ (የቀድሞ ኢቴቪ) መሥሪያ ቤቶች ላይ የተሞካከሩ ነገሮች ቢኖሩም በብዙዎቹ መሥሪያ ቤቶች ውስጥ ግን ለይሉኝታ ያህል እንኳን እርምት አልተደረገም፡፡ ከአቅም ማነስ፣ ከዳተኝነትም ሆነ ከሌብነት በተነሳ ጥፋት የተጎተቱ ፕሮጀክቶች ሀብታቸው ‹‹ባከነ›› (በፀረ ሙስናና ዋና ኦዲተር ጭምር) የተባሉ ተቋማት ጉዳይስ እንዴት ሊዳፈን ይችላል?

መንግሥት ተሃድሶ ውስጥ ገብቶ የሕዝቡን ጥያቄዎች ለመመለስ፣ በተለይ በሥራ ዕድል ፈጠራና ፍትሐዊ ልማት ረገድ (ብዙ ያልተጠበቁ የመንገድ ልማቶች ፕሮጀክቶች ይፋ እየሆነ ስለሆነ) ሥራ ጀምሯል፡፡ በተሃድሶው መሠረት የተነሱ የአመራር፣ የአሠራርና የአደረጃጀት ለውጦችን ፈጥኖ በማስተካከልና ከስብሰባ ወጥቶ በቁርጠኝነት ለውጥ ማሳየት ላይ ግን ግብዝነት ታይቶበታል፡፡ ለአብነት ያህል የኢንዶውንመንትና የመንግሥት ተግባራቸው የተደበላለቀው ድርጅቶች አካባቢ ያለው መብላላት፣ በአንዳንድ የልማት ማኅበራት ውስጥ ያሉ የሥነ ምግባር ጥሰቶች መቼና እንዴት ሊታረሙ ነው? በገቢዎችና በጉምሩክ ዘርፍ በብረትና በሌሎች የቀረጥ ነፃ ውንብድና የፈጸሙ 186 ሰዎች ጉዳይ፣ በስኳር ኮርፖሬሽን፣ ብረታ ብረት ኮርፖሬሽንና የመስኖ ፕሮጀክቶች አካባቢ ያለው መዝረክረክ በምን ሊቋጭ ነው? . . . ዝርዝሩ ብዙ ነው፡፡

በአጠቃላይ ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት በአገሪቱ የጀመረውን ዕድገትና ለውጥ ማስቀጠል ስላለበት፣ ሙስናና ኢፍትሐዊነትን በትጋት መታገል አለበት፡፡ አንዱን ይዞ ሌላውን ለቆ ወይም የኢትዮጵያ ’FBI’ ተቋቁሟል እያሉ የፀረ ሙስናና ሥነ ምግባር ኮሚሽንን በማዳከም ችግሩን እሻገራለሁ ማለት ግን ራስን ማታለል ነው፡፡ የተባለው ተቋም የሠራው ሥራ እዚህ ግባ የሚባል አለመሆኑም ‹‹ዶሮን ሲያታልሏት . . . ›› እየመሰለ ስለመጣ መንግሥት በጥብቅ ሊያስብበት ይገባል፡፡ የተሃድሶ አጀንዳው ሳይዳፈን ለላቀ ውጤት ሊበቃ ይገባል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊዋን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

       

Standard (Image)

ኢሕአዴግ የሚደራደረው በጠንካራ አቋም ላይ ሆኖ ነው

$
0
0

 

አዲሱ ዓመት ከጠባ ጀምሮ በመካሄድ ላይ ካለው ጥልቅ ተሃድሶ ፍሬዎች ውስጥ አንዱ በኢሕአዴግና በ21 ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የተጀመረው ውይይትና ድርድር ነው። ፓርቲዎቹ ውይይትና ድርድር  በማድረጉ አስፈላጊነት ላይ ተስማምተዋል፣ ውይይትና ድርድሩ የሚመራበትን ረቂቅ ደንብም በጋራ አዘጋጅተው እየመከሩበት ነው፡፡ ሒደቱ እስካሁን ያስገኘው ተጨባጭ ውጤት ባይኖርም ፓርቲዎቹ በመደማመጥና በመግባባት መንፈስ የሚፈጽሙትና የቅድሚያ ትኩረታቸውን ያገኘ የጋራ አጀንዳ ሆኖ መቀጠሉን ማየት ይቻላል፡፡

ይህ እንዳለ ሆኖ ይህን ውይይትና ድርድር አስመልክቶ የተሳሳቱ አስተያየቶች ሲሰጡ ይስተዋላሉ፡፡ አንዳንድ ወገኖች ኢሕአዴግ ከተቃዋሚዎች ጋር የሚያደርገው ውይይትና ድርድር ከፓርቲው መዳከም ወይም ከተሸናፊነት መንፈስ የሚመነጭ አድርገው ይመለከቱታል፡፡ ለዚህ መነሻቸው ደግሞ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተከሰተው አለመረጋጋትና ሁከት የተነሳ ኢሕአዴግን አጣብቂኝ ውስጥ የገባ ወይም የጨነቀው ፓርቲ አድርገው መውሰዳቸው ነው፡፡

ኢሕአዴግና ተቃዋሚዎች እጃቸው ከምን?” በሚል ርዕስ በሪፖርተር ጋዜጣ አስተያየታቸውን ያሠፈሩ አንድ ጸሐፊ ኢሕአዴግ እየተደራደረ ያለው በደካማ አቋም ላይ ሆኖ እንደሆነ የሚያመላክት ጽሑፍ አውጥተዋል። አንዳንዶቹ እንዲያውም ተቃዋሚዎች ከኢሕአዴግ ጋር ወደ ሌላ ውይይት ከመግባታቸው በፊት አጋጣሚውን ተጠቅመው የፖለቲካ እስረኞች እንዲፈቱና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ እንዲነሳ የሚሉ ቅድመ ሁኔታዎችን እንዲያስቀምጡ ወትውተዋል፡፡

በመሠረቱ ካለፈው ዓመት ጀምሮ አገራዊ ሁኔታው ለኢሕአዴግ ብቻ ሳይሆን ለመላው የአገራችን ሕዝቦችም ፈታኝ ነበር፡፡ በአማራ፣ በኦሮሚያና በደቡብ ክልሎች አንዳንድ ቦታዎች የተከሰቱ ግጭቶች ያስከተሉት ሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመት በኢሕአዴግ የመሪነት ዘመን ከተከሰቱት ሁሉ በስፋቱም በመጠኑም የላቀው ነው። ጉዳቱ ሁለንተናዊ እንቅስቀሴያችንን አደጋ ውስጥ የከተተ፣ የአገራችንንም ገጽታ ያጠለሸና በኢንቨስትመንትና በቱሪዝም ዘርፉ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳደረ እንደነበርም ይታወቃል፡፡ ከዚህም በላይ በኢሕአዴግ ውስጥ የተከሰተው የአመለካከት ዝንፈት አብዮታዊነቱን ስቶ የጥገኛ ዝቅጠት ባህሪዎችን አላብሶት ከርሟል። ከመጀመሪያው ተሃድሶ በኋላ በሰላ ትግል ተኮርኩመው አንገታቸውን የቀበሩት ትምክህትና ጠባብነት እንዲያንሰራሩ ዕድል ሰጥቷቸዋል። የውስጠ ድርጅት ትግሉ መዳከም አድርባይነትና ፀረ ዴሞክራሲያዊ ተግባሮች እንዲንሰራፉ ምቹ መደላድል ሆኗል፡፡ እነዚህ ድርብርብ ችግሮች በእርግጥም ኢሕአዴግን መስቀለኛ መንገድ ላይ አቁመውታል፡፡

ይህ ማለት ግን ኢሕአዴግ ችግሩም መፍትሔው የጠፋበትና በመላምት ዕርምጃዎችን የሚወስድ ነው ማለት አይደለም፡፡ በጊዜያዊ ችግሮች እጁን ተጠምዝዞ እነኛን ቀይ መስመሮቹን ያነሳል ማለትም አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ ያጋጠሙትን ጊዜያዊ ችግሮች ከነምንጫቸው መረዳት ብቻ ሳይሆን፣ የአጭር ጊዜና የረጅም ጊዜ መፍትሔያቸውንም ጭምር ጠንቅቆ ያውቃቸዋል፡፡ ለዚያም ነው እነዚህ ችግሮች የሚቀዱት በራሱ በፓርቲው ውስጥ ካሉ የአመለካከትና የተግባር ዝንፈቶች መሆኑን በመገምገም መሠረታዊ ለውጥ ሊያመጣ የሚችል ንቅናቄ ውስጥ መግባት አማራጭ እንደሌለው በፓርቲ ደረጃ ታምኖበት ዳግም ጥልቅ ተሃድሶው የተጀመረው።

ተሃድሶው በተቀመጠለት አቅጣጫ መሠረት ከኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚና ከምክር ቤቱ አባላት ጀምሮ በየብሔራዊ ድርጅቶቹም ከከፍተኛ አመራሩ ጀምሮ እስከ አባላት ድረስ ዘልቋል። በድርጅቱ ውስጥ ብቻም ሳይወሰን ወደ መንግሥት ሠራተኞችና መላው ሕዝብ ዘልቆ በመካሄድ ላይ ነው። በአፈጻጸም አቅጣጫው ብቻ ሳይሆን በይዘቱም ቀድሞ የተቀመጡለትን ግቦች በሚያሳካ መልኩ ነው ተሃድሶው እየተፈጸመ ያለው።

እዚህ ላይ በቅርቡ በወጣችው የድርጅቱ ልሳን አዲስ ራዕይ ላይ እንደሰፈረው ከአንዳንድ አመራሮች ስለተሃድሶውና ስለሚጠበቀው ውጤት የተሰጡ መግለጫዎች፣ ጉጉት የሚጨምሩና ከመግለጫዎቹ ማግሥት ተዓምር የሚመጣ የማስመሰል ዝንባሌ የሚታይባቸው ነበሩ፡፡ ይህ ሁኔታ በአንድ በኩል ተሃድሶውን ለሁሉም በሽታዎች መድኃኒት (Panacea) አድርጎ የመረዳት ችግር ሲያስከትል በሌላ በኩል ደግሞ ሁሉም በሽታዎች አሁኑኑ (Now or Never) እንዲድኑ የመፈለግ ዝንባሌና በሒደቱ እዚህም እዚያም የመጡ ለውጦችን አሳንሶ የማየት ዝንባሌን ፈጥሯል፡፡

ይህ እንዳለ ሆኖ ግን ገና በጅምር ጉዞ ላይ የሚገኘው የተሃድሶ ንቅናቄ ኢሕአዴግ እንደ ልማዱ ራሱን በራሱ አርሞ አንፀባራቂ ድሎችን ማስመዝገቡን እንደሚቀጥል ተስፋ የሰጡ ውጤቶችም የተመዘገቡበት ነው፡፡ የሥርዓቱ አደጋ ተብለው በተለዩ ጉዳዮችና የጥልቅ ተሃድሶ ንቅናቄውን አስፈላጊ ባደረጉ መሠረታዊ ነጥቦች ላይ በሁሉም ደረጃዎች ግልጽነት እንዲፈጠርባቸው፣ መግባባት ላይ እንዲደረስና ከችግሮቹ ለመላቀቅ ቁርጠኝነት እንዲያዝ ማድረግ ተችሏል፡፡ በፌዴራልና በክልል ከፍተኛ አመራር ደረጃ ሥልጣንን የኑሮ መሠረት የማድረግ አመለካከትና ተግባርን የሚሰብር በብቃትና ልምድ ላይ የተመሠረተ ሹመት ተሰጥቷል፡፡

በየደረጃው ባሉ የአስተዳደር እርከኖችም በውጤታማነት ላይ የተመሠረተ የሰው ኃይል ምደባ ማስተካከያ ተደርጓል። የአመለካከት ብልሽታቸው በተጨባጭ ደረቅ ወንጀል ላይ እንዲሳተፉ ላደረጋቸው አመራሮች፣ ከፖለቲካዊና ከአስተዳደራዊ ዕርምጃዎች (ማስጠንቀቂያ፣ ከኃላፊነት ዝቅ ማድረግ፣ ከማዕከላዊ ኮሚቴ ወይም አባልነት ማገድ፣ ወዘተ…) በተጨማሪ ሕጋዊ ተጠያቂነት እያስከተለ ነው። የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በጊዜ የለንም መንፈስ የመፍታት፣ በተለይ ደግሞ የወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራን ቀዳሚ አጀንዳ የማድረግ ንቅናቄ ውስጥ ተገብቷል፣ ለውጦችም በመታየት ላይ ናቸው፡፡

የእነዚህና ሌሎች ማስተካከያዎች ድምር ውጤት ኢሕአዴግን ስቶት ወደነበረው ወደቀደመ አብዮታዊነቱ እንዲመለስ ዕድል የፈጠረ፣ በእሱ የሚመራውን መንግሥትም የሕዝቡን አንገብጋቢ የልማት ጥያቄዎች በተለይም የወጣቶችን የሥራ ዕድል ጥያቄ ለመመለሰስ ወደሚችልበት ቁመና የመለሰ ነው፡፡ እናም አሁን ኢሕአዴግ የሚገኝበት ቁመና እነሱ እንደሚሉት ደካማ አቋም ሳይሆን እንደ ወትሮው በፈተና (An Acid Test) ውስጥ ካለፈ በኋላ ለላቀ አገራዊ ተልዕኮ ራሱን ያዘጋጀበት ነው፡፡

በሌላ በኩል አገራዊ ወቅታዊ ሁኔታውን ታሳቢ በማድረግ ኢሕአዴግ ፈተና ውስጥ ገብቶ ነበር ሲባል፣ ፈተናው የመነጨው የሚመራው ሕዝብ ካነሳቸው ፍትሐዊና ተገቢ ጥያቄዎችና ይህንኑ የሕዝብ ጥያቄ እንዳይመልስ ቀይዶ ከያዘው የራሱ የድርጅቱ ውስጣዊ ችግር እንጂ ከተቃዋሚ ፓርቲዎቹ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ ሕዝባዊ ተቃውሞው በሁከትና በረብሻ መልኩ በተገለጠበት ወቅትም ሆነ ከዚያ በፊት ተቃዋሚዎች የሚያነሱትና ሕዝቡ የሚያነሳቸው ጥያቄዎች ለየቅል ነበሩ፡፡ ሕዝቡ የመልካም አስተዳደር ዕጦት ከሚችለው በላይ ሸክም እንደሆነበት ሲገልጽ፣ እነርሱ ግን ከውስጥ ንትርክ በተረፋቸው ጊዜ እንደ ወትሯቸው በሕግ ቁጥጥር ሥር ያሉ የፓርቲ አመራሮች እንዲፈቱላቸው ሲጠይቁ ነው የከረሙት፡፡ በአንዳንድ አካባቢዎች ረብሻ በተነሳበት ወቅትም ብሶት ወደ አደባባይ ያወጣቸው ወጣቶች የፈጸሙትን ጥፋት ከማጃገን ያለፈ ሚና አልነበራቸውም፡፡

አሁን ባለንበት መድረክም ቢሆን ተቃዋሚ ፓርቲዎች አገራችንንና ሕዝቦቿን ካሉበት ወቅታዊ ችግር የሚያወጣ ፍቱን መድኃኒት ይዘው ሊቀርቡ ይቅርና የችግሮች ሁሉ ምንጭ አድርገው የሚቆጥሩትን ኢሕአዴግን በተባበረ ድምፅ ለመሞገት የሚያስችላቸውን ኅብረት መፍጠር  አልቻሉም፡፡ በዚሁ ሳምንት 21 አገር አቀፍ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ኢሕአዴግን እንዴት ተቀናጅተው መሞገት እንደሚችሉ ለመምከር ቀጠሮ ቢይዙም፣ 12 ብቻ መገኘታቸውንና እነሱም ቢሆኑ ሳይስማሙ መለያየታቸውን ልብ ይሏል፡፡

በመሆኑም ወቅታዊ ሁኔታው ለኢሕአዴግ የህልውና ጥያቄ ሆኖበት ለለውጥ ሲያነቃንቀው ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ግን የፈጠረላቸው አዲስ ነገር የለም ማለት ይቻላል፡፡ በአጭሩ ኢሕአዴግ በመታደስ ላይ ሲሆን፣ ተቃዋሚዎች ግን ባሉበት እንደቆሙ ናቸው፡፡ በዚህ ዓይነት ነባራዊ ፖለቲካዊ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ የሚደረግ የፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር ደግሞ በሰጥቶ መቀበል መርህ ይመራ ካልሆነ በቀር፣ የኢሕአዴግን እጅ በመጠምዘዝ ጠብ የሚል ነገር አይኖረውም፡፡

ከተጨባጭ ሁኔታው በመነሳት ጉዳዩን ለማብራራት በማሰብ እንጂ፣ ኢሕአዴግ በታሪኩም ቢሆን በፈታኝ ወቅቶች ለሚደረገቡት የውስጥም ሆኑ የውጭ ጫናዎች እጁን የመስጠት ታሪክ እንደሌለው ይታወቃል፡፡ ፓርቲው ሥልጣን ከያዘ ወዲህ ያሉትን ዓመታት ለፈተሸ እንኳን በምን ያህል ፈታኝ ሁኔታዎች ውስጥ ራሱን ብቻ ሳይሆን አገርና ሕዝብን እያዳነ የመጣ ፓርቲ መሆኑን መገንዘብ አይከብድም፡፡ በግንባሩ ውስጥ የተካሄደው የመጀመሪያው ተሃድሶ፣ አባል ብሔራዊ ድርጅቱ በሆነው ደኢሕዴን ውስጥ የተካሄደው ዳግም ተሃድሶ፣ በድኅረ 1997 ምርጫ በተለይ በከተሞች የተከሰተው ነውጥ መዳረሻዎች ለዚህ ዓቢይ ምስክሮች ናቸው፡፡

እነዚህን ፈታኝ ሁኔታዎች እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመውሰድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣ የውጭ መንግሥታትና ለጋሽ ድርጅቶች ከአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊው መስመሩ ሊያስወጡት ጥረዋል፡፡ ኢሕአዴግ ግን በሁሉም ክስተቶች ዴሞክራሲያዊ መድረኮችን በመክፈት፣ ችግሩን ወደ ውስጥ በማየት፣ ወቅታዊና ዘለቄታዊ መፍትሔዎችን በመተለም ቀድሞ ከነበረበትም ይበልጥ ጠንክሮ፣ ፈተናን ወደ መልካም አጋጣሚ የመቀየር ብቃቱን አስመስክሮ ወጥቶባቸዋል፡፡

በአንፃሩ በሌሎቹ የአገራችን ፓርቲዎች የተለመደው ግን ችግር ሲያጋጥማቸው ፀረ ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እርስ በርስ መናከስና የችግሩን ምንጭ ከውስጣቸው ከመፈለግ ይልቅ ውጫዊ ሰበቦችን መደርደር ነው፡፡ ለዚያም ነው ከፈተና በኋላ መዳረሻቸው አንድም መጥፋት አሊያም መሰንጠቅ ሆኖ የኖረው፡፡ በዚህ ዓይነት በወቃሽ ከሳሽነት (Blame Shifting) አባዜ ውስጥ ያሉ ኃይሎች አሁን ኢሕአዴግ የገጠመውን ፈተና ለፓርቲው የዓለም መጨረሻ አድርገው ቢወስዱት ከባህሪያቸው የሚመነጭ ነውና አዲስ ተደርጎ አይወሰድም፡፡ ሆኖም እነዚህ አስተሳሰቦች የሚገዛቸው ካገኙ ውይይቱና ድርድሩ ፍሬ አልባ እንዲሆን በር የሚከፍቱ ናቸውና መጋለጥና መነቀፍ አለባቸው፡፡

ነባራዊ ሁኔታውም ሆነ ታሪካዊ ዳራው ይህ ሆኖ ሳለ ታዲያ ኢሕአዴግ ከፓርቲዎች ጋር ለመወያየትና ለመደራደር የፈለገበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ ማንሳት ተገቢ ነው፡፡ ኢሕአዴግ መላ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ለ17 ዓመታት ያካሄዱትን የፀረ ደርግ አገዛዝ ትግል በመምራት ለፍጻሜ ባደረሰባቸው የመጨረሻዎቹ ቀናት እንኳን ሳይቀር የደርግ የኃይል ሚዛን መሽመድመዱን እያወቀም ቢሆን ከጠላቱ ጋር ለድርድር የተቀመጠ ድርጅት ነው፡፡ በ2002 ዓ.ም በተካሄደው ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ከፍተኛ ውጤት (Landslide Victory) ተጎናፅፎ እንኳን የፖለቲካ ፓርቲዎችን ጋብዞ ወራት የፈጀ ድርድር ማድረጉ ይታወሳል። ኢሕአዴግ እንዲህ በጦር ግንባርም ሆነ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ አሸናፊ ሆኖ ሳለ እንኳን ከተቀናቃኞቹ ጋር ለመደራደር ዝግጁ የሆነው፣ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ካለው ፅኑ እምነት በመነሳት ነው፡፡

ኢሕአዴግ በፕሮግራሙ ላይ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሕገ መንግሥቱና በአገሪቱ ሕጎች መሠረት ዓላማቸውን በሰላማዊ መንገድ እስካራመዱ ድረስ ሕገ መንግሥታዊ መብቶቻቸውን በጥብቅ ማክበርና ማስከበር እንዳለበት፣ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ዓላማውን ለማሳካት ሲንቀሳቀስም ፓርቲዎቹን በዴሞክራሲያዊ፣ በሕጋዊና ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ብቻ ሊታገላቸው እንደሚገባ አስቀምጧል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአንድም የምርጫ ጣቢያ ማሸነፍ ካልቻሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለመደራደር ቁርጠኝነቱን ያሳየው፣ የፓርቲዎችን የኃይል ሚዛን ግምት ውስጥ በማስገባት ሳይሆን ለዚሁ ድርጅታዊ መርሁ ካለው ተገዥነት ነው፡፡

እንደሚታወቀው በ2007 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ ኢሕአዴግ በተወዳደረባቸው የምርጫ ክልሎች ሁሉ አብላጫ ድምፅ በማምጣት አሸንፏል፡፡ ይህ ማለት ግን ሁሉም መራጭ ለኢሕአዴግ ድምፁን ሰጥቷል ማለት አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ ፍላጎቴን አያሟላልኝም ብለው የወሰኑ፣ ኢሕአዴግ ያሉበትን የአፈጻጸም ችግሮች መፍታት አይችልም ብለው ተስፋ የቆረጡ ወይም ተቃዋሚ ፓርቲ ፓርላማ ቢገባ ይሻላል ብለው ያመኑ ዜጎች ድምፃቸውን ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ሰጥተዋል፡፡ በአንዳንድ ትልልቅ ከተሞች እስከ 30 በመቶ የሚደርስ መራጭ ተቃዋሚዎችን መርጧል፡፡ ነገር ግን የመረጣቸው ፓርቲዎች በፓርላማ መቀመጫ አግኝተው ድምፁን ሊወክሉት አልቻሉም።

ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግ የመረጠውን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ያልመረጡትንም መወከሉና ማገልገሉ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ እነዚህ ወገኖች ይበጀናል የሚሉትን የፖለቲካና የኢኮኖሚ አላማዎች አንግቦ የሚንቀሳቀስላቸው፣ በሚወጡ አዋጆችና ደንቦችና በሚደረጉ ስምምነቶች ላይ ፍላጎታቸው እንዲደመጥ የሚገፋላቸው፣ አስፈጻሚውን አካል ከራሳቸው መብትና ጥቅሞች ተነስቶ የሚቆጣጠርላቸው እንደራሴ ቢኖራቸው የዴሞክራሲ ሥርዓቱን ሁሉን አቀፍ (Inclusive) ያደርገዋል፡፡ ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ በምርጫ 2002 ማግሥት ተቃዋሚዎች በፓርላማ ወንበር ቢኖራቸውም ባይኖራቸውም በአገራዊ ጉዳዮች ላይ ተመካክረን እንሠራለን ማለታቸውም፣ ይህንኑ የተለዩ ሐሳቦች የሚደመጡበት መድረክ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓቱ መጎልበት ያለውን ፋይዳ ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፡፡

በተጨማሪም ከፓርቲዎቹ ጋር የሚካሄደው ውይይት፣ ክርክርና ድርድር ለሰላማዊ የፖለቲካ ኃይሎች ሕጋዊ የመታገያ መድረክ ሆኖ ሲያገለግል እዚያው ሳለ ሕገወጥና የአመፅ አማራጭን ለመከተል የሚያማትሩ ኃይሎችን ፍላጎት የሚያመክን በመሆኑ፣ በሁለቱም ወገኖች እኩል ትኩረት ሊያገኝ የሚገባው ነው፡፡

በመጨረሻም በፓርቲዎቹ መካከል ለሚካሄደው ውይይት፣ ክርክርና ድርድር ሙሉ ፈቃደኝነቱን በማሳየቱ ኢሕአዴግ ብቻ ሳይሆን ሌሎቹም ተሳታፊ ፓርቲዎች ሊደነቁ ይገባቸዋል፡፡ በተለይም በውጭ ካለው ፅንፈኛ ኃይል የሚደርሳቸውን የአመፅ ጥሪና ሽንገላ ባለመቀበል ለሰላማዊ የትግል መድረክ ራሳቸውን ማዘጋጀታቸው ሊበረታታ የሚገባው ተግባር ነው፡፡ ይሁንና ተቃዋሚዎች በእርግጥም አሁን አገራችን ያለችበት ሁኔታ የሚያሳስባቸው መሆኑን፣ ውግንናቸው በባሌም ሆነ በቦሌ ለሚመጣ ሥልጣን ሳይሆን ለሕዝብ ተጠቃሚነት መሆኑን የሚያረጋግጡልን ለሕዝብና ለአገር የሚበጅ የውይይት ሐሳብ ይዘው በመቅረብ ነው። በክርክርና ድርድር ወቅትም ኢሕአዴግ ከያዘው የተሻለ መደራደሪያ በማቅረብ ለሰላምና ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታው መጠናከር የበኩላቸውን ኃላፊነት መወጣት አለባቸው፡፡ ኢሕአዴግ በተለይ ደግሞ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚያቀርቧቸውን ሐሳቦች ለሕዝብና ለአገር ካላቸው ጥቅም አንፃር ብቻ መዝኖ፣ የሕግም ሆነ የአፈጻጸም ማስተካከያዎችን ለማድረግ ዝግጁ መሆን ይጠበቅበታል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው kebedememe@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡     

Standard (Image)

የፍላጎት ናዳን የሚመክት ፍትሐዊ የመኖሪያ ቤቶች አቅርቦት መስፈን አለበት

$
0
0

 

የመኖሪያ ቤት ችግር የብዙ ዓለም አገሮች በተለይ የከተማ ነዋሪዎች ፈተና ነው፡፡ ዛሬ ሠለጠኑ በምንላቸው አገሮች እንኳን እስከ 36 በመቶ ከተሞች የቤት እጥረት ያለባቸው፣ በአማካይ እስከ 50 በመቶ ገቢያቸውን ለቤት ኪራይና መሰል የመኖሪያ ወጪ የሚገፈግፉ ዜጎች በርክተው ይታያሉ፡፡

የአገራችንም እውነታ ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በተለይ አዲስ አበባን ለመሳሰሉ ለዘመናት በኋላቀር ሁኔታ ያለፕላን ሲለጠጡ የቆዩ ከተሞች የፈተናው ገፈት ቀማሽ ናቸው፡፡ ከአሥር ዓመት በፊት በመዲናዋ መስተዳድር በተካሄደ ጥናት ከ160 ሺሕ በላይ (48 በመቶ) የሚሆኑ የከተማዋ ቤቶች ለኑሮ ተስማሚ አልነበሩም፡፡ የመፀዳጃ፣ የማብሰያ፣ ንፁህ የመኝታና የመኖሪያ ክፍሎች የሌላቸው ወይም የተጓደሉ፣ በአንዳንዱ አካባቢም ለድንገተኛ አደጋና ለአምቡላንስ አገልግሎት የሚውል የውስጥ ለውስጥ መንገድ እንኳን ያልነበራቸውም ነበሩ፡፡

እነ ባሻ ወልዴ ችሎት፣ ዶሮ ማነቂያ፣ ልደታ፣ ሰን ጋተራ፣ ሠራተኛ ሠፈር፣ አሜሪካ ግቢ፣ . . . ዓይነቶቹን የአዲስ አበባ ገጽታዎች የሚያስታውስ የአዲስ አበባ የቤት እጥረትና የአኗኗር ብልሹነትን በቀላሉ መገንዘቡ አይቀርም፡፡ ይኼ ብቻ ሳይሆን በሚሊዮን የሚቆጠረው የከተማዋ ነዋሪ የመኖሪያ ቤት ችግር ያለበት፣ በኪራይና በደባልነት የሚኖር ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በአንድ ቤት ውስጥ ከ20 እስከ 40 ሰዎች በጊዜያዊነት ‹‹ወገብ ለማሳረፍ›› (አንዳንዶች ኬሻ በጠረባ ይሉታል) የሚታደርባቸው ‹‹ቤቶች› ብዙ ናቸው፡፡

ይኼንን አስከፊ ገጽታ የተገነዘበው መንግሥት በከተሞች የጀመረው የቤቶች ግንባታ መርሐ ግብር በተለይ ባለፉት 13 ዓመታት ገደማ አበረታች የሚባል ሥራ ተከናውኖበታል፡፡ ለዚህ አብነት የሚሆነው በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ 140 ሺሕ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ተገንብተው እስከ 700 ሺሕ የሚደርስ ቤተሰብ ሊያስኖሩ በሚችሉበት ደረጃ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸው ነው፡፡ በአሁኑ ወቅትም በ10/90፣ በ20/80 እና በ40/60 ፕሮጀክቶች አማካይነት 130 ሺሕ ቤቶች እየተገነቡ መሆናቸውን የከተማዋ ከንቲባ አቶ ድሪባ ኩማ ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

ይኼ ጥረት በተለይ በከተማዋ ዳርቻ ቦታዎች በስፋት እየተከናወነ ቢሆንም፣ አሁንም ከዘርፉ አንገብጋቢ ፍላጎት አንፃር የሚነሱ በርካታ ጉዳዮች መኖራቸው አልቀረም፡፡ አንደኛው በተለይ በ2005 ዓ.ም. ከተመዘገበው አንድ ሚሊዮን ገደማ የሚደርስ ሕዝብ አንፃር ግንባታው ቀርፋፋ መሆኑ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ የግንባታ ወጥነት መታጣትና የጥራት ጉድለት አንዱ የመሆኑ እውነታ ነው፡፡ እንደ ሦስተኛ ሊነሳ የሚችለው የኮንትራት አስተዳደርና የሀብት ብክነት እየሰፋ የመምጣቱ ተግዳሮት ነው፡፡ እነዚህና ሌሎች የዘርፉ እንቅፋቶችን በዝርዝር ማሳየት የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ነው፡፡

የፍላጎቱን ጎርፍ የሚቋጥር ኩሬ የለም

ኢሕአዴግ መራሹ መንግሥት በተለይ መካከለኛና ዝቅተኛ ገቢ ያለውን የከተማ ነዋሪ የቤት ባለቤት ለማድረግ በሚኒስቴርና በቢሮ ደረጃ የቤት ገንቢ መሥሪያ ቤቶች አቋቁሞ ጥረት ቢጀምርም፣ ሒደቱ ግን ከፍላጎቱ ጋር አልተጣጣመም፡፡ በመሠረቱ የቤቶቹ ግንባታ የመሠረት ድንጋይ ሲቀመጥ ጀምሮ፣ በመቶኛ የግንባታ ሒደት፣ ተገንብተው ሲጠናቀቁ፣ ሲጎበኙ፣ ሲመረቁ፣ ዕጣ ሲወጣ፣ የቁልፍ ርክክብ ሲደረግ፣ . . . የሕዝብ ግንኙነት ሥራው (ፕሮፓጋንዳ ማለት ይሻላል) ስለሚደጋገምና ስለሚጮኽ እንጂ፣ ሥራው ገና ብርቱ ርብርብ የሚጠይቅ ነው፡፡ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች በተለየ ጉድ የሚባልለት ከፍተኛ የሚባል ግንባታም አይደለም፡፡

ለምሳሌ ‹‹ኮንስትራክሽን ሪቪው ኦንላይን›› የተባለ ድረ ገጽ በአፍሪካ ያለውን የቤት ፍላጎትና አቅርቦት በተመለከተ እ.ኤ.አ. በ2016 ያወጣው መረጃ ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር ከ95 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ያላት ግብፅ በመንግሥት ፕሮጀክቶች ብቻ በዓመት ከ100 ሺሕ በላይ ቤቶች እየገነባች (በነገራችን ላይ አዳዲስ ከተማ እስከ መፍጠር መሄዳቸውን ‹‹ፊውቸር ሲቲ››ን ማንሳት ይቻላል) ቢሆንም፣ ፍላጎቱ በዓመት ከሁለት ሚሊዮን በላይ ነው፡፡ በናይጄሪያም በተመሳሳይ በዓመቱ 200 ሺሕ ቤቶች በመንግሥትና በግል ተገንብተው የዓመት ፍላጎት በሰባት መቶ ሺሕ ሲያድግ ይታያል፡፡ በኬኒያ እንኳን በየዓመቱ የቤት ፍላጎት በሁለት መቶ ሺሕ እያደገ አቅርቦቱ ከ50 ሺሕ የበለጠ አይደለም፡፡

የደቡብ አፍሪካ መንግሥትም በድጎማ ጭምር እ.ኤ.አ. ከ1994 ጀምሮ ሦስት ሚሊዮን ቤቶችን በተለይ በከተሞች ቢገነባም፣ በፍላጎትና አቅርቦት መካከል ያለውን ልዩነት ማጥበብ አልቻለም፡፡ በኢትዮጵያም ቢሆን ከ1998 ዓ.ም. ጀምሮ በከተሞች በመቶ ሺዎች የመንግሥት የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ፣ የግል የሪል ስቴት ሥሪት ልማቶችም በአሥር ሺዎች የቤት ግንባታ ቢያከናወኑም አዲስ አበባን በመሳሰሉ ከተሞች የግል የመኖሪያ ቤት ግንባታ ተዳክሟል፡፡ ስለሆነም የአቅርቦትና የፍላጎት ክፍተቱ ከአንድ ሚሊዮን በላይ በዓመት መሆኑን መረጃው ያሳያል፡፡ በአዲስ አበባ ብቻ ማለት ነው፡፡  

በቅርቡ በአንድ መንግሥታዊ የኅትመት ሚዲያ የወጣ ትንታኔ በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ በሁለት ዙሮች ተመዝግበው ገንዘብ መቆጠብ ለጀመሩ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ዜጎች ቤት ለማዳረስ፣ በአሁኑ ከአካሄድ ከ52 ዓመታት በላይ እንደሚወስድ አሳይቷል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ (ባለፉት ሁለት ዓመታት) እንደታየው ደግሞ በበጀት፣ በቦታና በአቅም ማነስ ሥራው የሚቆራረጥ ከሆነ ከ65 ዓመታት በላይ ይወስዳል፡፡ ይኼን ሥሌት አሁን ካለው የአዲስ አበባና ኦሮሚያ የመሬት ፍጥጫ ጋር ካስተሳሰርነው ደግሞ አሳሳቢ ነው፡፡

የዘርፉ ባለሙያዎች እንደተናገሩትም 60 በመቶው የሚደርሰው የከተማዋ ነዋሪ ብቻ ሳይሆን የቤት ፈላጊው ቁጥርም እየጨመረ የሚሄድ ነው፡፡ ስለሆነም መንግሥት የአቅጣጫ ለውጥ አድርጎ አካሄዱን ካልፈተሸ ችግሩ በአጭር ጊዜ ሊቃለል አይችልም ሲሉ ይደመጣሉ፡፡

በእርግጥ ምንም ዓይነት የመንግሥት ቤት የመሥራት ፍላጎት ባልነበረበት አገር ውስጥ ጅምሩ መደነቅ አለበት፡፡ እስከ 18፣ 15፣ 12፣ 9 እና 7 ከፍታ ያላቸው የ40/60 ዘመናዊ ቤቶች ከመገንባት አንስቶ የተለያዩ የ10/90 አነስተኛ መኖሪያ ቤቶች በስፋት እየተሠሩ ነው፡፡ በዚህ የግንባታ ሒደት ውስጥም በርካታ ኮንትራክተሮች፣ የግብዓት አቅራቢዎችና አንቀሳቃሾች ተፈጥረዋል፡፡ ይነስም ይብዛም የሕዝቡ አኗኗርና የኑሮ ደረጃም የመሻሻል ምልክት አለው፡፡ ግን መስፋትና መጠናከር አለበት፡፡

አሁንም በአፅንኦት መታየት ያለበት ግን በየዓመቱ እየጨመረ የሚመጣውን የፍላጎት ጎርፍ የሚሸከመው የመንግሥት አቅም የለም የሚለው ነው፡፡ እነ ደቡብ አፍሪካ በሁለት አሥርት ዓመታት ውስጥ ሦስት ሚሊዮን ቤቶችን እንኳን ገንብተው ፍላጎቱን ማርካት አልቻሉም፡፡ እኛ ደግሞ 100 ሚሊዮን ሕዝብ (ይሁን ቢባል በከተሞች 20 ሚሊዮን) በ13 ዓመታት የሦስት መቶ ሺሕ ቤቶችን ግንባታ እንኳን አጠናቀን ውኃ፣ መብራት፣ መንገድ፣ ማኅበራዊ አገልግሎት አሟልተን ወደ ሕዝቡ ማድረስ አልቻልንም፡፡

የተለያዩ የዘርፉ ምሁራን እንደሚያነሱትም በቤቶች ግንባታው ላይ መንግሥት ወሳኝ ድርሻ ቢጫወትም፣ አልፋና ኦሜጋው ግን መንግሥት ብቻ ሊሆን አይችልም፣ አይገባም፡፡ የመንግሥት የተዳከመ ቢሮክራሲ፣ የግልጽነትና ተጠያቂነት አሠራር የሌለበት፣ የመልካም አስተዳደር ጫና ያረበበበት መዋቅር ብቻውን የሚሊዮኖችን ፍላጎት ሊመልስ አይችልም፡፡ ይልቁንም በተመጣጣኝ የሊዝ ዋጋና የድጎማ ቀመር የቤት መሥሪያ ቦታዎችን ለግል ተቋራጮች በመስጠት፣ የውጭ ልምድ ያላቸው ቤት ገንቢዎች በማሳተፍ፣ እንዲሁም ቤት በራስ የመሥራት ፍላጎትና አቅም ያላቸው ዜጎችን እንዲገነቡ በማድረግ ፈተናውን መቋቋም ያስፈልጋል፡፡ ዝቅተኛ ኑሮ ያላቸው ዜጎች በረዥም ጊዜ ‹‹ሞርጌጅ›› ቤቶች እንዲገነቡላቸው አቅም የፈቀደውን ሁሉ የማድረግ ጉዳይም ለነገ ሊባል አይችልም፡፡

የግንባታ ጥራትና ወጪ ቆጣቢነትም ይታይ

የጋራ ኮንዶሚኒየም ቤቶች ግንባታ ወጪ ቆጣቢ የምጣኔ ሀብት መርህን እንደሚከተል ይታወቃል፡፡ በተለይ መንግሥት የመሬትና የግብዓት ታክስን ከመደጎሙ ባሻገር፣ ዋጋቸው ተመጣጣኝ የሆኑ ማቴሪያሎችን ለግንባታ መጠቀሙና የታችኛው የሕንፃ ወለሎችን በጨረታ መሸጡ የቤቶቹን ዋጋ በመጠኑም ቢሆን እንዲቀንስ አድርጎታል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ዝቅተኛው የኅብረተሰብ ክፍል አሁንም በቤቶቹ ዋጋ ላይ የሚያነሳቸው ቅሬታዎች እንዳሉ መጤን ይኖርበታል፡፡

አንደኛው የወጪ ምሬት ከግንባታ መጓተት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ ቤት ይደርሰናል ብለው ከአፍ በመንጠቅ ጭምር ገንዘብ የሚቆጥቡ ሰዎች ቁጥር ትንሽ አይደለም፡፡ ይኼ ጅምር ምንም እንኳን የቁጠባ ባህልን ሊያሳድግ ቢችልም፣ ‹‹እነዚህን ያህል ዓመታት በገንዘቡ ብንሠራበት የት እንደርስ ነበር?›› የሚል ቁጭትም ይፈጥራል፡፡

ለምሳሌ የ40/60 ቤቶችን ዕጣ ከሚጠብቁ 160 ሺሕ ያህል ተመዝጋቢዎች መካከል እስከ 500 ሺሕ ብር የሚደርስ ገንዘብ ሙሉ በሙሉ ገቢ ያደረጉ 16 ሺሕ ዜጎች አሉ (በአማካይ ስምንት ቢሊዮን ብር ይሆናል)፡፡ 50 በመቶ የቆጠቡትም ከ20 ሺሕ እንደማያንሱ ተገምቷል፡፡ ለአብነት ይኼን እናንሳ እንጂ በሁሉም የቤት ሥራዎች ከአነስተኛ ቆጣቢው ጀምሮ ከፍ ያለ የሕዝብ ገንዘብ ወደ ባንክ መግባቱ በመንግሥት ግንባታ ፍጥነትና ጥራት ላይ ጫና መፍጠሩ ዕሙን ነው፡፡ ይኼ ግፊት በራሱም የፖለቲካ ተፅዕኖ እንደሚያሳድርም መታመን አለበት፡፡ ስለዚህ የግንባታ ፍጥነትና መጠናከር ጉዳይ በትኩረት ሊታይ የሚገባው ነው፡፡

በሌላ በኩል የግንባታ ወጪን የሚያባክኑ አሠራሮች ሊዳፈኑ አልቻሉም፡፡ ለአብነት ያህል ሕዝብ ቅሬታ የሚያነሳባቸው የጋራ ማብሰያ ቤቶች (ኮሙዩናል ሕንፃዎች) ጉዳይ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድ ሥራዎችና ለዓመታት በመጋዘኖችና በቆሻሻ ተይዘው ክፍት የሆኑ ቦታዎች ጉዳይ እልባት ማግኘት ይኖርበታል፡፡ በአንዳንድ የጋራ መኖሪያ ቤት ሳይቶችም መገንባት ካለባቸው ሕንፃዎች ያነሰ የግንባታ ቁጥር መኖሩ፣ ያላለቁ ሕንፃዎች ተገትረው መታየታቸውና ባለቤት አልባ ክፍሎች በእንጥልጥል መቅረታቸው የብዙዎችን ቁጭት ያጭራሉ፡፡

ከሰሞኑ በሪፖርተር ጋዜጣ ርዕስ አንቀጽ በግልጽ እንደተመለከተውም በ20/80 መርሀ ግብር በቱሉ ዲምቱ፣ በቦሌ አራብሳ፣ በኮዬ ፊጬ፣ በየካ አባዶ፣ በቂሊንጦና በመሳሰሉት የጋራ መኖሪያ ግንባታ ሳይቶች ወጥ አሠራር አልታየም፡፡ ምንም እንኳን የሁሉም የግንባታ ሳይቶች ዲዛይንና ጥራት ተመሳሳይ እንዲሆን ባይጠበቅም፣ በአንድ ወቅት በተቀራራቢ ግብዓትና በጀት የተሠሩ ቤቶች ላይ የጎላ ልዩነት መፈጠሩ ግን እንደ ክፍተት ተወስዶ መታየት ያለበት ነው፡፡ ከግንባታ ተቋራጮች፣ ከአማካሪዎችና ከመንግሥታዊ አካላት የቁጥጥር አቅምና አንዳንድ ጊዜም አሻጥር ጋር የሚገናኘው ይኼ የጥራት መጓደል ተፈጥሯዊ ቢመስልም፣ በአገርና በሕዝብ ሀብት ላይ የሚያሳድረው ጫናና ጉዳት የከፋ ነው፡፡

ሌላው ቀርቶ ‹‹በተመጣጣኝ ዋጋ›› ስም በብዙዎቹ የጋራ ኮንዶሚኒየም ቤቶች እየተገጠሙ ያሉት በርና መስኮቶች፣ የመታጠቢያና መፀዳጃ ዕቃዎች ጥራትም አሳሳቢ ነው፡፡ በቅርቡ በተደረገ አንድ መለስተኛ ጥናት እስካሁን ተገንብተው ከተላለፉ 140 ሺሕ ቤቶች ውስጥ ቢያንስ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆኑት ባለቤቶች ዕቃዎቹን ቀይረዋል፡፡ የማብሰያና መታጠቢያ ክፍሎችን ንጣፍ (ሴራሚክ) ቀይረዋል፡፡ ይህ እንግዲህ ‹‹ለቅንጦት›› ብለው የቅርፅና የዓይነት ለውጥ ለማምጣት ከሞከሩት ውጪ ነው፡፡

እነዚህ ነዋሪዎች በሒሳብ ቀመር ቢሠሉ እስከ መቶ ሺሕ ቢሆኑና እያንዳንዳቸውም በአማካይ ከ30 ሺሕ ብር በላይ ወጪ ቢያደርጉ፣ ከሦስት ቢሊዮን ብር በላይ የአገር ሀብት ባክኗል፣ ዜጎችም ለኪሳራ ተዳርገዋል ሲሉ ባለሙያዎች አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ይህ በመሆኑም አንዳንድ የመስኩ ሙያተኞች መንግሥት የዜጎችን ፍላጎት መገደብ ስለሌለበት የማጠናቀቂያ ግንባታ ሥራዎች በባለ ዕድለኞች እንዲሠሩ ማድረግ አለበት እስከ ማለት ደርሰዋል፡፡ ወይም በቤቶቹ ስፋት ልክ ደረጃቸውን የጠበቁ የማጠናቀቂያ ሥራዎች መከናወን እንዳለባቸው ያሳስባሉ፡፡

በኮንትራክተሮችና በመናኛ ‹‹ዕቃ አቅራቢዎች›› አሻጥር በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር የደሃ አገር ገንዘብ ያላግባብ በመርጨት የሚገኘው ፖለቲካዊ ትርፍ ሳይሆን ኪሳራ እንደሆነ መመርመርም ተገቢ ይሆናል፡፡ ስለዚህ አመርቂ መፍትሔ ማበጀት ይገባል፡፡

የቤቶች አስተዳደርና ማስተላለፍ ሥርዓቱም ይታይ

ከላይ የተጠቃቀሱ የአፍሪካ አገሮች በድጎማ፣ በብድርም ሆነ በግልጽ ጨረታ ገንብተው ለሕዝብ የሚያስተላልፏቸውን ቤቶች በማያሻማ አሠራርና የሕግ ማዕቀፍ መልሰዋል፡፡ ለምሳሌ በደቡብ አፍሪካና በናይጄሪያ ዜጎች በኑሮ ደረጃ፣ በብሔር፣ በፖለቲካ፣ በሥልጣን ወይም በሌላ መለኪየ ሳይለያዩ በቆጠቡት ገንዘብና በቅደም ተከተላቸው መሠረት የመኖሪያ ቤቶችን እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡

በኢትዮጵያ ሁኔታም ቤቶችን ገንብቶ በማስተላለፍ ረገድ የአሠራር ግልጽነትና ተጠያቂነትን ለመፍጠር የተደረገ ጥረት መኖሩ አልቀረም፡፡ ይሁንና ከምዝገባው ጀምሮ አሠራሩ ገና አዲስ ስለነበር ከነባሩ የከተማዋ ነዋሪ ይልቅ ከሌላ አካባቢ የመጣውና በሥርዓቱ መርሐ ግብር ተስፋ አድርጎ የነበረው ይበልጥ ተጠቃሚ ሆኗል፡፡ የቤት ዕደላ ሲደረግም በተለይ በቀዳሚዎቹ ዙሮች የአሠራር ክፍተት እንደነበር ውስጥ አዋቂ ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡ በዚህም ምክንያት አንዳንድ ጥገኛ የዘርፉ አመራሮች በዘር፣ በጥቅምና በመሳሰሉት ለተሻረኳቸው ሰዎች በክፍያም ቢሆን ቤት እንዲያገኙ ማድረጋቸው በቅርቡ ተሃድሶም ተገልጿል፡፡

ከአራተኛው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ አወጣጥ አንስቶ ግን በኮምፒዩተራይዝድና በጥብቅ ዲሲፒሊን ለማስተላለፍ የተደረገ ጥረት አለ፡፡ አሁንም መፈተሽ ያለባቸው አሠራሮች ቢኖሩም ሒደቱ በጥብቅ አመራር እንደሚፈጸም በቅርቡ የከተማዋ ከንቲባ ሲናገሩም ተደምጧል፡፡ ‹እንዲያውም እስካሁን ተመዝግቦ እየቆጠበ ያለውን የቤት ባለቤት ሳናደርግ ወደ አዲስ ምዝገባ አንገባም፣ ተመዝግቦ ያለውም ቢሆን የቀበሌም ሆነ የግል ቤትና ይዞታ እንደሌለው ሳናረጋጋጥ የሕዝብ ጥቅምን አሳልፈን አንሰጥም› ማለታቸው በተግባር መታየት ያለበት ነው፡፡

ከጋራ መኖሪያ ቤቶች አስተዳደር ጋር ተያይዞ የሚነሳው ሌላው ጉዳይ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች የጋራ ሀብት አስተዳደር፣ አጠባበቅና የጋራ ተጠቃሚነትን የተመለከተው ሥራ ነው፡፡ በእርግጥ አስተዳደሩ ቤቶቹን ለግለሰቦች ካስተላለፈ በኋላ የማስተዳደሩ ሥራ የነዋሪዎች ማኅበራት መሆኑ ቢታወቅም በጋራ ማብሰያ ኪራይ፣ በተሽከርካሪ ፓርኪንግ፣ በመጋዘን ኪራይ… የሚገኝ ገንዘብን እንዴት እንደሚያስተዳድሩ ቁጥጥር ያስፈልጋል፡፡ ሌላው ቀርቶ ነዋሪዎች በየወሩ የማከፍሉት መዋጮ ለፅዳት፣ ለፀጥታና ለጋራ ልማት ስለመዋሉ በጥብቅ ቁጥጥር ካልተረጋገጠ ሕዝብ መጎዳቱ አይቀርም፡፡ ስለዚህ የአካባቢ አስተዳደር አካላትና ሕዝቡ ራሱ ብርቱ ትግል ማድረግ ይጠብቀዋል፡፡

ለአብነት ያህል በአንድ የሕዝብ ውይይት ላይ በቅርቡ እንደተሰማው በትልልቅ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግቢ ውስጥ የጎዳና ንግድ፣ አነስተኛ የመንገድ ላይ ቡናና መሰል ሥራዎችን የሚሠሩ (የተሰማሩ) ሰዎች፣ በውንብድና ኪራይ የሚሰበስቡ የማኅበርና የወረዳ አመራሮች እንዳሉ ተጋልጧል፡፡ በግንባታ ግብዓት መያዣ ያገለግሉ የነበሩ መጋዘኖችን ለግል ጥቅም ያከራዩና ከግንባታ በኋላ በኋላ ያልተሰበሰቡ የመንግሥት ሀብቶችን ለዝርፊያ የሚያጋልጡ አሠራሮችም ተለይተዋል፡፡ (በቅርቡ በ15 ሲኖትራኮች የ40/60 ግንባታ ብረቶች ተሰውሮ በፍለጋ መገኘቱ የሚያሳየውም ይህንኑ ነው፡፡)

በአጠቃላይ መንግሥት የከተሞችን በተለይም የአዲስ አበባን የቤቶች ችግር ለመቅረፍ እያደገ ያለው ጥረት የሚደነቅ ነው፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ እንደተሠራ ተዓምርና እንደተገኘ መና ብቻ ከመቁጠር ወጥቶ አሠራሩን እየፈተሹ፣ እየገሰገሰ የመጣውን የፍላጎት ናዳ የሚመክት የቤት ግንባታ ማከናወን ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ መንግሥት ‹‹እኔ ብቻ ልገንባ›› ከማለት ወጥቶ ምቹ ሁኔታን በመፍጠር የተሳተፈውን ዓይነትና ብዛት ማሳደግ አለበት፡፡ ሕዝቡም በማስተላለፍ፣ በማስተዳደርም ሆነ በግንባታው ረገድ ተጠቃሚና ተሳታፊነቱን በፍትሐዊነት እያረጋገጠ መሄድ አለበት፣ ይገባልም፡፡ ይኼ ሲሆን ነው ጅምሩ የሚሰምረው፣ ከተሜው እፎይ የሚለው፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

 

 

Standard (Image)

የኦሮሚያ “የኢኮኖሚ አብዮት” የወለዳቸው ተስፋዎችና ሥጋቶች

$
0
0

አወዳይ ከጥቂት ዓመታት በፊት በሐሮማያ ወረዳ ሥር ያለች አንዲት ትንሽ ቀበሌ ነበረች፡፡ አሁን ከተማዋ ከሐረርጌ ከተሞች ምናልባት ከጭሮ (አሰበ) ቀጥሎ ሁለተኛዋ ትልቅ ከተማ ነች፡፡ ከተማዋ ለአገሪቱ በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ዓመታዊ ገቢ የሚያስገኝላት የጫት ንግድ (ቢዝነስ) ማዕከል ነች፡፡ የጫት ንግድ (ቢዝነስ) ተዋናዮቹን የአውሮፕላን ባለቤት እስከ ማድረግ የሚደርስ ትልቅ ንግድ ነው፡፡ ሌሎቹ የንግዱ ተዋናዮችም እንደየደረጃቸውና ሚናቸው ተጠቃሚ ናቸው፡፡ አሁን የአወዳይ ከተማ በእሷ ደረጃ ካሉ ሌሎች የአገራችን ከተሞች ሁሉ የበለጠ በርካታ ሚሊዮነሮች የሚኖሩባት ከተማ ነች፡፡ የአወዳይ ሚሊዮነሮችና ሌሎችም የመካከለኛ ገቢ ባለቤቶች በእነሱ ደረጃ እንዳለ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የኢንተርፕረነርሺፕ ክህሎታቸው ውስን ስለሆነ፣ ገንዘባቸውን ቅንጡ መኖሪያ ቤት በመገንባት፣ መኪና  በመግዛት፣ ወይም ባለሦስት ወይም አራት ፎቅ ሕንፃ በመገንባትና በመሳሰሉት የተለመዱ ዘርፎች ላይ ነው የሚያውሉት፡፡

በነገራችን ላይ ከአወዳይ ባሻገር እስከ ምዕራብ ሐረርጌ ድረስ ያሉ በርካታ ወረዳዎች በጫት ወጪ ንግድ ተሳታፊ ናቸው፡፡ የአዲስ አበባና የአካባቢዋን የጫት ገበያም ቀላል በማይባል ደረጃ የተቆጣጠረው ሐረርጌ ነው፡፡ ሐረርጌ ከጫት ባሻገር የአገሪቱ ምርጥ የሚባለው ቡና አምራች አካባቢም ነው፡፡

ግን ሌላ ተቃራኒ ሀቅም አለ፡፡ ሐረርጌ ከሌሎቹ የኦሮሚያ አካባቢዎች በላይ የምግብ ዋስትና ችግር ያለበት አካባቢ ነው፡፡ ከፍተኛ የመሬት ጥበት ያለበት አካባቢ ነው፡፡ በዚህም መሬትም ሥራም የሌላቸው ወጣቶች የሞሉበት አካባቢ ነው፡፡ እነኚህን ተቃራኒ እውነታዎች ማስታረቅ የመንግሥት ኃላፊነት ነበር፡፡ በተለይ ‹‹ግራ ዘመም›› የሆነው ኢሕአዴግ በዚህ ጉዳይ ላይ “ቀኝ ዘመሞች ቢሆኑ የማያደርጉትን” ዕርምጃ መውሰድ ነበረበት፣ ግን አልወሰደም፡፡ አወዳይ ላይ በተወሰኑ ሰዎች እጅ ብዙ ሚሊዮን ብር አለ፡፡ ይኼ ብር ግን ለብዙኃኑ የሐረርጌ ምንዱባን የሥራ ዕድልን ሊፈጥር በሚችልበት ሁኔታ አይደለም ኢንቨስት እየተደረገ ያለው፡፡

እዚህ ጋ ነው የኦሮሚያ የኢኮኖሚ አብዮት የዘገየ ቢሆንም አስፈላጊነቱ የሚታየን፡፡ ብዙም የኢንተርፕሩነርሺፕ ክህሎት የሌላቸው ሚሊዮነር አርሶ አደሮችና ከተማ ቀመሶች ከለመዱት ዘርፍ ውጪ ለብዙ ሺዎች የሥራ ዕድልን ሊፈጥሩ በሚችሉና ዘመን ተሻጋሪ በሆኑ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች መሰማራት የሚችሉት፣ ሐሳብ የሚያመነጭላቸውና የሚያስተባብራቸው ካለ ብቻ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር ኦሮሚያ እየሄደበት ያለው አቅጣጫ ሌሎች ክልሎችም ሊማሩበት የሚገባ ይመስለኛል፡፡

የኦሮሚያ የኢኮኖሚ አብዮት መቀጣጠልን ተከትሎ ብዙ ድምፆች እየተሰሙ ነው፡፡ አብዛኞቹ ድምፆች የተስፋና የማበረታቻ ናቸው፡፡ ጥቂት የሥጋትና የትችት ድምፆችም አሉ፡፡ ከሥጋት አንፃር እየተነሱ ያሉ ድምፆች የኢኮኖሚ አብዮቱ ሲጀመር ምንም እሴት የማይጨምሩ፣ የማዕድን ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች መሬት ነጠቃና የሲሚንቶ ፋብሪካዎች የፑሚስ ግብዓት በፋብሪካው በራሳቸው መሆኑ ቀርቶ በተደራጁ የኦሮሚያ ወጣቶች እንዲቀርብ መደረጉ ላይ የተመሠረቱ ናቸው (የታሰሩት ሳይፈቱ፣ የዴሞክራሲ ጥያቄዎች እንደዚህ ሳይሆኑ፣ እንደዚያ ሳይሆኑ፣ . . . የሚሉና ከኢኮኖሚ አብዮቱ ጋር ተያያዥነት የሌላቸውን አጀንዳዎች እዚህ ጋ አናይም)፡፡

 መሬት የተነጠቁ ሰዎች ‹‹ሕገ መንግሥታዊ መብታችን ተጣሰ!›› እያሉ ሲሆን፣ አቅም ያላቸው ባለሀብቶች አቅምና ቴክኖሎጂው በሌላቸው ወጣቶች ሊሠሩ የሚችሉ ሥራዎችን ሲሠሩ መቆየታቸውን መንግሥት እንዲያበረታታላቸው መጠበቃቸው ትክክል አይመስለኝም፡፡ ባይሆን ውሳኔው ድንገተኛ ነውና የመዘጋጃ ጊዜ እንዲሰጣቸው፣ ወይም የሥራ ዘርፍ ሲቀይሩ አስፈላጊው ማበረታቻና እንደ ሁኔታው ካሳም እንዲታሰብላቸው ቢጠይቁ ተገቢ ነው እላለሁ፡፡ 

በዚህ ረገድ ኢሕአዴግ ‹‹ማኅበራዊ መሠረቶቼ ናቸው›› የሚላቸውን አርሶ አደሮችን፣ የከተማ ንዑስ አምራቾችንና ላብ አደሮችን የረሳ በሚያስመስል ሁኔታ በ‹‹ማኅበራዊ መሠረቶቹ ላይ›› አንዳንዴ የቀኝ ኃይሎች እንኳ የማያደርጉትን ጫና ሲፈጥርባቸው ይስተዋላል፡፡ እዚህ ግባ በማይባል ካሳ አርሶ አደሮችና የከተማ ነዋሪዎች ከይዞታቸው እየተፈናቀሉ መሬታቸው ለባለሀብቶች ይሰጥባቸዋል፡፡ 30 ወይም 100 የከተማ ወይም የገጠር ነዋሪዎች ተፈናቅለው መሬቱን ያገኘው ‹‹ኢንቨስተር›› ሕንፃ ገንብቶ ቢሮዎችን በማከራየት ወይም የሸክላ አፈር ቆፍሮ በመሸጥ የራሱን ኑሮ ሲቀይር፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ ወይም በኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ግን የሚጫወተው ሚና ሳይኖር የቆየ ቢሆንም፣ ቡራኬውን ያገኘው ግን ከ‹‹ግራ ዘመሙ›› ኢሕአዴግ ነበር፡፡ ማኅበራዊ መሠረታቸውን መካከለኛና ከፍተኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች ላይ ያደረጉ በርካታ ምዕራባውያንም ሆኑ ወደ ብልፅግና እየተንደረደሩ ያሉት ምሥራቃውያን ፓርቲዎች እንኳ፣ በዚህ ደረጃ አቅም የሌላቸው የመሬት/ቤት ባለይዞታዎችን ሲጫኑ አይታይም፡፡

አዕላፍ ምንዱባን ከመሀል ከተማ እየተፈናቀሉ በእነሱ ቦታ ላይ ‹‹ኢንቨስተሮች›› ሕንፃ ገንብተው እንዲያከራዩ ከመፍቀድ፣ የመሬት ባለቤቶች በማኅበር ተደራጅተው ባንክም ብድር አመቻችቶላቸው ሕንፃውን እንዲገነቡ ቢደረግ እውነተኛ ሕዝባዊ ወይም ግራ ዘመም መንግሥት ያስብላል፡፡ በዚህ ረገድ ደኢሕዴን/ኢሕአዴግ በሐዋሳ ከተማ የመሬት ባለይዞታዎች ከባንክ ብድር እየተመቻቸላቸው የሚከራዩ ቤቶችን እንዲገነቡና የኢንዱስትሪ ፓርክ የጠራቸው አዳዲስ ነዋሪዎች በቤት እንዳይቸገሩ የጀመረውን አቅጣጫ ማጠናከር፣ ድጋፉ ለትልልቅ የንግድ ሕንፃዎችና ሪል ስቴቶች ግንባታ ጭምር ተፈጻሚ መሆን እንዲጀምር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

በገጠርም እሴት በማይጨምሩ የማዕድን ዘርፎች ተሰማርተው በርካታ ምንዱባን ሊሠሩ የሚችሉትን ብቻቸውን ሲሠሩ የነበሩ ‹‹ኢንቨስተሮች›› የእስከ ዛሬው ቡራኬ ኢሕአዴግ ማኅበራዊ መሠረቶቹን በመዘንጋት የተፈጠረ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋቸዋል፡፡ እንዲያውም ይኼው ዕርምጃ ወደ ከተሞችም ሊገባ እንደሚችል /እንደሚገባ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ 

የግዙፎቹ የሲሚንቶ ፋብሪካዎችን ግብዓት አቅርቦትን በተመለከተ ፋብሪካዎቹ በራሳቸው ለመሥራት ግሬደሮችን፣ ገልባጮችንና ሌሎችንም አስፈላጊ ግብዓቶች አሟልተው ሲሠሩ የነበሩ ከመሆናቸው አንፃር፣ ሠራተኞቻቸውም ሥራውን ለረዥም ጊዜ የለመዱትና የተካኑበት ከመሆናቸው አንፃር ብዙም ደስተኛ ባይሆኑ አይገርምም፡፡ እነሱ ላይ የሚፈጠር ቅሬታ ደግሞ በቀላሉ ሚዲያዎችና ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ አማካሪዎች ጆሮ ሊደርስ መቻሉን ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ በንድፈ ሐሳብ ደረጃ የግብዓት አቅርቦቱን ወጣቶች ተደራጅተው መሥራታቸው ተገቢ ቢሆንና የግብዓት መሸጫ ዋጋውም ፋብሪካዎቹ በተስማሙበት መጠን ቢሆንም፣ አፈጻጸሙ ላይ መንጠባጠቦች ሊኖሩ እንደሚችሉ፣ ይኼ ደግሞ ከፍተኛ ፉክክር ባለበት የሲሚንቶ ገበያ ላይ በኦሮሚያ ያሉ ፋብሪካዎችን ተወዳዳሪነት አነሰም በዛ ሊጎዳ እንደሚችል ማሰብ ተገቢ ይመስለኛል፡፡ ይኼ ላለመሆኑ ዋስትና መስጠት ከተቻለ ኦሕዴድ/ኢሕአዴግ በነደፈው አቅጣጫ በሺሕ የሚቆጠሩ ወጣቶች የሥራ ዕድል ይፈጠርላቸዋል፡፡  ፋብሪካዎቹን የጎሪጥ የሚያይም አይኖርም፡፡ ሒደቱን ግን በጥንቃቄ መከታተልና ከፋብሪካዎቹ ማኔጅመንት ጋር ተቀራርቦ መሥራት ይጠይቃል፡፡

በኦሮሞ የኢኮኖሚ አብዮት ላይ በይፋ እየተሰሙ ያሉ ሥጋቶች እነኚህ ብቻ ቢሆኑም፣ ትኩረትን የሚሹ ሌሎች ነጥቦችም ይኖራሉ፡፡

የመጀመሪያው አገሪቱ ወደ ኢኮኖሚያዊ ትራንስፎርሜሽን መሸጋገር ካለባት ከአንድ ኢንቨስተር እንዲመጣ የምንጠብቀውን ገንዘብ ከብዙ ሺሕ ነዋሪዎች በመሰብሰብ በራስ አቅም ግዙፍ ኢንቨስትመንቶችን መፍጠር ፋይዳው የሥራ ዕድል ከመፍጠር ያለፈ ነው፡፡ የነገዋ ኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በጥቂቶች እጅ ሥር አለመሆኑን ከወዲሁ የምናረጋግጥበትም ጭምር ነው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃም ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ ሆኖም በዚህ ረገድ ከዚህ በፊት ምንም አልተሠራም ማለት አይደለም፡፡

የዛሬ አሥር ዓመታት ገደማ የአክሲዮን ማኅበራትን ማቋቋም አጓጊና ብዙዎችን የሳበ ንግድ ሆኖ ነበር፡፡ አሁን የምናያቸው ስካይ ባስና አሊያንስ የከተማ አውቶብስ በዚህ መንገድ የተቋቋሙ ናቸው፡፡ የቅርብ ጊዜዎቹ ሦስት ቢራ ፋብሪካዎችም መሠረታቸው የአክሲዮን ቢዝነስ ነው፡፡ እስካሁን ከዳር ባይደርሱም የኅብር ስኳርና የሐበሻ ሲሚንቶም ሌሎቹ ተጠቃሽ አክሲዮን ወለድ ቢዝነሶች ናቸው፡፡

መንግሥት ይኼንን ዘርፍ በማጠናከር በርካታ ግዙፍ ኢንቨስትመንቶች እንዲፈጠሩ ማድረግ ሲገባው፣ ዜጎች በአክሲዮን በሚቋቋሙ ንግዶች ላይ አመኔታ እንዳይኖራቸው የሚያደርጉ ተደራራቢ መሰናክሎች ተፈጥረውባቸዋል፡፡ የፌዴራልም ሆነ የክልል ማኅበራት ማደራጃዎች በዚህ ረገድ ሲጫወቱ የነበረው ሚና ለብዙ ትችቶች የተጋለጠ ነው፡፡ መንግሥት በቅርቡ በዚህ ረገድ የነበሩ ክፍተቶችን ለመድፈን የሚያስችሉ ዕርምጃዎችን እወስዳለሁ እያለ ሲሆን፣ ዕርምጃው ማኅበራትን ከመደገፍ አልፎ የአገሪቱ ግዙፍ የኢኮኖሚ አንቀሳቃሾች በጥቂት ግለሰቦች ሳይሆን በብዙኃን ዜጎች ባለቤትነት ሥር እንዲሆኑ የማድረግና ያለማድረግ ጉዳይ ጭምር መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት የምር ለውጥ ሊያመጣ ይገባል፡፡

 እስከ ዛሬ ኢሕአዴግ ሕዝባዊ መሠረቶቼ ለሚላቸው ከተሜዎች ያመቻቸላቸው በጥቃቅንና አነስተኛ መደራጀትና አሁን ደግሞ በከተማ ሴፍቲኔት መታቀፍን እንጂ፣ ትልልቆቹ ቢዝነሶች ላይ መሰማራትን ሳይሆን መቆየቱ ያሳዝናል፡፡ ይኼንን ግዙፍ ስህተቱን ሊያርም የሚችበት ዋነኛ መንገድ ነው የአክሲዮን ቢዝነስ እንዲያብብ ማድረግ፡፡

የኦሮሚያ ኢኮኖሚ አብዮት የወለዳቸው ግዙፍ ኩባንያዎችም በዚህ ረገድ ከተጋረጠባቸው ሥጋት ነፃ ማድረግ ከኦሕዴድ/ኢሕአዴግ ይጠበቃል፡፡ የመንግሥት ባለሥልጣናት አላስፈላጊ ጣልቃ ገብነት መቅረት፣ የአክሲዮን ማኅበራቱ ማኔጅመንቶች አቅምና ተዓማኒነት ደግሞ አስተማማኝ መሆን አለበት፡፡

ከኦሮሚያ ኩባንያዎች ጋር ተያይዞ ትኩረት የሚያሻው ሌላው ሥጋት ደግሞ የኢንቨስትመንት ዘርፎች መረጣ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ አንዳንድ ዘርፎች በገበያው ውስጥ አስቀድሞ በቂ ተዋናይ የተሰማራባቸው ናቸው፡፡ ለዚህም የሲሚንቶ ፋብሪካንና የትራንስፖርት ንግድን መጥቀስ ይቻላል፡፡ የንግድ ዘርፎቹ በክልሉ ተወላጆች፣ በጎ ፈቃደኛ ምሁራንና በክልሉ አመራሮች የሚደገፉ ከመሆናቸው አንፃር፣ እንዲሁም ዘርፎቹ የግዙፍ ካፒታል ባለቤቶች ከመሆናቸው አንፃር ብዙም ባልተደፈሩ፣ ግን አዋጪ በሆኑ ዘርፎች ላይ መሰማራት ቢታሰብበት መልካም ይመስለኛል፡፡

በሌላ በኩል በኦሮሚያ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የክልል ኢንዶውመንቶችም ሊነሳ የሚችለው ሥጋት የአገሪቱን አንድ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ማኅበረሰብ የመፍጠር ራዕይን ሊሸረሽር በሚችል መንገድ ንግዶቹ ብሔር ተኮር እየሆኑ የመቋቋማቸው ጉዳይ ነው፡፡ ሥጋትነቱ ከአገሪቱ ራዕይ ባሻገር የተቋማቱንም በነፃ ፉክክር ላይ የተመሠረተ ገበያን የማስፋት ጥረትንም ሊጎዳ ይችላል፡፡ በዚህ ረገድ ነገ ምን ዓይነት የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ለመፍጠር ጥረት እያደረግን ነው? የሚለውን ማሰብ ከሁሉም ይጠበቃል፡፡ አንዱ ከጀመረ ግን ሌላውም መከተሉ አይቀሬ ነውና በዚህ ረገድ ኦሮሚያን መውቀስ አይቻልም፡፡ ምክንያቱም አሁን ከአማራ ክልል አካባቢ የግዙፍ ኩባንያ ምሥረታ እየተሰማ ነውና፡፡

በተረፈ አሁን በመላ አገሪቱ እየተቋቋሙ ካሉ የኢንዱስትሪ ፓርኮች መካከል የ49 በመቶ ድርሻቸው ልምድ ባላቸው የውጭ ባለሀብቶች የሚያዙ ግዙፍ የኢንዱስትሪ አክሲዮኖች እየተቋቋሙ፣ በየእጃችን ያለውን ገንዘብ አክሲዮን እንድንገዛበት የማኅበራት ማደራጃም ይሁን ሌላ አካል ቢሠራ የአገሪቱ ቁጥር አንድ ባለውለታ ይሆናል፡፡ የባንግላዴሽ፣ የቻይናና ሌሎች የምሥራቅ እስያ ልምድ ያላቸው ኩባንያዎችን ሎቢ እያደረጉ በአገሪቱ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ላይ እንዲሰማሩና 51 በመቶ ድርሻቸውን ደግሞ በአክሲዮን እንዲሸጡ ማድረግ ከተቻለ፣ በአገራችን የጨርቃ ጨርቅ ንግድ ላይ እመርታዊ ለውጥ ማምጣት ያስችላል፡፡ በሌሎች ዘርፎችም ላይ ተመሳሳይ ሥራዎችን መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ኅብረተሰቡ አመኔታ እንዲያድርበት ማድረግ ከተቻለ ተዓምር መሥራት ይቻላል፡፡ የኦዳ አውቶብስ አክሲዮን ማኅበር በአንድ ቀን ብቻ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ አክሲዮን መሸጡ የሚያሳየን ይኼንኑ ነው፡፡ ባለሀብቶችን እንጠብቅ ቢባል ኖሮ ይኼን ያህል ካፒታል ያለው ኢንቨስተር በቀላሉ የሚገኝ አልነበረም፡፡

 ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው addis2005chekol@gmail.com. ማግኘት ይቻላል፡፡

 

Standard (Image)

የውኃ ፍርኃትና ሥጋት (ኢትዮጵያና ግብፅ)

$
0
0

ጆርጅ ፍሬድማን የተባሉ የጂኦፖለቲክስ ምሁር ቦታና ፍራቻ በጂኦፖለቲክስ ጥናት ውስጥ ሁነኛ ሥፍራ አላቸው ይላሉ፡፡ ቦታና ፍራቻ የአንድን አገር የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ባህሪ በመወሰን ረገድም ወሳኞች ናቸው፡፡ ይኸው እውነታ ኢትዮጵያንና ግብፅን ለይቶ አልተዋቸውም፡፡ ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ዋነኛ መገኛ በመሆኗ ወንዙ በተመጣጠነና ምክንታዊ በሆነ መንገድ ጥቅም ላይ መዋል አለበት የሚል አቋም ሲኖራት፣ ግብፅ ደግሞ በወንዙ መጥለቂያ አካባቢ በመኖሯና ሥልጣኔዋና እስትንፋሷ የተገነባው በዚሁ ዳርቻ በመሆኑ አንድም ጠብታ ሳይጎድል ድንበሯ ውስጥ ,ልö እንዲገባ ትፈልጋለች፡፡ በመሆኑም ግብፅ ኢትዮጵያ፣ ግድብና መስኖ የሚባሉት ቃላት ፈጽሞ አይመቿትም፡፡

በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው የውኃና ጂኦፖለቲካዊ እሰጥ አገባ መነሻው ጥንት ነው፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርና በኃይድሮፖለቲክስ ጥናታቸው የሚታወቁት ዶ/ር ተስፋዬ ታፈሰ፣ እ.ኤ.አ. በ2001 ባሳተሙት THE NILE QUESTION: Hydropolitics, Legal Wrangling, Modus Vivendi and Perspectives” በተባለው መጽሐፍ ውስጥ ግብፆች በፍርኃት፣ በጥርጣሬና በሥጋት ተሸክመው ዕድሜ ልካቸውን አሳልፈዋል ይሉናል፡፡ የዚህ ሁሉ ምንጭ ደግሞ ኢትዮጵያ ውስጥ ሊከናወን ይችል ይሆናል ብለው የሚያስቡት ዓባይን የመገደብ ሥራ ነው፡፡ የጥንትም ሆነ የቅርቦቹ የግብፅ መሪዎች ለሕዝባቸው ሲነግሩት የኖሩት አንድ ነገር ብቻ ነው፡፡ የኢትዮጵያን የዓባይን ፍሰት የመቆጣጠርና የግብፅን ሕዝብ በረሃብ የመጨረስ ዕNድ፡፡

በመሆኑም ግብፃውያን ኢትዮጵያን በፍራቻና በጥርጣሬ ሲመለከቷት ኖረዋል፡፡ ዶ/ር ተስፋዬ በመጽሐፋቸው እንደጠቀሱት ይህንን በሚገባ የተገነዘቡት የኢትዮጵያ መሪዎች ምንም እንኳን አቅሙ ባይኖራቸውም፣ ዓባይን የመገደቡን ጉዳይ በማስፈራሪÃነት ሲጠቀሙበት የተስተዋሉባቸው ጊዜዎች ነበሩ፡፡ ግብፅ ውስጥ የሚገኙ የኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን ተከታዮች ጥቃት እንዳይደርስባቸውና ግብፅ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ እንድትልክ የዓባይን ወንዝ በ«ስፈራሪያነት ተጠቅመውበታል፡፡

ከ1066 እስከ 1072 ባሉት ሰባት ዓመታት ግብፆች በረሃብ በመጠቃታቸው፣ በወቅቱ የነበረው የግብፅ ካሊፍ መልዕክተኞችን ወደ ኢትዮጵያ በመላክ የተገደበው የዓባይ ወንዝ እንዲለቀቅላቸው የኢትዮጵያን ንጉሥ ለማሳመን ጥረዋል፡፡ በወቅቱ የረሃቡ መነሻ ኢትዮጵያ የዓባይን ወንዝ መገደቧ ነው ብለው ያምኑ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ የወንዙ መነሻ መሆኗና የግብፃውያን የግድብ ፍራቻ የኃይድሮና የጂኦፖለቲካዊ ንትርክ መነሻ ከሆነ እጅግ የቆየ መሆኑ ማመላከቻው ይህ ታሪክ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን መሪዎችም ግብፅ አንዳች ተንኮል ብታስብ ወንዙን መገደባቸው እንደማይቀር ሲዝቱ ቆይተዋል፡፡ ግብፅም መፍትሔው ኢትዮጵያን መቆጣጠር ወይም ማተራመስ መሆኑን ማሰብ ከጀመረች እጅግ ቆይታለች፡፡

በ17ኛው ክፍል ዘመን መጠናቀቂያ አካባቢ ግብፅ በቱርክ በመደገፍ ኢትዮጵያን ለመውረርና ለማተራመስ ሞክራለች፡፡ ግብፃውያን የዓባይ ወንዝ የሚፈስባቸውን አካባቢዎች በመቆጣጠርና ከግዛታቸው ጋር በማዋሀድ ታላቋን ግብፅ ለመፍጠርም አስበው ያውቃሉ፡፡ ምዕራባውያን አማካሪዎቻቸውም ጭምር ኢትዮጵያን መቆጣጠር፣ ወይም በኢትዮጵያ ሥርዓት አልባነት እንዲሰፍን ማድረግ፣ ኢትዮጵያውያን ዓባይን ስለመገደብ እንዳያስቡ ማስቻያ መሣሪያ መሆኑን ይነግሯቸው ነበር፡፡ ታላቋን ግብፅ የመመሥረት ህልማቸውን ለማሳካትም ግብፃውያን አሜሪካውያንን ስዊሶችን፣ እንግሊዞችንና ዴንማርካውያን ቅጥረኞችን በማሰማራት ኢትዮጵያን ለመውረር የሚያደርጉትን ጥረት እንዲያግዟቸው ያደርጉ ነበር ሲሉ ዶ/ር ተስፋዬ በመጽሐፋቸው አካትተዋል፡፡

ግብፃውያን ኢትዮጵያ ዓባይን ለመገደብ የገንዘብ አቅም የላትም ብለው ያምኑ የነበረ ሲሆን፣ ዓለም አቀፍ ለጋሾችና አበዳሪዎችም ለኢትዮጵያ ገንዘብ እንዳያቀርቡ ሌት ተቀን ሠርተዋል፡፡ ኢትዮጵያን ለማተራመስም መቀነታቸውን ፈትተዋል፡፡ የትኛውም የግብፅ መሪ ወደ ሥልጣን የወጣ ቀን የመጀመርያ ሥራው “ነጠላዬን አቀብሉኝ” በማለት ºቱን ወደ ኢትዮጵያ መጠቆም ነው፡፡ ዋነኛ ሥራው ፍርኃትና ሥጋትን ማስቀጠል ነው፡፡ አሁን በእስር ላይ የሚገኙት መሐመድ ሙርሲና ሚኒስትሮቻቸው ዓለም በቴሌቪዥን መስኮት እየተመለከታቸው ኢትዮጵያን ማተራመስና  ግንድቡንም ማፍረስ እንዳለባቸው ተነጋግረዋል፡፡ በመሆኑም ግብፅ የኢትዮጵያንና ዓባይን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ ማጠንጠኛ አንደኛው ዘንጓ አድርጋዋለች፡፡

ግብፅ በአሁኑ ፕሬዚዳንቷ አብዱልፈታህ አልሲሲ አማካይነት የተለየ ነገር አሳይታናለች፡፡ አልሲሲ ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርም ደሳለኝና ከፕሬዚዳንት አል በሽር ጋር በመሆን የመርሆዎች መግለጫና ለትብብር መነሻ የሆነውን ስምምነት ፈርመዋል፡፡ ስምምነቱ እርባና ቢስ ነው ብለው የሚያምኑ እንዳሉ ሁሉ፣ ታሪካዊና ጠቃሚ ነው ብለው የሚያምኑም በርካታ ናቸው፡፡ ዶ/ር ሳልማን የተባሉ የውኃ ፖለቲካ ምሁር ኢትዮጵያ አሸንፋለች ይላሉ፡፡ በእሳቸው እምነት ስምምነቱ የግብፅን የተዘጋ በር ከፍቷል፡፡ መነጋገርንና ትብብርን ይሰብካል፡፡ ልማትን፣ አካባቢያዊ ውህደትንና ዘላቂነትን ያበረታታል፡፡ በዚህ ስምምነት ግብፅ “ግድቡ ይገደብ፣ ነገር ግን ጉልህ የሆነ ጉዳት በማያደርስ ሁኔታ መሆን አለበት፤” ትላለች፡፡ ፍትሐዊ አጠቃቀምን ደግፋለች፡፡ አለመግባባት ቢፈጠር እንኳ የጠረጴዛ ውይይትን መርጣለች፡፡ ከግድቡ የሚመነጭ የኤሌክትሪክ ኃይልን ለመግዛትም ተስማምታለች፡፡

ከዚህ አንፃር ሲታይ ዶ/ር ሳልማን በፍፁም ትክክል ናቸው፡፡ ዶክተሩ ስምምነቱ ውስጥ ባይጠቀስም እ.ኤ.አ. የ1929 እና 1959 ስምምነቶች ፈርሰዋል ብለው ያምናሉ፡፡ ግብፅ እነዚህን ስምምነቶች ሳትጨምሩና ሳትቀንሱ እንዲሁም ሳታንገራግሩ ተቀበሉኝ በማለት ተቸክላ መቆየቷ ይታወቃል፡፡ ለውጡን ያመጣው ምዕራባውያን በዚህ ጉዳይ ላይ ፊት ስላነሷትና ኢትዮጵም በበርካታ መንገዶች እየገነገነች መምጣቷ XምI ነው፡፡ ሆኖም ግን የጦር ሠፈር የመመሥረት ዕቅዷ በሶማሌላንድ ተቀባይነት ያጣው ግብፅ ትብብር በመመሥረትና በማጠናከር ሰበብ ኢትዮጵያን እየከበበች መሆኗ ደግሞ “ያደቆነ ሰይጣን ሳያቀስ አይቀርም፤” አሰኝቷል፡፡ በመሆኑም ግብፅ እርግጡን እስካልነገረችን ድረስ አንፃራዊ ዝግጅት ማድረግ የግድ ይለናል፡፡

ግድቡን እየገደብን መሆኑና የኃይል ሚዛኑን እየቀየርን ለመሆኑ የማያጠራጥር ሲሆን፣ ይህ ውጤት የተገኘው በመሪዎች የፖለቲካ ቁርጠኝነትና ሕዝብን እያሳተፈ ያለ አገራዊ ፕሮጀክት በመፍጠራችን መሆኑ ሌላው የማያጠራጥር ጉዳይ ነው፡፡ ሕዝቡን ማስተባበርና የባለቤትነት ስሜት እንዲሰማው ማድረግ የመንግሥት ኃላፊነት ነው፡፡ ጎን ለጎንም መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን ማድረግ የግብፅን ዓይነት የጠብ አጫሪነት ፍላጎት በማዳፈን የውስጥ ሰላምን ለመጠበቅ፣ እንዲሁም ልማትን ለማረጋገጥ የሚረዳ በመሆኑ ትጋታችን እጥፍ ድርብ መሆን አለበት፡፡

የዓባይ ተፋሰስ አገሮችን በማስተባበር ወደ አንድ አቅጣጫ በማምጣት ለፍትሐዊ ተጠቃሚነት አጥብቃ የሠራችው ኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ግብፅ እንዲካተቱበት መሥራት ይጠበቅባታል፡፡ የመርሆዎች መግለጫ ስምምነቱን መሠረት አድርጋ ጫና ማሳደር አለባት፡፡ የዓባይ ተፋሰስ አገሮች የጋራ ፕሮጀክት ቢኖራቸው ለአካባቢው ውህደት ጉልህ አስተዋጽኦ ስለሚኖረው ኢትዮጵያ የጀመረችውን መቀጠል አለባት፡፡ ለዴሞክራሲው መጎልበት አሁን ግድ እያለ ያለውን የተቃዋሚዎችንና የመንግሥትን/ኢሕአዴግን ውይይት ወደላቀ ደረጃ ማሸጋገር የቤት ሥራችን ነው፡፡ የጀመርነውን በጎ ነገር ሁሉ ለማስቀጠልና ደንቃራዎቻችንን አስወግደንና አልፈን ለመሄድ ወታደራዊ ኃይላችንን ማጎልበትም መርሳት የለብንም፡፡ ወታደራዊ ኃይላችን ጠብ አጫሪዎችን ለማቀዝቀዝና  “ተመጣጣኝ” ብቻ ሳይሆን ሥር የሚነቅል ዕርምጃ ለመውሰድም እንጠቀምበት፡፡ ለዓለም አቀፍ ሰላም መስፈን የበኩላችንን ለማበርከት የምናደርገው ጥረትም እጅግ በተሻለ መንገድ መቀጠል አለበት፡፡

ግብፃውያን በተለይም መሪዎቻቸው ለዘመናት ተጣብቷቸው የቆየው ፍርኃትና ሥጋት እንዲህ በቀላሉ ይላቀቃቸዋል ብሎ ማሰብ የዋህነት በመሆኑ፣ ሕዝብና መንግሥት እጅና ጓንት በመሆን አገርን ማልማትና ድንበሯንም መጠበቅ ይገባናል፡፡ ይህ ለኢሕአዴግ፣ ለተቃዋሚዎች፣ ለዚህኛው ወይም ለዚÃኛው ብሔረሰብ ወይም ደግሞ ለተወሰነ የኅብረተሰብ ክፍል ብቻ የሚተው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሁላችንም ኃላፊዎች ነን፡፡ ለሚቀጥለው ትውልድ የምናስረክባት አገር ሁሌም የተሻለች መሆኗን ማረጋገጥ አለብን፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ያለንበት ጂኦፖለቲካዊና ኃይድሮፖለቲካዊ ሁኔታ ከምንጊዜውም በላይ እየተወጠረ መሄዱ ነው፡፡ ያለንበት ቦታና ሁኔታ ፍፁም የሚያስተኛ አይደለም፡፡  

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው leulsegedg@yahoo.comማግኘት ይቻላል፡፡      

 

 

Standard (Image)

የዓለም ፖለቲካ ኢኮኖሚና የኢትዮጵያ ህዳሴ በአቶ ዓለምነው መኮንን ብዕር ሲቃኝ

$
0
0

 

ካለኝ ቅርበት አኳያ አቶ ዓለምነውን አንተ እያልኩ ብገልጸው ደስ ባለኝ ነበር፣ ሆኖም በአገራችን ባህል መሠረት ትልቅ የፖለቲካ ሥልጣን ላይ የሚገኝን ሰው አንተ ማለት አንድም እንደ መዘርጠጥ፣ አሊያም አክብሮት እንደ መንፈግ ተደርጎ ስለሚወሰድ በዚህ መጣጥፍ ውስጥ አቶ ዓለምነውን አንቱ እያልሁ ለመግለጽ ተገድጃለሁ፡፡ ብዙዎቻችን እንደምናስታውሰው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በብአዴን/ኢሕአዴግ አባላትና በአማራ ክልል ሕዝቦች ዘንድ አቶ ዓለምነው መኮንን እየታወቁ የመጡት በአወዛጋቢ ንግግራቸው ብቻ ሳይሆን፣ በአንባቢነታቸውና አዳዲስ ሐሳቦችን በማመንጨት የተግባር መመርያ ለማድረግ በመንቀሳቀሳቸውም ጭምር ነው፡፡

በተለይም በአንድ ወቅት በግሉ ፕሬስና በማኅበራዊ ሚዲያው አካባቢ “የአማራን ሕዝብ ሰድበው ለሰዳቢ ሰጡት” በሚል ሽፋን የእሳቸውን ሰብዕና ለመግደል ጥረት ከመደረጉም በላይ፣ በአሁኑ ወቅት እሳቸውና የሥራ ባልደረቦቻቸው በፊታውራሪነት የሚመሩትን የፖለቲካ ድርጅት ከሕዝብ ለመነጠል አጋጣሚውን መጠቀማቸው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ በዋነኛነት ለብአዴን አባላት በሚሠራጨው አብዮታዊ ዴሞክራሲ መጽሔት ላይ በሚያቀርቧቸው መጣጥፎች ቀደም ሲል ባልተለመደ ሁኔታ ጥልቅ ትንታኔ በመስጠት፣ ይህንኑም ትንታኔያቸውን በበርካታ ማጣቀሻዎች በማስደገፍ አሳማኝ ንድፈ ሐሳባዊ አቀራረብን ከዓለማችንና ከአገራችን ነባራዊ ሁኔታ ጋር ለማጣጣም በመሞከራቸውም ይታወቃሉ፡፡

አሁን ደግሞ ፖለቲካ ኢኮኖሚና የኢትዮጵያ ህዳሴ በሚል ዓብይ ርዕስ በዋነኛነት 405 ገጾችን የያዘ ዳጎስ ያለ መጽሐፍ በማዘጋጀት አሳትመው፣ ቀደም ባለው ሳምንት በባህር ዳር ከተማ ውስጥ ማስመረቃቸውን በመገናኛ ብዙኃን አማካይነት በሰማን ማግሥት፣ አዲስ አበባ ለምንገኝ ወገኖቻቸው ዕድሉ እንዲደርሰን ለማድረግ በማሰብ ይመስላል በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ በድጋሚ ለማስመረቅ ዝግጅት ማድረጋቸውን በመስማታችን የዝግጅቱ ታዳሚ እንደምንሆን አስቀድመን አረጋገጥን፡፡ ስለሆነም የዚህ መጣጥፍ ዋና ዓላማም በመጽሐፉ ምረቃ ወቅት የነበረው ሁኔታ ምን ይመስል እንደነበረ በአጭሩ መግለጽ ሲሆን፣ የመጀመሪያ ደረጃ ንባብን መሠረት በማድረግ በመጽሐፉ አቀራረብና ይዘት ላይም ያለኝን የተመጠነ ምልከታ በወፍ በረር ቅኝት ለተደራሲያን ማሳየት ይሆናል፡፡ መልካም ንባብ!!

የመጽሐፉ ምረቃ ሥነ ሥርዓት ድባብ በብሔራዊ ቴአትር  

መጋቢት 9 ቀን 2009 ዓ.ም. የአቶ ዓለምነው መኮንን መጽሐፍ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ እንደሚመረቅ አስቀድሞ ስለተነገረኝ እኔም በቅርብ የማውቃቸውን ሰዎች እንዲገኙ ጋብዤ በሰዓቱ በቦታው ተገኘን፡፡ በመሆኑም ድባቡ እጅግ ደስ የሚል ሁኔታን ያንፀባርቅ እንደ ነበር ቀዳሚ ምስክር ነኝ፡፡ በእውነትም የመጽሐፍ ምረቃ መሆኑን ገና የቴአትር ቤቱ አዳራሽ በር ሲገባ ግራና ቀኝ በሁለት ጠረጴዛዎች ላይ መጽሐፉ ተደርድሮ ታዳሚው እየተሻማ ሲገዛው መታየቱ የድጋሚ ምረቃውን ተፈላጊነት በእጅጉ ያሳብቅ ነበር፡፡ ነገር ግን አቶ ዓለምነው ብአዴን/ኢሕአዴግ በሚመራው መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ የሥልጣን እርከን ላይ ሆነው ሳለ ባለ አምስት ኮከብ የሆኑትን ሸራተን አዲስን ወይም ካፒታል ሆቴልን አሊያም ራዲሰን ብሉን ወይም ኢሊሊ ሆቴልን ለምን አልመረጡም? እያልሁ ጥያቄዎችን ለማንሳት ብገደድም ምክንያታቸው ምንም ይሁን ምን ለእኔ ይኼኛው ውሳኔያቸው በእጅጉ ተመችቶኝ እንደነበር ከመግለጽ ግን አልቆጠብም፡፡ ምክንያቱም በአንድ በኩል ብሔራዊ ቴአትር የጥበብና የጥበበኞች ቤት በመሆኑ የጥበብ ሥራ ውጤትን በዚህ ቤት ማስመረቅ በራሱ ደስ የሚል ስሜት ነበረው፡፡ በሌላ በኩል ሁሉንም ዜጋ በእኩል ዓይን አየተመለከተ ተቀብሎ ያለ ልዩ መጥሪያ ካርድና አድሎዋዊ መስተንግዶን ከሚያስከትለው ፕሮቶኮል ነፃ አድርጎ ለመታደም የመጣው ሰው በእኩልነት እንዲስተናገድ ዕድልን የሚሰጥ መሆኑ ሌላኛው መልካም ገጽታው ነው፡፡

ስለሆነም እጅጉን ተስማምቶኝ ስለነበር ተደስቼበታለሁ፡፡ በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንንና የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶ/ር ሒሩትን ጨምሮ በርካታ የፌዴራል የመንግሥት ባለሥልጣናት የተገኙ ቢሆንም፣ ነባሮቹ የብአዴን/ኢሕአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ግን እንዳልተገኙ ታዝቤያለሁ፡፡ ለምን ለሚለው ጥያቄ ለጊዜው መልስ ባለማግኘቴ በሒደት እውነታውን ከደረስኩበት አንድ ሁለት ልልበት እችል ይሆናል፡፡ ለዛሬው ግን ከዚህ በላይ የምለው የለኝም፡፡ ይህም ሆኖ አዳራሹን ከአፍ እስከ ገደፉ የሞላው ወጣትና የእኔ ዓይነት ተራው ሰው መሆኑ በእውነት ነው የምላችሁ በእጅጉ አስደስቶኛል፡፡

ምክንያቱም ርዕሰ ጉዳዩ ወቅታዊ ከመሆኑም በላይ አሁን ባለው የአገራችን የፖለቲካ ኢኮኖሚ ግንዛቤ ላይ ተመሥርቶ የዓለምን ፖለቲካ በሰፊውና በጥልቀት ለመቃኘት የተቻለበት መጽሐፍ ስለሆነ፣ በወጣቱ ትውልድ በአጠቃላይና በድርጅቱ ደጋፊ ወጣት ምሁራን ላይ በተለይ ሁለንተናዊ ግንዛቤን በማሳደግ ረገድ የሚኖረው ፋይዳ እጅግ የላቀ ስለሆነ፡፡ በተለይ ደግሞ እንደዚህ ያለ ዳጎስ ያለ መጽሐፍ አዘጋጅቶ ለማሳተም ቀርቶ ለማንበብ ጊዜ የለንም የሚሉ ፖለቲከኞችና ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በብዛት በሚገኙባት አገር፣ ከመደበኛ ሥራ ጎን ለጎን በርካታ መጻሕፍትን አንብቦ በንፅፅር ለመተንተን ፍላጎት ማሳየት ብቻ ሳይሆን የዕረፍት ጊዜ መስዋዕት ማድረግን፣ የአዕምሮ ዝግጁነትንና ቁርጠኝነትን የሚጠይቅ ኃላፊነት ውስጥ ገብቶ መገኘት በራሱ ትልቅ ነገር መሆኑ አሌ የሚባል ጉዳይ አይደለም፡፡

የጥረት ውጤትንም እንዲህ በተግባር ማሳየት መቻል በራሱ ብዙም ሥራ ሳይኖራቸው ሥራ ይበዛብናል ለሚሉና ምንም ሳያነቡ አዋቂ ለመምሰል ለሚሞክሩ የዘመኑ ባለሥልጣናትና ፖለቲካኞቻችን ጠቃሚ ትምህርት የሚሰጥ ይመስለኛል፡፡ እዚህ ላይ አንድ ነገር ብቻ ብዬ ማለፍ እፈልጋለሁ፡፡ አቶ ዓለምነው ውድ የሆነውን ጊዜያቸውንና በጥረታቸው የተጎናጸፉትን ሁለገብ የሆነውን ክህሎታቸውን፣ እንዲሁም በትምህርትና በጥልቅ ንባብ ያሳደጉትን ዕውቀታቸውን በመስጠት ብቻ ሳይወሰኑ የማንንም ባለሀብት ሆነ የልማት ድርጅት ድጋፍ ሳይጠብቁ፣ ይልቁንም ያላቸውን ጥሪት አሟጠው በመጠቀም መጽሐፉን ማሳተማቸውና ለሥርጭትም ማዘጋጀታቸው በእርግጥም አርዓያነት ያለው ተግባር ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡

የአቶ ደመቀ መኮንን አባባል ልዋስና “አንድያ ቤታቸውን በባንክ አስይዘው ባገኙት የብድር ገንዘብ መጽሐፉን አሳትመው ለተደራሲያን አቅርበዋልና”፡፡ ይህም ድርጊታቸው በስፖንሰር ማፈላለግ ሽፋን በመቶ ሺዎች ወይም በሚሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ከሚሰበስቡ የዘመኑ ባለሥልጣናትና ግለሰቦች የተለየ ዕርምጃ መውሰዳቸው በእርግጥም የሚያበረታታ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ መጽሐፉን ለማስመረቅ ከውድ ባለቤታቸው ሰብለወርቅ አባተ ጋር ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ የአውሮፕላን ቲኬታቸውን በራሳቸው ገንዘብ ቆርጠው አዲስ አበባ ላይ የሚቀበላቸው የጓደኛ ተሽከርካሪ ብቻ መጠቀም መቻላቸው ሲታከልበት፣ እውነትም አቶ ዓለምነው ከማንም ምንም ነገር ላለመነካካት ያደረጉት ጥረት አካል ነውና መጽሐፉን ለማስመረቅ ለምን የብሔራዊ ቴአትር አዳራሽን መረጡ ለሚለው ጥያቄዬ ምላሽ ማግኘት ችያለሁ፡፡ የእሳቸው የሥልጣን ደረጃ የሚገኝ ሰው ቀርቶ ከዚያ በታች ባለ የሥልጣን ደረጃ ላይ የሚገኝ ፖለቲከኛ ሥልጣኑን በመጠቀም የግል ጥቅሙን ሲያሳድድ በሚገኝበት ወቅት፣ ለመንግሥትና ለድርጀት ሥራ በእጅጉ ጠቃሚ የሆነ መጽሐፍን ለማሳተምም ሆነ ለማሠራጨት የግል ሀብትን መጠቀም ብዙም የተለመደ አይደለም፡፡

በእርግጥ አቶ ዓለምነው ቀደም ሲል ጀምሮ ሳውቃቸው ንፁህ ታጋይ፣ ቀና አስተሳሰብ ያላቸውና የተሟላ ስብዕናን የተላበሱ ሰው መሆናቸውን ጠንቅቄ ባውቅም አሁን በፈሙት ፍጹም ከሙስና የፀዳ ተግባር ይበልጥ እንዳከብራቸውና እንድኮራባቸውም አድርጎኛል፡፡ ስለሆነም የዚህ ዓይነቱን ቅን፣ ለአገሩ ተቆርቋሪና ያለውን ሁሉ አሟጦ ለመስጠት የሚተጋን ሰው በፖለቲካ አቋም መለያየት ቢኖርና የተለያየ አስተሳሰብ ብንይዝም እንኳ ማበረታታት የሚኖርብን ይመስለኛል፡፡

ይህንን ሐሳባችንን ተግባራዊ የምናደርገው ደግሞ መጽሐፉን ገዝተን በማንበብና ሐሳባቸውን በመጋራት ስለሆነ ሁላችንም ይህንን መልካም ተግባር ሳንውል ሳናድር ብንፈጽም አንድም የአቶ ዓለምነው ድካም ውጤታማ መሆኑን እናረጋግጣለን፡፡ ሁለትም ስለአገራችን ፖለቲካ ኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን ስለዓለም ወቅታዊ ሁኔታ በቂ የሆነ እውቀት በመሸመት አጠቃላይ ግንዛቤያችንን እናሳድጋለን፡፡ በመሆኑም መጽሐፉን አሁኑኑ አግኝተን ልናነበው ይገባል እላለሁ፡፡

በመጽሐፉ ላይ ያለኝ አጠቃላይ ምልከታ

መጽሐፉ በመጀመሪያው ምዕራፍ ንድፈ ሐሳባዊ ትንታኔን መሠረት ያደረገ ገለጻን በሰፊው ያቀረበ ሲሆን፣ ለቀጣዮቹ ምዕራፎች መንደርደሪያ የሚሆን ግብዓትን አካቶ ይዟል፡፡ በመቀጠልም ንድፈ ሐሳባዊ ትንታኔን ከተግባራዊ እንቅስቃሴ ጋር አዛምዶ ለማቅረብ የሞከረ፣ ለበርካታ ጥያቄዎች በቂ ሊባል የሚችል መልስ እየሰጠ የመጣ በተለይም በፖለቲካው ዓለም ውስጥ እስከ ከፍተኛ የሥልጣን እርከን ላይ ደርሰው ስለኒዮ ሊበራሊዝም ጽንሰ ሐሳብም ሆነ ስለሶሻል ዴሞክራሲ ልዩ ባህሪያት፣ ከዚያም አልፎ የዕለት ከዕለት ተግባራቸው መሠረት ስለሆነው አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመር ምንነት፣ በአጠቃላይም ስለሦስቱ የዴሞክራሲ ዓይነቶች አንድነትና ልዩነት እዚህ ግባ የሚባል እውቀት ሳይኖራቸው ከፍተኛ የሥልጣን እርከን ላይ ተቀምጠው ግፋ በለው ለሚሉት ብቻ ሳይሆን፣ የተወሰነ ግንዛቤ ይዘው ብዙ እንደሚያውቁ ለሚያስቡ የፖለቲካ አመራሮችና የመንግሥት ባለሥልጣናት የተግባር መመርያ ሆኖ ሊያገለግል የሚችል መሆኑ ጥርጥር የለውም፡፡

ይህም ሆኖ ይህን ጭምቅ ሐሳብ ከማጣቀሻዎቹ ጋር እያገናዘቡና ከተቻለም አለፍ እያሉ የሌሎች ምሁራን ሥራዎችንም መዳሰስን በጠየቀ ንባብ መደገፍ እንዳለበት ይታመናል፡፡ ለዚህም ዋነኛዎቹ የመጽሐፉ ተደራሲያን የሆኑት የኢሕአዴግ ፖለቲከኞችና ባለሥልጣኖቻቸው ራሳቸውን በቅጡ ማዘጋጀት የሚጠበቅባቸው ይመስለኛል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ራስን ከወቅቱ ዓለማዊና አገራዊ ሁኔታ በተለይም ነባራዊ ሀቅ ጋር እያጣጣሙ የአመራርና የመፈጸም አቅምን በቀጣይነት ማሳደግን ሥራዬ ብለው ሊይዙት እንደሚገባ ከአቶ ዓለምነው መጽሐፍ ትምህርት ሊቀስሙ ይገባል፡፡ አጠቃላይ ሁኔታውን በዚህ መልኩ አስቀምጨ ሳበቃ በመጽሐፉ አቀራረብ፣ የቋንቋ አጠቃቀምና ይዘት ላይ የተስዋሉትን ሁኔታዎች በአዎንታም ሆነ በአሉታ የተወሰኑ ነገሮችን በማንሳት የሚታዩትን ክፍተቶች ጭምር ለማሳየት ጥረት አደርጋለሁ፡፡

የመጽሐፉን አደረጃጀትና አቀራረብ በተመለከተ

እኔ እስከማውቀው ድረስ ክፍል የሚለው ርዕስ ምዕራፍ ከሚለው ርዕስ ሰፋ ያለ ሆኖ ሳለ፣ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ምዕራፍ የሚለው በሥሩ በርካታ ክፍሎችን እንዲይዝ መደረጉ ተገቢ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ይልቁንም መሆን የነበረበት የተገላቢጦሹ ነው፡፡ ምክንያቱም በክፍል ሥር በርካታ ምዕራፎች ሊኖሩ ይችሉ እንደሆነ እንጂ በምዕራፍ ሥር ከንዑስ ምዕራፎች ያለፈ በርካታ ክፍሎች ሊኖሩ አይችሉምና ነው፡፡ ሌላው እንደ አውሮፓ አቆጣጠር የሚለው በልዩ ሁኔታ መታየት ሲገባው በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ግን እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር የሚለው ነው በልዩነት የተቀመጠው፡፡ ምንም እንኳ አቶ ዓለምነው ይህን ማድረጋቸው በብዛት የውጭ መጽሐፍትን በዋቢነት ከመጠቀማቸው ጋር ተያይዞ ሊሆን እንደሚችል ቢገመትም፣ መጽሐፉ ኢትዮጵያዊ በሆነው የአማርኛ ቋንቋ ጥርት ብሎ እስከተጻፈ ድረስ የዚህ ዓይነቱ አቀራረብ የተለመደ አይደለምና በወቅቱ መታረም ነበረበት፡፡

በሌላ በኩል በተለምዶ በአንድ መጽሐፍ ውስጥ ሊካተቱ ከሚገባቸው ነገሮች ውስጥ ምሥጋናና መቅድም በቀዳሚነት ይገኙበታል፡፡ የምሥጋና መልዕክቶችን ለማስተላለፍ የሚሰጠው ገጽም ከሁሉም ቀድሞ መገኘት ሲገባው በመጽሐፉ መጨረሻ ላይ መወሸቁ ብዙም ያልተለመደ ብቻ ሳይሆን፣ ተገቢ ቦታ ሊሰጣቸው የሚገቡ ሰዎችንና ተቋማትን አዎንታዊ አስተዋጽኦ በሚገባ አንዳይታወቅ ሊያደርግ ይችላልና እንደዚያ ባይሆን ይመረጥ ነበር፡፡ ሌላው ከአቀራረብ ጋር ተያይዞ መታየት ያለበት የመቅድምና የመግቢያ አጻጻፍን የሚመለከተው ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ መቅድም ተብሎ የቀረበው የመጽሐፉ መግቢያ ተደርጎ ሊወሰድ የሚችል ካልሆነ በስተቀር መቅድም ሊያሰኘው የሚያስችል ይዘት አላገኘሁበትም፡፡

በእኔ እምነት መቅድም በዋነኛነት መጽሐፉን ለመጻፍ ያነሳሳውን ሁኔታ፣ በሒደቱ የተከሰቱ መልካምና ሰፊ አጋጣሚዎች፣ እንዲሁም የታለፉ ፈተናዎች በመጨረሻም የተደረሰበት ሁኔታና የወሰደውን ጊዜ በአጭሩ በማመልከት ተደራሲያን ለካ ይኼም ኖሯል እንዲሉ ለማድረግ የምንጠቀምበት ገጽ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ እንዲሁም ከዚሁ ጋር ተያይዞ መታየት የነበረበት ሌላው ጉዳይ ደግሞ የግርጌ ማስታወሻና የዋቢ ጽሑፎች ዝርዝር በአንድ ላይ መቅረቡ ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ ላይ ሁለቱም በአንድ ላይ ተዘርዝረው የቀረቡበት ሁኔታ ታይቷል፡፡ የዚህ ዓይነት አቀራረብ ብዙም የተለመደ አይደለም ብቻ ሳይሆን፣ ዋና ዋና የማጣቀሻ ጽሑፎችን በአግባቡ ለይተን እንዳንመለከት የሚያደርግ በመሆኑ ያን ታሳቢ ማድረግ ነበረበት፡፡

ይልቁንም የግርጌ ማስታወሻዎች በየገጹ ቢመለከቱና መጨረሻ ላይ ደግሞ የዋቢ መጽሐፍት ዝርዝር በፊደል ቅደም ተከተል ቢቀመጥ ኖሮ አንባቢ የተጠቀሰው ሐሳብ ከየትኛው መጽሐፍ ወይም ሰነድ ላይ እንደተወሰደ ለማረጋገጥም ሆነ ተጨማሪ ግንዛቤ ለማግኘት ቢፈልግ በቀላሉ ለማግኘት ያስችለው ስለነበር፣ ይኼኛው አማራጭ ይበልጥ የተሻለ እንደነበር ከወዲሁ መገመት አይከብድም፡፡ ሌላው በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ያገኘሁት ለየት ያለ ነገር ደግሞ የኢታሊክስ አጠቃቀም ነው፡፡ በጥቅስ ውስጥ የሚቀመጡ ሐሳቦች በኢታሊክስ መልክ እንዲቀመጡ የሚደረገው በደራሲው አማካይነት ከአንድ ቋንቋ ወደ ሌላ ቋንቋ የተተረጎሙ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ ሆኖም በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ሁሉም በጥቅስ ውስጥ የሰፈሩ ሐሳቦች በኢታሊክስ መልክ እንዲቀመጡ ከመደረጉም በላይ፣ ሁሉም በጥቅስ ውስጥ የገቡ ሐሳቦች ደምቀው እንዲታዩ ተደርጓል፡፡ ይህንንም አቀራረብ ደራሲው ተሳስቶ ቢጠቀምበት እንኳ በዋነኛነት የአርትኦት ሥራውን በኃላፊነት ያከናወኑት ሰዎች ሊያስተካክሉት በተገባ ነበር፡፡  

በመጽሐፉ ውስጥ የታየው የቋንቋ አጠቃቀም ሁኔታ

ከቋንቋ አጠቃቀም ጋር ተያይዞ አቶ ዓለምነው በሚገርም ሁኔታ የአማርኛ ቋንቋን በአግባቡ ሥራ ላይ ማዋላቸውን በልበ ሙሉነት መመስከር እችላለሁ፡፡ እሳቸውም በመቅድሙ ላይ አስቀድመው ለመግለጽ እንደሞከሩት አብዛኛው ሐሳብ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ከተጻፉ መጻሕፍትና መጣጥፎች እየተወሰደ የተተነተነ በመሆኑ፣ በመጽሐፉ ውስጥ በርካታ የእንግሊዝኛ ቃላትን አገኛለሁ ብዬ ጠብቄ ነበር፡፡ ሆኖም አቶ ዓለምነው የቻሉትን ያህል ጥረት በማድረጋቸው ከቋንቋ አጠቃቀም አንፃር የጎላ ስህተት ሳይፈጽሙ መቅረታቸውን ተመልክቻለሁ፡፡ እናም የዚህ ዓይነቱ ጥረት በእጅጉ ሊበረታታ ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡

ሆኖም ሥራቸው አሁንም ከጉድለት የፀዳ አለመሆኑን አንዳንድ ምሳሌዎችን በማንሳት ለማሳየት ልሞክር፡፡ በቀላሉ ወደ አማርኛ ተመልሰው ጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ ቃላት ወይም ሀረጋት በእንግሊዝኛ እንዳለ የተገለጹበት ሁኔታ ተሰተውሏልና ነው፡፡ ለምሳሌ ቶርቸር፣ ፌልድ ስቴትስ (ገጽ 9)፣ ኋይ ኔሽንስ ፌል (ገጽ 107)፣ ሲቪል ሰርቪስ በብዙ ገጾች ላይ፣ ካፒታል ከንዑስ ርዕሱ ጀምሮ፣ ማኑፋክቸሪንግ በተለዋጭነት እየገባ፣ ኦን ሶቭዮት ሶሻሊስት፣ ወዘተ የሚሉት ባሉበት ሁኔታ ነገር ግን በአማርኛ ፊደላት ተጽፈው መግባታቸው በአንድ በኩል ቀጥተኛ የሆነ የአማርኛ ትርጉም ለመስጠት በማያስቸግሩበት ሁኔታ ለምን ጥቅም ላይ ዋሉ ያሰኛል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ያው የተለመደው የእንግሊዝኛ ቃላትን በየአጋጣሚው የመጠቀም ልማድ አቶ ዓለምነውንም ሙሉ ለሙሉ ያለቀቃቸው መሆኑን ያመለክታል፡፡ ከቋንቋ አጠቃቀም ጋር ተያይዞ ሊነሳ የሚችለው ሌላው ጉዳይ የአማርኛ ቃላት ወይም ሀረጋት አጠቃቀማችን ላይ አልፎ አልፎ የሚስተዋል ግድፈት ወይም ጉድለት ነው፡፡ በዚህ ረገድ አቶ ዓለምነው በመጽሐፋቸው ላይ የተጠቀሙበትን አንድ ሀረግ ብቻ መዘን እንመልከት፡፡ ይኸውም “ድህነት አደር” የሚለው ሀረግ ነው፡፡

ይህ ሀረግ በተለምዶ አርሶ አደር፣ አርብቶ አደር፣ ላብ አደር፣ ወዘተ እንደሚባለው ተደርጎ የተወሰደ ይመስላል፡፡ ነገር ግን ከላይ የተጠቀሱት ሀረጋት የአንድን የኅብረተሰብ ክፍል የምጣኔ ሀብት መሠረት ወይም መተዳደሪያ አሊያም የሥራ መስክ ለመግለጽ የሚያገለግሉ ሲሆን፣ ድህነት አደር የሚለው ሀረግ እስካሁን ድረስ በምንጠቀምበት የአማርኛ ቋንቋችን ውስጥ ትርጉም የለሽ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በቀን ተቀን ግንኙነታችን ተጠቅመንበት የማናውቅና በአማርኛ ተናጋሪው ሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ሀረግም አይደለም፡፡

ስለሆነም እንደዚህ ዓይነት ለአብዛኛው ተደራሲ ብዙም ትርጉም የማይሰጡ ሀረጋትን ወይም ቃላትን ከመጠቀም ይልቅ የተለመዱና ስሜት ሊሰጡ የሚችሉ ሀረጋትን ብንጠቀም የተሻለ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ በሌላ አነጋገር ለየት ያለ አቀራረብ የተጠቀምን መስሎን የምናስገባቸው ቃላት በአንድ በኩል ትርጉም የለሽ የሚሆኑበት አጋጣሚ ይፈጠራል፡፡ በሌላ በኩል የተደራሲያንን ንባብ ያደናቅፋልና አስቀድሞ ማረሙ ሳይሻል አይቀርም፡፡

የመጽሐፉ ይዘት

ይህ መጽሐፍ በአብዛኛው ሁሉን አቀፍና በርካታ ጉዳዮችን የዳሰሰ በመሆኑ በአንድ መጽሐፍ ውስጥ የበርካታ ዘርፎችን ልምድ፣ ክህሎትና እውቀት ለማግኘት ዕድል ይሰጣል የሚል እምነት አለኝ፣ ሆኖም በርካታ ጽንሰ ሐሳቦችን በአንድ መጽሐፍ ውስጥ አጭቆ ለማቅረብ ከመሞከሩ ጋር ተያይዞ በአንድ በኩል የሐሳቦች መደጋገምን ሲጋብዝ በሌላ በኩል አንዳንድ መሠረታዊ ሐሳቦች በአጭሩ ተገልጸው እንዲያልፉ አድርጓቸዋል ማለት ይቻላል፡፡ በዚህ ረገድ ከደከሙ አይቀር ሰፋ ብለው ቢዳሰሱና በአዲስ መልክም ቢካተቱ ያልኳቸው የተወሰኑ ሐሳቦች እንዳሉ አምናለሁ፡፡ ቀጥሎ በሚገኙት አንቀጾች በምሳሌ እያስደገፍሁ ለማሳየት ልሞክር፡፡

የዓለም ባንክ፣ የዓለም የገንዘብ ተቋምና የዓለም የንግድ ድርጅት አሉታዊ ተፅዕኖ ጠቅለል ባለ መልኩ የተገለጸ ቢሆንም፣ በአፍሪካ አገሮች ላይ በአጠቃላይና በኢትዮጵያ ላይ ደግሞ በተለይ የነበረው አሉታዊ ተፅዕኖ ምን ይመስል እንደነበር በምሳሌ ተደግፎ ቢገለጽ የተሟላ ሥዕል ይሰጥ እንደ ነበር መገመት ይቻላል፡፡ ሌላው ቀደም ሲል የነበረው የኦሮሞ የገዳ ሥርዓት በተወሰነ መልኩ የተጠቀሰ ቢሆንም፣ አሁን ባለው ፌዴራላዊ አደረጃጀት የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ብቻ ሳይሆን የፌዴራል መንግሥት አተያይ ምን እንደሚመስል እንደ መነሻ አለመውሰዱስ ተገቢ ነው ወይስ አይደለም በሚለው ሐሳብ ላይ የተወሰነ ነገር ቢባል ጥሩ ነበር፡፡

ከገጽ 107 አጋማሽ እስከ 112 አጋማሽ ድረስ ባሉት ገጾች ላይ ደግሞ ስለኢትዮጵያ ሕዝቦች የትግል ሒደት የተቀመጠው ሐሳብ አጭር ከመሆኑ የተነሳ፣ በተወሰኑ ገጾች ብቻ ቀንብቦ ማስቀመጥ ከአገራችን ተሞክሮ ጋር በማያያዝ ብዙ ትምህርት እንዳይገኝበት ያደረገ ይመስለኛል፡፡ ከዚህም ባሻገር በአገር ውስጥ ምሁራን ሥራዎች ላይ ተመሥርቶ ትንሽ ቢዳብር መልካም ነበር፡፡ በዚህ ረገድ የፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴንና የዶ/ር አሰፋ ፍሰሐ ሥራዎችን በስፋት መጠቀም ይቻል ነበር፡፡ በዚህ ረገድ የአቶ ዓለምነው መጽሐፍ ከመንግሥት ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ከኢሕአዴግ ጽሑፎች ውጭ የሚገኙ የአገር ውስጥ ምሁራን ሥራዎችን ወደ ጎን የተወ ይመስላል፡፡ ምናልባትም የዶ/ር ምሕረት ደበበን መጽሐፍ አንድ ጊዜ እንዲሁም አቶ ዓለሙ አበበ የተረጎሙትን መጽሐፍ ሁለት ጊዜ ጠቅሰው ካልሆነ በስተቀር፣ የአገራችን የታሪክና የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን እንዲሁም የምጣኔ ሀብት ሙያተኞች ሥራዎች አለመዳሰሳቸው ለራሳችን የምንሰጠውን ትኩረት አናሳነት በግልጽ ያመለክታል፡፡

በዚህ አጋጣሚ አንድ ምሳሌ ልጨምርና የችግራችንን ስፋት ለማሳየት ልሞክር፡፡ የደቡብ ኮሪያ መሪዎች ችንግዶ የምትባል መንደር ነዋሪዎችን እንቅስቃሴ ከተመለከቱ በኋላ በተሞክሮነት ቀምረው ለሌሎች አካባቢዎች ማስተላለፋቸውን በምሳሌነት አንስተው ሰፊ ትንታኔ አቅርበዋል፡፡ የሚገርመው ነገር አቶ ዓለምነው ሩቅ ምሥራቅ እስያ ድረስ ርቀው ሳይጓዙ እሳቸው በሚያስተዳድሩት ክልል ውስጥ እሳቸው ከሚኖሩበት 77 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኙት አውራምባዎች፣ ከዚህች መንደር በተሻለ ደረጃ ሊቀመርላቸው የሚችል መልካም ተሞክሮ እንዳላቸው ጠጋ ብለው በመመልከት በጥሞና ቢመረምሩት ኖሮ ምንኛ ጠቃሚ ትምህርት ባገኙ ነበር፡፡        

ኪራይ ሰብሳቢ የሚለው ቃልና ሀረግ በመጽሐፉ ውስጥ እዚህም እዚያም ተደጋግሞ ተጠቅሷል፡፡ ሆኖም ትርጉሙ ምን እንደሆነ፣ ታሪካዊ አመጣጡና አሁን ያለበት ደረጃ ግምት ውስጥ ገብቶ በሚገባ ቢተነተን እግረ መንገዱን በዚህ ቃል ወይም ሀረግ ላይ በበርካታ ሰዎች ዘንድ የተፈጠረውን ብዥታ መግፈፍ ይቻል ነበር፡፡ በእኔ እምነት ይኼ ሀረግ ለመባል የተፈለገውን ሐሳብ በትክክል የሚያስተላልፍ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ ሌላው በምዕራፍ ሁለት ክፍል ሁለት በተለይም 2.3 ወይም ከገጽ 127 እስከ 129 አጋማሽ ድረስ ያለው ሐሳብ ቀደም ብለው ባሉት ገጾች በሚገባ የተገለጸ ስለሆነ፣ እንዲሁም ክፍል ስድስት ማለትም ከገጽ 373 እስከ 377 የተቀመጡት ሐሳቦች ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ የተደገሙ በመሆናቸው በዚያ መልክ በድጋሚ መካተታቸው አስፈላጊ አልነበረም፡፡

ሌላው ከመጽሐፉ ገጽ 147 እስከ 149 በተለይም በ5.3 እና በ5.4 ሥር የሚገኙት ንዑሳን ርዕሶች ቢቀያየሩ ይበልጥ ስሜት ይሰጡ እንደነበር በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል፡፡ ምክንያቱም በመርህ ደረጃ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት የመጨረሻ አማራጭ ሆኖ መታየት ስላለበት፡፡ አንዲሁም በ5.4 ላይ የተቀመጡት ሁለት ትልልቅ ሐሳቦች ከሁለት ተከፍለው በሚገባ መተንተን ነበረባቸው፡፡ ይኸውም በአንድ በኩል የሁለቱም ጽንሰ ሐሳቦች መነሻና መድረሻ የተለያየ ከመሆኑ አንፃር ራሳቸውን ችለው ቢዳሰሱ መልካም ይሆን ነበር፡፡ በሌላ በኩል ለኅብረት ሥራ ማኅበራት ሰፊ ሽፋን ሰጥቶ ስለአክሲዮን ማኅበራት ምንም ያልተባለበት ሁኔታም ስለተፈጠረ ቀላል የማይባል ክፍተት እንዲኖር አድርጓል፡፡

ልብ ብሎ ለሚመለከት ሰው በአገራችንም ሆነ በተቀረው ዓለም የአክሲዮን ማኅበራት ሚና እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገራችን እየታየ ያለውን የኢንቨስትመንት ሁኔታ ስንመለከት የአክሲዮን ማኅበራት ድርሻ እጅግ ጉልህ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በዚህ ረገድ በዋነኛነት የአክሲዮን ማኅበራት በስፋት የተሳተፉባቸውን የባንክ፣ የኢንሹራንስና በሪል ስቴት ልማት ዘርፍ ተሰማርተው የሚገኙ ኩባንያዎችን ወቅታዊ እንቅስቃሴ ብንመለከት የድርሻቸውን ጉልህነት መገንዘብ እንችላለን፡፡ ስለሆነም የአክሲዮን ማኅበራት ሚና በሚገባ ቢተነተን መልካም ነበር፡፡

ቅድመ 1983 ኢትዮጵያ ላይ በተወሰነ መልኩም ቢሆን ዘርዘር ያለ ሐሳብ መቅረብ ነበረበት እላለሁ፡፡ ስለሌሎች አገሮች ቅድመ ታሪክ ሰፊ ሽፋን እየሰጡ መጥተው የራስን ማሳነስ ለራስ ሲቆርሱ የሚለውን አባባል የሚቃረን ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ በተለይም በንጉሡ የመጨረሻ የሥልጣን ዘመን በውጭም ይሁን በአገር ውስጥ ባለሀብቶች ተጀምረው የነበሩት ዘመናዊ እርሻና የኢንዱስትሪዎች ማቆጥቀጥ፣ በደርግ ጊዜ በእጅጉ ተስፋፍቶ የነበረው የመንግሥት እርሻና የኅብረት ሥራ ማኅበራት እንቅስቃሴ በአዎንታም ሆነ በአሉታ ብዙ ሊባልለትና ጠቃሚ የሆነ ትምህርትም ሊወሰድበት የሚገባ ጉዳይ እንደነበር በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡

በዚህ ረገድ ጠቃሚ ልምድም ሆነ ትምህርት ከውጭ ብቻ ይገኝ ይመስል የራስን ወደ ጎን በመተው የውጭዎች ላይ መመሥረት “የራስን ጥሎ የሰው አንጠልጥሎ” ሊያሰኝ ይችላልና በአግባቡ ቢታሰብበት መልካም ሳይሆን አይቀርም፡፡ ሌላው በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ስለዴሞክራሲ ጽንሰ ሐሳብም ሆነ አስፈላጊነት ላይ ብዙ ተብሏል፡፡ ሆኖም በኢሕአዴግ የሚመራው የአገራችን መንግሥት ባለፉት 26 ዓመታት ከዴሞክራሲ ጽንሰ ሐሳብ አተገባበር ጋር ተያይዞ ያለበት ሁኔታ በምሳሌ ተደግፎ፣ እንዲሁም እየገጠሙት የሚገኙት ተግዳሮቶች በምሳሌ ተደግፈው ቢገለጹ መልካም ትምህርት ይገኝበት ነበር የሚል እምነት አለኝ፡፡

ሌላው ስለዴሞክራሲ ሲወሳ የምርጫ አፈጻጸምና የምርጫ ዓይነቶችን መርጦ ጥቅም ላይ የማዋሉ ጉዳይ ጎልቶ መነሳቱ አይቀርም፡፡ በዚህ ረገድ በመጽሐፉ ሰፋ ያለ ማብራሪያ ቀርቧል፡፡ ሆኖም በአንድ በኩል በአገራችን እስካሁን ድረስ ከተካሄዱት ምርጫዎች ምን ትምህርት አገኘን በሚለውና የተለያዩ የምርጫ ማስፈጸሚያ ሥልቶችን መርጦ ሥራ ላይ በማዋል ረገድ የታየው ክፍተት ከመብቶች ትግበራ ሒደት አኳያ የሚኖራቸውን አሉታዊ ወይም አዎንታዊ ተፅዕኖ መዳሰሱ ትርጉም የነበረው ይመስለኛል፡፡ ሆኖም መጽሐፉ ይህን ሁኔታ በለሆሳስ የዘለለው ይመስላል፡፡ በተረፈ በመጽሐፉ ውስጥ የተደጋገሙ ሐሳቦች ያሉ ቢመስልምና አንዳንድ ጠቃሚ ጉዳዮች ሳይዳሰሱ የቀሩ ቢሆንም፣ ንድፈ ሐሳባዊ ትንታኔ ከተግባራዊ እንቀስቃሴ ጋር ተገናዝቦ የቀረበበት ስለሆነ ጠቃሚ ትምህርት እንደሚገኝበት ይታመናል፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርና የሰብዓዊ መብቶች የዶክትሬት ዕጩ፣ እንዲሁም የሕግ አማካሪ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካካት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው sisaymengiste@gmail.com  ማግኘት ይቻላል፡፡  

   

Standard (Image)

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁና ውጤቱ እንዴት ይገምገም?

$
0
0

 

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ካጋጠመን ሽንፈት ወደ ሌላ ጥልቅ ሽንፈት እንዳንጓዝ ተብሎ የታወጀ ነው፡፡ ሆኖም እንደ አገር ሲታይ የሽንፈት መንገድ መሆኑ አልቀረም፡፡

መንግሥት የሕዝቦችን መሠረታዊና ተገቢ ጥያቄዎችን መመለስ አቅቶት ሲንገዳገድና በኢዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እንቅስቃሴውን ለማፈን ሲሞክር፣ ሕዝቦች መብቶቻቸውን ለማረጋገጥ በሰላማዊ መንገድ ከፍተኛ ትግል ሲያደርጉ በፅንፈኞች ተጠልፎ አገር ወደማያባራ ሁከት እንዳታመራ ለመግታት የታወጀ ነው፡፡ እንደ አገር በሰላማዊና በሠለጠነ መንገድ የሕዝቦችን ጥያቄዎች መፍታት አቅቶን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ውስጥ እንገኛለን፡፡ ለዚህ ነው ሽንፈት የሚሆነው፡፡

በተዘበራረቀ መንገድ ቢሆንም መንግሥት የሕዝቦችን ጥያቄዎች ተገቢነት አምኖ ውስጡ መሠረታዊ ችግሮች ተከስተዋል ብሎ ራሱን ለማደስ ያውም በጥልቅ ለመታደስ ወስኖ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ በመሆኑም የአዋጁ ጊዜ ገዥው ፓርቲ/መንግሥት ‹‹በጥልቅ እታደሳለሁ›› ብሎ፣ በከፍተኛ ደረጃ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች በሚነካ መንገድ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ አዋጁን ከ‹ጥልቅ ተሃድሶ› እንቅስቃሴ ለይቶ ለመገምገም አይቻልም፡፡ በ2008 ዓ.ም. የነበረውን ሁከት ለመግታት ሲታወጅ መሠረታዊ መነሻው ፖለቲካ መሆኑ ታምኖበት ነው ወደ ፖለቲካ ተሃድሶ የተገባው፡፡

በተደጋጋሚ እንደተገለጸው ኢትዮጵያ አገራችን በሽግግር ወቅት ላይ ትገኛለች፡፡ ከአምባገነናዊ አገዛዝና ጥልቅ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ኋላቀር አስተሳሰብና ባህል ወደ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር፣ ወደ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብና ግንኙነት፣ ከተበታተነ ኢኮኖሚ (Subsistent Economy) ወደ ዘመናዊ ሉላዊ ካፒታሊስት ኢኮኖሚ፣ ከኋላቀር የደኅንነት አስተዳደር፣ ወደ ሕዝቦችን ማዕከል ያደረገ ዘመናዊ የቁጥጥር፣ የደኅንነት፣ ወዘተ ሽግግር ላይ ትገኛለች፡፡

አገራችን ከብዙ ምዕተ ዓመታት እንቅልፍ በኋላ በመጨረሻው በ19ኛው ክፍለ ዘመን አሁን ያላትን ቅርፅ ይዛ ዘመናዊውን የአገር ግንባታ ሒደት (State Building Process) ነው የተያያዘችው፡፡ የአውሮፓ አገሮችን ሒደት ዋቢ አድርጎ ቻርለስ ቺሊ ‹‹ጦርነት አገሮችን ይገነባል›› (War Makes States) እንዳለው በተለያዩ የውስጥና የውጭ ጦርነቶች አልፋ፣ ነፃነትዋን ጠብቃ፣ በአንፀባራቂ ድሎች ታጅባ፣ ነገር ግን ሕዝቦችዋ የጦርነት በተለይም የእርስ በርስ ጦርነት ሰለባ ሆነው በሒደት ላይ ትገኛለች፡፡ ከገቡበት የድህነት አረንቋ ለመውጣት በሒደት ላይ ይገኛሉ፡፡

የግለሰብና የቡድን በተለይም ‹የራስን ዕድል በራስ መወሰን› (Self Determination) የሚገለጽ፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሕዝቦቻችን ጥያቄዎች ሆነውና ዓለም አቀፋዊ ቅቡልነት (Norm) ባገኙበት ሁኔታ፣ ወታደራዊው መንግሥት እነዚህን መብቶች ባለመቀበልና በመርገጥ አገራችንን ለከፋ የእርስ በእርስ ጦርነት ዳርጓታል፡፡

የኢትዮጵያ ሕዝቦች በዋናነት በኢሕአዴግ እንዲሁም በሌሎች ድርጅቶች መሪነት አምባገነናዊ ሥርዓቱን አሸንፈውና አዲስና የተሟላ ሕገ መንግሥት አፀድቀው፣ የአገር ግንባታ ሒደቱን እንደ አዲስ ‹‹አንድነት በብዝኃነት›› (Unity in Diversity) በአዲስና በጎለበተ ኢትዮጵያዊነት መንፈስ ተያይዘነዋል፡፡

እንደ ማንኛውም የአገር ግንባታ ሒደት (ሁልጊዜ ከነበረው ወደ አዲስ መገስገስ ስለሆነ) የአዲስ ሥርዓት ግንባታ ጉዞ አልጋ በአልጋ አይደለም፣ ሊሆንም አይችልም፡፡ ውጣ ውረድ/መንገራገጭ (Uphevals) የሚታይበት መሆኑ የግድ ነው፡፡ ጠንካራና ሕዝባዊ መንግሥት በሚኖርበት አኳኋን ሁለት ዕርምጃ ወደፊት አንድ ዕርምጃ ወደኋላ መሆኑ አይቀርም፡፡ ይህ በሁሉም አገር የተከሰተ ሒደት ነው፡፡ ቀጥተኛ (Smooth) የሚባል የአገር ግንባታ ሒደት ሊኖር አይችልም፡፡ በሌላ አገላለጽ በኅብረተሰቡ ውስጥ ያለ ኋላቀርነት በመሪዎችም ዘንድ በተለያየ ደረጃ ስለሚንፀባረቅና በሽግግር ባሉ አገሮች ጠንካራ ተቋማት ባለመኖራቸው ምክንያት፣ ወደፊት በሚደረገው ጉዞ መንሸራተት (ሽንፈት ሊያጋጥም ይችላል) ሕዝቦችና ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ማድረግ በሚችሉት የተሟላ ግስጋሴ፣ ጥልቀትና የተራዘመ እንዲሆንና መንሸራተቱ እንዲያጥርና ጥልቀት እንዳይኖረው መከላከል ነው፡፡

የግስጋሴው ጥልቀት ስንል ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር እንዲያብብ፣ በኅብረተሰቡ ውስጥ በጎ አስተሳሰብ እንዲጎለብትና ኋላቀርነትን በቀጣይነት ለመታገል፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀጣይና ፈጣን ዕድገት ለማስመዝገብ፣ ድህነትን ታሪክ ለማድረግ ጉዞውን የማቀላጠፍና በሕዝቦች መካከል መተማመንን ብሎም ሰላምን የማረጋገጥ ሒደት ተቋማዊ እየሆነ ሲመጣ ነው፡፡

መንሸራተት (ሽንፈት) ስንል በተቀራኒው ፀረ ዴሞክራሲ አስተሳሰብና ተግባር መጎልበት፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች (Crisis) በከፍተኛ ደረጃ ሲከሰት፣ በሕዝቦች መካከል መጠራጠር ሲሰፋ፣ የተገኘው ሰላም ሲናድና ተቋማት ልፍስፍስ ሲሆኑ ነው፡፡

ቅድመና ድኅረ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የአገራችንን ሁኔታ መንሸራተት (ሽንፈት) ያሳያል፡፡ የሕዝቦች ጥንካሬ ብሎም የአገሪቱና የመሪዎች ማንነት የሚታየው ግን በመንሸራተት ሆነ፡፡ ለቀጣይ ግስጋሴ የሚረዳው ያሉትን ዘሮች (Seeds) በማድነቅ፣ በማጎልበትና በፍጥነት ወደ ቀጣዩ ግስጋሴ መጓዝ መቻላችን ነው፡፡

በትግላችን ያገኘነውን ሕገ መንግሥት፣ በኅብረተሰቡ ውስጥ ያሉት በጎ እሴቶችና ልፍስፍስ እያሉ ያሉትን ተቋማት እያስተካከልን በቀጣይነት መገስገስ ይኖርብናል፡፡

ይህ እንዲሆን በቀበሌ፣ በወረዳ ብሎም በክልልና በፌዴራል ደረጃ፣ እንዲሁም በሲቪልና በፖለቲካዊ ተቋማት አዋጁ ሽንፈት መሆኑን ተቀብለን ከዚያ በኋላ ያሉት እንቅስቃሴዎች ቀስ በቀስ ወደ እውነተኛ ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት በአጠቃላይ ወደ ድል የሚያመሩ መሆኑን መገምገም ይኖርብናል፡፡

  1. ከነበረው አንፃራዊ ሰላም መደፍረስ ማገምገም ችለናል ወይ?
  2. የተወሰዱት ዕርምጃዎች በሕግና በሕግ ብቻ የተወሰዱ ናቸው ወይ? የታሰሩት ሰዎች ሰብዓዊ መብታቸውን በሚያረጋግጥ መንገድና ለመብታቸው በሰላማዊ መንገድ የበለጠ እንዲታገሉ በሚያበረታታ አካሄድ ነው ወይ?
  3. በሕዝቦች መካከል እየተከሰተ የመጣውን የመጠራጠር ሁኔታ በተወሰነ ደረጃ ለመግታት ተችሏል ወይ?
  4. በኅብረተሰቡና በተቋማት የተደረጉት ግምገማዎች በኅብረተሰቡ ጠያቂነት የተቋማት ግዴታዎችን መወጣት በሚያበረታታ መንገድ ነው የተካሄደው? ወይስ ከእንግዲህ እንዳይደገም መቀጣጫ ነው የሆነው? የሲቪልና የሙያ ማኅበራት ሕገ መንግሥታዊ ነፃነታቸውን እያረጋገጡ ግዴታቸውን በሚወጡበት መንገድ ነው ወይ የተካሄደው?
  5. ሁከቱ የተፈጠረው በአንድ በኩል ጠያቂ ኅብረተሰብ እየጎለበተ በመምጣቱ፣ በሌላ በኩል የልሂቃን ፖለቲካ በመዝቀጡ (Stagnation) እና የፖለቲካ ፓርቲዎች (ገዥው ፓርቲ ጭምር) ሕዝቦችን በብቃት መምራት አቅቷቸው የተፈጠረ መንሸራተት ነው፡፡

     ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተፈጠረውን የሕዝብ መነሳሳት ለምን በሰላማዊ መንገድ ሊጠቀሙበት አልቻሉም? የጠራ ፕሮግራም፣ ፖሊሲ፣ ስትራቴጂና ሥልት እንደሚጎድላቸው አውቀው ለማረም እየተንቀሳቀሱ ነው ወይ? ድርጅታዊ ነፃነታቸውን ከገዥው ፓርቲም ሆነ ከዳያስፖራ ፅንፈኞች ተፅዕኖ ለማላቀቅ እየሠሩ ነው ወይ? ገዥው ፓርቲ ሕገ መንግሥቱን ለማስከበርና ዴሞክራሲያዊ ከባቢ ለማጎልበት እስከምን ድረስ ቁርጠኛ ነው? ገዢው ፓርቲ ከመንግሥት ጋር ያጣበቀውን ለማቋረጥና አገር (State) መንግሥት፣ (Government) እና ገዢው ፓርቲ (Ruling Party) ያላቸውን ተነፃፃሪ ነፃነት ለማስጠበቅ በቁርጠኛነት እየተንቀሳቀሰ ነው ወይ? ውስጣዊ እድፎችን ለመቅረፍ ተዘጋጅቷል ወይ? ወይስ እንደነበረው ሊሸመግል ነው፡፡

በአጠቃላይ የአገራችን ሕዝቦችና ተቋሞቻችን ስንገመግም በስድስት ወር ጊዜ ወይም በአንድ ዓመት መሠረታዊ ለውጥ ይመጣል ለማለት አስቸጋሪ በመሆኑ የምንገመግመው መሠረታዊ ዕድገት የሚሆኑትን ምልክቶች እያመላከተ ነው ወይ በሚል መስፈርት ነው፡፡

ከአዘጋጁ፡ጸሐፊው የቀድሞ የኢሕአዴግ ታጋይና የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ የነበሩ ሲሆን፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

 

Standard (Image)

ኢኮኖሚያዊ አብዮቱና ሕዝባዊ ተጠቃሚነት

$
0
0

 

በአገራችን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ዓውድ ውስጥ በአሁኑ ወቅት ገኖ እየተነሳ የሚገኘው ሐሳብ የኢኮኖሚ ወይም የኢንዱስትሪ አብዮት የሚል ነው፡፡ በኦሮሚያና በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥታት በቅርቡ በተለያዩ ፕሮጀክቶች ሥራ ላይ እንዲውል እየተደረገ ያለውን ዕቅድ በተመለከተ የሚቀርቡ የተለያዩ ሐሳቦች ናቸው፡፡ የሐሳቦቹ ይዘት ሲታይ በሁለቱም ጽንፍ ማለትም የማያስፈልግና እስካሁን የተገኘውን ውጤት የሚያበላሽ ነው ከሚለውና ከዚህ አካሄድ ውጪ ለውጥ ማምጣት አይቻልም እስከሚለው ድረስ የሚደርስ ሲሆን፣ በመሀሉ ምክንያታዊ የሆኑ የክርክር ሐሳቦችን የሚያቀርቡ ግለሰቦች አሉ፡፡ በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ሪፖርተር ጋዜጣን ጨምሮ በተለያዩ የኅትመት ሚዲያዎች የቀረቡትን ሐሳቦች መነሻ በማድረግ በእርግጥም በክልሎቹ የተወሰዱ ወይም ሊወሰዱ የታሰቡ ዕርምጃዎች ፌዴራላዊ መንግሥት ከሚከተላቸው የተለያዩ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ዕቅዶች ጋር ይጋጫል ወይ? የግሉ ባለሀብትን ሊያቀጭጭ ወይም ፍትሐዊ የንግድ ውድድር እንዳይኖር ሊያደርግ ይችላል ወይ? ለእነዚህ ዕርምጃዎች መውሰድ መሠረታዊ ምክንያት የሆኑ ጉዳዮች ጊዜያዊ ግልባዊ ምክንያቶች ናቸው? ወይስ ከዚህ በላይ ሊታይ የሚገባው ነገር አለ? ውሳኔዎቹ ጽንሰ ሐሳባዊ መሠረትስ አላቸው ወይ? በክልሎቹ አካሄድ ተጠቃሚ ወይም ተጎጂ የሚሆነው ማን ነው? የሚሉት ነጥቦች ላይ ምልከታዬን ለማቅረብ ነው፡፡

ኢኮኖሚያዊ አብዮት ለምንና ለማን?

መንግሥታት ቃላትን ሲጠቀሙ ከሕዝብ ጋር ግንኙነት የሚያደርጉባቸው መሣሪያዎች በመሆናቸው ምክንያት የአፍ ወለምታ በሚያስብል ደረጃ ዝም ተብለው የሚወረወሩ አይደሉም፡፡ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የኢኮኖሚ አብዮት መሠረታዊ መርህ ብሎ ያስቀመጠው የክልሉ ነዋሪዎች ውኃ ዳር ቆመው ውኃ ሊጠሙ አይገባም የሚል ሲሆን፣ በተለይም በክልሉ ውስጥ ብዙ ተፈጥሮአዊ ሀብቶች ያሉ ቢሆንም፣ እነዚህን ሀብቶች የክልሉ ሕዝብ በመጠቀሙ ኑሮውን መግፋት አቅቶት በድህነት ውስጥ የሚኖር በመሆኑ ይህ ሁኔታ መቀየር አለበት የሚል ነው፡፡ ስለሆነም ሐሳቡ ከመሠረታዊነቱ አግላይ ሳይሆን፣ ይልቁንም የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንዲቻል ነው፡፡ ኢኮኖሚያዊ አብዮት ማካሄድ አለብን ሲባል ማኅበረሰቡ በሀብቱ መጠቀም እንዳይችል ያደረጉ መሠረታዊ መዋቅራዊ ምክንያቶችን በመለየትና እነዚህን ከሥራቸው መንግሎ በመጣል፣ የሕዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ የሚችሉ ሥራዎችን ማከናወን ነው፡፡ ስለሆነም የሐሳቡ አልፋና ኦሜጋ ድህነት መገለጫና መርህ የሆነበትን ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት፣ ብልፅግናና ተጠቃሚነትን መሠረታዊ መገለጫና መርህ ባደረገ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ማንበር ነው፡፡

የክልል መንግሥታት የኢኮኖሚ አብዮት በሚል በማለት ዘርፊ ሲታዩ የነበሩ ችግሮችን ለመፍታት እንዲያስችል የወሰዱዋቸው ውሳኔዎች ጥልቅ ኢኮኖሚያዊና ጽንሰ ሐሳባዊ ምክንያቶች ያላቸው ናቸው፡፡ ዌበር (Weber) የሚባለው ፈላስፋ በመንግሥትና በማኅበረሰብ ወይም በግሉ ዘርፍ መካከል ሊኖር የሚገባው ግንኙነት፣ መንግሥት ራሱን ነፃ አድርጎ ለግሉ ዘርፍ ጥሩና ተገማች ሁኔታዎችን የማመቻቸት ኃላፊነት መወጣት አለበት የሚለው ሐሳብ ለብዙ ዘመናት ተቀባይነት ያለው ነው ይላል፡፡ መንግሥት ይህን የሚያደርግበት ምክንያት ከግሉ ዘርፍ ተፅዕኖ ነፃ የመሆኑ አቅሙ፣ የግሉ ዘርፍ በበቂ ደረጃ ሥጋቶችን አሸንፎ መሥራት ላይ እጥረቶች በመኖራቸው የዚህ ሐሳብ ቅቡልነት እንዲቀንስ አስገድዶታል፡፡ ከዚህ በኋላ በተለይም የልማታዊ መንግሥታት ንድፈ ሐሳቦችን ትርጉም ባለው መንገድ በመቅረፅ የሚታወቁት የኢንስቲትዩሽና ኢኮኖሚክስ ምሁራን የሆኑት ግሬሽንክሮን (Gerschenkron) እና ሔርሽማን (Hirschman) መንግሥት ከማኅበረሰቡ ወይም ከግሉ ዘርፍ ጋር ሊኖራቸው ስለሚገባቸው ግንኙነቶች በተመለከተ ገዥ የሆኑ ሐሳቦችን አቅርበዋል፡፡ የግሉ ዘርፍ በተለያዩ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች በተለይም በማኑፋክቸሪነግ ዘርፍ ላይ ለመሰማራት በተለያየ መንገድ ሥጋት የሚያጋጥማቸው በመሆኑ በዚህ ዘርፍ ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ይቸገራሉ፡፡ ስለሆነም መንግሥት የግሉ ባለሀብት ያለውን ገንዘብ እንዲያሰባሰብና የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች አቅም ክፍተት በመሙላትና የሚቸግራቸውን በጋራ በመቅረፍ የኢንቨስተመንት እንቅስቃሴዎች ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ፡፡ ስለሆነም መንግሥት የኢንቨስትመንትና የኢንተርፕሩነርሺፕ አዋላጅነት (Surrogate Entrepreneurship) ሥራውን ያከናውናል ማለት ነው፡፡

በሌላ በኩል ኢንቨስትመንት ማካሄድ አትራፊ መሆኑን የግሉ ዘርፍ አመኔታ ቢኖረውም፣ ይህን አመኔታ ወደ ተግባር በመቀየር በኢንቨስትመንት መሳተፍ ላይ ያለውን ልዩነት ለማጥበብ እንዲቻል መንግሥት የሚያስተላልፈው ውሳኔ ‹‹Maximizing Induced Decision-Making›› እጅግ አስፈላጊ ይሆናል፡፡ የክልል መንግሥታት ትልልቅ ፕሮጅከቶችን በመቅረፅ አክሲዮን ማኅበራት እንዲቋቋሙ ሲፈልጉና መነሻ ምክንያታቸውን ሲያስቀምጡ በባለሀብቶች መካከል መተማመን ለመፍጠር ኩባንያው በሁለት እግሩ እንዲቆም ለማድረግና ለመሳሰሉት መሆኑ ሲታይ ውሳኔው ምን ያህል ጽንሰ ሐሳባዊ ምክንያትና መሠረት እንዳለው መገንዘብ ይቻላል፡፡

የክልል መንግሥታት የወሰዱትን ዕርምጃ በተመለከተ የሚነሳው ሌላው የተሳሳተ አመለካከት ክልላዊና ሲብስም ብሔራዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥና ሌላውን ለማግለል የተወሰነ ነው የሚል ነው፡፡ በእርግጥ የክልል መንግሥታት ሕገ መንግሥታዊ ኃላፊነታቸው በመጀመርያ በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶችን በመጠቀም የክልላቸውን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ነው፡፡ የክልሎቹ ተጠሪነት ለክልላቸው ሕዝብ ሲሆን፣ በክልሉ ውስጥ ለሚፈጠሩ በጎ ነገሮች ወይም መጥፎ ነገሮች ተጠያቂ የሚሆኑት ራሳቸው ክልሎቹ ናቸው፡፡ ይህ መሠረታዊ ሐሳብ እንደተጠበቀ ሆኖ ከክልሉ ውጪ የሚመጡ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ማለትም በመደበኛ ነዋሪዎች ወይም የንግድ ተቋማት በተለየ ሁኔታ እንዲጎዱ የሚያደርጉ ዕርምጃዎችን መውሰድ አይጠበቅባቸውም፡፡ ይህን ማድረግ አንድ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ለመገንባት የሚካሄደውን እንቅስቃሴ መጉዳቱ የማይቀር በመሆኑ፡፡ በሌላ በኩል ሲታይ ደግሞ በሕገ መንግሥቱ መሠረት አንድ የኢኮኖሚ ማኅበረሰብ ለመገንባት የፌዴራል መንግሥት የኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ያለው ሁሉን አቀፍ ሥልጣን እንደተጠበቀ ሆኖ፣ ክልሎች እንደ ራሳቸው ተጨባጭ ሁኔታ የክልሉን ሕዝብ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ ሕይወትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ፖሊሲዎችንና ዕቅዶችን የማውጣትና እንዲተገበር የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡

መንግሥታቱ የንግድ ማኅበራት የሚፈጠሩበትን ሁኔታዎች ሲያመቻቹ ወይም ሲያስተባብሩ እነዚህ ድርጅቶች የአገሪቷን የንግድ ሕግ ባከበረ ሁኔታ መመሥረት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የሚመሠረቱት ድርጅቶች የአክሲዮን ማኅበራት እስከሆኑ ድረስ ግልጽ በሆነ ማስታወቂያ ፍላጎት ያላቸው ግለሰቦች አክሲዮን በመግዛት መሳተፍ እንደሚችሉ በተለያየ መንገድ ተገልጿል፡፡ ኦሮሚያ ወይም አማራ ክልል ውስጥ በሚገኙ አክሲዮን በሚሸጥባቸው ባንኮች ብቻ ሳይሆን፣ ከኦሮሚያ ወይም ከአማራ ክልል ውጪ በሚገኙ አክሲዮን በሚሸጥባቸው ባንኮች አክሲዮን መግዛት የሚፈልግ ግለሰብ ሊገዛ የሚችል መሆኑ ሲታይ፣ አካሄዱ ምኑን ያህል የንግድ ሥርዓቱ በሚፈልገው መንገድ እየተከናወነ የሚገኝ መሆኑ ነው፡፡

የክልል መንግሥታት ተሳትፎ እንዴት?

በኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂ ላይ በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ መካከል ሊኖር ስለሚገባው ግንኙነት መርህን መሠረት ያደረገ ሐሳብ ተቀምጧል፡፡ በዚህ መሠረት መንግሥት ብዙኃኑ ሕዝብ ተጠቃሚ የሚሆንበት ልማት ለማረጋገጥ እንዲቻል የግሉን ዘርፍ ግልጽ በሆኑ መርሆች መደገፍና አስፈላጊ የሆነ ዕርምጃዎችን ለመውሰድ እንዲችል፣ ተነፃፃሪ ነፃነት ይዞ መንቀሳቀስ የሚጠበቅበት መሆኑ ተመልክቷል፡፡

በሌላ በኩል መንግሥት በግሉ ባለሀብትና በአርሶ አደሮች መካከል ያለው ግንኙነት ሰላማዊ እንዲሆን ለማድረግ፣ የጥቅም ግጭቶችን ለማርገብ ግብርና መር የሆነው ኢንዱስትራላይዜሽን ተግባራዊ ለማድረግ በግሉ ባለሀብትና በአርሶ አደሮች መካከል የጋራ ራዕይ እንዲኖር መሥራት እንዴት እንደሚገባው እንዲህ ሰፍሯል፡፡ ‹‹መንግሥት ከዚህ አኳያ ከፍተኛ የአመራር ሚና መጫውት አለበት፡፡ በመጀመርያ ደረጃ ግብርና መር በሆነው የኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂ ውስጥ አርሶ አደሩና ባለሀብቱ መሠረታዊ የሆነ የጋራ ጥቅም እንዳላቸው፣ በዚህ ውስጥ የጥቅም ግጭቶች እንዲሚኖሩና የጥቅም ግጭቶቹን በምን ዓይነት መንገድ ማጣጣም እንደሚቻል በማሳየት አርሶ አደሩና ባለሀብቱ ለጋራ የልማት ዓላማ አብረው የሚሠለፉበት የጋራ ራዕይ እንዲፈጠር መሥራት አለበት፡፡ የአርሶ አደሩንና የባለሀብቱን የጥቅም ግጭቶች ማጣጣም የሚቻለው ይህንን ለማድረግ የሚያስችል መሠረት ሲነጠፍ፣ አርሶ አደሩም ባለሀብቱም  ምርታማነታቸው በከፍተኛ ደረጃ ሲጨምሩ መሆኑን በመገንዘብ ለምርታማነት መጨመር ሁለቱም ወገኖች በመደገፍና በማስተባበር መንቀሳቀስ አለባቸው፤›› ይላል፡፡

የክልል መንግሥታት የአክሲዮን ማኅበራት ምሥረታ ላይ ያላቸው ድርሻ በአብዛኛው በመንግሥት የልማት ድርጅቶች በኩል የሚይዙት ነው፡፡ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች የራሳቸው ሕጋዊ ሰውነት ያላቸው በቦርድ የሚተዳደሩ፣ በአንድ በኩል ትርፍ የማግኘት ዓላማ በሌላ በኩል ደግሞ ማኅበራዊ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው፡፡ ድርጅቶቹ ሲመሠረቱ የራሳቸው ዓላማዎች ያላቸው ሲሆን፣ እነዚህን ዓላማዎች ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመተግበር እንዲያስችላቸው ሌሎች ተግባራትንም ሊያከናውኑ ይችላሉ፡፡ ድርጅቶቹ የቢዝነስ ተቋማት በመሆናቸው ምክንያት ዓላማቸውን ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚያስችላቸው ሌሎች የገቢ ማግኛ ሥራዎች ውስጥ ሊሳተፉ፣ ማለትም የንግድ ድርጅቶችን የማቋቋም ወይም የአክሲዮን ድርሻ ባለቤት የመሆኑ ሕጋዊ ችሎታ አላቸው፡፡ ስለሆነም የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ድርሻ ያለባቸው የንግድ ማኅበራት የራሳቸው ሕጋዊ ሰውነት ያላቸው ሲሆን፣ ይህም የሰውነታቸው ሁኔታ ከባለ አክሲዮኖች ካላቸው ሕጋዊ ሁኔታ የተለየ ነው፡፡

ስለሆነም ከዚህ ሐሳብ በመነሳት ሲታይ የክልል መንግሥታት የአኮኖሚ አብዮት ሲሉ እኔ እንደሚገባኝ፣ መንግሥት እንደ መንግሥት የግሉ ዘርፍ ሊሠራው የሚችለውን የንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ በመግባት የመንግሥትነት ድርሻውን በመዘንጋትና የግሉን ዘርፍ ለማቀጨጭ በሚል ምክንያት ሳይሆን፣ በተለያዩ የኢኮኖሚ ተዋናዮች መካከል በተለይም በግል ባለሀብትና በአርሶ አደሩ መካከል ያለውን ቅንጅታዊና ኅብረታዊ ግንኙነት ውጤታማ ለማድረግ እንዲያስችለው ነው፡፡ እንዲሁም ጊዜያዊ የማስተባበርና የጋራ ራዕይ እንዲይዙ የማድረግ፣ በዚህም በኢንዱስትሪ ልማት ስትራቴጂ ላይ የተቀመጠውን የመሪነት ሚናውን ለመወጣት በሚል የሚያከናውነው እንደሆነ መረዳት ይቻላል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን የክልል መንግሥታት በንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ በመግባት የመንግሥትነትንና የነጋዴነትን ሀሁ ሳያውቁ በዚያው የሚቀሩ ሳይሆን፣ በተደጋጋሚ ሲገለጽ እንደነበረው ድርጅቶቹ ህልውና እንዲያገኙ ከተደረገ በኋላ በልማት ድርጅቶች በኩል መንግሥት ያለውን ድርሻ ለአርሶ አደሮችና ለወጣቶች በማስተላለፍ እንደሚወጠሩ ፍላጎቱም ድርጅቶቹ ተገንብተው ማየት መሆኑ ተገልጿል፡፡

ኢኮኖሚያዊ አብዮትና የንግድ ውድድር ማረጋገጥ

የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ ሥርዓት ከንግድ ውድድር መርህ ውጭ ከቶ ሊታሰብ አይችልም፡፡ በተለይም የንግድ ውድድር ፍትሐዊነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሥራዎች በአገር አቀፍ ደረጃ ብቻ ሳይሆን፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆኑ ባለሀብቶች ለማፍራት እጅግ መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ክልሎች የኢኮኖሚ አብዮት በሚል የተለያዩ የኅብረተሰብ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ የአክሲዮን ማኅበራት እንዲመሠረቱ ማድረጋቸው፣ በኢኮኖሚው ውስጥ የሚኖሩ ተዋናዮች ቁጥር እንዲጨምር በማድረግ ገበያውን በበላይነት በመያዝ ሊፈጸሙ የሚችሉ ፀረ ንግድ ውድድር ተግባራት እንዲቀንሱ ያደርጋል፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይም ሸማቹ ማኅበረሰብ አማራጮችን አንዲያገኝ፣ የምርቶችና የአገልግሎቶች ዋጋ እንዲቀንስ በማድረግ የሸማቾች መብትና ጥቅም እንዲረጋገጥ ያደርጋል፡፡

በፕሮጀክቶቹ መሠረት የሚቋቋሙት የንግድ ማኅበራት በመሆናቸው ምክንያት የንግድ ውድድርን ፍትሐዊነት ለማረጋገጥ የወጣው ሕግ ተፈጻሚ የሚሆንባቸው ይሆናል ማለት ነው፡፡ የድርጅቶቹን መቋቋም በተመለከተ የሚነሳው ሐሳብ የግሉ ዘርፍ የሚሠራቸውን ሥራዎች ድርጅቶቹ ይሠራሉ፣ ስለዚህም ይህ የነጋዴውን ጥቅም የሚጎዳና በሌላ በኩል የክልሎቹን ውሳኔዎች ስህተትነት ለማንበር የሚቀርበው ሐሳብ መንግሥት የፕራይቬታይዜሽን ፕሮግራም እየተገበረ በሚገኝበት በአሁኑ ወቅት የክልል መንግሥታት በኢኮኖሚ ውስጥ ፈርጣማ አቅም ለመገንባት የሚሄዱበት ጉዳይ እርስ በርሱ የሚቃረን ነው የሚል ነው፡፡ በመሠረቱ የፕራይቬታይዜሽን ፕሮግራም ዓላማው በግሉ ዘርፍ ውጤታማ ሆነው ሊሠሩ የሚገባቸውን ሥራዎች የሚያከናውኑ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ወደ ግል ማዛወርና በዚህም ምክንያት የግሉ ዘርፍና መንግሥት በኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸውን ድርሻ መቀየር ሲሆን፣ አሁን በክልሎች እየተደረገ ያለው የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ማቋቋም አይደለም፡፡ ወይም ፕሮጀክቶቹ ይተገበርባቸዋል ተብለው በተያዙ አካባቢዎች ላይ እነሱን የሚመስል ድርጅት በመመሥረት ከሕዝቡ ፍላጎት በላይ በማምረት ገበያውን ማጥለቅለቅ አይደለም፡፡ ከመነሻው በድርጅቶቹ የመንግሥት ድርሻ ከፍተኛ ሆኖ ተፅዕኖ የማድረስ አቅም የሚያረጋግጥ አይደለም፡፡ ስለሆነም አፕልና ብርቱካን አንድ አድርጎ ለማነፃፀርና በሁለቱ መካከል ያለውን ተቃርኖ ለማሳየት መሞከር የሚያስኬድ አይደለም፡፡

በሌላ በኩል መንግሥት በዚህ አግባብ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ መግባት የሙስናና ኪራይ ሰብሰቢነት ችግሮች እንዲኖሩ በማድረግ ከግል ባለሀብቶች ጋር የማይፈለግ ግንኙነት እንዲኖር የንግድ ውድድሩ ፍትሐዊነት ይዛባል በሚል የሚቀርብ ሐሳብ አለ፡፡ በእርግጥ በአገራችን ነባራዊና ህሊናዊ ሁኔታዎች በግሉ ባለሀብትና በመንግሥት መካከል የሚኖረው ግንኙነት መርህን መሠረት እንዲሆን ካልተደረገና ይህን በጥብቅ ዲስፒሊን የሚተገበርበት ሁኔታ ካልኖረ፣ የመንግሥት መዋቅር በግል ባለሀብቶች የሚያዝበት በዚህም መንግሥት ለሕዝቡና መንግሥትን ላልያዙት ባለሀብቶች ጉዳት እንደሚሆንና በአጠቃላይ የእኩል ተጠቃሚነት ጥያቄዎችን ሊያነሳ እንደሚችል ይታወቃል፡፡ ስለሆነም አማራጩ በአንዱ በኩል ከግሉ ባለሀብት በመራቅ የግሉ ባለሀብት ኢኮኖሚያዊ ውጤት የሚያመጡ የማኑፋክቸሪንግ ሥራዎች እስከሚገባ መጠበቅ፣ እሱም ከገባ ማለት ነው ወይም የግሉ ዘርፍ ያሉበትን ነባራዊና ህሊናዊ ሥጋቶችን አሸንፎ ኢንቨስትመንት ላይ እንዲሳተፉ መንግሥት የማስተባበርና መንገድ የማሳየት ሚናውን ሊያከናወን ይገባል የሚል ነው፡፡

የግሉ ዘርፍ እስከሚገባ ድረስ እንጠብቅ ማለት በተለመደው መንገድ ሒደቱንና ዕድገቱንም እናዘግየው ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም መንግሥት በዚህ አግባብ ኢኮኖሚ ውስጥ የሚገባ ከሆነ ለሙስናና ለኪራይ ሰብሳቢነት ችግሮች ምክንያት ይሆናል ማለት፣ አንድም መግባት አለመግባቱ ዋስትና የሌለበት በዚህም ሊገኝ የሚችለው ጥቅም የሚታጣበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ በሌላ በኩል ከግሉ ዘርፍ ጋር የሚደረግ ግንኙነት መርህን የተከተለ እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ ሁለቱም አማራጮች የራሳቸው እጥረቶች ያለባቸው ቢሆንም፣ የሚመረጠው ግን አነስተኛ ችግሮችን ሊፈጥር የሚችለው አማራጭ ማለትም መንግሥት የግሉ ዘርፍ ወደ ኢንቨስትመንት እንዲገባ ለማድረግ የሚያስችል ሥራዎችን እንዲሠራ ማድረግ የሚለው በመሆኑ፣ በዚህ አግባብ የክልል መንግሥታቱ ወስነው መግባታቸው ተገቢና ትክክል ነው፡፡

ሌላው ሁለቱ የክልል መንግሥታት ፋብሪካዎችን ለማቋቋም እየሠሩባቸው የሚገኙት ዘርፎች የግሉ ዘርፍ የገባባቸው ናቸው፡፡ በእርግጥ ከዚህ በላይም ለማስቀመጥ እንደሞከርኩት ፋብሪካዎቹን የሚያቋቁሙት የክልል መንግሥታት አይደሉም፡፡ የክልል መንግሥታት እያደረጉ ያሉት በሌሎች በልማታዊ መንግሥታት የሚታወቀውን ፋብሪካዎች እንዲወለዱ የማድረግ የአዋላጅነት ሚና (Midwifery Role) እየተጫወቱ የሚገኙ መሆናቸው ነው፡፡ በአንድ አገር ውስጥ የተወሰኑ የሲሚንቶ፣ የብረታ ብረት፣ የለስላሳ መጠጦች፣ የእንጨት ሥራዎች፣ ትራንስፖርትና ነዳጅ ማደያዎች፣ ሪል ስቴቶች መኖራቸው ብቻ በአገሪቷ ውስጥ በእነዚህ ፋብሪካዎች በቂ የሆነ አቅርቦት አለ የማያስብል መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ እነዚህ ፋብሪካዎች ምን ያህሉን ለአገር ውስጥ ምን ያህሉን ለውጭ በመላክ የአገራችንን የውጭ ምንዛሪ ፍላጎት እያረኩ የንግድ ሚዛኑን እያስጠበቁ ነው? በማለት መታየት ይኖርበታል፡፡

በአገር አቀፍ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳድሮ ሸማቹን የሚያማልሉ ምርቶችና አግልግሎቶችን በማቅረብ አሸናፊ መሆን የሚፈልግ ድርጅት ወይም የድርጅቱ የንድፈ ሐሳብ አቀንቃኝ ውድድርን የሚጠላው፣ ወይም ሌላ ድርጅት እንዳይመጣበት የሚፈልገው ተወዳዳሪነት ካለ እሱን ከተመራጭነት ውጪ ስለሚያደርገውና በንፋስ አመጣሽ መንገድ የሚገኘውን የአብዛኛውን ሕዝብ ተጠቃሚነት የሚጎዳ ሁኔታ እንዲቀጥል ስለሚፈልግ ነው፡፡ ሐሳቡ ግለሰቡ ካለው ውግንና የሚነሳ በመሆኑ የሚቀርበውን ሐሳብ ከዚህ አንፃር ማየት ይቻላል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የትራንስፖርት ዘርፍ ስለተባለ ብቻ ክልሎች በአንድ መስመር ብቻ የተገናኙ በሚያስመስል ሁኔታ በክልሎች ድጋፍ እንዲመሠረቱ የተባሉት ድርጅቶች ከሌሎች የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ከሚሠሩት ሥራ ጋር ይደራረባል ማለት ይቻላል፡፡ ግን የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ምክንያቱም በአንድ መስመር ላይ የባቡር ሐዲድ ተሠራ ማለት ከዚህ የባቡር ሐዲድ ውጪ ከተጓዡ ፍላጎት ወይም ከሚጓጓዘው ዕቃ አንፃር ሌሎች አማራጮችን ሊያቀርብ የሚችል የትራንስፖርት አገልግሎት ሊኖር አይገባም በሚል የሚቀርበው ኢኮኖሚያዊ ብቻ ሳይሆን፣ እርግጥ ህላዊ ተቀባይነት ያለው ሐሳብ አይሆንም፡፡ በእርግጥ ክልሎቹ ይህን መሰል ትራንስፖርት እንዲመሠረት ሁኔታዎችን ሲያመቻቹ ያለ ጥናት የሚገቡበት እንደማይሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት በመንግሥት የልማት ድርጅቶች በኩል ካለው አነስተኛ ድርሻ አንፃር እንኳን ወደ ትግበራ ልግባ ቢል ሌሎች ባለአክሲዮኖች በተለይም የግሉ ባለሀብቶች በፈቃደኝነት መንግሥት በልማት ድርጅቶች በኩል ድርሻ ስላለው በሚል ብቻ ወደ ምሥረታው ይገባሉ ማለት የዋህነት ነው፡፡

ኢኮኖሚያዊ አብዮትና የትራንስፎርሜሽንን ዕቅድ

ሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ኢኮኖሚያዊ ትራንስፎርሜሽን ማለትም በኢኮኖሚ ውስጥ ግብርናና ኢንዱስትሪ መካከል ያለውን ግንኙነት ውጤታማ በማድረግ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መሠረት መጣል ነው፡፡ ዕቅዱ በተለይም በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ ሊኖር የሚገባውን ግንኙነት በተመለከተ የተለያዩ ሐሳቦችን ያስቀምጣል፡፡ በዕቅዱ መሠረት ‹‹በተመረጠ አኳኋን በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ በተናጠልና በሽርክና የማሽን መሣሪያዎች፣ ለከባድ የኤሌክትሪክ መሣሪያዎች፣ ለከባድ የትራንስፖርት፣ የግንባታና የማዕድን ቁፋሮ መሣሪያዎችና ለከባድ የፔትሮ ኬሚካልና ኬሚካል ማምረቻዎች እንዲሁም ለታዳሽ ኢነርጂ ማመንጫዎቸ ትኩረት ይሰጣል፤›› በሚል ያስቀምጣል፡፡

ስለሆነም ከዚህ በላይ በተገለጹ ዘርፎች ላይ መንግሥትና የግሉ ዘርፍ በሽርክና አሠራር መሠረት የተለያዩ የንግድ ማኅበራትን በማቋቋም፣ ጉልበትንና የግብርና ምርቶችን በስፋት በግብዓትነት ለሚጠቀሙ ኢንዱስትሪዎች ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት በዘርፉ ሰፊ የሥራ ዕድል እንዲፈጠር፣ የግብርና የኢንዱስትሪና የገጠርና ከተማ ትስስሮች እንዲጠናከሩ ማድረግ አስፈላጊ ይሆናል፡፡  በዕቅዱ በማክሮ ኢኮኖሚ ዘርፍ ውስጥ ከታዩ ዋና ዋና ጉዳዮች አንዱ የሥራ ፈጠራና የድህነት ሁኔታ መሆኑን፣ የሚታቀደው ማንኛውም የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ልማት በዜጎች የሥራ ሥምሪትና የደኅንነት ሁኔታ ላይ ለውጥ ማምጣት ያለበት ስለመሆኑና መንግሥት በተለይ ይህን ተልዕኮ እንዲወጣ ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ትኩረት በመስጠት የግል ኢንቨስትመንትን ማበረታታት የሚገባው ስለመሆኑ ተቀምጧል፡፡

የክልል መንግሥታት ለወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር በማለት የወሰዱዋቸው ዕርምጃዎች ሲታዩ፣ በአንድ በኩል በግል ባለሀብቶች ተይዘው እሴት ሳይጨመርባቸው የተያዙ የማዕድን ቁፋሮ ቦታዎችን በገቡት ውል መሠረት ባለማከናወናቸው በመቀበል ለሥራ አጥ ወጣቶች መስጠት ነው፡፡ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ የማዕድን ዘርፍ ልማትን በተመለከተ ከተቀመጡ መሠረታዊ አቅጣጫዎች ወስጥ አንዱ ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር በሚያስልች ሁኔታ ዘርፉ ሊለማ ይገባል የሚለው አንዱ ነው፡፡ ይህንን የዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ደግሞ እሴት የማይጨምሩ ጥሬ የማዕድን ምርት እያወጡ ለገበያ በማቅረብ ከገቡት ውል ውጪ ንፋስ አመጣሽ ትርፍ የሚያጋብሱ አንዳንድ ‹‹ባለሀብቶች›› እንዳይኖሩ ማድረግ እየመረረም ቢሆን ተገቢም አስፈላጊም ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ለወጣቶች የሥራ ዕድል መንግሥት ማመቻቸቱን በተመለከተ የሚቀርቡ የተሳሳቱ አስተሳሰቦች አሉ፡፡ የመጀመርያው ወጣቱን ኃይል በተለይም ሥራ አጦች የራሳቸውን የቢዝነስ ተቋም ለመመሥረትና ለመምራት የሚያስችል ልዩ ክህሎት ብቃትና ልምድ የላቸውም። ምንም ያህል ድጋፍና ማበረታቻ ቢደረግላቸው በገበያ ውስጥ ተወዳዳሪ የሆነ ምርትና አገልግሎት ለማቅረብ የሚስችል ግለሰባዊና ተቋማዊ አቅም መገንባት ይሳናቸዋል፡፡ በማለት ወጣቱን ኃይል ዝቅ አድርጎ የመመልከትና በተለያዩ መንገዶች ቢሠራም ሊለወጥ አይችልም የሚል ነው፡፡

ይሁንና በዓለማችን ከፍተኛ የሆኑ ለውጦች እንዲመጡ ያደረጉ ሰዎች በመጀመርያ ሥራ አጦች የነበሩና መንግሥት ባደረገላቸው ድጋፍ ውጤታማ የነበሩ ወይም የሆኑ ናቸው:: ይህ እንኳን ቢቀር ወጣቱን ቢዝነስ የመመሥረትና የመምራት ክህሎት፣ ብቃትና ተወዳዳሪነት እንዲያጎለብቱ ማድረግ የሚቻልበትን አግባብ ከማስቀመጥ ይልቅ ወጣቱ ሥራ አጥ የመሆኑ ዕጣ ፋንታው ይመስል ሊለወጥ አይችልም ማለት ጤነኝነት አይደለም፡፡ እዚህ ላይ በጣም የሚገርመው (Ironic) ወጣቱ የሥራ ዕድል አላገኝም፣ ለመብቱ መታገል አለበት እያሉ ወጣቱን ለማይገባ እንቅስቃሴ የዳረጉ ሰዎች ወጣቱ የሥራ ዕደል ካገኘ አብዛኛው ጥያቄዎቹ መልስ ያገኛሉ፣ ይህ ከሆነ ደግሞ ወጣቱን ለማይገባ ነገር በመዳረግ በመጨረሻ የሚንቁት ወጣት ላይ ለመንገሥ ያላቸው ጥማት የማይሳካ በመሆኑ በዚህ ሥሌት የሚንቀሳቀሱ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ሁለተኛው ለወጣቶች መንግሥት በዚህ አግባብ ድጋፎችን አድርጎ ወደ ሥራ እንዲገቡ ማድረግ ሳይደክሙ ሳይለፉ ማትረፍ እንደሚቻል የማይገባ መልዕክት ያስተላልፋል የሚል ነው፡፡ በእርግጥ በዚህ አገር ላይ ልማታዊ በሆነ መንገድ ለፍቶ ያተረፈው ምን ያህል እንደሆነ ሁላችንም የምናውቀው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ የክልል መንግሥታቱ ገንዘብ ብቻ ለወጣቱ ሰጥተው የቁጥጥር ሥርዓት ሳያበጁ የሚተው ከሆነ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን ይሆናል፡፡ ስለሆነም መንግሥት ለወጣቱ እርሾ የሚሆን ገንዘብ ሰጥቶ በዚህ አግባብ እንዲጠናከሩ ማድረግ ግን አስፈላጊ መሆኑ ለሐሳብ አቅራቢዎቹም ቢሆን የራቀ አይመስለኝም፡፡ 

በነገራችን ላይ ወጣቶች ተነሱ በሚል መንግሥት የሚወስደው ውሳኔ ወጣቶቹን ለማስደስትና የማይፈለግ ‹ፖፑሊስት› ለመሆን ሳይሆን ይህን ማድረግ ካልቻል እንደ አገር መቀጠል አስቸጋሪ በመሆኑ ነው፡፡ በእርግጥም የወጣቶችን የሥራ አጥነት ጥያቄ ከመመለስ ውጪ እንደ አማራጭ ሊወሰድ የሚችል ጊዜ የሚሰጥ ሌላ አማራጭ ካለ ቢቀርብ የሚመረጥ ይሆናል፡፡ በተለይም በየዓመቱ በከፍተኛ መጠን እየጨመረ የሚገኘውን የወጣት ኃይል የሥራ ዕድል ሊፈጥሩ የሚችሉ ሥራዎች መከናወን አለባቸው፡፡ በከተማም ይሁን በገጠር የሚገኙ ወጣቶች በሥራ ላይ የማይሰማሩ ከሆነ፣ ያለው አሉታዊ ውጤት አንድም ወጣቶች በራሳቸው ደስተኛ እንዳይሆኑ ማድረግ፣ ወደፊት በቀጣይነት ተቀጥረው የሚሠሩበት ዕድል ማጣበብ፣ ማኅበራዊ ኃላፊነትና ግንኙነታቸው ላይ ጉዳት ያስከትላል፡፡ በዚህም ምክንያት ሥራ አጥ በሆነው የወጣት ኃይልና በባለሀብቱ መካከል ሰላማዊ የሆነ ግንኙነት እንዳይኖር በማድረግ የግል ባለሀብት የሆኑ ድርጅቶች ለማይገባ ችግር እንዲጋለጡ መንገድ የሚከፍት ይሆናል፡፡ በሌላ በኩል መንግሥት ማኅበረሰቡ ወጣቶች በትምህርትም ሆነ በሌላ በኩል አሁን ያሉበት ደረጃ እንዲደርሱ በተለያየ መልኩ ወጪ አውጥተውባቸዋል፡፡ እነዚህ ወጣቶች ያላቸውን ዕውቅት፣ ትምህርት በመጠቀም ለማኅበረሰቡና በአጠቃላይ ለአገራቸው የሚጠበቅባቸውን ለመወጣት እንዲያስችላቸው የሥራ ዕድል አያገኙም ማለት በራሱ ኢኮኖሚያዊና ሌሎች ኪሳራዎችን የሚያስከትል ነው፡፡ ስለሆነም ሥራ የሚፈልጉ ወጣቶች የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ማድረግ፣ መንግሥትም የግሉ ባለሀብትም ትኩረት ሰጥተው የጋራ አጀንዳ አድርገው ሊሠሩት የሚገባ ሥራ እንደሆነ መወሰድ አለበት፡፡

በተጨማሪም በአሁኑ ወቅተ የግሉ ባለሀብት በኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ ያለው ድርሻ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱ እንደተጠበቀ ሆኖ፣ በሚፈለገው ደረጃ ላይ ማኅበረሰቡ የሚፈልጋቸውን ምርቶችና አገልግሎቶች በተመጣጣኝ ዋጋ አማራጮችን በማብዛት የማያቀርብበት፤ እንዲሁም አገራችን እንደ አገር በዓለም አቀፍ ኢኮኖሚ ውድድር ውስጥ ጎልቶ እንድታይ ማድረግ ላይ እጥረቶች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ እነዚህን እጥረቶች በበቂ ደረጃ ለመፍታት ኢንዱስትሪዎች ወይም ፋብሪካዎች መኖራቸው በጣም አስፈላጊ በመሆኑ እየተወሰደ ያለው ዕርምጃ፣ በተለይም የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማረጋገጥ ያለው ጠቀሜታ ተተኪ የሚገኝለት አይደለም፡፡

በመጨረሻም የክልል መንግሥታት ሕገ መንግሥታዊ ሥልጣናቸውን በመጠቀምና የተጣለባቸውን ሕዝባዊ ኃላፊነትና በሕዝቡ የተሰጣቸውን የመጨረሻ ዕድል ለመወጣት የክልላቸውን ነዋሪ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀማመሩ ሥራዎችን የራሳቸው እጥረቶች ሊኖራቸው ቢችልም፣ ማንኛውም ሥራ ከእጥረት የፀዳ ባለመሆኑ የሚያመጡትን አዎንታዊ ጥቅሞች በበቂ ደረጃ ባለመረዳት ወይም መረዳት ባለመፈለግ የሚቀርቡ ሐሳቦች ተቀባይነት አይኖራቸውም፡፡ ክልሎቹ የጀማመሩዋቸው ሥራዎች የራሳቸው ጽንሰ ሐሳባዊ መሠረት ያላቸው፣ ሕገ መንግሥታዊ ኃላፊነትን በመወጣት ላይ የተመረኮዙ፣ የገበያ መር የመንግሥት ፖሊሲን የማይጋፉ፣ በመንግሥት የተለያዩ ሰነዶች ውስጥ በተለያየ መንገድ የተገለጹ፣ አሁን ካለንበት ተጨባጭ ሁኔታ አንፃር በተግባር ያለባቸውና ውጤታቸውም በተግባር እየታየ የሚሄድበት ሁኔታ በመኖሩ፣ የሚነሱ ሐሳቦችንና ከሐሳቦቹ ጀርባ የማን ፍላጎት እንዳለ በማወቅ አቋም መያዝ ተገቢ ይሆናል፡፡

ከአዘጋጁ፡-ጸሐፊው የሕግ ባለሙያ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ ጸሐፊውን በኢሜይል አድራሻቸው tesfayeniway@gmail.comማግኘት ይቻላል፡፡

 

 

Standard (Image)
Viewing all 213 articles
Browse latest View live